Saturday, 28 June 2014 11:51

2 ሚሊዮን ዶላር የተሸጠው የዘፈን ግጥም

Written by 
Rate this item
(0 votes)

የታዋቂው ድምጻዊ ቦብ ዳይላን አንድ የዘፈን ግጥም፣ ሰሞኑን ሱዝቤይ በተባለው አለማቀፍ አጫራች ኩባንያ አማካይነት ለጨረታ ቀርቦ 2 ሚሊዮን ዶላር በመሸጥ ክብረወሰን ማስመዝገቡን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
ከቦብ ዳይላን ታዋቂ ስራዎች አንዱ የሆነው ‘ላይክ ኤ ሮሊንግ ስቶን’ የተባለው ዘፈን ግጥም፣ በራሱ በድምጻዊው የተጻፈ ሲሆን፣ በአራት ነጠላ ወረቀቶች ላይ በእርሳስ የተጻፈው የግጥሙ ኦሪጅናል ኮፒ ነው በጨረታው የተሸጠው፡፡
ቦብ ዳይላን የከፍተኛ መደብ አባላት በሚኖሩበት ማህበረሰብ ውስጥ የብቸኝነት ኑሮን በምትገፋ አንዲት ባይተዋር ሴት ዙሪያ የሚያጠነጥነውን ይህን የዘፈን ግጥም፣ የ24 ዓመት ወጣት ሳለ ነበር እ.ኤ.አ በ1965ዓ.ም የጻፈው፡፡
የአጫራቹ ኩባንያ ባልደረባ የሆኑት ሪቻርድ ኦስቲን እንዳሉት፣ የቦብ ዳይላን ሥራዎች በዘመናዊው ሙዚቃ ጉዞ ላይ የራሳቸውን አስተዋጽኦ ያበረከቱና አቅጣጫ የቀየሩ ናቸው፡፡
ግጥሙን ለአጫራቹ ኩባንያ ያቀረበው ግለሰብ ማንነት ባይገለጽም፣ የድምጻዊው የረጅም ጊዜ አድናቂ መሆኑ ተነግሯል፡፡
ከዚህ በፊት ለጨረታ ቀርቦ በከፍተኛ ዋጋ በመሸጥ ክብረወሰኑን ይዞ የነበረው፣ እ.ኤ.አ በ1967 በታተመው ‘ሎንሊ ሃርትስ’ የተሰኘ አልበም ውስጥ የተካተተው የታዋቂው ድምጻዊ ጆን ሌነን ሙዚቃ፣ ‘ፎር ኤ ዴይ ኢን ዘ ላይፍ’ የተሰኘ ግጥም ነበር፡፡ ግጥሙ ከሶስት አመታት በፊት ለጨረታ ቀርቦ በ1 ነጥብ 2 ሚሊዮን ዶላር መሸጡን ቢቢሲ አስታውሷል፡፡  

Read 3558 times