Saturday, 14 May 2022 00:00

በውጭ ምንዛሬ እጥረት ሳቢያ በርካታ ፋብሪካዎች እየተዘጉ ነው

Written by 
Rate this item
(3 votes)

 ከ400 በላይ ኢንዱስትሪዎች ምርት አቁመዋል ተብሏል

              በአገሪቱ የተለያዩ ክፍሎች የሚገኙ ከ446 በላይ ኢንዱስትሪዎች በገጠሟቸው የተለያዩ ችግሮች ሳቢያ ምርት አቁመው መዘጋታቸውን የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል፡፡
ለኢንዱስትሪዎቹ መዘጋት በዋናነት የተጠቀሱት ምክንያቶች፡- የጥሬ እቃና የፋይናንስ እጥረት፣ እንዲሁም የመሰረተ ልማት ችግርና የተቀናጀ የመንግስት ድጋፍ እጦት ናቸው ተብሏል፡፡
በተመሳሳይ በውጭ ምንዛሬ እጥረት ሳቢያ የምርት ግብአት ከውጭ አስመጥተው ማምረት ያልቻሉ 26 የኤሌክትሮኒክስና የማሽነሪ ፋብሪካዎች ባለፉት ዘጠኝ ወራት ውስጥ መዘጋታቸው ታውቋል፡፡
 ከማኑፋክቸሪንግ ፋብሪካዎች ውስጥ ወደ ውጭ የሚላከውን ምርት ከፍተኛ ድርሻ የሚይዙት የኤሌክትሮኒክስ ኩባንያዎች በውጭ ምንዛሬ እጥረት ሳቢያ ከፍተኛ ተግዳሮት ገጥሟቸዋል ተብሏል፡፡ የማኑፋክቸሪንግ ቴክኖሎጂና ኢንጅነሪንግ ኢንዱስትሪ ምርመራና ልማት ማዕከል እንደገለጸው፤ ባለፉት 9 ወራት ውስጥ የፓወር ኬብል፣ ትራንስፎርመር፣ የቴሌኮሙኒኬሽን ኬብል፣ ቴሌቪዥን፣ ሬዲዮ፣ ፍሪጅና ሞባይል የመሳሰሉትን ምርቶች የሚያመርቱ 26 የማኑፋክቸሪንግ ፋብሪካዎች በውጭ ምንዛሬ እጥረት ሳቢያ ተዘግተዋል።
ከውጭ ምንዛሬ እጥረት በተጨማሪ የሃይል መቆራረጥ፣ የፋይናስ አቅም እጥረትና የመሥሪያ ቦታ ችግር  ለፋብሪካዎቹ ተግዳሮት እንደሆነባቸው የጠቆመው ማዕከሉ፤ በዚህም ሳቢያ በማምረት ላይ የሚገኙም ፋብሪካዎች ቢሆኑ ባለፉት 9 ወራት ሲያመርቱ የነበረው ከ20 በመቶ በታች  አቅማቸውን በመጠቀም እንደሆነ አመልክቷል፡፡
የውጭ ምንዛሬ እጥረትና ተያያዥ ተግዳሮቶች የውሃና መጠጥ ማምረቻ ኢንዱስትሪውም ላይ ተፅዕኖ ማሳደራቸው አልቀረም፡፡ በቅርቡ 20  የሚደርሱ የታሸገ ውሃ አምራች ኩባንያዎች ተግዳሮቱን መቋቋም አቅቷቸው መዘጋታቸው አይዘነጋም።

Read 9419 times