Saturday, 13 May 2023 20:56

ኢሎን መስክ ለትዊተር አዲስ ዋና ሥራ አስፈፃሚ መቅጠሩን አስታወቀ

Written by 
Rate this item
(0 votes)

 አዲስ ሃላፊ መቅጠሩ መሰማቱን ተከትሎ የቴስላ አክሲዮን በ2 በመቶ አድጓል

         ቢሊየነሩ ኢሎን መስክ ለትዊተር አዲስ ዋና ሥራ አስፈፃሚ መቅጠሩን ከትላንት በስቲያ ሃሙስ ያስታወቀ ሲሆን፤ አዲሷ የኩባንያው ሥራ አስፈፃሚ በጥቂት ሳምንታት ውስጥ ሃላፊነቱን ከባለ ሃብቱ ትረከባለች ተብሏል፡፡
“ለትዊተር አዲስ ዋና ሥራ አስፈፃሚ መቅጠሬን ሳስታውቅ በመጥለቅለቅ ስሜት ተሞልቼ ነው፡፡ በ6 ሳምንት ጊዜ ውስጥ ስራ ትጀምራለች!” ሲል  መስክ በግል የትዊተር ገፁ ፅፏል፡፡ የአዲሷን ዋና ሥራ አስፈፃሚ ማንነት ግን ከመግለፅ ተቆጥቧል፡፡“የእኔ ሚና ወደ ዋና ሊቀ መንበርነትና ዋና የቴክኖሎጂ ሃላፊነት ይሻገራል” ያለው ኢሎን መስክ፤ በኩባንያው ውስጥ በዋና የቴክኖሎጂ ሃላፊነት በንቃት እንደሚሳተፍም አስገንዝቧል፡፡
ባላሃብቱ ባለፈው የካቲት ወር፣ በ2023 መጨረሻ ላይ ለትዊተር አዲስ ዋና ሥራ አስፈፃሚ እንደሚቀጥር ማስታወቁ አይዘነጋም፡፡መስክ የኤሌክትሪክ መኪኖች አምራቹ ቴስላ እንዲሁም የጠፈር መንኮራኩር አምራቹና የሳተላይት ኮሙኒኬሽን ተቋም የሆነው SateliteX  ዋና ሥራ አስፈፃሚም መሆኑ ይታወቃል፡፡
ባለፈው ህዳር ወር መጀመሪያ፣ የማህበራዊ ሚዲያ መድረኩን በ44 ቢሊዮን ዶላር ከገዛ ከጥቂት ሳምንታት በኋላ፣ ቢሊየነሩ ለዴልዌር ፍ/ቤት፣ የኩባንያው ዋና ሥራ አስፈፃሚ የመሆን ፍላጎት እንደሌለው ተናግሮ እንደነበር ቢቢሲ አስታውሷል፡፡
በሚያስገርም ሁኔታ ራሱ መስክ ፈጠረው የትዊተር አስተያየት መሰብሰቢያ ፖል፣ በሚሊዮን የሚቆጠሩ የትዊተር ተጠቃሚዎች፣ ባለሃብቱ ከሃላፊነቱ እንዲወርድ የጠየቁ ሲሆን እሱም ለአስተያየታቸው ተገዢ እንደሚሆን ቃል ገብቶ ነበር ተብሏል፡፡
 ቢሊየነሩ የማህበራዊ ሚዲያ መድረኩን ገዝቶ መምራት ከጀመረ ወዲህ ኩባንያው ብዙ ምስቅልቅሎች እንደገጠሙት የሚያስታውሱ የቴክኖሎጂ ተንታኞች፤ ለትዊተር ጤናማ የወደፊት ጉዞ አዲስ ዋና ስራ አስፈፃሚ መቀጠሩን ትክክለኛ ውሳኔ ነው ብለውታል፡፡
አሶሼትድ ፕሬስ እንደዘገበው፤ መስክ ለትዊተር አዲስ ዋና ሥራ አስፈፃሚ መቅጠሩን ማስታወቁን ተከትሎ፣ ባለፈው ሃሙስ፣ የኤሌክትሪክ መኪና አምራቹ ቴስላ አክስዮን በ2 በመቶ  ገደማ አድጓል፡፡ የኤሌክትሪክ መኪና አምራች ኩባንያው ባለ አክሲዮኖችም የመስክ ምን ያህል ትኩረት በትዊተር ላይ ይውላል ከሚለው አሳሳቢ ጉዳያቸው እፎይታ ያገኛሉ ተብሎ ተገምቷል፡፡
የቴስላም ሆነ የማናቸውም ኩባንያዎች ዋና ሥራ አስፈፃሚ የመሆን ፍላጎት ፈፅሞ ኖሮኝ አያውቅም የሚለው ኢሎን መስክ፤ ራሱን ከዋና ሥራ አስፈፃሚነት ይልቅ እንደ ኢንጂነር መቁጠር እንደሚመርጥ ይገልፃል፡፡

Read 1223 times