Saturday, 29 October 2022 11:56

በእርግዝና ወቅት የሚያጋጥም የደም ግፊት

Written by  ሀይማኖት ግርማይ ከኢሶግ
Rate this item
(0 votes)

በእርግዝና ወቅት የሚያጋጥም የደም ግፊት ወይም ፕሪኢክላምሲያ እና ኢክላምሲያ [Pre-Eclampsia and Eclampsia] ከ5 ወር በላይ በሆኑ ነፍሰጡሮች እንዲሁም አንዳንድ ጊዜ ልጅ ከተወለደ በኋላ በእናት ላይ የሚከሰት በሽታ ነው። በሽታው በአለምአቀፍ ደረጃ ከ20 ሳምንት (5ወር) በላይ በሆኑ ነፍሰጡሮች ላይ ከ3- 7 % የሚያጋጥም ሲሆን 25% ደግሞ ልጅ ከተወለደ ከ4ቀን - 6 ሳምንት ባለው ጊዜ ውስጥ በእናቶች ላይ ይከሰታል።
በቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል የፅንስ እና የማህፀን ህክምና ስፔሻሊስት የሆኑት ዶ/ር ድልአየሁ በቀለ “እናቶች ላይ የሚከሰት የደም ግፊት እና ተያያዥ በሆኑ ሁኔታዎች የእናትየውን የተለያየ የሰውነት ክፍል የሚጎዳ እንዲሁም በእናት እና በጽንስ ላይ እስከ ህይወት ማጥፋት የሚያደርስ የህመም አይነት ነው” በማለት በእርግዝና ወቅት የሚያጋጥመውን የደም ግፊት ገልጸውታል። በሽታው ፕሪኢክላምሲያ እና ኢክላምሲያ በመባል ለሁለት ይከፈላል። ፕሪኢክላምሲያ የበሽታው የመጀመሪያ ደረጃ ሲሆን በዚህ ወቅት በህክምና ከበሽታው የማገገም ሰፊ እድል አለ። ኢክላምሲያ ደግሞ በሽታው ተባብሶ በእናት ወይም በፅንስ ላይ ጉዳት የሚደርስበት ደረጃ ነው። በተጨማሪም ፕሪኢክላምሲያ የከፋ እና ያልከፋ በሚል ደረጃ እንደሚከፈል የህክምና ባለሙያው ገልጸዋል።
የፅንስ እና የማህፀን ህክምና ስፔሻሊስት የሆኑት ዶ/ር ደምሰው አመኑ እንደተናገሩት በእርግዝና ወቅት የሚያጋጥም የደም ግፊት በሽታ መንስኤ ከመላምት ባለፈ አይታወቅም። የህክምና ባለሙያው ያስቀመጧቸው መላምቶች የእንግዴ ልጅ አፈጣጠር[አቀማመጥ]፣ አመጋገብ እና የዘረመል ሁኔታ ናቸው።
ተጋላጭ የሆኑ የህብረተሰብ ክፍሎች
የመጀመሪያ እርግዝና ላይ ያለች እናት ከ2ኛ እና ከዛ በላይ ካሉ እርግዝናዎች ጋር ሲነጻጸር በዚህ በሽታ የመጠቃት እድሏ ከፍ ያለ ነው።  
በልጅነት ወይም እድሜያቸው ከገፋ በኋላ የጸነሱ እናቶች ተጋላጭ ናቸው።
ከእርግዝና በፊት የተለያየ ህመም ያላባቸው እናቶች ይበልጥ ተጋላጭ ሲሆኑ እነዚህም የደም ግፊት፣ የኩላሊት እና የስኳር ህመሞች ናቸው።
በቀደመ እርግዝና ላይ የፕሪክላምሲያ ተጠቂ የነበረች እናት በቀጣይ እርግዝናዋ ላይም በሽታው የመከሰት እድል አለው።
የመንታ ልጆች እርግዝና፤  
የልጅ አባት ሲለወጥ ማለትም ከዚህ ቀደም ከተወለዱት ልጆች አባት ሳይሆን ከሌላ ሰው እርግዝና ሲፈጠር ልክ እንደመጀመሪያ ልጅ እርግዝና ለበሽታው ሊያጋልጥ ይችላል።
ከመጠን ያለፈ ውፍረት፤
በእርግዝና ወቅት የሚያጋጥም የደም ግፊት ህመም ምልክቶች
የእራስ ምታት ህመም፤
የአይን ብዥታ፤
የሰውነት እብጠት [እጅ፣ እግር እና ፊት]
በአጭር ጊዜ ውስጥ የክብደት መጨመር፤
በቀኝ ጡት ስር [ጉበት ያለበት አከባቢ] የህመም ስሜት መኖር
የመተንፈስ ችግር [ትንፋሽ ማጠር]
እራስን ስቶ መውደቅ እና ማንቀጥቀጥ፤
በመጀመሪያ ደረጃ ላይ በሽታው ምንም ምልክት ላያሳይ እንደሚችል ዶ/ር ድልአየሁ በቀለ ተናግረዋል። ስለሆነም በደም ግፊት መጠን እና በላብራቶሪ የሽንት ምርመራ በሽታው የከፋ ደረጃ ሳይደርስ እንዲታወቅ እናቶች የቅድመ ወሊድ ክትትል ማድረግ አለባቸው ብለዋል የህክምና ባለሙያው።
በእርግዝና ወቅት የሚያጋጥም የድም ግፊት ህክምና ሳያገኝ ወደ ኢክላምሲያ ደረጃ ካደገ የሚያደርሰው ጉዳት ከፍተኛ ነው። የደምግፊት ከፍ በሚልበት ወቅት የእንግዴ ልጅ ከቦታው የመልቀቅ እድል ስለሚኖረው ደም እንዳያስተላልፍ ያደርጋል። ይህም ጽንሱ ሆድ ውስጥ እንዳለ እንዲቀጭጭ ከዛም ጽንስ እንዲቋረጥ ሊያደርግ ወይም የመወለጃ ጊዜ ሳይደርስ ልጅ እንዲወለድ በማድረግ እንዲሁም ከተወለዱ በኋላ በጨቅላ ህጻናት ላይ የተለያዩ ጉዳቶችን ሊያስከትል ይችላል። በእናት ላይ የኩላሊት፣ የጉበት እና የአተነፋፈስ [የሳንባ] በሽታ ሊያስከትል እንዲሁም አንጎል[ጭንቅላት] ውስጥ ደም እንዲፈስ ሊያደርግ ይችላል። በሽታው ሲባባስ የእናትን ህይወት ይቀጥፋል።
በእርግዝና ወቅት የሚያጋጥም የደም ግፊት በአለም አቀፍ ደረጃ ለእናቶች ሞት ምክንያት ከሆኑ 5 በሽታዎች መካከል ይመደባል። በዚህም በወሊድ ወቅት ከሚያጋጥም የደም መፍሰስ ቀጥሎ በ2ኛ ደረጃ ተቀምጧል። በአለም ላይ በዚህ በሽታ ምክንያት በ1 አመት ውስጥ እስከ 63ሺ የሚሆኑ እናቶች ህይወታቸውን ያጣሉ።
የኢትዮጵያ ብሄራዊ ድንገተኛ የጽንስ እና ጨቅላ ህጻናት ድጋፍ ሰጪ [Ethiopian National Emergency Obstetric and Newborn Care] መረጃ እንደሚያሳየው በቀጥታም ሆነ በተዘዋውሪ 10 በመቶ ለእናቶች ሞት ምክንያት በመሆን የተቀመጠው በእርግዝና ወቅት የሚያጋጥም የደም ግፊት ነው። በሀገሪቱ ከ1መቶ ሺ ወላድ እናቶች መካከል 412 እናቶች ህይወታቸው ያልፋል። ህይወታቸውን ከሚያጡበት ምክንያቶች ውስጥ 19በመቶ የሚይዘው በእርግዝና ወቅት የሚከሰት የደም ግፊት ነው። እንዲሁም ዶ/ር ድልአየሁ በቀለ እንደተናገሩት በቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል በተደረገ ጥናት መሰረት በሆስፒታሉ ለእናቶች ሞት ምክንያት በመሆን ቀዳሚውን ስፍራ ይዟል። ለዚህም በዋነኝነት እንደምክንያት ያስቀመጡት የእናቶች የቅደመ ወሊድ ክትትል አለማድረግን ነው።
ሚድ ዋይፍ አሸናፊ ተስፋዬ በኢትዮጵያ ገጠራማ ቦታዎች እንዲሁም ከተሞች ላይ በህክምና ሙያ ለ12 አመታት ሲሰራ ቆይቷል። እናም በዚህ ወቅት ህብረተሰቡ ለበሽታው ያለው ግንዛቤ እናቶች የህክምና ክትትል እንዳያደርጉ ምክንያት መሆኑን ታዝቧል። “በኢክላምሲያ በሽታ እናቶች እራሳቸውን ስተው ሲወድቁ ወይም ሲያንቀጠቅጣቸው ህብረተሰቡ የሚገምተው የሚጥል በሽታ ስለሆነ ክብሪት ይለኩሳል” በማለት ችግሩን ያለመገንዘብ ሁኔታ መኖሩን ተናግሯል የህክምና ባለሙያው።
ሚድ ዋይፍ የሆኑት ዋሴ ጉልላት በተመሳሳይ በህብረተሰቡ ዘንድ ስለበሽታው የተዛባ አመለካከት መኖሩን ተናግረዋል። በደብረ ብርሀን አየርጤና ጤና ጣቢያ የሚሰሩት ባለሙያው በህብረተሰቡ ዘንድ በሽታውን ከባእድ አምልኮ እና ከሀጢያት ጋር የማያያዝ ሁኔታ መኖሩን አስተውለዋል። ይህ የሚስተዋለው በሽታው ኢክላምሲያ ደረጃ ላይ ደርሶ የማንቀጥቀጥ ወይም የመጣል ሁኔታ ሲኖረው ነው። ስለሆነም በዚህ ወቅት የሚሰጠው ህክምና አስፈላጊ እንዳልሆነ በማሰብ ህክምናውን እንዳይሰጥ የማድረግ [የመከልከል] ሁኔታ አለ። በተለይ ገጠራማ አከባቢ ባለው ማህበረሰብ ዘንድ ይህ እሳቤ እና ተግባር መኖሩን ነው ባለሙያው የተናገሩት። ለዚህም ታማሚዎች ለከፋ ደረጃ ይዳረጋሉ።
ማንኛውም በሽታ የከፋ ጉዳት ከማድረሱ አስቀድሞ መከላከል እንደሚገባ ወይም በሽታው እናዳይከሰት ማድረግ ያስፈልጋል። ስለሆነም ይህ በሽታ እንዳይከሰት አስቀድሞ ለመከላከል መደረግ የሚገባቸው ሁኔታዎችን እንዲያብራሩልን ለዶ/ር ድልአየሁ በቀለ ጥያቄ አቅርበንላቸዋል።
“…በእርግዝና ወቅት የሚያጋጥም የደም ግፊት እንዳይከሰት አስቀድሞ ለመከላከል በሳይንስ የተገኘ ግኝት ወይም የተረጋገጠ ነገር የለም” ብለዋል ዶ/ር ድልአየሁ በቀለ። ነገር ግን ለበሽታው አጋላጭ የሆኑ ሁኔታዎች ውስጥ ያሉ እናቶች እርግዝና ከተፈጠረበት ወቅት ጀምሮ አስፈላጊውን የቅድመ ወሊድ ክትትል ካደረጉ በሽታው ወደ ከፋ ደረጃ ሳይደርስ ማለት ኢክላምሺያ ከመሆኑ አስቀድሞ ህክምና እንዲያገኙ ይደረጋል። በተመሳሳይ ሁሉም ነፍሰጡር እናቶች ከእርግዝና የመጀመሪያ ወራቶች ጀምረው የቅድመ ወሊድ የህክምና ክትትል ማድረግ አለባቸው። በሽታው ጉዳት ከማድረሱ አስቀድሞ ለመከላከል ዋነኛው መፍትሄ አስፈላጊውን የቅድመ ወሊድ ክትትል ማድረግ በመሆኑ እናቶች ወደ ጤና ተቋማት እንዲሄዱ በማለት የህክምና ባለሙያው መልእክታቸውን አስተላልፈዋል።  

Read 12087 times