Saturday, 23 October 2021 13:04

ከሃዲው ህውሃት ብቻውን አይደለም፤ ከውጪ ጠላቶቻችን ጋር አብሮ ነው የሚሰራው

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

  • የአማራ ክልል ነባራዊ ሁኔታ ፈተናዎች ተስፋዎች (በጦርነት- መፈናቀል- መስዋዕትነት)
        • ወደ 4ሚ. የሚጠጋ ህዝብ ነው እርዳታ የሚጠብቀው
        • በእርዳታና በመድሃኒት እጦት ሰዎች እየሞቱ ነው

        አሁን አገራችን የምትገኝበትን ወቅታዊ የህልውና ዘመቻ ተከትሎ በተለይ በአማራ ክልል የሰሜን ወሎ የዋግ ህምራና የሰሜን ጎንደር አካባቢዎች ላይ ከፍተኛ ችግር መፈናቀልና ሰብአዊ ቀውስ እየደረሰ ይገኛል። የዚህ ጉዳይ ዋነኛ ባለቤት የሆነው የአማራ ክልል መንግስት ጉዳዩን እንዴት ያየዋል? ጦርነቱ እንዴት ነው የሚቋጨው፣ በጦርነቱ የተፈናቀሉና በተወረሩ አካባቢዎች ያሉት ወገኖች ጉዳይ እንዴት ይታያል? የእርዳታ አሰጣጡስ ጉዳይ ምን ይመስላል በሚሉና በተያያዥ ጉዳች ዙሪያ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ ባህርዳር ተጉዛ የክልሉን መንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ዋና ዳይሬክተር አቶ ግዛቸው ሙሉነህን በጽ/ቤታቸው እንደሚከተለው አነጋግራቸዋለች። እነሆ፡-


           በክልሉ የአዲስ መንግስት ምስረታው እንዴት ነበር? የመንግስት ባለስልጣናት ሹመትስ ምን ይመስላል? ህዝቡስ  በአዲሱ መንግስት ስሜቱ ምን ይመስላል?
እንግዲህ ስድስተኛው አገር አቀፍ ምርጫ ተካሂዷል። ይህ ምርጫ ከሌሎች ጊዜያት ምርጫዎች በብዙ ምክንያት ለየት ብሎ የተካሄደ ነው። የመጀመሪያው ለየት የሚልበት ወቅቱን ጠብቆ የተካሄደ  አልነበረም። በኮረና ወረርሽኝና በሀገራችን የተለያዩ አካባቢዎች በተፈጠሩ ግጭቶች ምክንያት በተለይም ኮሮና ቫይረስ ባደረሰው ከፍተኛ ጫና ምርጫውን በወቅቱ ማስኬድ አልተቻለም። አንዱ ይሄ ነው። ሁለተኛ ይህ ምርጫ ከሌሎቹ አምስት ምርጫዎች በተለየ ሁኔታ ህዝቡ የተሳተፈበት፣ እውነተኛ፣ ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ የተካሄደበትን ሂደት ያሳየ ነው። ምንም እንኳ በአንዳንድ አካባቢዎች በፀጥታ ችግር፣ ምርጫው ዘግይቶ ቢካሄድም ያሸነፈው ፓርቲ ከፌደራል እስከ ክልል የመንግስት ምስረታ ተካሂዷል። የመንግስት ምስረታ ማካሄድ ብቻ አይደለም፤ አጠቃላይ የመንግስት ምስረታና አደረጃጀቱን መልሶ የማጠናከር ስራው አሁን ላይ በክልላችን ከዞን እስከ ወረዳዎች ደርሶ እየተሰራ ነው።
ይህን ስንመለከት እንደ አማራ ክልል፣ በአዲስ መንግስት ምስረታ፣ በተለይም የአመራር የሃላፊነት ቦታ አሰጣጥን በተመለከተ ከ75 በመቶ በላይ አዳዲስ አመራሮች የመጡበት መንግስት ምስረታ ነው የተካሄደው። የአዳዲስ አመራሮች መምጣት ብቻ ሳይሆን ከቀድሞው ባልተለመደ ሁኔታ ተቃዋሚ ፓርቲዎች አሸንፈው መንግስት ባይመሰርቱም እንኳን የዴሞክራሲ ስርጭቱን የበለጠ ለማስፋት፣ በተለይ የማቻቻል ባህላችንን ለማሳየትና አዲስ የፖለቲካ ምዕራፍ ለመክፈት፣ በተለይም ከብሄራዊ መግባባትና ከሀገር ግንባታ አኳያ፣ የተለየ ገጽታ ስላለው፣ በካቢኔ ደረጃ የተሾሙበት ለየት ያለ ስልት የፈጠረ ነው። በሌላ በኩል፤ ምሁራን የመጡበት፣ በስነ- ምግባራቸው ላቅ ያለ ደረጃ ያላቸው፣ የመስራት ፍላጎታቸው ከፍተኛ የሆነ ጭምር ሰዎችን ለመቀላቀል ተሞክሯል።
ሌላው ከተዋፅኦ አኳያ ብንመለከት ከሁሉም አካባቢዎች የመመልመል ስራ ተሰርቷል። ይህ እንግዲህ የተሳካ አካሄድ ነው ብለን እናምናለን። ከመቼውም ጊዜ በላይ ህዝቡ ተስፋ የሚያደርግባቸው መሪዎች የመጡበት ጊዜም ነው። ክልሉ አንደምታውቂው ብዙ ውስብስብ ችግር ያሉበት ነው ። ጠላቶቹም ብዙ ናቸው። አሁን ካለው ነባራዊ እውነታ አኳያ፣  የተደረገው የአመራር ስምሪትና የመንግስት ምስረታው ችሮችን ሁሉ ይፈታል የሚል ተስፋ በህብረተሰቡ ዘንድ ከፍተኛ ነው። እንዴት ካልሽኝ? ከመንግስት ምስረታው በኋላ የህዝብ አስተያየት እስከ ታች ድረስ ሰብስበን ነበር። ከመጣው የህዝብ አስተያየት መካከል  ማለትም ከተሰበሰበው የሕዝብ አስተያየት ከ90 በመቶ በላይ ምስጢር ተጠብቆ ሳይዝረከረክ ስነ-ስርዓቱን ጠብቆ የተካሄደ ምርጫ ነው የሚል ነው። የሌላ ሶስተኛ ወገን ተፅዕኖ ሳይኖር፣ በአውጫጭኝና በጎጥ ሳይመደብ፣ ራሽናል በሆነ መንገድ የተካሄደ ስለመሆኑ ህዝቡ በአስተያየቱ  ተገልጿል። በአጠቃላይ የመንግስት ምስረታው፣ በምስረታው የተመረጡ አመራሮችና በአጠቃላይ ሂደቱ ህዝብ ተስፋ እንዳደረበት የሚያሳይ ነው።
ሌላው ከመንግስተ ምስረታው ቀጥሎ የተዋቀረው የካቢኔ አባል አጠቃላይ የስራ ድርሻችን ምንድን ነው? በሚል የመግቢያ ኮርስ ውይይት ተደርጓል። አሁንም በክልሉ ተቀዳሚው ሥራ፤ ሰላምና ደህንነትን ማስጠበቅ ሲሆን የክልሉ ህዝብ ህልውና ላይ የተጋረጠውን አደጋ የማሳየትና የደህንነት ጉዳይ ቀዳሚ ነው ብሎ ስራውን ጀምሯል። ቀጥሎ ደግሞ የአማራ ህዝብ ጥያቄ የሆኑ ሌሎች ጉዳዮችን በዝርዝር ለመፍታት የሚያስችሉ እቅዶች ላይ ኦሬንቴሽን ተሰጥቶ አዲሱ መንግስት ወደ ስራ የገባበት ሁኔታ አለ።
ትህነግ ጦርነት ከከፈተ እነሆ አንድ ዓመት ሊሞላው ቀናት ብቻ ናቸው የቀሩት። በአጭር ጊዜ ይጠናቀቃል የተባለው ጦርነት እየተስፋፋ ይገኛል። አሁን በምንነጋገርበት ወቅት  እንኳን እንደነ ወልዲያ ላሊበላና ሌሎች ከተሞች ተይዘው ይገኛሉ።  በርካታ የአማራ ህዝብ ለሞትና ለመፈናቀል ተዳርጓል። ይህንን ጦርነት በአጭሩ ለማጠናቀቅ ምን መደረግ ነው ያለበት? የዚህ ጦርነት ገፈት ቀማሽ የሆነው የአማራ ህዝብ፣ በአሁኑ ሰዓት ጦርነቱን ከመመከት፣ ሰራዊቱን ከመደገፍና ከመታገል አኳያ ያለው ስሜት ምን ይመስላል? ምክንያቱም በመንግስት በኩል መዘናጋትና ክፍተቶች አሉ የሚል ቅሬታ ይሰማል…
መልካም! እንዳልሽው የህልውና አደጋን በተመለከተ ስናነሳ፣ ክልላችን ላይ አሸባሪው የህወሃት ሀይል ሁለት ጊዜ ወረራ ፈጽሟል። ጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ.ም የነበረው ወረራ አለ። በድጋሚ ከአንድ ወገን የተኩስ አቁም ስምምነቱ በኋላ ሌላ ወረራ ተፈጽሞብናል። ስለዚህ የመጀመሪያው የህግ ማስከበር ዘመቻ ነበር። ሁለተኛው ህልውና ላይ የተጋረጠ ወረራ ስለሆነ የህልውና ዘመቻ ተደርጓል። እንዳልሽው አጠቃላይ ወረራው ከ11 ወራት በላይ የዘለቀ ነው።
በታሪክ አጋጣሚ ደግሞ ክልላችን አጎራባች በመሆኑ ዋጋ እየከፈለ ነው ያለው። በአጠቃላይ የአሸባሪውን የህወሃት እንቅስቃሴ በተመለከተ በወረራ ብቻ የሚቆም አይደለም።
የወረራው መንፈስና ዓላማ፣ አጠቃላይ አገርን የማፍረስ፣ ከተቻለም ዳግም አገርን እየመራ እንዳለፉት 30 ዓመታት መበዝበዝ ነው። ይሄ ነው አጠቃላይ እንቅስቃሴውና የፕሮጀክቱ ዓላማ።
ስለዚህ ይህ ፕሮጀክት የሚሳካ አይደለም። እንዳይሳካም አስፈላጊው ነገር ሁሉ እየተደረገ ነው ያለው። የሀገር መከላከያ ሰራዊት፣ ከሁሉም ብሄር ብሄረሰቦች የተውጣጡ ልዩ ሀይሎች፣ ሚሊሻዎችና ወጣቶች በከፍተኛ ደረጃ ተደራጀተው ህልውናቸውን ለማስከበር ትግል ላይ ናቸው።  በደንብ እየተዋጋን አይደለም፤ ክፍተት አለ ላልሺው፣ ይሄ ሀሰት ነው። በዚህ ጉዳይ ኦፕሬሽኑን እየመራ ያለው የሀገር መከላከያ ሰራዊት ነው።  ጦርነት ሳይንስ ነው።  ይህንን የሳይንሱ ባለቤቶቹ የሚተነትኑት ነው። መቼ ያበቃል? ለምን አላለቀም? የሚሉና መሰል ጥቄዎች በዚያው ይመለሳሉ። እርግጥ የኦፕሬሽኑን ሥራ ፖለቲከኛው በበላይነት ይመራዋል። ይሄ ምንም ጥያቄ  የለውም። ነገር ግን እነዚህ አይነት ነገሮች ከደህንነት ጉዳይ አኳያ ቴክኒክ የሚጠይቅ በመሆኑ በዚህ ጉዳይ ላይ በዝርዝር መነጋገር አንችልም። አጠቃላይ ዝግጅቱን በተመለከተ ግን ከእኛ የሚጠበቀውን በሙሉ እያደረግን ነው። ከመቼውም ጊዜ በላይ ኢትዮጵያ እስካሁን  ከሰራቻቸው በተለየ ሁኔታ የመከላከያና የልዩ ሀይሉን ለማጠናከር ከፍተኛ የሰው ሀይል የማደራጀት ስራ ተሰርቷል። ይሄ አንድ ትልቅ ለውጥ  የሚታይበት ነው።  ህዝቡ ከአንድ ቤት ሁለትና ከዚያ በላይ ልጆቹን ጭምር “ለህልውናህ ዝመት” ብሎ መርቆ የሚልክበትን ሁኔታ እያየን ነው። ልጆቹን ከመላክ ባሻገር በስንቅ ዝግጅት፣ ገንዘብ በማዋጣትና በሌሎች ድጋፎችም ጭምር ሁሉም የማህበረሰብ ክፍል ደሃ የሚባለውን የህብረተሰብ ክፍል ጨምሮ  እስከ ትልልቅ ባለሀብቶች ድረስ ያሉት ለዚህ የህልውና ዘመቻ አስፈላጊውን ድጋፍ እያደረጉ ነው ያሉት። በውጪ ያሉ ዲያስፖራዎች፣ ምሁራን፣  የመንግስት ሰራተኞች… ሳይቀሩ አሁን ያለው የኑሮ ውድነት ጫና ሳይገድባቸው፣ ህልውናቸውን በማስቀደም ደሞዛቸውን እስከ መስጠት ነው ትግል እያደረጉ ያሉት። እንደሚታወቀው ጦርነት አውዳሚ ነው። በሁለቱም በኩል ጦርነት ጎጂ ነው። በዚያ ላይ የጠላት ባህሪ የተለየና እጅግ አስቀያሚ ነው። ወረራ በፈጸመባቸው አካባቢዎች በኢኮኖሚ ሰብአዊ ቀውስ እንዲደርስ ለማድረግ፣ አጠቃላይ ኢኮኖሚው እንዲደቅ  የሚያገኘውን ሁሉ የሚያጠፋ ሃይል ነው።
ሰብአዊ ሀብትን ከማጥፋት፣ ሰውን ከመረሸን ባሻገር… መቼም አይታችሁት ይሆናል እንስሳትን እስከ መግደልና እስከ ማውደም የዘለቀ አረመኔነት ነው ያለው። ይህን የሚያደርገው ሆን  ብሎ በክልሉ ላይ የኢኮኖሚ ጫና በማድረስ ህዝቡ እንዲጎሳቆል ለማድረግ ነው። ሆስፒታሎችን ይዘርፋል፣ ት/ቤቶችን ያፈርሳል፣ ሌሎች ተቋማትንም ይዘርፋል፣ መሰረተ ልማቶችንም ያወድማል። የሚጭነውን ይጭናል፤ የቀረውን ያቃጥላል። ለምሳሌ ሆስፒታል ውስጥ ገብቶ የሚጭነውን ይጭንና የማይጫን ማሽነሪና ሌላ ካለ ያቃጥላል። ይህ ሆን ተብሎ ነው- ህዝብን ለመጉዳት ወራሪና አሸባሪ ሀይሉ የሚያደርሰውን ጉዳት ህዝቡ ተገንዝቧል። ይህንን ሀይል ለመዋጋትና  ከስሩ ለማጥፋት የአማራ ህዝብ በሙሉ ዝግጁ ነው። የአማራ ህዝብ ብቻ አይደለም፤ ሌሎች ብሄር ብሄረሰቦችም በዚህ ጉዳይ ያሳዩት ምላሽ በጣም ከፍተኛ ነው። በአጋጣሚ ጦርነቱ የሚካሄድበት አማራ ክልል ሆኖ ጫናውን ሌሎችም ክልሎች ስለሚገነዘቡ፣ እገዛ ሲያደርጉ ትመለከታላችሁ።
ይሄ ድጋፍ ተጠናክሮ የሚቀጥል ነው። አሸባሪው ህውሃት የጋራ ጠላታችን መሆኑን የኢትዮጵያ ህዝብ ስለተገነዘና ይህን ጠላት ካላስቆምነው ነገም ለሌሎቹ አደጋ ስለሚሆን፣ ከስሩ ለማጥፋት እየተሰራ ነው። በነገራችን ላይ አሸባሪው ህውሃት ማለት ባለፉት 30 ዓመታት በመላ ሀገሪቱ ውስጥ በተለይም ባለፉት  ሶስት ዓመታት በሁሉም ክልሎች ለተፈጠሩትና እየተፈጠሩ ላሉት ችግሮች መነሻና ዋናው አቀንቃኝ እሱ ነው።  ሰሞኑን  ኦሮሚያ ላይ ለተፈጠረው ግጭትም ሆነ ሌላ ጊዜ በሌላ ቦታ ለሚፈጠርም ለእያንዳንዱ ግጭት እጁ አለበት።
ከሀዲው ህወሃት ብቻውንም አይደለም፤ ከውጪ ጠላቶቻችን ጋር አብሮ ነው የሚሰራው። በዚህ ደረጃ ጨካኝ የሆነውን ጠላታችንን ህውሃትን፣ የኢትዮጵያ ህዝብ በተለይም ወጣቱ በሚገባ አውቆታል፤ ተገንዝቦታልም። ስለዚህ አስፈላጊውን ሁሉ ለማድረግ ዝግጁ ነው፤ አንድ የሚነሳ ሃቅ ግን አለ። ጦርነቱ እየተራዘመ በሄደባቸው አካባቢዎች በተለይም ወረራ በተፈጸመባቸው አካባቢዎች በተለይም ደግሞ የዋግ ብሄረሰብ አስተዳደር፣ የሰሜን ወሎ አስተዳደርና የደቡብ ወሎ ደግሞ ውስን ቀበሌዎች፣ ሰሜን ጎንደርም የተወሰኑ አካባቢዎች ላይ ወረራ ከመፈጸሙም በላይ ጦርነት እየተካሄደ ያለባቸው አካባቢዎች ናቸው።
እርስዎ እንዳሉት ጦርነት ሳይንስ ነው። ሚሊተሪ ሳይንስም የሳይንሶች የበላይ ነው ይባላል። ይሄ ያግባባናል። አሁን ለብዙ ኢትዮጵያዊያን ግራ እያጋባ ያለው የህወሃት ጡንቻ እንዴት ፈረጠመ? የሚለው ነው። በህግ ማስከበሩ ዘመቻ በሶስት ሳምንት ተበታትኖ ዋሻ የገባው ህወሃት፤ አሁን ከክልሉ አልፎ የአማራና አካባቢዎችን እስከ መውረር የደረሰው  በምን አቅም ነው ይላሉ?
እውነት ለመናገር መጀመሪያ አካባቢ፣  እዚህ ወረራ ይፈጸማል የሚል እምነት አልነበረንም። እኛ ትኩረታችን ልማት ላይ እንጂ የጦርነት ዝግጅት አልነበረንም። ሲጀመር ደግሞ ያ ሁሉ  ከተካሄደ በኋላ የትግራይ ህዝብ ነጻነት እንዲያገኝ፣ ወደ ልማት እንዲገባ በሚል በመንግስት በኩል አቋም ተወስዶ፣ የአንድ ወገን የተኩስ አቁም ስምምነት ሲፈጸም፣ ምናልባትም ተጸጽቶ የትግራይን ህዝብ ነፃ ያደርጋል፤ የትግራይን ህዝብ ይተዋል የሚል እምነት ነበረን እንጂ ከዚህ በላይ  የትግራይን ህዝብም ሆነ ሌላውን ለመበደል ይንቀሳቀሳል የሚል ግምት አልተወሰደም ነበር። በዚህ መልኩ ያንን እድል ተጠቅሞ ሀይል አደራጅቶ ወረራ ፈጽሟል። ከውጪ ሃይልም ጋር ተቀናጅቶ ነው ሀገር እየወጋና እያፈረሰ ያለው። በሌላ በኩል የትግራይን ህዝብ  አስገድዶ የሰው ማዕበል (HUman wave) ነው የለቀቀው።
አሁን ላይ የህወሃት በደል ለትግራይ ህዝብም እየገባው  እንደሆነ እገምታለሁ። በጣም ብዙ ሀይል ነው ያለቀበት። ብዙ ህፃናት ናቸው የረገፉት። ብዙ ወጣቶችን ነው እያስጨረሰ ያለው። ይህንን የሚያደርገው በውሸት ፕሮፓጋንዳና አስገድዶ በመያዝ ስልጣን ላይ የሚወጣ በማስመሰል ነው። በውሸት ትርክትና ቅጥፈት የትግራይን ወጣት እየማገደ እዚህ ደርሷል። በኢትዮጵያ መከላከያም በኩል ህወሃት ሂውማን ዌቭ ሲለቅ እንዴት ህዝብ እመታለሁ በሚል ችግር ውስጥ የገባበትና ርህራሄ ለማሳየት የሞከረበት ጊዜም ነበር።
በነገራችን ላይ ወራሪ ሲመጣ ማህበረሰቡ ደጀን ሆኖ ካልጠበቀ ችግር ይመጣል። ማህበረሰቡ ይሄ ነገር አለ ብሎ ነቅቶ መጠበቅ አለበት። እንጂማ ወታደርማ ድሮም አለን እኮ። ወታደር የለም ማለት አይደለም። ዝግጅት ሲባል ማህበረሰቡን እዚህ ቦታ ይሄ አለ ብለሽ፣ በስነ-ልቦና ማዘጋጀትና ማንቃት ማለት ነው። ይህ ሲሆንና ማህበረሰቡ ደጀን ሲሆን ነው ውጤት የሚመዘገበው። ዞሮ ዞሮ በሀይል ደረጃ የወገን ጦር በቂ ሀይልና አቅም አለው። በቂ ሃይልና  ዝግጅት ካለ ለምንድነው ጦርነቱ በፍጥነት የማይቋጨው ለምትይኝ፣ አሁንም ኦፕሬሽኑን የሚመሩት አካላት ናቸው ሳይንሱን መተንተን የሚችሉት ብዬ ነው የምመልስልሽ። አንዳንዴ ለሚዲያም ግልፅ የማይደረግበት አግባብ ሊኖር ይችላል፤ የሚለውም ግንዛቤም መወሰድ አለበት።
ሰሞኑን በምዕራብ ወለጋ ኪረሙ ወረዳ ሸኔ የተባለው አሸባሪ ታጣቂ ሀይል፣ ዘር ተኮር ጥቃት በማድረግ ንፁሃንን እየጨፈጨፈ ይገኛል። ይህ የሚያሳየው የአማራ ህዝብ በየአቅጣጫው አደጋ ውስጥ መሆኑን ነው፡፡ በቤንሻንጉል ጉሙዝም እንደዚሁ ተመሳሳይ ችግር አለ። በሰሜን ሸዋ ማጀቴ በሚባል አካባቢም ሰሞኑን የ15 አርሶ አደሮች ምርት በተከመረበት በእሳት ቃተሎ ወድሟል፡፡ አንድ የክልል መንግስት ባለበት ያውም በተደጋጋሚ ይህ ሁሉ ጥቃት ሲደርስ፣ የአማራ ክልል መንግስት ከነዚህ ክልል አመራሮች ጋር ተመካክሮ ችግሩን የሚፈታበት አግባብ የለም? ለዚህ ሁሉ ጥፋት ማንስ ነው ተጠያቂው? በጉዳዩ ላይ ከእነ አቶ ሽመልስ አብዲሳስ ጋር ትነጋገራላችሁ?
በመጀመሪያ ደረጃ ቅድም እንዳነሳሁልሽ፣ ከአሁን ቀደምም በተደጋጋሚ ማጀቴና አጣዬ አካባቢ ከኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደር የሚፈጠሩ ግጭቶች፣ በኦሮሚያ ክልል አካባቢዎች የሚፈጠሩ ጥቃቶች ቤኒሻንጉልም ላይ የሚፈጸመውን ጨምሮ መነሻቸው ህውሃት ነው። ይህንን የሚቀበሉ ተላላኪና ባንዳ ሃይሎች አሉ። አንዱ ኦነግ ሸኔ ነው። ኦነግ ሸኔም ብቻ አይደለም። ከመንግስት ሃይሎች ውስጥም እነሱን የሚተባበር ባንዳ አለ። በተለይ ከታችኛው መዋቅር ከዞንም ከወረዳም ከቀበሌም ውስጥ እነዚህ ባንዳዎች አሉ። ይህ በግልጽ ታውቆ ከአንዴም ሁለትና ሶስት ጊዜ የኦሮሚያ ክልል መንግስት እርምጃ ወስዶበታል። በሰሜን ሸዋም እንደዚሁ ተመሳሳይ ተግባር ላይ የተሰማሩ ጠላቶች አሉ። እነዚህ ሁሉ ግጭቶች ግን ተራና ደራሽ ግጭቶች አይደሉም። በረጅሙ ታቅዶ አማራን ለማጎሳቆል፣ ክልሉ ዝቅ እንዲል ቀጥሎም አገር የማፍረስ ስትራቴጂ ነው። እንግዲህ ከዚህ በፊት የውሸት ተረክ አለ። ያንን መነሻ በማድረግ በሰሜን ሸዋም በሌሎቹ የኦሮሚያ ክልል አካባቢዎችም እህል እስከማቃጠል የሚደርሰው ትንኮሳ፣ ብሄርን ከብሄር፣  ሃይማኖትን ከሃይማኖት በማጋጨት አገር ለማፍረስ የተሰራ ፕሮጀክት ነው። ይሄ ግን አይቀጥልም፤ አይሳካም። የአማራ ህዝብም ሆነ ሌሎች ኢትዮጵያ ብሄር ብሄረሰቦች ቀንደኛ ጠላታቸው ማን እንደሆነ ጠንቅቀው ያውቀቃሉ። አሸባሪው ህውሃት ላይ የሚደረገውን ዘመቻ በጭራሽ ችላ ሊሉት አይችሉም። ችላ ሊባል አይገባም። ሁለተኛ እየደረሰ ላለው ጥፋና በደል መንግስት ሃላፊነት መውሰድ አለበት።
የትኛው መንግስት፣ የክልሉ ወይስ የፌደራል መንግስት?
ሁለቱም! የክልሉ መንግስትም ሃላፊነት መውሰድ አለበት  የፌደራል መንግስትም ሃላፊነት በመውሰድ የዜጎችን ደህንነት የመጠበቅ ግዴታ አለበት። ይሄ ጥያቄ ውስጥ የሚገባ አይደለም። ከእኛም ክልል አኳያ እየደረሰ ያለውን ነገር ማስቆም አለብን። በኦሮሚያም ሆነ ሌላው ቦታ ላይ የሚደርሰውን የአማራን ህዝብ ጥቃት ማስቆምና ህዝቡን ከአደጋ መጠበቅ አለብን። እንደ መንግስት ማለቴ ነው።
ይህን ብለን ስናበቃ ግን እኛም ዝም ብለን እጃችንን አጣጥፈን አልተቀመጥንም። ይሄ መታወቅ አለበት። ከኦሮሚያ ክልል መንግስት ጋር በቅርበት እየሰራን ነው ያለነው። በፊት የነበሩትም ችግሮች የተቀረፉትና እየተቀረፉ የመጡት በመስራታችን ነው። አሁንም፣ የተመሰረተው አዲሱ መንግስት ፣ይህን ችግር ለመፍታት ከፍተኛ አመራሮች ከፌደራልና ከኦሮሚያ መንግስት ጋር  በጋራ እየተወያዩና በቅርበት እየሰሩ ነው ያሉት። ከኦሮሚያ ክልል መንግስት ፕሬዚዳንት አቶ ሽመልስ አብዲሳም ጋር ቢሆን ከአዲሱ የክልላችን ፕሬዚዳንት ዶ/ር ይልቃልና ከፌደራል አመራሮች ጋር ተገናኝተው በጥልቀት ተወያይተዋል።
በዚህ መንገድ  እዚያ ችግሩ ያለበት ቦታ ላይ መሰማራት ያለበት ሀይል እንዲሰማራ አድርገዋል። ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታት በሚቻልበት መንገድ ላይም ተደጋጋሚ ውይይት እየተደረገ ነው ያለው። አሁንም ችግሩ በአንድ ጀምበር የሚፈታ አይደለም።  ይህ ጉዳይ በይድረስ ይድረስ ወይም በድንገት የመጣ አይደለም። ታቅዶና ታስቦ የሚፈጸም እስከሆነ ድረስ ፣ ጠላቶቻችንን ለኢትዮጵያና ለአማራ ክልል አደጋ የማይሆኑበት ደረጃ ላይ ከላደረስንና በተለይም አሸባሪው ህወሃት ላይ አስፈላጊውን እርምጃ ወስደን ስጋት እንዳይሆን ካልታገልነው ይሄ ችግር በተዓምር ሊቆም አይችልም። ነገም ሊከሰት ይችላል። ይሄ ችግር ዳግም እንዳይከሰት እየለፉና እየጣሩ ነው ያሉት። ኦሮሚያ ኦነግ ሸኔ ላይ ብዙ እርምጃ ወስዷል፤ እየወሰደም ነው ያለው።  እርግጥ ነው ጥቃቱ ሆን ተብሎ ዘር ተኮር ሆኖ የሚከሰት ነው። ነገር ግን ደግሞ ሌሎቹም ላይ ጭምር ጥቃት እያደረሰ ይገኛል። አማራ ላይ ብቻ አይደለም ማለቴ ነው። አማራ ግን በስፋት ተጎድቷል። በአጠቃላይ ይሄ የአሸባሪው ህውሃት ከውስጥና ከውጪ ጠላቶቻችን ጋር በማበር አገር የማፍረስ፣ ፕሮጀክት የማስፈጸም እንቅስቃሴ ውጤት መሆኑ ተወስዶ፣ ዋናውን የፕሮጀክቱን ባለቤት በሚገባ መምታትና ማክሰም ዋነኛ ሥራ ተደርጎ መወሰድ አለበት።
ጦርነቱ በግንባርና በነፍጥ ከመካሄዱ ባሻገር ዋነኛው ጦርነት ተብሎ የሚነገርለት የሳይበሩ አለም ጦርነት ነው። በሳይበሩ ጦርነትም በዲፕሎማሲያዊ እንቅስቃሴም የእኛ ወገን ደከም ያለ መሆኑ በተደጋጋሚ የሚገለጽ ነው። ቅድም እንዳልነው አጎራባች በመሆኑ ዋነኛ ተጠቂ የሆነው የአማራ ክልልና ህዝቡ  በሳይበሩ በኩል ምላሽ የሚሰጡ የተማሩ ወጣቶች አሉት ወይ?
የሳይበር ጦርነት አሁን ጊዜው የፈጠረውና ሊሰራበት የሚገባ ዘርፍ ነው። አሁን ያለንበት  የዲጂታል ዘመን በዚህ ላይ እንድንሰራ ግድ ይለናል። እንደ ሀገርም እንደ ክልልም በዚህ ዘርፍ ላይ ስራችን ክፍተት ያለበት ነው። ነገር ግን ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በጣም ብዙ በጎፈቃደኞች መሰማራት ጀምረዋል።
አሸባሪው ህውሃት የተጠቀመበት የሳይበር ሰራዊቱን ቀደም ሲል አገር ሲመራ በነበረበት ጊዜ ጀምሮ አስቦበት አዘጋጅቶ አገር ለማፍረስም እየተጠቀመበት ነው። በአገር ውስጥ በግልም በመንግስትም ሚዲያዎች ውስጥ ጭምር የሱን ጋሻ ጃግሬዎች በመሰግሰግ በውጪ አገር ያሉትንም በማሳለፍ፣ እንደ አንድ መሳሪያ እየተዋጋበት ይገኛል። በተለይ የተሳሳተ መረጃ በማሰራጨትና በማደናገር እየሰሩበት ይገኛሉ። ይህ ስለተነቃበትና ህዝቡም እየገባው በመሆኑ ለሳይበሩ ጦርነት በእኛም በኩል የሳይበር ጦረኛ ማዘጋጀት ስለሚያስፈልግ ሀቅ ላይ የተመሰረተ እውነትነት ያለውን የሳይበር መረጃ የሚያሰራጭና የህውሃትን ውሸት የሚያጋልጥ የሳይበር ሰራዊት  እየተደራጀ ነው ያለው፡፡ በአገር አቀፍ ደረጃ የተጀመረ ስራ አለ፡፡ እኛ እንደ ክልል ያንን ሞዴል ተጠቅመን በጎ ፈቃደኞችን ማደራጀትና በዋናነት በመንግስት ኮሙኒኬሽን ስር ተቋማዊ መዋቅር አስይዘን የሚቀጥል ይሆናል፤ ጥሩ ጅምር ላይ ይገኛል። በነገራችን ላይ ጦርነቱን ሁሉም መቀላቀል፣ ካድሬውም ጭምር የሳይበር ተዋጊ መሆን አለበት። ካድሬ ዝም ብሎ እስከዛሬ በተለመደው መንገድ ብቻ መጓዝ የለበትም የመንግስት ሃላፊ በቲውተር ሳይቀር ትክክለኛ መረጃ ለህዝብ መስጠት አለበት። ካድሬው በሳይበሩ አለም ያሉ የተለያዩ የመገናኛ አውታሮችን ሁሉ መጠቀም መቻል አለበት። በዚህ ደረጃ ለውጥ አለ። አሁን የትዊተር ዘመቻውን ብትመለከቺ፣ በፌደራል ደረጃም የተቀናጀ ሆኖ ቀጥሏል። በጣም ጥሩ ነው። የሳይበር ጦርነቱ በክልልም በፌደራልም ቀጥሏል። በጣም ጥሩ ነው። እዚህ የሚወድመው መሰረተ ልማት የሀገር ሀብት ነው። እዚህ የሚረሸነው ንፁህ ዜጋ የሌላው ህዝብ ወንድም ነው። ስለዚህ ሁሉም በጋራ ጠላትን የመዋጋት ሃላፊነት ነው ያለበት። ጦርነቱ ያመጣው አንዱና ትልቁ ነገር ኢትዮጵያዊ አንድነትን ያጠናከረ መሆኑ ነውና፣ ሁሉም በጋራ መስራት ለውጤት መብቃት ያለበት ጊዜ ላይ ነን እንጂ ችግሩ የአማራ ክልል ብቻ ሆኖ መታየት የለበትም።
በክልሉ የአማራ ምሁራን መማክርት የሚባል መቋቋሙም ይታወቃል። እነዚህ ምሁራን በዚህ ወቅት ለተፈጠረው ችግር መፍትሄ የሚሆን ሃሳብ ከማፍለቅ አኳያ ሚናቸውን በአግባቡ እየተወጡ ነው ይላሉ?
አሁን ባለው ነባራዊ ሁኔታና አሁን በገጠመን የአማራ ክልል አጠቃላይ ጫና አኳያ፣ የአማራ ምሁራን መማክርት አባላት በደንብ የተደራጁ ናቸው። እውነት ለመናገር ብዙ እያገዙንም ነው ያሉት። እነዚህ አባላት በአብዛኛው ሳይንሳዊ በሆነው፣ የእውቀትና ምርምር ጉዳይ ላይ በማማከር በደንብ እየተሳተፉ ይገኛሉ። ሰነዶችን በማዘጋጀት፣ ሁኔታዎችን በመተንተን፣ የነገን የአማራ እጣ ፈንታ፣ የነገን የሀገር እጣ ፈንታ፣ ዓለም አቀፍ፣ አገር አቀፍና ክልላዊ ሁኔታውን ነባራዊና ህሊናዊ እውነታውን በመተንተን ለዚህ የሚያስፈልገውን ነገር እያደረጉ፣ ወደ ኦፕሬሽን እንድንገባ በማድረጉ ረገድ በእጅጉ እያገዙን ይገኛሉ። ይህም ብቻ አይደለም።
አጠቃላይ አሁን የምንገኝበትን ሁኔታ የሚመራና በኮማንድ ፖስት በክልሉ ፕሬዚዳንት የሚመራ ቡድን አለ፣ በአይነትም በገንዘብም ሎጂስቲክ የሚያሳስብ አለ፣ ሌሎች ሚዲያና ኮሙኒኬሽን እንዲሁም አጠቃላይ የህዝብ ንቅናቄውን የሚመራ አለ በዚህና በርካታ ጉዳዮች የምሁራኑ መማክርት ሁለንተናዊ ድጋፍ ያደርጉናል። በየዘርፍ በየዘርፋቸው ምሁራዊ አስተያየት ያመጣሉ። ትንታኔ ለሚስፈልገው ነገር ትንተና ይሰራሉ። እኛ  የምናደርገው ትግል ለአጭር ጊዜና  ህወሃትን ለማስወገድ ብቻ አይደለም። መጪው የተጋረጠ አደጋ ምንድነው? የሚለውና የውጪው አሰላለፍ በዚህ  ደረጃ ይህን መልክ የያዘው ለምንድነው? የሚለው  በነዚህ ምሁራን ተተንትኖ ተቀምጧል። ቀጣይ አደጋ የሚሆኑ እነማን ናቸው? በምን መልኩ ነው ወረራስ እተፈጸመ ያለው? ለምን? የሚለውም ጉዳይ በምሁራን እየተተነተነ ለዚህ ሁሉ አጠቃላይ ዝግጅት እየተደረገ ነው ያለው ለአሸባሪው ህወሃት ብቻ አይደለም።
አሁን ጦርነቱን ተከትሎ ስለተፈናቀሉ ወገኖች እናንሳ። በኮምቦልቻ ፣ በደሴ፣ አሁን አባይ ማዶ ዘንዘልማ በጎንደር እብናት አካባቢ በደባርቅና በመሳሰሉ ቦታዎች በርካታ ተፈናቃዮች ይገኛሉ። ከነዚህ ተፈናቃዮች ኮምቦልቻ፣ ደሴና ህርዳር የሚገኙትን የማየት አጋጣሚውን አግኝቻለሁ። በተለይ በደሴ ያሉት በጣም አስቸጋሪ ሁኔታ ላይ እንዳሉ ለመታዘብ ችያለሁ። ከመንግስት፣ ከበጎ ፈቃደኞች ፣ ከዲያስፖራው ከአማራ የአስቸኳይ ጊዜ እርዳታ አስተባባሪዎች ከግለሰቦችና ከተለያዩ የልማትና የንግድ ድርጅቶች እርዳታ በአይነትም በገንዘብም ይገባል። እርዳታው በትክክል አልደረሰንም የሚሉ ዱቄት መጥቶ ማብሰያና ማገዶ አጣን የሚሉ ቅሬታዎች ይሰማሉ፡፡ ችግሮች በርካቶች ናቸው። በዚህ ላይ እርስዎ ምን ይላሉ? እርዳታ አሰጣጡን በምን መልኩ ነው እየመራችሁት ያለው?
ተፈናቃዮቹን በሚመለከት በተለያየ ጊዜና ቦታ በተፈጠሩ ግጭቶች በተለይ የቅርብ ጊዜውን የአሸባሪውን የህውሃን ወረራ ተከትሎ እስካሁን በክልላችን ከ1.7 ሚሊዮን ህዝብ በላይ ህዝብ ተፈናቃይና ተረጂ ሆኗል። ይህን ስልሽ በየዘመድ ቤት፣ በበጎ ፈቃደኞች ቤት እየተጠጉ ያሉትን ጨምሮ። በክልሉ ከ30 ያላነሱ መጠለያዎች አሉ። በነዚህ መጠለያዎች የሚኖሩት ከ1.7 ሚሊዮን ጥቂት ፐርሰንቱ ብቻ ናቸው። ከነዚህ ውስጥ ወደ 800 ሺህ የሚጠጋው በቅርብ ጊዜ አሸባሪው ህውሃት ወረራ ከፈጸመባቸው አካባቢዎች የተፈናቀለ ህዝብ ነው ማለት ነው። እነዚህ በተጨባጭ በእኛ ማኔጅመንት ስር ያሉ ናቸው ማለት ነው። ነገር ግን ወረራ በተፈጸመባቸው አካባቢዎች ያለው ህዝብም ድጋፍ ይፈልጋል። አሁን እንደውም አሳሳቢ ችግር ውስጥ ያለው ሰሜን ወሎ  ያለው ህብረተሰብ ነው። ዋግ ላይ ያለውም ህዝብ አሳሳቢ ደረጃ ላይ ነው።
በተለይ ቶሎ የማይድኑና ከሰዎቹ ጋር የሚዘልቁ ህመሞች (ክሮኒክ)ያለባቸው ሰዎች ስኳር፣ ደም ግፊት ኤች አይቪና የመሳሰሉ ህመሞች ያሉባቸው በመድሃኒት እጥረት እየሞቱ ነው። ምክንያቱም አሸባሪው ህወሃት ጤና ጣቢያዎችን ዘርፏል፤ የቀረውን አቃጥሏል። በሌላ በኩል፤ በረሃብ እያለቁ ነው ያሉት። እርዳታ ማቅረብም አልተቻለም።
የውጪ የእርዳታ ድርጅቶች ለትግራይ ህዝብ እያቀረቡ ያሉትን እርዳታ፣ ለእኛ ወገን እያደረሱ አይደሉም፡፡ በቁጥር ደረጃ ወደ 4 ሚ. ህዝብ ነው እርዳታ የሚጠብቀው። በሁለቱ ዞኖች ብቻ ማለቴ ነው፡ በቁጥር በእኛ ወገን ያለው ነው የሚበልጠው። በአጠቃላይ ይህን ያህል ህዝብ ችግር ላይ ወድቋል። በተለይ ደግሞ እኛ ልንደርስላቸው ያልቻልባቸው የተወረሩ አካባቢዎች ላይ ያለው ህዝብ በጣም አሳሳቢ ደረጃ  ላይ ነው ያለው።
በሁለተኛ ደረጃ ተፈናቅሎ በተለያዩ ጊዜዊ መጠለያ ጣቢያዎች ላይ ያለውና በአብዛኛው በዘመድና በበጎ ፈቃደኞች ቤት ተጠልሎ የሚገኘው (በነገራችን ላይ ተፈናቃይ የሌለበት ዞን የለም ክልላችን ውስጥ) የደሴው ከፋ ስለሚል ነው ብዙ ጊዜ ደሴ የሚነሳው እንጂ በሁሉም ዞኖችን ውስጥ  ተፈናቃይ አለ። እነዚህን በተመለከተ እርዳታ ከሚያቀርቡ አንዳንድ አለምአቀፍ ድርጅቶችም ጋር በተመሳሳይ የፌደራል መንግስት የአደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽንና ከክልላችን የአደጋ ስጋ አመራር ኮሚሽን ጋር በመተባበር ድጋፍ እያቀረብን ነው። ድጋፉን በተመለከተም ቢሆን የድጋፍ አሰጣጡ እንዲሁ በዘልማድ የሚመራም አይደለም። ይህንን የሚመራ የአስቸኳይ ጊዜ ምላሽ ማስተባበሪያ ማዕከልና ኮሚቴ ተቋቁሞ በጽ/ቤት ደረጃ ስራ እየተሰራ ነው። (Emergency Coordionation Center) በዚህ ደረጃ ከሁሉም ከሚመለከታቸው ዘርፎች የተቀናጀ ኮሚቴ ይህን ይሰራሉ፤ ያቀናጃሉ ያስተባብራሉ፡፡ በነገራችን ላይ ይህን በሙሉ ሰዓት ስራነት ነው የሚሰሩት፡፡ ይህ ለጉዳዩ ምን ያህል ትኩረት እንደሰጠነው የሚያሳይ ነው፡፡ የዳሰሳ ጥናት ይሰራሉ፣የት አካባቢ ምን አይነት ድጋፍ ያስፈልጋል የሚለውን ይለያሉ ማለት ነው፡፡ ምን ያህል ዘይት ፣ምን ያህል አልባሳት፣ ምን ያህል አልሚ ምግብ፣ ለየትኛው መጠለያ እንደሚያስፈልግ ያጠናሉ በዚያ መሰረት ያደርሳሉ፡፡
ፅ/ቤቱ በማን ስር ነው የሚመራው?
ፅ/ቤቱ በአደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽን ስር ሆኖ ነገር ግን ብዙ አመራሮች በባለበኔትነት የሚመሩት ነው፡፡ ይሄ በየጊዜው ከፕሬዚዳንቱም ከምክትል ፕሬዚዳንተሩም፣ እኛን ጨምሮ በጥብቅ የምንከታተለው ጉዳይ ነው፡፡ በዚህ መንገድ ነው የድጋፍ አሰጣጡ የሚሰራው፡፡ የደሴ አካባቢው እንደዚህ አይነት ፅ/ቤትና ቡድን ተቋቁሞ እየሰራ ነው፡፡ ከቡድኑ ጋር የፌደራል አካላትም አብረው እየሰሩና እየተከታተሉ ነው። በተቻለ መጠን በወረራ ካሉት ውጪ ያሉትን እስካሁን የእርዳታ አቅርቦት ችግር አለ የሚል ግምገማ የለንም፡፡ ነገር ግን በዚህ ሂደት በየጊዜው ተፈናቃይ እየጨመረ ስለሚመጣ፣ በአንዳንድ በኩል ያልፈፈናቀለውም አጋጣሚውን ለመጠቀም ስለሚቀላቀል ማኔጅመንት አካባቢ ያልጠሩ ነገሮች ሊኖሩ እንደሚችሉ ጥርጣሬ አለ፡፡ እሱን ለማስተካከል እየሰራን ነው፡፡ ለምሳሌ ዱቄት ተሰጥቶ ማብሰያ ቀርቶ ከሆነ ይሄን ለማስተካከል እየተሰራ ነው። በቅርቡ ይስተካከላል። በየጊዜውም ከፍተኛ አመራሩ በየመጠለያ ጣቢያዎቹ እየሄደ እየጎበኘ፣ ጉድለት አለ የሚባልበትን ቦታ እያስተካከለ ነው ያለው። ለጽ/ቤቱ ብቻ ስራውን ሰጥቶ አመራሩ ቁጭ  አላለም ለማለት ነው።



Read 1960 times