በሰሜን ሸዋና በኦሮሚያ ብሔረሰብ ዞን በተደጋጋሚ ያጋጠሙ ሁከትና ጥቃቶች በገለልተኛ አካል በአስቸኳይ እንዲመረመር የጠየቀው ኢህአፓ፤ በሰሜን ሸዋ ኦነግ ሸኔ እንዴት ሊገኝ ቻለ የሚለው ጥያቄም ሊመለስ ይገባዋል ብሏል፡፡
የኢትዮጵያ ህዝብ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢህአፓ)፤ “የሰሜን ሸዋ ጭፍጨፋና የኦነግ ሸኔ ጉዳይ፤ ያልተመለሱ ጥያቄዎች” በሚል ከሰሞኑ ባወጣው መግለጫ፤ በዋናነት ስለ ኦነግ ሸኔ መሃል ሀገር መገኘት መንግስት ለህዝቡ ሙሉ ማብራሪያ እንዲሰጥ ጠይቋል።
ኦነግ ሸኔ በርካታ የታጠቀ ሃይል ይዞ እንዴት ሰሜን ሸዋ ሊገባ ቻለ? በዚህ ጊዜ ሁሉ እንዴት የአስተዳደርና የፀጥታ ሃይሉ ሊያስቆሙትና እርምጃ ሊወስዱበት አልቻሉም? ከአንድ ቦታ ወደ አንድ ቦታ ያለ ቁጥጥር እንዴት ሊንቀሳቀስ ቻለ? እንቅስቃሴውን ችላ ብሎ መንገድ ከፍቶ ያሳለፈው ማን ነው? ይህ ሃይል የተደራጀው እዚያው ሰሜን ሸዋ ነው ወይስ በአካባቢው የነበረውን የመንግስት ፀጥታ ሃይል እየደመሰሰ ነው እዚያ የደረሰው?; ለእነዚህ ጥያቄዎች መንግስት ቀጥተኛ መልስ እንዲሰጥ ኢህአፓ በመግለጫው ጠይቋል፡፡
ከዚህ በኋላም በአካባቢው ልዩ ትኩረት በመስጠት የተጠናከረ ጥበቃ እንዲደረግለት እንዲሁም በሰሜን ሸዋና በሌሎችም አካባቢዎች የተፈጠሩትን ጭፍጨፋዎች በገለልተኛ አካል በአስቸኳይ እንዲጣሩና ወንጀለኞች ለህግ እንዲቀርቡ ኢህአፓ ጠይቋል፡፡