Wednesday, 16 November 2022 09:48

ፀደይ …የስነተዋልዶ ጤና ክሊኒክ

Written by  ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ
Rate this item
(0 votes)

ፀደይ በአዲስ አበባ የሚገኝ የአንድ ክሊኒክ መጠሪያ ነው፡፡ አንዲት ታካሚ ወደ ክሊኒኩ ስትገባ ነበር የተመለከትናት፡፡ ሰላምታ ተለዋወጥን፡፡ ምን ሆነሽ ነው?…የኛ ጥያቄ ነበር፡፡ እንግዲህ እሱንማ ለሐኪሙ ነው የምነግረው አለች… ትክክል ነሽ …እንዲያው ስለጤናሽ መጠየቃችን እንጂ…ስንላት እናንተም ሐኪም ከሆናችሁ ቁጭ ብለን እናውራ…እንዲሁ ከደጃፍ ሲገቡ መጠየቅ አይገባም አለችን፡፡ እኛም ተስማማን፡፡ ትክክል ነበረች፡፡
ከዚያም ስትነግረን ወደ ክሊኒኩ ለሶስተኛ ጊዜ መምጣትዋ  ነበር፡፡ ይህች ሴት ላቀረበችው የጤና ጉዳይ ስፔሻሊስት ያስፈልጋት ስለነበር ...ሁለት ጊዜ በክሊኒኩ በቀጠሮ ታይታ በሶስ ተኛው ልዩ ሐኪም ተቀጥሮላት ነበር እኛ ያገኘናት፡፡
ለመሆኑ ጸደይ ማንናት የመጀመሪያው ጥያቄአችን ነበር፡፡ ለማንኛውም ከክሊኒኩ ሁለት እንግዶችን ጋብዘናል፡፡ ያብራሩልናል። እንግዶቻችን ዶ/ር ተስፋዬ ሁሪሳ የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስት፤ በቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል የስነተዋልዶ ጤና ፕሮግራም ዳይሬክ ተር እና በጸደይ ክሊኒክ በዳይሬክተርት እና በተቆጣጣሪነት የሚሰሩ ናቸው፡፡ ሌላው እንግ ዳችን ዶ/ር እስማኤል ኢብራሂም የፀደይ ክሊኒክ ሜዲካል ዳይሬክተርና ስራ አስኪያጅ እን ዲሁም ጠቅላላ ሐኪም ናቸው፡፡  
ኢሶግ….ፀደይ ክሊኒክ ማን ናት?
ዶ/እስ    ይህ ብዙ ጊዜ የሚነሳ ጥያቄ ነው። ፀደይ ማን ነች? ፀደይ ምንድነች? የሚሉ ጥያቄዎች ይቀርቡልናል፡፡ የዚህም ምክንያት የአሰያየምዋን ምንነት ለመረዳት ነው፡፡ ፀደይ ግለሰብ አይደለችም፡፡ ፀደይ ፍካትን ለመግለጽ ከክረምት ወደ በጋ ሲገባ የሚ ገኘውን ደስታ የሚፈነጥቀውን ወቅት የምትወክል ስያሜ ነች። ክሊኒኩ ፀደይ መባ ሉም በሴቶች ጤንነት ዙሪያ ልንሰራ ያሰብናቸው የጤና ጉዳዮች ህክምናውን ለሚሰ ጠውም ሆነ ለሚቀበለው ውጤቱ ደስታን እንዲያጎናጽፍ፤ህመም ተወግዶ ጤንነትን መላበስ እንዲቻል አስፈላጊውን ሁሉ ለማድረግ ክሊኒኩ የነደፋቸው ፕሮግራሞች፤ ያዘጋጃቸው የህክምና መገልገያዎች፤ አገልግሎቱን ለመስጠት የተዘጋጁ ባለሙያዎ ችን ሁሉ የሚያካትት ስያሜ ነው ፀደይ። ፀደይ ክሊኒክ ከተቋቋመ ከአንድ አመት በላይ ሆኖታል፡፡ ይህንን ክሊኒክ ያቋቋመው Saint Pawl Institute for RH and right የሚባል በቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሚሊኒየም ሜዲካል ኮሌጅ የሚገኝ መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት ነው፡፡ ይህ መንግስታዊ ያልሆነ አካል በቦርድ የሚመራ ሲሆን በቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሚሊኒየም ሜዲካል ኮሌጅ በቀጥታ ያልተ ቀቋመ ነገር ግን ተያያዥ በሆነ መንገድ እጅ ለእ ተያይዞ የሚሰራ ነው
ዶር ተስፋዬ አክለው እንደገለጹት በእኛ ሀገር ያሉ የህክምና ተቋማትን ሁኔታ ስንመለከት የግል ተቋማት ከሆኑ ተገልጋዩ የሚመረረው ከክፍያ ጋር በተያያዘ ነው፡፡ ወደመንግስት ጤና ተቋም ሲሄዱ ደግሞ የታካሚው ብዛት ታካሚዎችን ሊያስጨንቅ የሚችል ነው፡፡ ስለዚህም ጥሩ የሆነ የህክምና አገልግሎት ፤ዋጋው አቅምን በማይ ፈታ ተን መልኩ የሚቀርብበት ጤና ተቋም ማግኘት ከባድ ስለሚሆን ፀደይ የስነተዋልዶ ጤና ክሊኒክ ይህንን ለማሟላት በሚያስችል መልኩ ታቅዶ የተቋቋመች ክሊኒክ ናት፡፡
ዶ/ር እስማኤል አክለው ሲገልጹም ይህ ክሊኒክ ሲቋቋም መንግስት ባወጣው ህግ ላይ ተመስርቶ ነው፡፡ ህጉ የሚለው፡-
(….መንግስታዊ ያልሆኑ እና ለትርፍ ያልተቋቋሙ ድርጅቶች እራሳቸውን ለመደገፍ ፤ሌሎች አላማዎቻቸውን ለማስኬድ ለትርፍ የተቋቋመ ድርጅት መክፈት ይችላሉ ….ይላል። ስለሆነም ፀደይ የማህጸንና ጽንስ ክሊኒክ የተቋቋመው ያንን አዋጅ ተከትሎ ነው፡፡)
ይህ Saint Pawl Institute for RH and right የተሰኘው መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት በአገር ውስጥ የተመዘገበ መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት  ነው፡፡ የቦርድ አባላቱም ኢትዮጵያ ውያን ናቸው፡፡ እንደማንኛውም አገር በቀል መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት ድጋፍ እያሰባሰበ ስራውን የሚሰራ እና አንዱ አቅጣጫውም የህክምና አገልግሎትን መስጠት በመሆኑ ነው ፀደይ ክሊኒክን ያቋቋመው። ይህ አገር በቀል መንግስታዊ ያልሆነ ተቋም በኢትዮጵያ መን ግስታዊ ያልሆነ ድርጅት ሆኖ የተመዘገበው እ.ኤ.አ ሴፕቴምር 2019/ነው። ይህ መንግስ ታዊ ያልሆነ ተቋም በአራት አቅጣ ጫዎች ስራዎችን የሚሰራ ሲሆን እነርሱም 1/ጥናትና ምርምር 2/ ስልጠናና ትምህ ርት(አቅምን ማጎልበት) 3/ ስነተዋልዶ ጤና ላይ መረጃዎችን ማሰራጨት(አድቮኬሲ) 4/ ጥራት ያለው የጤና አገልግሎት መስጠት ነው፡፡ ስለዚህም ፀደይ ክሊኒክ ከእነዚህ አራት እቅዶች ውስጥ በጤናው ዘርፍ የተመዘገበ ነው፡፡ ይህን መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት ከሌሎች ለየት የሚያደርገው አድራሻው በቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ውስጥ ሲሆን ከሆስፒታሉም ጋር እጅና ጓንት ሆኖ የሚሰራ ነው፡፡ በዋናነት የህክምና ስራው የሚተገበረውም በቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ውስጥ በሚሰሩ የህክምና ባለሙያዎች ነው፡፡ በመሆኑም ቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሚሊኒየም ሜዲካል ኮሌጅ ለዚህ መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት እንደ አንድ ባለድርሻ አካል በመሆን ያገለግላል፡፡  
በፀደይ ክሊኒክ ምንም አይነት ታካሚ ለህክምና ቢቀርብ ቀጠሮ በመያዝ በሙያቸው በተለያዩ ሕመሞች ስፔሻላይዛድ ያደረጉ ሐኪሞች ስለሚገኙ ካለምንም ችግር መታከም መቻሉ አንዱ ለየት የሚየደርገው ነገር ነው፡፡ ዶ/ር እስማኤል እንዳብራሩት በማህጸንና ጽንስ ዙሪያ ባሉ የጤና መታወኮች ኢትዮጵያ ውስጥ ወደ 5/አምስት የሚደርሱ ልዩ ሕክምና የሚያስፈልጋ ቸው ሕመሞች አሉ፡፡ እነዚህም፡-
የመካንት ልዩ ሕክምና አገልግሎት፤
የስነተዋልዶ(የጽንስ አጠባበቅ አገልግት)
የስነተዋልዶ ጤናና የቤተሰብ እቅድ፤
የማህጸን መውረድና የፌስቱላ፤
የነፍሰጡርና የጽንስ ሕክምና እና የማህጸን ካንሰር ሕክምና በመባል ይታወቃሉ፡፡
ከላይ የተዘረዘሩት ሕክምናዎች በተሌም በመንግስት የህክምና ተቋማት በረዥም ጊዜ ቀጠሮ የሚገኙ ናቸው፡፡ ፀደይ ክሊኒክ ግን ከቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል የህክምና ባለሙያዎች ጋር በመተባበር ወይንም ከእነሱ ጋር ቀጠሮ በመያዝ ታካሚዎችን በማቅረብ በሁሉም የጤና መጉዋደሎች ላይ ተጨማሪ እውቀት ያላቸው (Sub Specialists) እየተገኙ ሕክምናውን ይሰጣሉ ብለዋል ዶ/ር እስማኤል፡፡ እንደ ዶ/ር እስማኤል እማኝነት የጽንስና ማህጸን ሕክ ምናን በሚሰጡ የተለያዩ ክሊኒኮች በተመላሽ ሕክምና ላይ አምስቱንም ልዩ ሕክምናዎች (Sub Specialists) ማግኘት አስቸጋሪ ሲሆን በፀደይ ክሊኒክ ግን ካለምንም ችግር ማግኘት እንደሚቻል ነው፡፡
የዚህም ዋናው ምክንያቱ ከቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሚሊኒየም ሜዲ ካል ኮሌጅ ጋር እጅ ለእጅ ወይንም በቅርበት መስራት በመቻሉ ነው፡፡    
ጸደይ ክሊኒክ ገላጣ እና ሰው ያልበዛት አካባቢ አልተቋቋመችም፡፡ ብዙ ሰው የሚኖርበት እንዲሁም የሚሰራበት አካባቢ ነው፡፡ የዚህን ምክንያት ዶ/ር እስማኤል ሲገልጹ ክሊኒኩ የሚገኘው ከአውቶቡስ ተራ ወደመሳለሚያ በሚወስደው መንገድ ላይ ነው፡፡ አካባቢውም በጣም ሰው የበዛበት ከአውራ ጎዳናም ዞር ብሎ ወደ መንደር ውስጥ በሚሄድ ጠባብ መንገድ ላይ ሲሆን በግልም ሆነ በትናናሽ ድርጅቶች አማካኝነት የግል ስራቸውን የሚሰሩ እንዲሁም ቤታቸውን ሰርተው የሚኖሩ ሰዎች ያሉበት ጥንታዊ መንደር ነው፡፡ ፀደይን የሚጎራበቱዋት አብዛኛዎቹ ቤቶች መኖሪያዎች ሲሆኑ የክሊኒኩን አገልግሎት የሚሹ ብዙ ታካሚዎች ይገኛሉ፡፡
ዶ/ር ተስፋይ በዚህ ላይ ሲያክሉ ነዋሪዎቹ ብዙዎቹ ከፍተኛ አቅም የሌላቸውና በግል ክሊኒክ ደረጃ ገንዘብ ቢጠየቁ ከፍለው መታከም ሊያስቸግ ራቸው የሚችል በመሆኑ እዚያ ቢከፈት ብዙውን ሰው ማገልገል ይቻላል ከሚል እምነት በተደራጀ መልኩ የተቋቋመ ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ደህንነቱ የተጠበቀ የጽንስ ማቋረጥ፤ያልተፈለገ እርግዝናን መከላከል፤ የማማከር አገል ግሎትን ይሰጣል፡፡ ይህንን አገልግሎት የሚሹ ወጣቶች፤ተማሪ ዎች የመሳ ሰሉት ተገል ጋዮች በነጻነት ካለምንም መሸማቀቅ እራሳቸውን ሳያጋልጡ አገልግሎቱን ማግኘት እንዲችሉ ታስቦም ነው ጸደይ ክሊኒክ የተቋቋመው ፡፡
ክሊኒኩ ለስራው በደንብ የተዘጋጀ እና በክፍያ ጉዳይም የሚታማ አለመሆኑን ባለሙያዎቹ ገልጸዋል፡፡ የህክምናው አገልግሎትም ሙሉ በሙሉ እውቀቱ ባላቸው ባለሙያዎች እና በተ ደራጁ መሳሪያዎች በመታገዝ አቅምን በማይጎዳ መልኩ ጥሩ ሕክምና በመሰጠት ላይ ነው፡፡  
ለዚህ እትም ምንጮቻችንን ዶ/ር ተስፋዬ ሁሪሳ የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስት፤ በቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል የስነተዋልዶ ጤና ፕሮግራም ዳይሬክተር እና በጸደይ ክሊኒክ ዳይሬክተርት እና ተቆጣጣሪ እንዲሁም ዶ/ር እስማኤል ኢብራሂም የፀደይ ክሊኒክ ሜዲካል ዳይሬክተርና ስራ አስኪያጅ እንዲሁም ጠቅላላ ሐኪምን በአንባቢዎች ስም እናመሰግናለን፡፡  

Read 5735 times