Print this page
Saturday, 12 February 2022 11:41

80ኛ ዓመቱን የሚያከብረው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ፤ ባለ 48 ወለል የዋና መስሪያ ቤት አዲሱን ህንጻ ነገ ያስመርቃል

Written by 
Rate this item
(0 votes)

  የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ8 ቢሊዮን ብር ገደማ አዲስ ያስገነባውን ባለ 48 ወለል ህንጻ ዋና መስሪያ ቤት በነገው ዕለት  ያስመርቃል፡፡ ንግድ ባንኩ 80ኛ ዓመት የምስረታ በዓሉንና የአዲሱን ህንጻ  ምርቃት በአንድ ላይ እንደሚያከብር ታውቋል፡፡
የአዲሱ ህንጻ ግንባታ ሰባት ዓመት የፈጀ ሲሆን ስምንት ቢሊዮን ብር ገደማ እንደወጣበት ታውቋል፡፡  አዲሱ ህንጻ በተለያዩ ቦታዎች ተበታታትነው ሲሰሩ የነበሩ ከ5 ሺህ በላይ የባንኩ ዋና መስሪያ ቤት ሰራተኞችን በአንድ ላይ የሚያሰባስባቸ ሲሆን የባንኩ ፕሬዚዳንት፣ ምክትል ፕሬዚዳንቶች፣ ሥራ አስኪያጆችና ሌሎችም ሰራተኞች ከሁለተኛ እስከ 46ኛ ያሉትን ወለሎች ይይዛሉ ተብሏል፡፡
የህንጻው 47ኛ ወለል ለሬስቶራንት አገልግሎት የሚውል ሲሆን፤ 48ኛው ደግሞ ከአራቱም አቅጣጫ ከተማዋን ለማሳየት በሚያስችል መልኩ እንደገና ዲዛይን ተደርጎ መገንባቱ ተጠቁሟል፡፡ ህንጻው፤ ለ1,500 መኪኖች ማቆሚያነት የሚያገለግሉ ከምድር በታች የተገነቡ አራት ወለሎችም አሉት።
የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አዲሱ ዋና መስሪያ ቤት፤ ከዋናው ህንጻ በተጨማሪ ስድስትና ስምንት ፎቆች ያሏቸው ሁለት ተደራቢ ሕንፃዎችን ይዟል። በአንደኛው ተደራቢ ህንጻ ሁለት ሺህ ሰዎች ማስተናገድ የሚችል ሰፊ የስብሰባ አዳራሽ አለው፡፡ ሁለተኛው ተደራቢ ህንጻ ክፍል ደግሞ፤ ለተለያዩ የንግድ ስራዎች፤  ሬስቶራንቶች፣ የንግድ ሱቆች፣ ለስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራ፣ ለህፃናት ማቆያ የሚሆኑ ቦታዎችን ይዟል፡፡ በዚህ ህንጻ ላይ ስድስት ሲኒማ ቤቶችም እንደሚኖሩ ለማወቅ ተችሏል፡፡
በ1942 ዓ.ም በ43 ሰራተኞችና በሁለት ቅርንጫፍ ሥራውን የጀመረው ባንኩ፤ በአሁኑ ወቅት ከ54 ቢሊዮን ብር በላይ ካፒታል እንዳለው ታውቋል፡፡

Read 1113 times
Administrator

Latest from Administrator