Saturday, 26 April 2014 12:37

ለአገር ገፅታ ግንባታ - የአገርን ስም መለወጥ

Written by 
Rate this item
(0 votes)

“ካዛኪስታን” የምትባለውን አገር እስከነመፈጠሯ ባታውቋት ችግር የለውም፡፡ የትም ብትሄዱ፣ የካዛኮችን ምድር የሚያውቅ ብዙ አታገኙም፡፡ እንዲያውም፤ ቱሪስቶች ወደ አገራችን ዝር የማይሉት ለምንድነው በማለት የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ማማረር ከጀመሩ ውለው አድረዋል፡፡ ለነገሩ እንኳን በአካል ይቅርና ካዛኪስታንን በስም የሚያውቁ ሰዎች ጥቂት ናቸው፡፡ እነዚህ ጥቂት ሰዎችስ እንዴት አወቋት? እንግሊዛዊው ኮሜዲያን “ቦራት”፣ በካዛኪስታን ላይ የሚሳለቅ ፊልም ስለሰራ ነው፡፡
ፊልሙ በመላው አለም መታየት የጀመረ ጊዜ፣ የካዛኪስታን መንግስት የእገዳ መመሪያ አውጥቶ ነበር፡፡ ለምን መሰላችሁ? በካዛኮች ምድር፣ ያለመንግስት ፈቃድ፣ ያለ ባለስልጣን ይሁንታ መጽሐፍ ማሳተምም ሆነ ፊልም መሥራት አይቻልም፡፡ በአገራችን በደርግ ዘመን እንደነበረው፤ በሳንሱር ጽ/ቤት ታይቶና ተመርምሮ፣ ተቆራርጦና ተበርዞ ነው ለፊልምና ለመጽሐፍ ዝግጅት ፈቃድ የሚሰጠው፡፡ ያው፣ ካዛኪስታንም እንደኛው አገር፣ በኮሙኒዝም ውስጥ የነበረች እና በራሺያ ቅኝ ግዛት ስር የቆየች አገር ስለሆነች፣ የሳንሱር አሰራር ገና አልለቀቃቸውም፡፡ አሁንም የመንግስት ስልጣን በአንድ ፓርቲና በአንድ መሪ የተያዘ ነው፡፡ አሁንም ኢኮኖሚው በአብዛኛው በመንግስት ቁጥጥር ስር ነው፡፡ ቱሪስት እና ኢንቨስተር ወደ ካዛኪስታን ዝር የማይለው በዚህ ምክንያት አይደለም እንዴ?!
የአገሪቱ ፕሬዚዳንት በዚህ አይስማሙም፡፡ አንደኛው ችግር የአገሪቱ የህዝብ ቁጥር 7 ሚሊዮን ብቻ መሆኑ ነው ይላሉ ፕሬዚዳንቱ፡፡ ነገር ግን ሁለት ሚሊዮን ህዝብ ያላት ሞንጐሊያ፣ በርካታ የውጭ ቱሪስቶችንና ኢንቨስተሮችን ለመሳብ ችላለች፡፡ ሞንጐሊያማ ምን ሃሳብ አላት እድለኛ ነች፡፡ የአገር ገጽታን የሚያበላሽ እዳ የለባትም፡፡ ካዛኪስታን ግን እድሏ አልሰምር ብሎ ገጽታዋን ጥላሸት የሚቀቡ ነገረኞችን ተጐራበተች፡፡ ይህ አልበቃ ብሎ ስሟን አሳደፉት፡፡ እነ ማን? እነ ፓኪስታን፣ አፍጋኒስታን ናቸዋ፡፡ ስማቸው ተመሳሳይ ስለሆነ ብቻ፣ ካዛኪስታን የሽብርና የትርምስ አገር ትመስላለች፡፡ ሞንጐሊያ ከዚህ ጥላሸት ነፃ ነች፡፡ ስለዚህ መፍትሔው እንደሞንጐሊያ መሆን ነው፡፡ አፍጋኒስታን ማለት የአፍጋን ቦታ እንደማለት ነው፡፡ ካዛኪስታን ደግሞ የካዛክ ቦታ፡፡ ሞንጐሊያ ማለት የሞንጐል ምድር ስለሆነ፣ የካዛኪስታንን ስም ወደ ካዛኪያ እንቀይረው ብለዋል - ፕሬዚዳንቱ፡፡

Read 2571 times