Print this page
Saturday, 04 February 2012 11:53

በሚቀጥለው ዓመት መውሊድን በአለም አቀፍ ደረጃ ለማክበር ዝግጅት እየተደረገ ነው

Written by  መታሰቢያ ካሣዬ
Rate this item
(0 votes)

በአወሊያና በአንዳንድ መስጊዶች አስተዳደሩን በመቃወም የፊርማ ማሰባሰብ እየተካሄደ ነው

የዛሬው የነቢዩ መሀመድ ልደት (መውሊድ) ከቀድሞዎቹ በተለየ መልኩ እንደሚከበርና በቀጣዩ አመት በአሉ በአለም አቀፍ ደረጃ ኢትዮጵያ ውስጥ እንዲከበር ለማድረግ ዝግጅት መጀመሩን የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ፕሬዚዳንት ሼህ አህመዲን አብዱላኢ አስታወቁ፡፡ ፕሬዚዳንቱ ሰሞኑን በኡማ ሆቴል በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ እንደተናገሩት፤   በዓሉን ካለፉት ዘመናት በተለየ መልኩ ለማክበር ታስቦ ከአሜሪካ ግብፅ፣ ሳውዲ አረቢያ፣ የመንና ሱዳን ከ30 በላይ ታላላቅ ኡላማዎችና እንግዶች መጠራታቸውን ገልፀው ይህም በቀጣዩ ዓመት በዓሉን በአለም አቀፍ ደረጃ ለማክበር ለሚደረገው  ዝግጅት ከፍተኛ አስተዋፅኦ እንደሚኖረው ጠቁመዋል፡፡

ሰሞኑን በአወሊያ ትምህርት ቤትና በአንዳንድ መስጊዶች የተነሣውን ውዝግብ አስመልክቶ ከአዲስ አድማስ ለቀረበላቸው ጥያቄ በሰጡት ምላሽ፤ ውዝግቡ በአንዳንድ አክራሪ አስተሳሰብ ባላቸውና ህገወጥ ተግባራትን ለማራመድ በተዘጋጁ ሰዎች የተፈጠረ መሆኑን ጠቁመው እነዚህ ግለሰቦች የግል ጥቅሞቻቸው የተነኩባቸውና በህገወጥ መንገድ ፍላጐታቸውን ለማስፈፀም የተዘጋጁ ናቸው ብለዋል፡፡ ተቃዋሚ አካላቱ የሚያነሱት የምርጫ አለመኖር ወይም ለአመታት መዘግየት ምክንያቱ ምንድነው በሚል ላቀረብንላቸው ጥያቄም፤ ጠቅላይ ምክር ቤቱ በየወቅቱ ምርጫዎችን እያከናወነ መሆኑንና እሣቸውም በ2001 ዓ.ም በተካሄደ የምክር ቤቱ ምርጫ ወደ ስልጣን መምጣታቸውን፣ የተሰጣቸው ኃላፊነት በምርጫ እንጂ በሹመት አለመሆኑን ተናግረዋል፡፡ ቀጣዩን ምርጫ በአገር አቀፍ ደረጃ ለማድረግ የበጀት ማሰባሰቡ ሥራ መጀመሩንም ፕሬዚዳንቱ ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡

ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ በተለያዩ ት/ቤቶችና በአንዳንድ የክልልና የአዲስ አበባ መስጊዶች አስተዳደሩን በመቃወም የፊርማ ማሰባሰብ ተግባር በማከናወን ላይ የሚገኙ ቡድኖች መኖራቸውን የጠቆሙት ፕሬዚዳንቱ፤ ይህም ሙስሊሙን ከሌላ እምነት ተከታዮችና ከመንግስት ጋር ለማጋጨትና በሙስሊሞች መካከል ልዩነትን ለመፍጠር የሚደረግ ዘመቻ በመሆኑ ህዝበ ሙስሊሙ ሊያወግዘው ይገባል ብለዋል፡፡  በአወሊያ ት/ቤትና በአንዳንድ መስጊዶች የጠቅላይ ምክር ቤቱን አስተዳደር በመቃወም ባለፈው ሳምንት የተለያዩ እንቅስቃሴዎች መደረጋቸውን መዘገባችን ይታወሳል፡፡

 

 

 

Read 8908 times Last modified on Saturday, 04 February 2012 13:38