Saturday, 06 October 2012 12:48

አንድነት ፓርቲ የፕሬስ አፈና እንዲቆም ጠየቀ

Written by  ሠላም ገረመው
Rate this item
(7 votes)

የፓርቲው ልሳን ጋዜጣ ወደ መጽሔት ሊቀየር ነው

መንግስት በፕሬስ ላይ የሚያደርሰው አፈና እንዲቆም ያሳሰበው አንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ፤ ከህትመት የታገዱት የፓርቲው ልሳን “ፍኖተ ነፃነት” እና “ፍትህ“ ጋዜጣ ለህትመት እንዲበቁ ጠየቀ፡፡ የፓርቲው አመራሮች ሰሞኑን በሰጡት መግለጫ፤ “ፍኖተ ነፃነት” ወደ ህትመት እንድትመለስና የፕሬስ አፈናው እንዲቆም ለጠ/ሚኒስትር ኃ/ማርያም ደሳለኝ፣ ለመንግስት ኮሙኒኬሽን ሚኒስትር ለአቶ በረከት ስምኦን እንዲሁም ለብሮድካስት እና ለብርሃንና ሰላም ማኔጂንግ ቦርድ ደብዳቤ ቢጽፉም ምላሽ አላገኘንም ብለዋል፡፡ ልሳን ጋዜጣው ፓርቲው አባላቶቹንና ደጋፊዎቹን የሚያነቃበትና ከህዝቡ ጋር የሚገናኝበት ድልድይ እንደሆነ ጠቁሞ፤ መንግስት ይሄን ድልድይ ነው የናደው ብሏል፡፡

መንግስት ጋዜጣውን የዘጋው ሆን ብሎ ፓርቲውን ለማፍረስና በመጪው የአዲስ አበባ ማሟያ ምርጫ እንዳይሳተፍ ለማድረግ ነው ሲልም አክሏል፡፡ የጋዜጣውን መታገድና የፕሬስ አፈናን በመቃወም በቅርቡ ሠላማዊ ሰልፍ እንደሚያደርጉ የገለፁት የፓርቲው አመራሮች፤ ህጋዊ ሠውነት ስላለን የሠላማዊ ሠልፍ ጥያቄያችን ተቀባይነት ያገኛል ብለን ተስፋ እናደርጋለን፤ ፈቃዱን ካላገኘን ግን የራሳችንን የትግል መንገድ እንከተላለን ብለዋል፡፡ አንድነት ፓርቲ የታገደውን ጋዜጣ ለመተካት ሁለት አፋጣኝ እርምጃዎችን ለመውሰድ መወሰኑን ገልፀው፤ አንዱ ጋዜጣዋን ወደ መጽሔት በመቀየርና ከግል ማተሚያ ቤቶች ጋር በመነጋገር በቀጣዩ ሳምንት ለገበያ ማቅረብ ሲሆን ሁለተኛው ፓርቲው የራሱን  የማተሚያ ማሽን በመግዛት ጋዜጦችን እራሱ ለማተም ውሳኔ ላይ መድረሱንም አመልክቷል፡፡

 

Read 2553 times Last modified on Saturday, 06 October 2012 12:59