Print this page
Saturday, 13 May 2023 21:01

“ዓለምን ለመመገብ ከሩሲያ ጋር ስምምነቱ መታደስ አለበት”

Written by 
Rate this item
(2 votes)

 የዓለም ምግብ ፕሮግራም ሃላፊ፤ ሩሲያ ከዩክሬን የእህል ኤክስፖርት ስምምነት ከወጣች ዓለምን መመገብ ፈታኝ እንደሚሆን አስጠነቀቁ፡፡
ሲንዲ ማክኬይን ሰሞኑን ለቢቢሲ እንደተናገሩት፣ የፊታችን ሜይ 18 ቀን 2023 ዓ.ም የጊዜ ገደቡ እንደሚያበቃ የሚጠበቀው ስምምነት መታደስ ይኖርበታል፡፡
የእህል ኤክስፖርት ስምምነቱ ዩክሬን፣ ጦርነቱ እየተካሄደም ቢሆን፣ ብዙ ሚሊዮን ቶን ምግብ እንድታጓጉዝ አስችሏታል ተብሏል፡፡ ስምምነቱን ያሸማገሉት የተባበሩት መንግስታት ድርጅትና ቱርክ ነበሩ-ባለፈው ሃምሌ ወር፡፡ዩክሬን የበቆሎ፣ ስንዴና ገብስ ትልቋ ዓለማቀፍ ላኪ አገር ስትሆን፤ባለፈው ዓመት በዓለም ምግብ ፕሮግራም ከተከናወነው የስንዴ ግዢ ከግማሽ በላይ የሚሆነው የተገኘው ከዩክሬን እንደነበር ታውቋል፡፡  “ስምምነቱን ማደስ አለባቸው፡፡ ካላደሱ በስተቀር እንኳን ዓለምን ቀርቶ ክልሉንም መመገብ አንችልም፡፡” ብለዋል፤ የዓለም ምግብ ፕሮግራም ሃላፊዋ፡፡ “እንደምታውቁት ዩክሬን የአውሮፓ የዳቦ ቅርጫት ነበረች፣ አሁን ግን ያ እየሆነ አይደለም፤ እናም እህሉን ከዚያ ማውጣት አለብን፤ ምክንያቱም ሌሎች አገራትን እየጎዳ ነው” ሲሉ አስረድተዋል፤ ሃላፊዋ፡፡
ስምምነቱ በአንድ ጊዜ የሚራዘመው ለ120 ቀናት ነው፤ ነገር ግን ሩሲያ በእህልና ማዳበሪያ ኤክስፖርቷ ላይ በገጠማት መሰናክል ሳቢያ፣ ሜይ 18 ከስምምነቱ እንደምትወጣ በመግለፅ፣ በዓለም ላይ  ሥጋት ጋርጣለች ተብሏል፡፡
ቢቢሲ እንደዘገበው፤ የሩሲያ፣ ዩክሬን፣ቱርክና የተባበሩት መንግሥታት ከፍተኛ ሃላፊዎች ስምምነቱን በማራዘም ሃሳብ ላይ ለመወያየት ባለፈው ሃሙስ በኢስታንቡል ተሰብስበው ነበር፡፡ ቁርጥ ያለ ውሳኔ ላይ ግን አልደረሱም፡፡
“ጉዳዩ በእጅጉ ያስጨንቀኛል፡፡ የተቀረውንም ወገን ሁሉ ሊያስጨንቀው ይገባል፡” ብለዋል፤ ሃላፊዋ፡፡
“ሁሉም የዓለም መሪ” ስምምነቱ እንዲታደስና ግጭቱ እንዲቆም ሁኔታዎችን በማመቻቸት ያግዝ ዘንድ ጥሪ አቅርበዋል - የዓለም ምግብ ፕሮግራም ሃላፊዋ ሲንዲ ማክኬይን፡:



Read 1145 times
Administrator

Latest from Administrator