Wednesday, 05 January 2022 00:00

ሰው የመሆን መፍጨርጨር

Written by  ያዕቆብ ብርሃኑ
Rate this item
(0 votes)

አሁን በቀደም ዕለት የአይሁዳዊቷን ልጃገረድ አና ፍራንክ ‹‹anna frank the diary of a young girl›› ከአስር ዓመታት በኋላ በድጋሜ እያነበብኩ ነበር፡፡ መጽሐፉን እጄ ላይ የተመለከተ አንድ የንባብ ወዳጄ ‹‹የናዚዎችን ጭካኔ በብዙ መጻሕፍት ላይ አንብበነዋል፡፡ ምን ይሁነኝ ብለህ ነው ከዚህ መጽሐፍ ጋር የምትታገለው›› አለኝ። ምስኪን ይህች ሚጢጢ ትንግርተኛ ልጃገረድ በጠያቂ ነፍሷ፣ ነፍሴን ስንት ጊዜ እንዳራቆተቻትና እንደቧጨረቻት ቢያይልኝ ምናለ፡፡ ከ10 ዓመታት በፊት ይህንን መጽሐፍ አንብቤ ስጨርስ እንባ እንደተናነቀኝ አስታውሳለሁ። በዚህኛው ንባቤ ከማልቀስ ይልቅ ‹‹ሰው የመሆን መፍጨርጨር ግን ምንድን ነው?›› የሚል ግማሽ ድንቁርና የታከከበት ጥያቄዬን ታቅፌ ተመለስኩ፡፡ ፍቅር ምንድን ነው? ሕይወት ምንድን ነው? ብሎ ጥያቄ ከግማሽ ድንቁርና ውጭ ምን ሊሆን ይችላል?
አዎ ሰው የመሆን መፍጨርጨር ብሎ መጀመር ትንሽ ግር የሚል ነገር አለው፡፡ ግን እኮ ከላይ ከላይ ስታዩት የቀለለ የሚመስለው ሰው የመሆን ነገር በጥያቄ መልክ ሲቀርብ ለመመለስ ከሚያዳግቱ ጥያቄዎች ቁንጮው ይሆናል፡፡ ኸረ እንዲያውም የእግዚአብሔርን ሕልውና ከማጠየቁ ሂደት ጋር ሳይስተካከል ይቀራል?
ሰው የመሆን መውተርተር የመነሻ ውሉ እኔነት ይመስለኛል፡፡ በበኩሌ ከጊዜ ወንዝ ላይ በጨለፍኳቸው የእኔነት ዓመታት ባሰመርኩት መስመር ላይ እልፍ የደበዘዙ ምስሎች ይታዩኛል፡፡ አንዳንድ ጊዜ የኢየሱስ ደቀመዝሙር ሆኜ በሰፋፊ የእግር ዳናዎቹ ላይ ትንንሽ ፈለጎቼን እያለካካሁ በተሰጠኝ መክሊት ሚጥጥዬ ክዋክብትና ጨረቃዎችን ስፈጥር አያለሁ፡፡ ሌላ ጊዜ ከውሻ ወዳጁ ዛራስቱራ የሚቀዳ ድቅል ማንነት እንዳለኝ አስብና ይምታታብኛል፡፡ ደግሞ ሌላ ጊዜ የባይተዋር ገድሌ የሚነበብ የሲሲፐስ አቻ ፍጥረትነት ይሰማኝና እኔነቴ ይሳከርብኛል፡፡
ይህንን ሁሉ ከንቱ ቅዠት ብለን ልናልፈው ብንችል አንኳን ሰው የመሆን መፍጨርጨር ምንድን ነው የሚለውን ጥያቄ መሸሽ እንዴት ይቻለናል? በእርግጥስ አያቶች ‹‹ሰው ለመሆን ጣር›› ሲሉ ምን ማለታቸው ነው? ደጃች፣ ፊታውራሪ፣ ራስ፣ እንቶፍንቶ ሁን ለማለት ፈልገው? እንዲያ ከሆነ እንደ ጎልድመንድ አሊያም እንደ ዛራስቱራ የትም ውሎ የትም የሚያድር መድረሻ ቢስ በመሆን ሰውነትን መላበስ አይቻልም ልንል እኮ ነው? ቆይ ቆይ የኢየሱስ ምድራዊ ማንነትስ በጥልቀት ሲጠና ከዚህ ወለፈንዲ ኑረት ምን ያህል ኢንች ይርቃል? በበኩሌ ምንም እላለሁ፡፡
እኛ በውስጣችን የሚመላለሱ የጥያቄዎች ንጥር ውጤቶች ሳንሆን እንቀራለን? እኔ እኮ ያለ ጥያቄዎቼ ከዘመናት በፊት ንቦቹ እንደ ለቀቁት ቀፎ ምንም ነኝ፡፡ የአንድ ሰው ማንነትስ በዕልፍ የሚለካውስ በእነዚህ የጥያቄዎች ውል የለሽ ፍጭርጭሮሽና እሱን ተከትሎ በሚመጣው ሽሽት አይደለም ትላላችሁ? ‹‹የራስን ልብ በራስ አዕምሮ መፋለም ምን ያክል ከባድ ነው፡፡›› ትላለች አና ፍራንክ፡፡
ይሄ ሁሉ እንዳለ ሆኖ ሰው የመሆን መፍጨርጨር ምን ማለት ነው? ፀጥ ያለ፣ በኑሮው የረካ፣ የተረጋጋ፣ ግርማ የተላበሰ… ዓይነት ሰው መሆን ማለት ይሆን? ግን እኮ በየአደባባዩ፣ በየመዝናኛ ማዕከሉ፣ የሰከነና የተከበረ የሚመስለው ሰው ሁሉ በሩን ዘግቶ ግን የራሱ ዓለም ያለው፣ የማናውቀው ሌላ ሰው እኮ ነው፡፡ በየብቻ ዓለሙ የሚንሰቀሰቅበት፣ የሚፈነድቅበት የራሱ ዓለም ያለው፤ በጥቂት መዳፈር በብዙ ውስልትናና ውንምብድና ያደፈች ነፍስ ያለው፤ እንደገና ይህችን በሃጥያት የደቀቀች የመሰለችውን ነፍሱን ነፃ ለማውጣት ለሱባዔ የሚተጋ፣ ለምህላ የሚሰለፍ ተፍገምጋሚ ነፍስ ያለው፤ ከሞላ ጎደል የሁሉም ሰው ዓለም በግርድፉ ሲነበብ እንዲህ ነው፡፡
እናስ ሰው የመሆን መፍጨርጨር በመጠኑ ወደ ሰከነ በሀብትና በዕውቀት ወደ መጠቀ የሕይወት ፅንፍ መጓዝ ነው ብለን መደምደም እንችል ይሆን? ግን ግን ለምንም ባለመጓጓትና ለምንም ባለመታዘዝ ቤተ ክርስቲያን የገባች ውሻ የሚገጥማት ዓይነት ሕይወት ውስጥ ሰው የመሆን መፍጨርጨርን ማግኘት አይቻልም ለማለት ምን አመክንዮ አለን? ምንም፡፡ ጀግኖች ሆነን ሳለን የፈራንባቸው አጋጣሚዎች ሺህ ምንተሺህ ይሆኑብናል፡፡ ትጉሃን ሆነን ሳለን እልፍ ጊዜ ሰነፎች ነበርን። ለማንም ደንታ የለኝም ብለን እንዳልደፋን የሆኑ ሰዎች ከሕይወታችን በመውጣታቸው ለዓመታትና ከዚያም ለበለጠ ጊዜ ተብከንክነናል፡፡ ሌላም ሌላም… ይህም ሁሉ ሆኖ ሰው የመሆን መፍጨርጨር እንዲህ ነው ብለን ያንን ለመኮነን ይሄንን ለማድነቅ አንዴት ይቻለናል?
ደግነቱ ለተነሳንለት የሚገዳደር ጥያቄ አንድ ዓይነት መልስ የማግኘት ግዴታ ውስጥ አይደለንም፡፡ ቀድሞ ነገር ‹ምንድን› ብሎ ጥያቄ ግማሽ ድንቁርና የታከለበት የፈላስፎች ጥያቄ መሆኑን ተናዘናል፡፡ ቢሆንም የመጠየቅ መብታችንን ተጠቅመን ሰው የመሆን መፈጨርጨር ምንድን ነው? እንላለን፡፡ እርስ በርሱ በሚጣረስ ዕጣ ፋንታ በተምታታ ህልውና ውስጥ መሆናችንን እያወቅን እንኳን መጠየቃችን አይቀርም። በአገኘነው አጋጣሚ ሁሉ ሰው የመሆን መፍጨርጨር ምንድን ነው? እንጮሃለን። እንደእኔ እንደእኔ ትውልዶች ሁሉ በዕልፍ ዓመታት ሂደት እየተቀባበሉ ይህንን ጥያቄ ቢያስተጋቡት እንኳን መልሱ ያው መልሱ አልተሰጠም ይመስለኛል፡፡

Read 2982 times