የፍጻሜው ዳር ድንበሩ
የአዙሪት ሽክርክሩ
ቆም አለና ለዘንድሮ
ጥይት ወጣ ተስፈንጥሮ
ክብ ቀለበት ህይወት አምሳል
የገጠመ መስመር ጥቅልል
ቀጣይ መስሎ ሩቅ ዑደቱ
ድንበሩን ጣሰ ጥይቱ
በስመአብ ብሎ ሩቅ ጀምሮ
ምስጢረ አለም ካብ በርብሮ
የአለም የሥጋ ዕቃ ዕቃ
ሳይገባው ኖሮ ሙዚቃ
ለራሱ አዳልቶ ቆርሶ
ሺዎች መግቦ አጉርሶ
ለራሱ ምሎ አስምሮ
ታሪኩን ስሎ አሳምሮ
ረስተን ሰንብተን ሞቱን
ድንገት አጠፋ መብራቱን
የዘመን ነጥብ ጥይቱ
የቃላት ፈርጡ ተረቱ
የስሜት ፍሙ ግለቱ
ዕድሜ ያልተፈታ አዛውንቱ
የታሪክ የመዝገብ ቤቱ
ፈረሰ ብዬ የማወራው
አይታመንም እውነቱ
በስመአብ ብሎ ጀምሮ
ሳንጠግብ ስብሀት ዘምሮ
ለምን ፈጠነ ፍታቱ
ራቀ ለምድር ጥይቱ?
ከኢሳያስ ከበደ
የካቲት 12 ቀን 2004 ዓ.ም
ለጋሽ ስብሃት እረፍት መታሰቢያ