Print this page
Monday, 07 April 2014 15:31

“አኬልዳማ” ኢቴቪን ካሣ ሊያስጠይቅ ነው

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(9 votes)

ኢቴቪ የማረሚያ ፕሮግራም እንዲያስተላልፍ ፍ/ቤት አዟል
“መልካም ስሜን የሚጠግን ተመጣጣኝ ፕሮግራም ሠርቼ አቀርባለሁ”

      የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን  ባስተላለፈው “አኬልዳማ” የተሰኘ ዘጋቢ ፊልም፣ መልካም ስሜን አጉድፏል ሲል አንድነት ለፍትህና ለዲሞክራሲ ፓርቲ፤ኢቴቪን መክሰሱ የሚታወስ ሲሆን ሰሞኑን የፌደራሉ ከፍተኛ ፍ/ቤት በሰጠው ውሣኔ፣ ጣቢያው ቀደም ብሎ ለ“አኬልዳማ” በሰጠው የአየር ሽፋን መጠን የሚቀርብ፣ በፓርቲው ላይ የደረሰውን ጉዳት የሚያካክስ ፕሮግራም ሠርተው ያቅርቡ ሲል ትእዛዝ አስተላልፏል፡፡
አንድነት በበኩሉ፤ በፍ/ቤቱ ትዕዛዝ መሠረት መልካም ስሜን የሚጠግን፣ተመጣጣኝ ፕሮግራም ሠርቼ አቀርባለሁ፤ ለደረሰብኝ የወጪ ኪሣራም ተገቢውን ካሣ እጠይቃለሁ ብሏል፡፡
ፍ/ቤቱ በሰሞኑ ውሣኔው ተከሳሽ (ኢቲቪ)፤ ከህዳር 16 እስከ ህዳር 18 ቀን 2004 ዓ.ም በጣቢያው ባስተላለፈው “አኬልዳማ” ዘጋቢ ፊልም፣ ከሣሽን  ከግንቦት 7 የሽብር መረብ አንዱ መሆኑን፣ አባላቱም ብጥብጥና ሁከት ፈጣሪ መሆናቸውን፣ ለአሸባሪዎች አመራርና አባላቱ ሽፋን እንደሚሰጡ በማመላከት ዘገባ ማቅረቡንና የፓርቲውን ስም ማጥፋቱን ጠቅሶ  ድርጊቱ አግባብ አይደለም ብሏል፡፡ በዚህም መሰረት ተከሣሽ ይሄንኑ ዘገባ በሚያርም መልክ ተመጣጣኝ ፕሮግራም በጣቢያው እንዲያስተላልፍ ወስኗል፡፡ ከሣሽ በዚህ ክስ ምክንያት የደረሰበትን ወጪ ዘርዝሮ፣ ተከሣሽን ካሣ የመጠየቅ መብቱ የተጠበቀ እንደሆነም ፍ/ቤቱ ገልጿል፡፡
“ፍ/ቤቱ ለደረሰብን የሞራልና የቁስ ኪሣራ ካሣ መጠየቅ እንደምንችል በውሳኔው ስላመለከተ፤በዚህ መሠረት ተገቢውን ካሣ አስልተን እንጠይቃለን” ብለዋል- አቶ ሃብታሙ፡፡
በፍ/ቤቱ ውሣኔ ሙሉ ለሙሉ አለመርካታቸውን የገለፁት ሃላፊው፤“በተለይ በሽብር የተከሰሱት ግለሰቦች ጉዳያቸው በፍ/ቤት የተያዘ መሆኑ እየታወቀ፣ ከህግ አግባብ ውጭ በንፁህ የመገመት መብታቸውን ተነፍገዋል” ለሚለው የፓርቲው የክስ ነጥብ፣ ውሣኔ አለመሠጠቱ ቅር እንዳሰኛቸው ጠቁመው፤አሸባሪ የተባሉት ግለሰቦች ነፃ እስኪወጡ ድረስ የፓርቲው ትግል እንደሚቀጥል ገልፀዋል፡፡
በሌላ በኩል አንድነት ፓርቲ መጋቢት 28 ቀን 2006 ዓ.ም በአዲስ አበባ ከሚያካሂደው ሠላማዊ ሠልፍ ጋር በተገናኘ ከአስተዳደሩ ጋር አለመግባባት መፈጠሩንና ፓርቲው ያቀረባቸው ሶስት  አማራጭ  ቦታዎች ውድቅ መደረጋቸውን አቶ ሃብታሙ ጠቅሰው፣ አስተዳደሩ ሠልፉን ለማደናቀፍ  እየሞከረ ቢሆንም ፓርቲያቸው ሠላማዊ ሠልፉን ከማከናወን ወደ ኋላ እንደማይል ገልፀዋል፡፡   

Read 4502 times