የትብብር ለኢትዮጵያ አንድነት ጥምረት ባወጣው ባለ 11 ነጥብ መግለጫ በቅድመ-ምርጫ ሂደት ላይ በርካታ ሕገ-ወጥ ድርጊቶች መፈጸማቸውን አስታውቋል። ጥምረቱ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል 15 ዕጩዎቹ "በሲስተም ምክንያት" እንዳይመዘገቡ መደረጉንና በተለያዩ አካባቢዎችም በዕጩዎች ላይ የማወከብና የግድያ ማስፈራሪያ መፈጸሙን አመልክቷል። በተጨማሪም በኦሮሚያና በአማራ ክልሎች 97 በመቶ ምርጫ ለማካሄድ አስቻይ ሁኔታ አለ ተብሎ የቀረበው ሪፖርት ፍጹም የተዛባና አሳሳች ነው ሲል በጽኑ ተችቷል።
በመግለጫው ማጠቃለያ ላይ ጥምረቱ የመራጮች መረጃ ምንተፋና ሥነ-ልቦናዊ ጫናዎች በአስቸኳይ እንዲቆሙ የጠየቀ ሲሆን፣ በመንግስት ላይም ጠንካራ ጥሪዎችን አስተላልፏል። በዚህም መሰረት መንግሥት የገባውን የለውጥ ቃል እንዲያከብር፣ የታሰሩ የፖለቲካ እስረኞችን በአስቸኳይ እንዲፈታና ለዘላቂ ሀገራዊ አንድነት ሲባል ከሁሉም ባለድርሻ አካላት ጋር በጋራና በትብብር እንዲሠራ ጥሪ አቅርቧል።


