ባለፈው ቅዳሜ ታህሳስ 29 ቀን 2015 ዓ.ም በደቡብ ኦሮሚያ፣ ምዕራብ ጉጂ ዞን፣ በቡሌ ሆራ ከተማ የኦነግ ሸኔ ታጣቂዎች ከ480 በላይ እስረኞችን ማስለቀቃቸው ተጠቆመ።
የመንግስት ባለሥልጣንና ነዋሪዎች ለ”አዲስ ስታንዳርድ” እንደተናገሩት፤ የአማፂ ቡድኑ አባላት በጎሮ ጉዲና ቀበሌ በሚገኘው ማረሚያ ቤት ቅዳሜ እኩለ ሌሊት ላይ ጥቃት በመሰንዘር እስረኞችን አስለቅቀዋል፡፡
የቡሌ ሆራ ከተማ ምክትል ከንቲባ ጊርጃ ኡራጎ እንደገለጹት፤ ታጣቂዎቹ በሥራ ላይ የነበሩ አምስት የማረሚያ ቤቱ የጥበቃ አባላትን ከገደሉ በኋላ ነው እስረኞቹን ያስለቀቁት፡፡
“የአማፂ ቡድኑ አባላት አምስት የማረሚያ ቤቱን ጠባቂዎች ከገደሉ በኋላ ከ480 እስከ 500 የሚደርሱ እስረኞችን ማስለቀቅ ችለዋል” ሲሉ ከንቲባው ለ”አዲስ ስታንዳርድ” ተናግረዋል።
ከማረሚያ ማዕከሉ አቅራቢያ የሚኖሩ አንድ እማኝ እንደተናገሩት፤ በአካባቢው በሁለቱ ሃይሎች መካከል ከባድ የተኩስ ልውውጥ ነበር።
“የተኩስ ልውውጡ ከምሽቱ 5፡30 ጀምሮ እስከ ሌሊቱ 9፡30 ዘልቋል። በሁለቱ ሃይሎች መካከል ከባድ ተኩስ ነበር። ከዚያ በኋላ ነው የአማጺው ቡድን አባላት ወደ ማረምያ ማዕከሉ ዘልቀው በመግባት እስረኞቹን ያስለቀቁት።” ብሏል፤ አንድ ስሙ እንዳይጠቀስ የፈለገ የአካባቢው ነዋሪ።