Saturday, 02 December 2017 08:43

በስንፈተ ወሲብና ፀረ እርጅና ህክምና ላይ ያተኮረ ክሊኒክ ሥራ ጀመረ

Written by  ናፍቆት ዮሴፍ
Rate this item
(41 votes)

 “ወንድ ታካሚዎች ቢጎርፉም እስካሁን ሁለት ሴቶች ብቻ ናቸው የመጡት”
            
    በስንፈተ ወሲብ በፀረ እርጅና፣ በውበትና ቁንጅና ማሻሻል ላይ አተኩሮ የሚሰራ “ዚኒያ” የተባለ ክሊኒክ በአዲስ አበባ አገልግሎት መስጠት ጀመረ። ክሊኒኩ የሚመራው ላለፉት 25 ዓመታት በዘርፉ ስፔሻላይዝድ አድርገው በአሜሪካ ሲሰሩ በቆዩት በትውልደ ኢትዮጵያዊው ዶ/ር አንተነህ ተስፋዬ ሮባ ነው፡፡ እንደ ሃኪሙ ገለፃ፤ በካናዳና አሜሪካ በዘርፉ ስፔሻላይዝ ካደረጉ 2500 ዶክተሮች አንዱ ሲሆኑ በተለይ በኢትዮጵያ ያለውን የዘርፉን ህክምና ክፍተት ለመሙላት የአሜሪካ ቴክኖሎጂዎችን ወደ አገር ውስጥ በማስገባት፣ ማህበረሰቡን እያገለገሉ መሆኑን ባለፈው ሳምንት መጨረሻ በክሊኒካቸው በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ተናግረዋል፡፡
ኢትዮጵያ ውስጥ በተለይ ስንፈተ ወሲብን በማከም ደረጃ የተለያዩ ክሊኒኮች ቢኖሩም ዓለም የደረሰበትን የህክምና ቴክኖሎጂ ከአሜሪካ በማምጣታቸው የእሳቸውን የተለየ እንደሚያደርጋቸው የጠቆሙት ዶ/ር አንተነህ፤ ክሊኒካቸው ከተከፈተ ጀምሮ ወንድ ታካሚዎች እየጎረፉና ውጤታማ ህክምና እያገኙ ቢሆንም ስንፈተ ወሲብን በተመለከተ ለህክምና የመጡት ሴቶች እስካሁን ሁለት ብቻ መሆናቸውን ገልፀዋል።
ክሊኒካቸው በተጨማሪም እርጅናን ተከትለው የሚመጡ የውስጥና የውጭ ችግሮችን በማከም፣ ጤናንና ውበትን ለማሻሻል የሚረዱ ህክምናዎችን በዘመናዊ ቴክኖሎጂ በመታገዝ በስኬት እንደሚያከናውኑም ተናግረዋል፡፡ የጋዜጣዊ መግለጫውን ዋና አላማ በሚመለከት ዶ/ሩ ሲናገሩ፤ በአገራችን ባህል ምክንያት ግልፅ ውይይት በተለይ በወሲብ ጉዳይ ባለመኖሩ በችግሩ ምክንያት ብዙ ጥንዶች ትዳራቸውን ለመፍታት እንደሚገደዱ ጠቁመው፣ ወደ ክሊኒኩ ጎራ በማለትና በሳምንት ሁለት ቀን ለ6 ዙር “ፒቫት PRP” እና “ዌቭ ቴራፒ” በመጠቀም ህክምና ካደረጉ ውጤታማ እንደሚሆኑ አስረድተዋል፡፡
አንዳንድ ታካሚዎች ገና በሶስት ዙር ስኬታማ እንደሚሆኑ ታካሚዎቻቸውን በምሳሌነት ጠቅሰዋል፡፡ ስንፈተ- ወሲብ በሆርሞን መዛባት፣ በእርጅና እና በተለያዩ ሥር የሰደዱ ህመሞች ሊከሰት እንደሚችል ጠቁመው፤ በሁሉም መንገድ ለሚመጣ ስንፈተ ወሲብ ስኬታማ የህክምና እርዳታ እንደሚደረግ ተናግረዋል፡፡

Read 13026 times