Saturday, 14 June 2014 12:04

የኢትዮጵያ ታሪክ

Written by 
Rate this item
(9 votes)

...በዚያም ወራት ደጃች ብሩ፤ ጭልጋ አርባ አምባ ታስሮ ሳለ፣ ሚሽቱ ወይዘሮ የውብዳር ከእልፍኝ አሽከሮቿ አንዱን መልምላ ውሽማ አበጅታ ነበረ፡፡ ይህን ነገር ደጃች ብሩ በሰማ ጊዜ አዘነ፡፡ በበገና እንዲህ ብሎ አለቀሰ፡፡ ...
“መከራን በሰው ላይ እንዲያ ሳቀለው፣
ምንኛ ከባድ ነው እኔ ብይዘው፡፡
መከራ ሲመጣ አይነግርም አዋጅ፣
ሲገሠግሥ አድሮ ቀን ይጥላል እንጅ፡፡
ዘሃው ሰለሰለ ሸማኔው ተቆጣ፣
እስተወዲያው ድረስ መጠቅለያ ታጣ፡፡
የኔታም አይመጡ እኔም አልመለስ፣
ዋ ቢቸና ቀረ እስተወዲያው ድረስ፡፡
ከእልፍኝ ሰው አይግባ ሚሽቴን ሰው አይያት አይሉም አይሉም፣
ፈረሱን ሰው አይጫነው፣ በቅዬን ሰው አይጫነው አይሉም አይሉም፣
ጠጁ ቀጠነብኝ፣ ሥጋው ጎፈየብኝ አይሉም አይሉም፣
ቀን የጣለ ለታ፣ የጨነቀ ለታ፣ ይደረጋል ሁሉም። አለ፡፡
የደጃች ብሩ ግጥም ብዙ ነው፡፡ በሰራው ክፋት ብድሩን ከፈለ፡፡ በዘመኑ ጎጃምን ሲገዛ ያደረገው ክፋት ተጽፎ አያልቅም፡፡ ሚሽቱ ወይዘሮ የውብዳር ቤተክርስቲያን ልትሳለም በምትወጣበት ቀን አስቀድሞ ሰው የገባ እንደሆነ የዱላ በረዶ ይወርድበት ነበር፡፡ በደረቤ በየወረዳው ፲ ፲ (አሥር አሥር) እንስራ ጉንዳን ለምስጥ ማጥፊያ ብሎ ደሃውን አስጨንቆት ነበረ፡፡ ያንን ጊዜ ባላገር ጉንዳን በሣምባ ሥጋ እየተሰለበ በእንስራ ውስጥ እየከተተ ወደ ሶማ አምባ ሲወስድ ጆሮውንና ትክሻውን እየነከሰ አስቸገረው፡፡ የዚህ ጊዜ በለቅሶ ሲአንጎራጉር እንዲህ አለ፡፡
ከመከራው ሁሉ የጉንዳኑ ባሰ፣
የተሸካሚውን ጆሮና ትክሻ እየተናከሰ፡፡ አለ፡፡
ደግሞ የሴት ብልት ጠጉር የበቅሎ ቁርበት ይበጃል ብሎ ፭፻ ጉንዲ ጠጉር በሚዛን አምጡ ብሎ በየወረዳው ጥሎ ደኃውን አስለቀሰው፡፡ በሚዛን ሳይሞላለት ጊዜ የራሱን ጠጉር እየጨመረ ቢሰጥ እምቢ እያለ ወርቅ ተገላገለው፡፡
ያን ጊዜ የሴት ዘመድ የሌለው ተቸግሮ ነበረ፡፡ ደግሞ አፄ ቴዎድሮስ እንዳይሰብረው ብሎ ሶማን ሊያሰራ ፴ ጎበዝ ግንድ ተሸክሞ ሲወጣ፣ ከጠባብ ቦታ ላይ ተጨናንቆ ግንዱ ወንጥሎት ገደል ይዞት ገባና አለቀ፡፡ ይኸን ደጃች ብሩ በሰማ ጊዜ ገበሬ ምንኛ ተዋዳጅ ነው፡፡ አንድነት ወርዶ አለቀ ወይ ብሎ ቀለደ፡፡ አለሚገባ እጁን  እግሩን የቆረጠው ሰውም ብዙ ነው፡፡
ይህን ሁሉ ክፋት ክርስቶስ መዝኖ ጊዜው ሲደርስ፣ በአጼ ቴዎድሮስ እጅ አግብቶ ሚሽቱን ለጠብደል ማላገጫ አድርጎ ሲአስለቅሰው ኖረ። የደጃች ብሩን ልቅሶ አጼ ቴዎድሮስ በሰማ ጊዜ ሎሌዎች በድለዋል አሉና ልቅጣዎ ብሎ ላከበት። ደጃች ብሩም ለጊዜው ኀዘን አብርትቶ ነበረና መንግሥትዎን ያሰንብትልኝ፡፡ ቃሉ ደረሰኝ፡፡ ግን የጮሁለት ሰው አለና የዚያን ቁርጥ ሳውቅ ይሁን አለ፡፡
መልክተኛው ከመድረሱ ውሽማዋን መብረቅ ገደለው፡፡ ደጃች ብሩም ክርስቶስ ሰማኝ፡፡ ፍርዱን ፈረደ፡፡ ባላጋራየ ሞተ ብሎ ላከ፡፡ አጼ ቴዎድሮስም ሰምቶ ተደነቀ፡፡ ለካስ ደጃች ብሩ አጥብቀው አዝነዋል፡፡ ክርስቶስም ሰማቸው፤ በኔም ቢአዝኑ ያደርሱብኛል ብሎ ፈተህ አምጣልኝ አለ፡፡
ከታሰረበት ፈትቶ ወደ አጼ ቴዎድሮስ እጅ ሊነሣ ሲኸድ፣ ያው ጋኔኑ ጥንተ ትቢቱ አልለቀው ብሎ ተከናንቦ ሎሚ ታህል ደንግያ በትከሻው ይዞ ሊታረቅ መጣ፡፡ አጼ ቴዎድሮስም ክንንቡንና የድንጋይቱን ማነስ አይቶ ተበሳጭቶ፣ ትቢትዎ አለቀቀዎምሳ ቢለው፣ ክንብንቤን እንደሆነ የጭልጋ በረሃ  ጠጉሬን ጨርሶት ባፍር ነው አለ፡፡ አጼ ቴዎድሮስም ከአብራጃው አገር መቅደላ ይቆዩ፡፡ እኔ ልፈታዎ ነበረ፡፡ ነገረ ክርስቶስ ማቆያ በትቢት ምክንያት አመጣብዎ፡፡ ፈቃዱ ሲሆን ይፈታሉ አለው፡፡  
ምንጭ - (አለቃ ተክለኢየሱስ፣ የኢትዮጵያ ታሪክ፤ ሐተታ (በሥርግው ገላው (ዶ/ር))

Read 9519 times