በትላንትናው ዕለት የሽምግልናውን ሂደት አስመልክቶ ለፍ/ቤት ያስረዱት ባለጉዳዮቹ ሽማግሌ በማሰባሰብ ላይ መሆናቸውን በመግለፃቸው ፍ/ቤቱ ለጥር 14 ቀን 2004 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ መስጠቱን ተወካይ የሆነችው እህቷ ቤተልሄም ደምሴ ለአዲስ አድማስ ተናግራለች፡፡ የሽምግልና ሂደቱ ትላንት ከፍ/ቤት እንደወጡ መጀመሩን የገለፀችው ተወካዩዋ፤ እርቁ በካሳ ይሁን ወይም ማስተባበያ በመስራት የሚለው ጉዳይ ገና አለመወሰኑን ተናግራለች፡፡ የሽምግልና ሂደቱ ምንእንደሚመስል የጠየቅነው ጋዜጠኛ ሰይፉ በበኩሉ፤ ጉዳዩ በፍ/ቤት የተያዘ በመሆኑ አስተያየት ለመስጠት ፈቃደኛ አለመሆኑን ገልጿል፡፡ ጋዜጠኛ ሰይፉ ከአሜሪካ ባስተላለፈው ዘገባ ድምፃዊት ሳያት ባቀረበችው ኮንሰርት፤ መድረክ ላይ በድምጿ መዝፈን አቅቷት ከመድረክ ጀርባ በቴፕ ዘፈኗ ይጫወት እንደነበር ጠቁሞ በዚህም ታዳሚዎች ተቃውሞ ማሰማታቸውን መግለፁ ይታወሳል፡፡ ከዚሁ ጋር በተያያዘም ሳያት ማስተባበያ እንዲሰራላት ጠይቃ የፕሮግራሙ አዘጋጆች ፈቃደኛ ሳይሆኑ በመቅረታቸው የጣቢያው ባለቤቶች ድምፃዊቷን ይቅርታ መጠየቃቸው ይታወሳል፡፡