Error
  • JUser: :_load: Unable to load user with ID: 62
Saturday, 06 October 2012 12:12

የታላቁ ሩጫ ሀብት ሊወረስ ነው መባሉ ተስተባበለ Featured

Written by 
Rate this item
(3 votes)

“መንግስት የማንኛውንም በጐ አድራጐት ድርጅት ሀብት የመውረስ ስልጣን የለውም”

የበጐ አድራጐት ማህበራት ኤጀንሲ

የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ሀብትና ንብረት ሊወረስ ነው በሚል የወጣውን ዘገባ የበጐ አድራጐት ማህበራት ኤጀንሲ አስተባበለ፡፡ መንግስት እንኳንስ የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያን ይቅርና የማንኛውንም በጐ አድራጐት ድርጅት ሀብትና ንብረት የመውረስ ሥልጣን እንደሌለውና አዋጁም እንደማይፈቅድለት የኤጀንሲው የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ አቶ አሰፋ ተስፋዬ ገልፀዋል፡፡

ከትናንት በስቲያ በሒልተን ሆቴል በተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ እንደተነገረው፣ ከንጉሱ ዘመን ጀምሮ የተመዘገቡ የበጐ አድራጐት ማህበራትን ፋይል ለማጣራትና ምዝገባ ለማካሄድ የሰነድ ምርመራ በሚደረግበት ጊዜ የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ተፈጥሮአዊ ባህሪው የበጐ አድራጐት ሥራ አለመሆኑ መረጋገጡን አቶ አሰፋ ተናግረዋል፡፡

ይህ በሚሆንበት ጊዜም የድርጅቶቹን አመራሮች በስልክ ያነጋገሯቸው መሆኑን ጠቅሰው፣ በጉዳዩ ላይ ከመግባባት ደረጃ መድረሳቸውንና ለማጭበርበር ተግባር ተሰለፈ ስለሚባለው ጉዳይ እንደማያውቁ ተናግረዋል፡፡

የበጐ አድራጐት ማህበራት በተለያዩ ምክንያቶች ሥራቸውን ቢያቆሙ፣ ቢዘጉ ወይንም ቢፈርሱ ሀብታቸው ለተመሳሳይ ዓላማ፣ተቀራራቢ ለሆነ ተግባር ወይም ደግሞ ለልማት ይውላል እንጂ መንግስት ሊዘርፈው አይችልም ያሉት አቶ አሰፋ፤ ሊወረስ ነው የሚባለው ዘገባ የተሳሳተ ነው ብለዋል፡፡

ጉዳዩን አስመልክቶ አትሌት ኃይሌ ገብረስላሴ በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ እንደተናገረው፤ ታላቁ ሩጫ አትራፊ ድርጅት ሆኗል መባሉን ተቃውሞ “እኛ አገር በስፖርት ማትረፍ ሃጢያት ነው፡፡ እንዴት በስፖርት ታተርፋላችሁ ይሉናል፡፡

በሌሎች አገራት ስፖርት ትልቅ የገቢ ምንጭ ነው፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ በደንብ መነጋገርና መወያየት ይኖርብናል” ብሏል፡፡

ታላቁ ሩጫን እናቁም ብንለው እንኳን ልናቆመው አንችልም፡፡ ላረጋግጥላችሁ የምፈልገው ጉዳይ ቢኖር ለሚቀጥሉት 100 ዓመታት ታላቁ ሩጫ እንደሚካሄድ ነው ሲል ተናግሯል - አትሌት ኃይሌ፡፡

Read 5113 times Last modified on Saturday, 06 October 2012 14:47