Print this page
Saturday, 28 December 2013 11:53

የአውራምባ የጉዞ ማስታወሻ

Written by  ነቢይ መኰንን
Rate this item
(6 votes)

ወደ አውራምባ የተጓዝነው በጠዋት ነው፡፡
ወረታን አልፈን ወደሰሜን ጐንደር የሚሄደውን መንገድ ትተን ወደ ቀኝ ወደ ደቡብ ጐንደር ኮረኮንቹን ይዘን ታጠፍን፡፡

ከወረታ ወደ አሥር ኪሎ ሜትር ገደማ ነው አውራምባ፡፡ ፊትለፊት ካለው ዛፍ ሥር የሚፈትሉ አባወራና ሴቶች እያየን

ነው ወደ አውራምባ ስዕላዊ መግለጫ/እግዚቢሽን ክፍል የገባነው፡፡ አንድ አስረጅ ለፈረንጆች ገለፃ ያደርጋል፡፡ እኔን

የምታስጐበኝ አንዲት ጠይም መልከ - መልካም፣ ንግግሯ ትንታግ የሆነች ልጅ ናት! ጥሩ ሰው ነው ስሟ፡፡
“ከንባቡ ጀምር” አለችኝ ወደተለጠፈው ጽሑፍ እያሳየችኝ፡፡
“ማንበብ ባልችልስ?” አልኳት፡፡
“እሱን ለእኛ ብትተውልን ይሻላል” ብላ ከት ብላ ሳቀች። ከአዲሳባ የመጣ ሰው ሁሉ ማንበብና መፃፍ ይችላል፤ የሚል

እሳቤ እንዳላት ገባኝ፡፡ ለፈረንጆቹ ገለፃ በእንግሊዝኛ የሚሰጠው ልጅ ይሰማኛል፡፡ “በዚያን ጊዜ የደርግ ጦርነት ነበር፡፡

ያካባቢው ህዝብና መንግሥት በደግ ዐይን አያየንም ነበር፡፡ ህዝቡ ለደርግ “ኢህአዴግ ናቸው” ብሎ ነገረ፡፡ ደርግ

ባህላችንን አጠፋ፡፡ አጠፋን፡፡ ማህበረተሰቡ ወደ ደቡብ መሰደድ ነበረበት፡፡ ከ5 ዓመት በኋላ ያ መንግሥት በኢህአዴግ

ሲተካ ተመልሰን መጣን - ሰላም ሆነ” አለ፡፡
እኔ ጽሑፌን ማንበብ ቀጠልኩ፣
“ሶስት ዓይነት ሰዎች አሉ፡፡ ታላቅ ሰው የሚያውቅም የሚጠይቅም ሰው ነው፡፡
ከዚያ መካከለኛ የሚባለው ሰው የማያውቅ ግን የሚጠይቅ ሰው ነው፡፡ ትንሽ ሰው የማያውቅም፣ የማይጠቅም ነው፡፡”
አለፍ አለፍ ብዬ ብዙ ጥቅሶች እያነበብኩ አለፍኩ፡፡ የመጀመሪያዎቹ በእንግሊዝኛ ናቸው፡፡ ሌሎቹ በአማርኛ ናቸው፡፡
“ሁለት መጥፎ ነገሮች” ይላል አንዱ ጥቅስ “መጥፎ ምግባርና መጥፎ ንግግር!”
“ከህብረተሰብ የተነጠሉ ሰዎች፤ ከባህር የወጣ አሳ ናቸው፡፡ አስጐብኝዬ ጥሩ ሰው ወደ አቶ ኑሩ እየጠቆመችኝ፤
“የአውራ አምባ የህብረት ሥራ ማህበር ሊቀ መንበር ነው፡፡ የዚሁ የአውራ አምባ ማህበረሰብ ልጅ ነው” አለች፡፡
የእየሩሣሌም የህፃናትና ማህበረሰብ ልማት ተወካይ አብሮኝ ወደ አውራምባ መጥቷል፡፡ እሱ ብዙ ጊዜ ስለሚመላለስ ጥሩ

ሰውን ያውቃታል፡፡ ሞቅ ያለ ሰላምታ ተለዋወጡ፡፡ “የተለያዩ የህ/ሥ/ማኅበራት አሉ፡፡ የእኛ ማህበር አንዱ ነው” አለኝ፡፡

ገጠር ላይ ስላሉ ወደ ከተማም እየሄዱ ይሠራሉ…” አለና በሉ ከአቶ ኑሩ ጋር ቀጥሉ ብሎ የጄክዶው ተወካይ፤ ዞር ዞር

ሊል እኛን ትቶን ሄደ፡፡
“እስቲ ስለራስህ፣ ስለማዕረግህ፣ ምን ስትሰሩ ኖሯችሁ? ቀለል አርገህ እንደሰው፣ እንደሚገባኝ አርገህ ነገረኝ” አልኩት፡፡

ኑሩ ከት ብሎ ሳቀ፡፡ ዘለግ ያለ፣ ረጋ ብሎ የሚናገር እንደዕውነቱ ከሆነ የማይከብድ ልጅ ነው፡፡ ወደ 30-35 ሳይጠጋ

አይቀርም ዕድሜው፡፡ እንደሰማሁት የዙምራ (ማለትም የአውራምባ ማህበረሰብ መሪ) የወደፊት ወራሽ ነው፡፡
“ሰውና ሰው ሆነን እናውራ ማለቴ ነው፡፡ ደረቅ ሥራ እንዳናገረው… ብትፈልግ ስለራስህ፣ ብትፈልግ ስለሥራህ፣

የፈለከውን ንገረኝ፡፡ መጀመሪያ ግን ስምህን አስተዋውቀኝ” አልኩት፡፡
“ኑሩ በላይ እባላለሁ” አለኝ፡፡ “ማህበረሰቡ በሁለት ዓይነት አደረጃጀት የተደራጀ ማህበረሰብ ነው፡፡” አለ። አነጋገሩ

ገርሞኛል፡፡ (ኢህአዴግ አዲስ አበባ ከገባ በኋላ የሚዘወተሩ ዐረፍተ - ነገሮች ዓይነት መስሎ ነው የተሰማኝ)። ቀጠለ:-
“በአንድ በኩል በኮኦፕሬቲቭ የተደራጀ፣ በሌላ በኩል ደሞ ያው በአውራምባ ማህበረሰብ በሚል የተደራጀ ነው።  

“የአውራምባ ማህበረሰብ ግንባታ ህጋዊ ዕውቅና ያለው ማህበር ነው፡፡ በሁለት መልክ የተደረገው፤ ለአስተዳደርም

እንዲመች ነው፡፡ በኮኦፕሬቲቭ ውስጥ ለጊዜው የማህበሩ ሰብሳቢ ነኝ፡፡ እዚያ ላይ ነው የምሠራው…”
“ኮኦፕሬቲቩ እንዴት ተመሠረተ?”
“ማህበረሰቡ ረዘም ያሉ ዓመታትን ያስቆጠረ ማህበረሰብ ነው፡፡ ከ64 ዓ.ም ጀምሮ፡፡ ማህበረሰቡ ለየት ያለ አኗኗር፣ ለየት

ያለ ባህል እንዳለው ብዙ ጊዜ በሚዲያ ተነግሯል፡፡ ለዚህ እንግዳ ትሆናለህ ብዬ አላስብም፡፡ በባህላችን አንተ እያሉ

መጥራት ይቀለናል፡፡ አንተ ልበልህ እ?...”
“ትክክል ነው ቀጥል” አልኩት፡፡
“በአደረጃጀት ባህሉ የእኛ ማህበረሰብ ለሰው ልጅ ትልቁ ሀብቱ ሰው ነው፤ ብሎ ነው እሚያምነው፡፡ ሰው ሳለ በህይወት

መተሳሰብ፡፡ መተጋገዝ፡፡ ሰው በሰውነቱ ሰው ነው ለማንም ሰው ሀብቱ ሰው ነው፡፡ ተፋቅረን መኖር አለብን። ይሄ

ለማንም ነው ሀብቱ ሰው ነው፡፡ ተፋቅረን መኖር አለብን፡፡
“አንተ እዚህ ተወላጅ ነህ ማለት ነው?”
“እዚሁ ተወልጄ ነው ያደግሁት”
“ሰው ነው የሰው ዋና ሀብቱ! ተሳስቦ እንዲኖር ነው ነው ያልከኝ?”
“ያው ዙሮ ዙሮ ቀጣዩ ሀብት ነው፡፡ ሀብት ለማግኘት መሥራት ያስፈልጋል፡፡ የሥራ ፕላኖችን መንደፍ፣ ማንቀሳቀስ፣

ማገር፣ ይጠይቃል፡፡ ሠርተን በጋራ ነው የምንኖረው፡፡ ትርፍ ክፍፍላችን እኩል ነው፡፡ አንተ ደካማ ነህ፣ እኔ ጉልበት

አለኝ በሚል የተለያየ ክፍያ የለንም፡፡ የሥራ መስኩን ነው መደብ የምንሰጠው፡፡ ሥራ ክፍፍላችን ኃይል አሟጠን

እስከተጠቀምን ድረስ እኩል ሠርተናል፤ ብለን ነው እምናምነው፡፡ ምክንያቱም ጠንካራ ሥራ፤ በደካማ ሰውም ካልተደገፈ

ጠንካራ ሆኖ አይቀጥልም ብቻውን፡፡ ለምሳሌ ዕደ ጥበብ ላይ፣ አልባሳት ሥራ ላይ ብንሠራ፣ እሚሸምነውን ከሥር ከሥር

እሚሠራለት ሰው አለ፡፡ እሚሻም ነው ጠንካራ ጉልበት እሚጠይቅ ከሆነ፣ ያኛው ቀለል ባለ ጉልበት ካልመገበው ጠንካራ

ሥራ ሠርቶ አይውልም፡፡ ስለዚህ ያንና ያን አመጋግበን እኩል ነው የምንሰጣቸው፡፡ እያንዳንዱ የሥራ መስክ በንጽጽር

ብናየው መደጋገፍ የሚገባቸው ነገሮች አሉ፡፡ መሠረታችን ሥራ ነው - ማምረት፡፡ ትርፍ ክፍፍል ላይ እኩል

እንሰጣለን፡፡ በማህበራዊ ችግሮች ላይ ማህበራዊ መፍትሔ እንሰጣለን፡፡ የአንድ ግለሰብ ችግር ብቻ ሊሆን አይገባም፡፡

ሰው በሰውነቱ ወገን ሁኖ ዋስትና ማጣት የለበትም፡፡ የሰው ልጅ ለሰው ልጅ ዋስትና ሊሰጠው ይገባል፡፡ ዋስትና ሊያገኝ

ይገባዋል፤ ብለን ነው እምናስበው፡፡ ባህላዊ አኗኗራችን ባጭሩ ይሄን ነው የሚመስለው፡፡ ታሪኩን ታቀዋለህ ብዬ ነው

ያልነገርኩህ…
“ግዴለም አጫውተኝ” አልኩት፡፡
“ይሄንን የመሠረተው ዶክተር ዙምራ ኑሩ፤ ያው በቅርብ አመታት ከጅማ የኒቨርሲቲ የዶክተሬት ማዕረግ የተሰጠው ነው፡፡

አጋጣሚ አዲሳባ ነበረ - ልታገኘው ትችል ነበር፡፡”
“ይህ ፍልስፍና እንዴት መጣ? ህብረተሰባችን ሌላ ዓይነት ያኗኗር ዘይቤ እየተከተለ ይሄኛው ለምን ብቻውን ያለ

ይመስላል?” አልኩት፡፡ “ነገስ ከሌላ ማህበረሰብ ጋር አይጋባም ወይ? ጋብቻ አይፈፃፀምም ወይ? እርስ በርስ አይተሳሰርም

ወይ? ባህሉ አይለወጥም ወይ? አንዱ አንዱ ውስጥ አይፈስስም ወይ? እንደዚህ እንደዚህ ያሉ ነገሮችን አጫውተኝ”“እ…

ጋብቻ ላይ እኛ normally ግልጽ ነን፡፡ እኛ ከሌላ ማምጣት ችግር የለብንም፡፡ ሌሎችም ከእኛ መውሰድ ችግር

የለባቸውም፡፡ ግን በመሠረታዊ መንገድ ወደተግባር ሲለወጥ ባህላዊ ተጽእኖዎች አሉ፡፡ የብዙዎቹ ወደዚህ ማምጣት ለነሱ

ሊያስቸግር ይችላል፡፡ በተለይ ከፆታ አኳያ የሚደረገው ነገር ማለት ነው፡፡ ከእዚህ ወደዛ ግን በጭራሽ አያስቡትም፡፡

እዚያ ጋ ያለ አይመጣጠንላቸውም፤ አያስቡትም፤ ሴቶቹ ማለት ነው፡፡ ከዚህ ወደዚያ መሄድ አያስቡም፡፡ ከዚያ ወዲህ

መምጣት ከቻለ ግን ችግር የለውም፡፡ ያ ሲመጣ ደግሞ ባህላዊ አስተሳሰቦቻችን እንዲከበሩ እንፈልጋለን፡፡ ሊያፈርስብን፣

ሊያበላሽብን መሆን የለበትም የሚመጣው። ራሱን አዘጋጅቶ ይሄን ባህል እጠብቃለሁ አስከብራለሁ ብሎ ነው መምጣት

ያለበት፡፡ በዚያ ዝግጁ ሆኖ ከመጣ መቀላቀል ይችላል በጋብቻ፡፡ በተለያየ መልኩ…”
“ግን ከዚህም ነፃ ናቸው፡፡ ሴቶቹ አያስቡትም እንጂ? አሁን ለምሳሌ አንዷ ልጅ አንዱን ወንድ ለማግኘት ብታስብ

መጀመሪያ ወይ በገበያ መገናኘት አለባት፡፡ ወይ በሆነ ዘመድ ወይም ምክንያት መሄድ አለባት እሱ ዕድል እንዴት

ይገኛል?” አልኩት፡፡
“ለምሣሌ ት/ቤት አለ፡፡ አሁን እዚህጋ ካንድ እስከ ስምንት አለ…ከ9-10 አለ…የህዝብ ት/ቤት ነው፡፡
ማንም እሚማርበት፡፡ ቢበዛ የእኛ ልጆች ከመቶ አምስት ፐርሰንት በላይ አይሆኑም፡፡ በዚህ ስሌት ይገናኛሉ፡፡ ሌላው

አብዛኛው ማህበረሰብ እዚህጋ ነው እሚውለው ለማለት ይቻላል፡፡ ወይ ገበያ ላይ፣ ወይ ወፍጮ አገልግሎት ያገኛል፣

የሱቅ አገልግሎት ያገኛል፣ እንዲሁ ባንዳንድ ሰላም በመሳሰሉ ነገሮች እንገናኛለን፡፡ ግንኙነቱ አሁን ሰፊ ነው።  ስለዚህ

በሰፊው የመገናኘቱ ዕድል አለ፡፡ ዙምራ እንዴት እንደጀመረው ሲናገር በአስተሳሰቡ በጣም የተለየ ሰው መሆኑን፤ ነው

የሚያሳየው፡፡ ሩህሩህ ነው በተፈጥሮው፡፡ በሰው ልጅ አንድነት ነው እሚያምነው፡፡ ለምሳሌ ከዚህ በላይ ወገን ነው፤

ከዚህ በታች ወደባዕድነት እየተቀየር ይመጣል፤ ብለን በተለምዶ የምናስበው አስተሳሰብ፤ ከእሱ ዘንድ ምን ማለት ነው

የሚል ጥያቄ ነው እሚያስነሳው፡፡ የሰው ልጅ በሰውነቱ ወገን አደለም ወይ? ከየት መጥቶ ዘሩ ተቀየረ? ለምሣሌ ይሄንን

ዛፍ እዩት ሥሩን፡፡ ከላይ ግን ቀንዘሉ ሰፊ ነው፡፡ በቀንዘሉ ያፈራል ባዕድ ነወይ? ለሥሩ ቀንዝሉ ባዕድ ነወይ? እንደዚህ

ብሎ ነው እሚያስበው፡፡ እና ፍልስፍናው በጣም የረቀቀ ነው ከዛ አኳያ ማንም ሰው ውስጥ ሊወደዱ እማይገባቸው

ባህሪዎች አሉ፡፡ እነሱን ብቻ ነጥሎ በማስተማር፣ በመለወጥ፣ ሰውን መለወጥ ይቻላል፡፡ ሰው ተማሪ ነው ሰው፡፡

በተፈጥሮው ተማሪ ነው ይማራል፣ ስለዚህ እነዛን ባህሪዎቹን ነጥሎ፤ አይወደዱም፣ ሰላም ይነካሉ የሌላን ሰው መብት

ይነካሉ፣ ለራስም ሥነምግባርን ያጐድፋሉ፣ ለህሊናም እሚያረኩ አይሆኑም…የምንላቸውን በደንብ እስከሚወጡ ድረስ

እነዚህን መለወጥ እስከተቻለ ድረስ… ሁሉንም ባንድ ሚዛን መውሰድ ነው ተገቢ እሚሆነው፡፡ እናቱ፤ አሁን ቅርብ ጊዜ

እኛ ከደረስን ነው ያለፈችው፡(ይቀጥላል)

Read 5991 times