መንግስት በሰሜን ሸዋ ከተሞች በተደጋጋሚ የሚፈጸመውን የታጣቂዎችና አሸባሪዎች ጥቃት በዘላቂነት የሚያሰቆም እርምጃ እንዲወስድና የዜጎችን ደህንነት የመጠበቅና የማስጠበቅ ሃላፊነቱን እንዲወጣ ኢዜማና እናት ፓርቲ አበክረው ጠይቀዋል።
“ለአሸባሪ በልኩ መልስ መስጠት ሀገርን ለመታደግ የመጀመሪያም የመጨረሻም መፍትሄ ነው” ያለው እናት ፓርቲ፤ “ሃገርን ለማፍረስ እየተንቀሳቀሰ ያለው “ሸኔ” ከሰሞኑ በሰሜን ሸዋ ከተሞች ላይ የፈጸመው ጥቃት፣ 10ሺህ ሰው የሚኖርባት ሞላሌ ከተማ ላይ ያደረሰው ውድመት እጅግ ዘግናኝ ነው ብሏል።
ይህን ድርጊት የፌደራልና የሁለቱ ተጎራባች ክልል ባለስልጣናት በቸልታ መመልከታቸውና ከዚህ ባለፈ የንፁሃንን ሞት ለፖለቲካ ትርፍ ለመጠቀም መሯሯጣቸው ለደረሰው ጥፋት ተጠያቂ ያደርጋቸዋል” ሲል ከስሷል ፓርቲው።
በርካታ ውድመቶችንና ጥፋቶችን እየፈጸመ የሚገኘው ሸኔ ላይ ትጥቁን እስኪፈታ ድረስ የተቀናጀ ማጥቃት እንዲወሰድበት፤ ህዝቡም ተደራጅቶ ከሽብር ቡድኑ ጥቃት ራሱን እንዲከላከል እናት ፓርቲ ጥሪ አቅርቧል።
በተመሳሳይ የኢትዮጵያ ዜጎች ለማህበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) ባወጣው መግለጫም፤ ጥቃቱ መንግስት ሃላፊነቱንና ተግባሩን ባለመወጣቱ የተፈጸመ መሆኑን አመልክቶ ይህ መሰሉ ጥቃት በድጋሚ እንዳይከሰት መንግስት ሃላፊነቱንና ግዴታውን እንዲወጣ በጥብቅ አሳስቧል።
በመንግስት መዋቅር ውስጥ ተሰግስገው የዜጎችን ደህንነት አደጋ ላይ የሚጥሉ አካላትን በአፋጣኝ በማጽዳት፣ ለህግ እንዲያቀርብም ኢዜማ አሳስቧል።
Saturday, 23 April 2022 14:07
መንግስት በዜጎች ላይ የሚፈጸሙ ጥቃቶችን በዘላቂነት እንዲያስቆም ፓርቲዎች አሳሰቡ
Written by አለማየሁ አንበሴ
Published in
ዜና