Saturday, 13 May 2023 20:29

“የቃል ሠሌዳ” - ዳሰሳ

Written by  - በረከት ተስፋዬ
Rate this item
(0 votes)

 “የአሞራ ዐይን ባላየው፤
ጭልፊትም ወደ ‘ማያውቀው፤....”  /ገፅ 112/
ወደ ‘ማይሰፈር ፣ ወደ ‘ማይመተር ... በመኖር ብቻ ወደ’ሚገባ እዉነት ፥ ቃልን እንደ ቃል ልናትም ሠሌዳ ፍለጋ .. ችሎት  የሚሸከመውን....
“ትንሽ ልፋሰሰዉ
በሰማያት ደርባ በማይጎረብጠዉ ...”  እንዳለዉ ወንድዬ ዓሊ፣ የሰውን ልጅ የምናብ /imagination/ ደረጃ ... የማይታወቅን ወደ ማወቅ ... በቃል ሠሌዳ በኩል ...
በመንበረ ወደ መንበር
በማርያም ወደ አርያም...
ስለ ቃል አቅም ፣ ስለ ቃል ኃይል /power/ እንዲህ ትለዋለች....
“ቃል ኃይል ፣ ቃል መለኮት ፣ ቃል እስትንፋስ ፣ ቃል ኹሉን አድራጊ ፣ ቃል ህያዉ ነዉና..
/ገፅ 8/
የሥነ-ግጥሞቹን ልብ የሥነ-ግጥሞችን እስትንፋስ ለመቋደስ በርዕሱ በኩል እናዝግም...
የቃል ሠሌዳ ... ???
ለትርጉምነቱ አንድ አቻ ሐሳብ ያለው ያስመስለዋል። /በብቻነት አይደለም!/
አካላዊ ቃል /logos/ የገመደበትን እንደ ሠሌዳ ...
/ሌላም ብዙ ብዙ ..በአንድምታ../
“እልፍ ዘመናት ተሻግረን ፣ አእላፍ ዕድሜ ብንገብር ፤
አይነኬ ኹነት አለ ፤ እንደ ዕድል ኾኖ እንደ ግብር።”. /ገፅ 11/
የሰውን ልጅ አቅም ... የመድረስ ልክ ጠጠር አድርጎ ያበክራል። የመቻልን ሀቂቃ የመኖርን እውነት ሁለት ስንኝ ሲሸብበዉ...!!
ደግሞም ... ነፍስ የምትሻቸውን ሁኔታዎች ፣ የምትረጋባቸውን መቼቶች እንዲህ ትላቸዋለች።
“ጠይም ሰማይ፣
ሙሉ ጨረቃ፣
አረንጓዴ ባህር፣
ቀዝቃዛ አየር፣
ወርቃማ እሳት፣
ደረቅ እንጨት፣
ጣፍጭ ወይን፣
ትዝታ...
ክራር...
ሙዚቃ...
ግጥም...
ቀለም...”   /ገፅ 53/
ብላ እርግት ፥ እርክት ያለን ህይወት በእነዚህ በኩል እንድናጣጥማቸዉ
እንደ መንገድ ... / በሌባ ጣት ማመልከት/
ስለ ቃል ጉልበት ፣ ስለ ቃል አቅም ፣ ስለ ቃል ሁለንታነት የሆነዉ ሁሉ የሆነበትን
በቃል ስፍር እንዲህና እንዲያ አለመባሉን ... መረታት ፣ ፈቅዶ መ’ገበር ፣ መገዛትን
ከልባዊ ሐሳብ ፣ ስሜት ጋር ሲቆራኝ /ዓሜን ያስብላል...!/
“ንፋስ ከብርሃን ይረቃል
ያንተም ቃል...
ከነፍሴ ማሳ ይፀድቃል።...”  /ገፅ 14/
ንፃሮትንም ፣ ተመንንም ፣ አንፃርንም አይፈልግም። ዝም ብሎ ዝም ማለትን
ነዉ እንደ ሎሬቱ...
“የንፋስ መንገድ፣
የብርሃን መንገድ፣
ቃል ተመስሎ፣
ዉበት አክሎ፣...”  /ገፅ 14/
የማይዳሰሰዉን ያስዳስሳል ፤ ከረቂቁ ጋር ያስተያያል ፤ ተመስሎም አክሎም የልቦናዋን ጌጥ በዚህ በኩል ስትተነፍሰዉ ... ለነፍስ ድግፍ ፣ እርፍን ያቀዳጃል።
“ሲገለጥ በተስፋ አምሳል፣
ካንተ እኩል ይተካከላል፤
እምነት ባንተ ይበረታል፤
ኹሉ በቃልህ ይረታል።
እኔም!”.  /ገፅ 14/
አምላካዊ ሥነ-ባህርይ ጋር ትከሻ ለትከሻ ታለካካዋለች፤ እሱነቱን... ‘ኹሉ በቃልህ ይረታል’ በሚለዉ አንቀፅ እንዲያዉም ትንሽ መግዘፍን ያስደፍራል። ከተስፋ /ነገ/ እኩልነቱ ፣ እምነት ማበርታቱ ሲታከል ሥነ-ሰብዕነቱን ያስጠረጥራል። /የገጣሚ ጉልበቱም ይሄዉ ነዉ።/
እንዲህና እንዲያ በሚመስሉ ስሜቶችን በክራር ድርድር እየተባበለ  ምልከታዎቿን ታስቃኘናለች... በቃል ሠሌዳ...። “የፀሐይቱ መሠልጠን ፣ በቀን ብርሃን ነበረ ፣
የጨረቃ መገለጥ ግን ፣ ክቡድ ጨለማን ሰበረ።”   /ገፅ 11/ መፅሐፏ በአጠቃላይ ስለ ቃል ፣ ስለ ትዝታ ፣ ስለ ፍቅር ፣ ስለ መንገድ .... አበክሮ ... የሰው ልጅን ልብ ይበልጡን የሚይዙትን ግዙፍ ሐሳባት ስሙር  በሆነ ቃላት ከሽና የቀረበች ሸጋ መድበል ናት።
እንዲህና እንዲያ ብለን ገጣሚና ከያኒ ስዩም ተፈራ ስለ መፅሐፉና ገጣሚዋ ያሉትን ፈክረን እንወጣለን...
“ገጣሚ ከተነኮሰዉ ምንም ጋር ሲተናነቅ ሲመልስና ሲጠይቅ ኑሮን ይገፋ ይመስለኛል። አራት ነጥብ ሳንኖር የፀናን ሲጠይቅ የደረሰበትን ሲንቅ የተስፋ ህመምን ሲጨምቅ ይዘልቃል። በትናንት ማልቀስ በድል መኮፈስ ግቡ አይደለም። ግቡን ገና እየፈተሸ ከሚያገኘዉ ዉስጥ ይጠልቀዋል፤ ያም ምንም አያጠግበዉም። “አንች የዚህ ኑሮ አዝጋሚ ነሽ። ቢጠጉት ለሚርቅ ቆመዉበት ለሚርቅ የግጥም አባዜ መልካም ጅማሮ ነዉና ጉዞዉን ባለመመለስ ተንደርደሪ፤ ከቃልና ከቃላት በቀር ከደመና በላይ አቅጣጫ ጠቋሚ አታገኝም፤ የአንችኑ ዱካ ተከተይ።”



Read 1045 times