Monday, 08 July 2024 19:56

ነቢይ ፍጥሞ ደሴትን ይመስላል

Written by 
Rate this item
(0 votes)

አዲስ አበባ ለኮሪደር ልማት ስትፈርስ፣ ቼ ባር ወይም በአካል ባር እንዳልሆነ መሆን ወይም ፒያሳ እንደ ኢራቅ የቴምር ዛፎች ስትገነደስ፣ ዶሮ ማነቂያ እንደ ካርቴጅ ስርወ መንግስት ስትገረሰስ አልታመምኩም፡፡

የጆሊ ባር እንዳልነበረ መሆንም ይሁን እንደ ጃፓኗ ከተማ እንደ ዋጂማ እንደ ትናንት ታይታ ዛሬ የወደመችው አዋሬ መጥፋት፣ የወይዘሮ ደኸብ ሬሲፒም ይሁን የገብረ ትንሣኤ ኬክ ቤቶች refurbish መደረግ አላስደነገጠኝም፡፡

ናይጄሪያዋን አቡጃን ሌጎስ፣ ኤሚሬቶች Old dubai ን በኒው ዱባይ፣ ግብፆች ጥንታዊ ካይሮ በአዲሱ ካይሮ፣ ህንዶች ጥንታዊውን ደልሂ በአዲሱ ዴልሂ እንደቀየሩ እኛም አዲስ አበባን ትተን አዲስ ከተማ ቢፈጠር የሚል ክርክርም አይመስጠኝም፡፡

የኔ ትዝታ እንደ ታይታኒክ ልትሰምጥ ያለችው ጋዜጦች ይነበቡበት የነበረ ቦታ ነው፤ ነቢይ ልጅነቴን ከጥበብ የሰፋበት ቦታ፤ እዚያ ነው የኔ ትዝታ።

እኔ ግን የነቢይ መኮንን አዲስ አድማስ ነው የሚያስደግጠኝ፤ ያ ቀይ ዳማ፣ ያ ብሩህ ኢትዮጵያ ለብቻው የመዘገበችለት ሪከርድ ነበረው። በምን በሉኝ ? ስሞትላችሁ

ወንጌላዊው ዮሐንስ እና ነቢይ መኮንን፡፡

ነቢይ እስረኛ ነበር፤ ወንጌላዊው ዮሐንስ ኢየሱስን በታማኝነትና በተለይ በትህትና እስከ መስቀሉ ተከትሎት ስለነበር ኢየሱስ ለዮሐንስ ምስጢር  ገለጠለት፤ በሮማው ንጉስ ዶሚሽያን ፍጥሞ ደሴት ታስሮ ሳለ ራዕይን ፃፈ ፤ በጌታና በባርያዎቹ መሀል ብራና ተወ፡፡

ነቢይ ያው ነው፤ ለኢህአፓነቱ ፈፅሞ ታዛዥ ሆነ፤ ደርግ ለአመታት አሰረው፤ ታስሮ ግን ተስፋ ነበረዉ፤ ትሁት ነውና አያሌ መጻሕፍትን አነበበ፤ እገደላለሁ የሚለውን ስሜት ትቶ Gone with the wind ይተረጉም፣ ግጥም ደግሞ የሲጃራ ወረቀት ላይ ይፅፍ ነበር፤ደርግ ነቢን አልገደለውም፤ እግዜር ይስጠው!!

ከእስር ወጣና እንደ ዮሐንስ በጥበብ ጌቶች (መጻሕፍት እና ፀሐፍያን ) እና ባርያዎች መሀል ተወዳዳሪ አልባ ድልድይ ሆነ፤ ነባ እጅግ ምጡቅ ነበር ፤ በሀርቫርድና ኦክስፎርድ መሀል መዋለል እየቻለ በኢትዮጵያዊ ሀሳብ መሀል ተጋ፤ ለIVy league ተወልዶ በካዛንቺስ ነሆለለ፡፡

በውጭ ሀገር First class መኪና፣ First class ቤትና ኑሮ ተመቻችቶለት ለአዲስ አድማስ ጋዜጣ ተሰዋ፤ ቅዱስ ዮሐንስ እነኋት እናትህ ተብሎ የጌታ እናት ተሰጠችው፤ ነቢይ ጥበብ እነኋት እናትህ ብላ የሰጠችውን አደራ ተወጣ።

ሳይቀና፣ ሳይሰደድ፣ ሳይማረር ገንዘብ ማጣትን ተቋቁሞ ትውልድ አፈራ፤ በኢትዮጵያ ታሪክ የነቢይ ብቻ የሆነ፣ ያ የአዳማ ጀንትል ማን የፈጠረው ቀመር አለ።

የአዲስ አድማስ ርዕሰ አንቀፅ

በ9ዐዎቹ  እና በ2000 መጀመሪያ የነበርን፣ ጋዜጣ የመግዣ ገንዘብ ያለውም ሆነ የሌለው፣ ምሁርም ይሁን ያልተማረ፣ አዲስ ነገርን፣ አዲስ ጉዳይን፣ ጦቢያን ያነበብን ሁላችን መጀመሪያ የምንመርጠው የነቢይን ርዕሰ አንቀፅ ማንበብ ነበር። የነቢይ ርዕሰ አንቀፅ ዝም ብሎ ርዕሰ አንቀፅ አይደለም፡፡
* ማንም ከያኒ
* ማንም ሀያሲ
* ማንም አዘጋጅ እርሱን ሊሆን አልቻለም።
እርሱ Simplicity ነው።

ማርክ ትዌይንን አቅልሎ እንዴት እንደሰጠን፤ በርናንድ ሾውን እንዴት እንዳፍታታልን? ኒዛር ቃባኒን እንዴት መሬት እንዳወረደው? ነባ አንድን ርዕሰ ጉዳይ ሲያፍታታ ሲፈልግ Leonardo -  Simplicity is the ultimate sophistication  እንዳለው ያደርጋል፤ ወይም ደግሞ Albert Einstein - If you can't explain it simply, you don't understand it well enough እንዳለው፡፡

ትልቁን concept በተረት ፣ በምሳሌ በገጠመኝ እያዋዛ በርዕሰ አንቀፁ ያጫውትሀል፤ አንድ ደራሲ ወዳጄን  ስለ አዲስ አድማስ ጋዜጣ ጠይቄው እንዲህ ብሎኝ ነበር :- "ርዕሰ አንቀፁን አንብቤ ሌላውን እተወዋለሁ"

ምነው ስለው፤ " ነብይ ነዋ" አለኝ። እውነት ነው፤ የራዕየ ዮሀንስ መጠቅለያ " ከዚህ መፅሐፍ የጨመረና የቀነስ " ይላል ፤ የኢትዮጵያ ፖለቲካም ይሁን ወቅታዊ ሁኔታ መጠቅለያ የአዲስ አድማስ ርዕሰ አንቀፅ ውስጥ ነበረ።

ነቢይ እና ፍጥሞ ደሴት

ደርግ እግዜር ይስጠው አልገደለውም ፤ ኢህአዴግ እግዜር ይስጠው ጋዜጣውን አልዘጋበትም፤

ለምን ?

ኢትዮጵያዊው ዮሐንስ እጅግ ጥበበኛ ነበር፤ ብሶታችንን የሚተነፍሱልን ጋዜጦች ሲዘጉ ነባ ነበር። ህመማችንን የሚያስተጋቡልን መፅሄቶች ጥለውን ሲሄዱ መፅናኛችን ህይወት ፖለቲካ ብቻ አይደለም የምትለን አዲስ አድማስ በነቢይ ብልጠት ቀጠለች፡፡

የግሪኳ ፍጥሞ ደሴት በኦቶማን ቱርክ በተያዘች ጊዜ ኦቶማኖች ፍጥሞን አላጠፉም፤ ታሪክ ነውና አስቀሩት ፤ የነባ ርዕሰ አንቀፅ ሊጠፋ ነበር፤ ኢህአዴግ አዲስ አድማስን ተወልን።

ነቢይ depth ሰጠን ፤ በሩቅ ምስራቅ ፍልስፍና  እያሰከረ፣ በምስራቃውያን ሀሳብ እያጠመቀን አበራን።

* የፀጋዬ ገብረመድህንን ሀሳብ አቅልሎ መሬት አወረደልን፤ ተደመምን፤ የሼክስፒርን ድርሰት "ሼክስፒር በፀጋዬ ብዕር እንዳለው" እያለ አስገረመን።

* ጌታቸው ቦሎድያን ስለሚባል ባዮኬሚስት ነግሮን የማናውቀውን ሠው በልባችን ሀውልት እስክንሰራለት አሰገደን።

* ምሁራን ከአደባባይ ጀርባ ስላለው ውሎአቸውና እውነት የሀገራቸውን ችግር ተረድተዋል ወይ የሚል ቃል ሲያወጣ ? በሱ ዘመን የፈኩ በምሁራን መካከል ስላለው አለመግባባት ሲያጠይቅ ፣ መቀናናታቸው ላይ ክስ ሲያነሳ የኢትዮጵያን ችግር ላይ ላዩን ሳይሆን ከስር ከመሰረቱ ሲያሳየን እውነትም ይህ ሰው ከአዳማ ሳይሆን ከፍጥሞ ደሴት ነው ያስብላል።

ነባ didn't give us Knowledge, but he taught us how to manage knowledge.

በመጨረሻ መፅናኛ አንድ፡-

ከመሞቱ በፊት መንግስት ቤት ሰጥቶታል ፤
ሀገሪቷን ሳይረግም በመሞቱ
Thank you ብልፅግና!

መፅናኛ ሁለት

እግዜር በሰማይ የገብረክርስቶስ ጭዌ ፣ የተስፋዬ ገሠሠ ጨዋታ ፣ የሰለሞን ደሬሣ ግጥም ፣ የበዓሉ ግርማ ወግ ሠለቸው፤

እንደ ህፃን መሣቅ ፣ መፈንደቅ ፣ በፈጠረው ፍጡር መገረም እና መኩራት አማረው ፤ ወግ እና የጣፈጠ ወሬ አማረው ፤ እርጋታ አማረው፤

ወሰደው ፤

መፅናኛ ሶስት

የነባን የጥበብ ጠብታ ለመወጋት

* ከስኮላ በስተደቡብ ወይም የኤጂያን ባህር ማቋረጥ አይጠበቅብህም።

* ሚዲትራኒያንን ማቋረጥ አልያም ትኬት ቆርጠህ  ግሪክ አትሄድም፤

* ራዕየ ዮሐንስ  " ኦሂ ስቶ 666 " የሚል አደናጋሪ ፅሁፍ ድንጋይ ላይ ተፅፎ ማግኘት አይጠበቅብህም፤

በፍጥሞ ደሴት ቁርጥራጭ ወርቆች ፣ የከበሩ ድንጋዮች እና ቁርጥራጭ የማርቆስ ወንጌል አለ።

የኢትዮጵያዊውን ዮሐንስ ቁርጥራጭ ጥበብ መቀጠል የፈለገ ሩቅ እንዳይሄድ

አዲስ አድማስ ርዕሰ አንቀፅን ይመልከት።

(ናትናኤል ከበደ)

Read 599 times