Error
  • JUser: :_load: Unable to load user with ID: 62
Saturday, 17 November 2012 10:26

የዋልድባ መነኰሳት “ኳሬዳ” በተሰኘ ትልና ምስጥ ተቸግረዋል

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

ለመነኰሳቱ የአስቸኳይ ጊዜ የምግብና የአልባሳት እርዳታ ጥሪ ቀርቧል
በሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት ዓዲ አርቃይ ወረዳ የሚገኘው የጥንታዊው ዋልድባ ደልሽሐ ኪዳነ ምሕረት ማኅበረ ደናግል ገዳም ሴት መነኰሳት ኳሬዳ በተሰኘ ትልና በአካባቢው በብዛት በሚፈላው ምስጥ መቸገራቸውን ለገዳሙ የራስ አገዝ ልማት ርዳታ ለማሰባሰብ የተቋቋመው ኮሚቴ ገለጸ፡፡ ትሉ መነኰሳ ቱ ለዘመናት የኖሩባቸውን ጎጆ ቤቶች /የሣር መክደኛ/ ምቹ መራቢያ እንዳደረገው የተገለጸ ሲሆን ትሉን በምትገበው ኩቱ የተባለች ወፍ በሚራገፍበት ወቅት በመነኰሳቱ ቆዳ ላይ እያረፈ ሰውነታቸውን ያሳብጣል፤ ዕብጠቱ ከሚፈጥረው ሥቃይ ለመዳን መነኰሳቱ ሰውነታቸውን በምላጭ ስለሚበጡት ተጨማሪ ጉዳት እያስከተለባቸው ነው፡፡ በአካባቢው በብዛት የሚፈላው ምስጥ ሌላው የማኅበረ ደናግሉ ፈተና መኾኑ ሲሆን አረጋውያትና ሕሙማን መነኰሳት የሚረዱባቸውን የአልጋ ቆጦችና የቤት ቋሚዎች እየቦረቦረ በመጣል ለጉዳት እየዳረጋቸው መኾኑ ታውቋል፡፡

ኳሬዳ ለተሰኘው ትል በምቹ መራቢያነት የተጠቀሰውን የሣር ጎጆ በቆርቆሮ ክዳን በመለወጥ ለመከላከል እንደሚቻል በተሞክሮ የተረጋገጠ ሲሆን ቤቶቹ የተደገፉባቸውን የዕንጨት ምሰሶዎች በግንብ /ኮንክሪት/ በመተካት ደግሞ የምስጡን ጥቃት መቋቋም የሚቻል በመኾኑ በጎ አድራጊ ግለሰቦችና ድርጅቶች በሀገረ ስብከቱ ጥያቄና በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ፈቃድ ከተቋቋመው የገዳሙ እርዳታ አሰባሳቢና ልማት ኮሚቴ ጋራ የተጠየቁትን የግንባታ ቁሳቁሶች በዐይነትና በገንዘብ በመስጠት የተቻላቸውን እገዛ እንዲያደርጉ የኮሚቴው ሓላፊዎች ጥሪያቸውን አቅርበዋል፡፡
በቁጥር ከሦስት መቶ ኀምሳ ያላነሱ ሴት መነኰሳዪያት ብቻ በማኅበር ለሚኖሩበት ገዳም የእህል ወፍጮ፣ የውኃ መሳቢያ ሞተርና የውኃ ማጠራቀሚያ ታንኮችን ለመትከል፣ ዘመናዊ የንብ ማነብ/የማር ምርት/ እና ሌሎችም የራስ አገዝ ልማት ፕሮጀክቶችን ለመተግበር እንደሚንቀሳቀስ የጠቆመው ኮሚቴው አክሎ እንደገለጸው÷ እንደ ጾሙና ጸሎቱ ሁሉ ሥራን የጽድቅ መሠረት አድርገው በማኅበር የሚኖሩት ከሦስት መቶ ኀምሳ በላይ ማኅበረ ደናግሉ፤ በከፍተኛ ሙቀትና በሌሎችም የአካባቢ ለውጦች ሳቢያ ራሳቸውን የሚረዱባቸው የዳጉሳና የማሽላ ሰብሎቻቸው ፍሬ ሊሰጧቸው ስላልቻሉ አስቸኳይ የምግብ (ባቄላ፣ ዘንጋዳ፣ ዳጒሳ፣ ሰሊጥ፣ ኑግ፣ ጨው፣ በርበሬ) እና የአልባሳት (ስድሳ ጣቃ አቡጀዲ ጨርቅ) እርዳታ እንደሚያስፈልጋቸውም አስታውቋል፡፡

 

Read 6197 times Last modified on Saturday, 17 November 2012 10:32