Print this page
Saturday, 02 January 2021 11:23

COVID-19 የያዛት እናት ለጨቅላዋ የምታደርገው ጥንቃቄ፡፡

Written by  ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ
Rate this item
(2 votes)

   የኮሮና ቫይረስ ካለባቸው እናቶች የሚወለዱ ህጻናት ምንያህል በቫይረሱ ይጎዳሉ የሚለውን በሚመለከት እስከአሁን ብዙም የተረጋገጠ ነገር የለም፡፡ ቢሆንም ግን ጨቅላዎችን በሚመለከት የሚታወቅ ነገር አለ፡፡
የኮሮና ቫይረስ ከያዛቸው እናቶች ሕጻናት በሚወለዱበት ጊዜ የኢንፌክሽኑ መተላለፍ የተለመደ ወይንም በግልጽ በዚህ ምክንያት ነው የሚባል አይደለም፡፡ በአለም ላይ አንዳንድ ጨቅላዎች ልክ እንደተወለዱ በኮሮና ቫይረስ መያዛቸው ግን ተረጋግጦአል፡፡ እነዚህ ጨቅላዎች የኮሮና ቫይረሱ ከመወለዳቸው በፊት፤ በሚወለዱበት ጊዜ፤ ወይንም ከተወለዱ በሁዋላ ቫይረሱ ካለበት ሰው በቅርብ ግንኙነት ምክንያት ይዞአቸዋል የሚ ለውን ማረጋገጫ መስጠት አስቸጋሪ መሆኑን የተደረጉ ዳሳሰዎች ያመለክታሉ፡፡
አብዛኛዎቹ ጨቅላዎች ቫይረሱ እንዳለባቸውና እንደሌለባቸው ለማወቅ ምርመራ ሲደረግላቸው መጠነኛ ህመም ኖሮአቸው ወይንም ምንም ምልክት ሳይኖራቸውና ከቫይረሱም አገግመው የሚገኙ ይሆናሉ፡፡ በእርግጥ አንዳንድ ጨቅላዎች ሕመሙ ጠንቶባቸው መገኘታቸው ተረጋግጦአል፡፡
የኮሮና ቫይረስ ካለባቸው እናቶች የተረገዙ ልጆች በእርግዝና ጊዜ የተለያዩ ችግሮች በመፈጠራ ቸው ምክንያት የመወለጃ ጊዜያቸውን ሳይጨርሱ ማለትም ከ37 ሳምንታት በታች በሆነ ጊዜ መወለዳቸው ተገልጾአል፡፡ በእርግዝና ጊዜ አጋጥመው የነበሩ ችግሮች ምናልባትም ከኮሮና ቫይ ረሱ ጋር በተያያዘ ሊሆን እንደሚችል ይገመታል፡፡
የኮሮና ቫይረስ ከያዛት እናት የተወለደው ልጅ በሆስፒታል ውስጥ ከእናቱ ጋር በተመሳሳይ ክፍል የሚቀመጥ ከሆነ አንዳንድ ጥንቃቄዎች ሊደረጉለት ይገባል፡፡ CDC እደሚለው አዲስ የተወለዱ ህጻናት ለኮሮና ቫይረስ የመጋለጣቸው እድል አነስተኛ ነው፡፡ ቢሆንም ግን እናቶች የአፍና የአፍንጫ መሸፈኛ mask ማድረግ እንዲሁም እጅን መታጠብ የመሳሰሉትን ጥንቃ ቄዎች ማድረግ ይገባቸዋል፡፡
በCOVID-19 ምክንያት በልዩ ክትትል የምትቀመጥ እናት ከልጅዋ ጋር ክፍልን የምትጋራ ከሆነ ልጅዋን ከማግኘትዋ በፊት ልታደርገው የሚገባትን ጥንቃቄ አምዱ ማስታወስ ይወዳል፡፡
ልጁን ከመታቀፍ በፊት እጅን በሳሙናና በውሀ ለ20 ሴኮንድ ያህል በደንብ መታጠብ፤ ውሀና ሳሙና በቅርብ የማይገኝ ከሆነ ቢያንስ ቢያንስ 60%አልኮሆል ያለበት የእጅ ማጽጃ Sanitizer ተጠቅሞ እጅን ማጽዳት ይገባል፡፡
አዲስ ከተወለደው ልጅ 6 ጫማ ያህል መራቅና በፈት ላይ mask ማድረግ ይገባል፡፡
አዲስ የተወለደውን ልጅ በተቻለ መጠን 6 ጫማ ያህል እርቆ እንዲተኛ ማድረግ ይገባል፡፡
ስለልጁ ምን ማድረግ እንደሚገባ ምንጊዜም ከጤና ባለሙያ ጋር መመካከር  ይገባል፡፡
ከላይ የተገለጹት ጥንቃቄዎች እናትየው በኮሮና ቫይስ ምክንያት ከገባችበት ከልዩ ክትትል ውጭም ብትሆን መቀጠል የሚገባው ነው፡፡ ከልዩ እንክብካቤ ውጭ ሳትሆን ወደቤትዋ ብትመለስም የሚከተሉትን ነገሮች ማሟላት ይጠበቅባታል፡፡
እራስን ከቤት ውጭ ከሚመጡ ጠያቂዎች አግልሎ በቤት ውስጥ መቆየት፤
በቤት ውስጥም ቢሆን የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ካላደረጉ ሰዎች ከተወሰነ እርቀት ውጭ መቀራረብን ማስወገድ፤
ለጨቅላው ምንም ጉዳት የማያስከትልና በጥሩ ሁኔታ የሚንከባከበው አገልግሎት ሰጪን መምረጥ ይገባል፡፡
ለተወለደው ልጅ ጥንቃቄ በማድረግ ጥሩ አገልግሎት የሚሰጥ ሰው ከጠፋ እናትየው እራስዋ ለልጅዋ እንክብካቤ ማድረግ አለባት፡፡ በቤት ውስጥ ያሉት የቤተሰብ አባላት ልጁን ከመንከባከብ እራሳቸውን እንዲያቅቡ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ ማድረግ ካለባቸውም ኮሮናን ለመከላከል ሊደረጉ ይገባል የተባሉ ጥንቃቄዎችን ማድረግ አለባቸው፡፡
አዲስ የተወለዱ ህጻናት የአፍና የአፍንጫ መሸፈኛ ሊደረግላቸው አይገባም፡፡ ምክንያቱም ድን ገተኛ መታፈንን ሊያስከትል ስለሚችል ነው፡፡ ህጻናት በፍጥነት የመንቀሳቀስ ባህርይ ስላላቸው መሸፈኛው አፍና አፍንጫቸውን ሊዘጋው ይችላል፡፡ CDC እንደሚገልጸው  የሁለት አመት እና እድሜ ያቸው ከዚያ በላይ የሆኑት ትኩረትን ሳይነፈጉ መሸፈኛውን መጠቀም ይችላሉ፡፡በተለይ ግን ከአምስት አመት በላይ የሆኑ ልጆች ስሜታቸውን ስለሚገልጹ Face mask መጠቀም ይችላሉ፡፡
COVID-19 ባለበት ሁኔታ እናቶች ወይንም ቤተሰብ የጨቅላውን የእንቅልፍ ሁኔታ ምን መምሰል እንዳለበት ያላወቁና መሆን የሚገባውንም የማያውቁ ስለሚመስላቸው ይጨነቃሉ፡፡ በእርግጥም ወላጆች ወይንም ቤተሰብ በጨቅላው አስተኛኘት ምክንያት ሊከሰት የሚችለውን ድንገተኛ ሞት ለማስወገድ ጥንቃቄ ማድረግ አለባቸው፡፡
ጨቅላውን ምንጊዜም በጀርባው ማስተኛት፡፡
መኝታውን የተስተካከለ እና ምቹ…ወጥ የሆነ ማድረግ ይገባል፡፡
ህጻኑ የወላጁን የመኝታ ክፍል እንዲጋራ ማድረግ ይቻላል፡፡ ነገር ግን መኝታን መጋራት የለበትም፡፡ በተቻለ መጠን ህጻኑ በአዋቂዎች አልጋ ላይ ከአዋቂዎች ጋር መተኛት የለበትም፡፡
የሚለብሳቸውን ብርድ ልብሶች እና እንደትራስ የሚያገለግሉትን ነገሮች ቀለል ያሉና ምቹ መሆን አለባቸው፡፡
የልጁን ጭንቅላት መሸፈን ወይንም ተጨማሪ ሙቀት እንዲያገኝ ማድረግ አያስፈልግም፡፡ ህጻኑ ሙቀት ከበዛበት በከባድ ላብ ሊዘፈቅና ሊጨነቅ ይችላል፡፡
ህጻኑ በሚስተናገድበት አካባቢ በጭራሽ የሲጋራ ጢስ ሊኖር አይገባም፡፡ የሚያጤሱ ሰዎች ካሉ መከልከል አለባቸው፡፡   
ባጠቃላይም የኮሮና ቫይረስ ከያዛት እናት የሚወለዱ ህጻናት በወላጆቸው አማካኝነት ከሚደረግ ላቸው ጥንቃቄዎች በተጨማሪ በሕክምና ባለሙያዎች ሊጎበኙ በሚገባቸው ጊዜ ሁሉ መታየት አለባቸው፡፡ ስለአመጋገባቸው፤ ስለጤንነታቸው፤ስለእድገታቸው ሁሉ ማወቅና ወደፊት ምን ማድረግ እንደሚገባ የምክር አገልግሎት ማግኘት ጠቃሚ ነው፡፡  
የኮሮና ቫይረስ ካለባት እናት የተወለደ ልጅ ጡት በመጥባቱ ምክንያት በጡት ወተት ምክንያት ቫይረሱ ይተላለፍበታል የሚል ምንም መረጃ የለም፡፡ ቫይረሱ የያዛት እናት ስለጡት ማጥባት ከህክምና ባለሙያዎች ቀጥታ ምክር ማግኘትና መተግበር ይጠበቅባታል፡፡ ጡት ማጥባት የህጻ ኑን ጤንነት እና እድገት በመጠበቅ በኩል ተወዳዳሪ የሌለው የተሟላ ምግብ መሆኑ አስቀድሞ መታወቅ ይገባዋል፡፡ ኮሮና ቫይረስ የያዛት እናት ጡት በማጥባትዋ ምክንያት ከጡት ወተቱ ቫይረሱ ወደልጅዋ ይተላለ ፋል የሚል መረጃ ባይኖርም በተለይም በሆስፒታል ውስጥ በቫይረሱ ምክንያት እናትየው ልዩ እንክብካቤ ውስጥ ከሆነች እና ከልጅዋ ጋር ከተራራቀች የሚከተሉትን ምክሮች ተግባራዊ ማድረግ ትችላለች፡፡
በሆስፒታሉ በኩል በሚደረጉ ድጋፎች በተደጋጋሚ ጡትን በማለብ ለልጁ ወተቱ እንዲሰጠው ማድረግ፤
በ24 ሰአት ጊዜ ውስጥ ቀንና ማት ቢያንስ ከ8-10 ጊዜ ጡትን በማለብ ህጻኑ ከሁለት-ሶስት ሰአት ባለው ጊዜ ወተት እንዲያገኝ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ በህመሙ ምክንያት ጡትን ማለብ እና ወተት መስጠት ካልተቻለ ሌላ የተዘጋጀ ወተት ለመስጠት በህክምና ባለሙያዎቹ እንዲወሰን ማድረግ ይጠቅማል፡፡
ለህጻኑ የጡት ወተት ለመስጠት ከቻሉ ልጁን አቅፎ ጡት ከመስጠት አስቀድሞ የኮሮና ቫይረስን ለመከላከል የወጡ ህጎችን በሚገባ መተግበር ያስፈልጋል፡፡   


Read 12266 times