Saturday, 11 September 2021 00:00

የዓመቱ አበይት ክንውኖች - ፈተናዎችና ስኬቶች

Written by 
Rate this item
(0 votes)

 ዛሬ የሚጠናቀቀው  2013 ዓ.ም ለኢትዮጵያውያን የመከራም የስኬትም ዘመን ሆኖ ማለፉ ይታወቃል፡፡ ዘመኑ አገሪቱ እንደ አገር መቀጠል እንዳትችል የሚገዳደሯት በርካታ ችግሮችና መሰናክሎችን የተጋፈጠችበትና በሺዎች የሚቆጠሩ  ዜጎችን በጦርነት በግጭትና ተፈጥሮአዊ አደጋዎች ያጣችበት፣ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ዜጎች ለስደት የተዳረጉበት ነበር። በሌላ በኩል፤ አገሪቱ ከውስጥና ከውጭ ጠላቶቿ የሚደርስባትን ጫና ተቋቁማ ሰላማዊ ምርጫ ያካሄደችበት፣ ሁለተኛውን ዙር የህዳሴ ግድብ ሙሌት ያከናወነችበትና  በርካታ ፕሮጀክቶችን አጠናቃ ወደ ስራ የገባችበት የስኬት ዘመንም ነበር፡፡
በ2013 ዓ.ም በአገራችን ከተከናወኑ አበይት ጉዳዮች መካከል ዋና ዋናዎቹን ለመቃኘት እንሞክራለን፡፡
የብር ኖት ቅያሬ
ኢትዮጵያ ከ23 ዓመት በላይ ስትገለገልበት የቆየችውን የ10፣ የ50 እና የ100 ብር  ኖቶች ቅያሬ ያደረገችውና በታሪኳ ለመጀመሪያ ጊዜ የባለ 200 ብር ኖት ያሳተመችው በዚሁ ባጠናቀቅነው ዓመት ነበር፡፡ ከገንዘብ ጋር የተገኙ ህገ ወጥ ተግባራትን ለመቆጣጠርና ከባንክ ውጪ ያለውን የጥሬ ገንዘብ ዝውውር ለመግታት ያስችላል የተባለው ይኸው የገንዘብ  ኖት ቅያሬ ይፋ የተደረገው በጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ መስከረም 4 ቀን 2013 ዓ.ም ነበር። ከባንኮች ውጪ የሚገኘው ጥሬ ገንዘብ እጅግ ከፍተኛ በመሆኑ ይህንን ገንዘብ ወደ ትክክለኛው የግብይት ስርዓት ለማስገባት ባለመቻሉ ምክንያት እርምጃ መወሰዱን የተናገሩት የብሔራዊ ባንክ ገዢው ዶ/ር ይናገር ደሴ፤ ጥሬ ገንዘብ በአገር ውስጥ ብቻ ሳይሆን በጎረቤት አገራትም በከፍተኛ ሁኔታ እንደሚገኝና ይህም ለህገወጥ ተግባራት እየዋለ መሆኑ እንደተደረሰበት በዚሁ አዲሱን የብር ኖት ይፋ ማድረጊያ ፕሮግራም ላይ ተናግረው ነበር፡፡ የብር ኖት  በ3 ወራት ውስጥ እንዲጠናቀቅ የተደረገ ሲሆን በትግራይ ክልል በነበረው የህግ ማስከበር ዘመቻ እንቅስቃሴ ምክንያት የብር ቅያሬው እስከ መጋቢት 10 ቀን 2013 ዓ.ም እንዲራዘም ተደርጓል፡፡


Read 9736 times