Saturday, 20 August 2011 10:41

ኢህአዴግ ሌላ አገር ያስተዳድራል እንዴ?

Written by  ኤልያስ
Rate this item
(0 votes)
  • ሕዝብ ቀልድ ሲተው ጥሩ ምልክት አይደለም

ባለፈው ሳምንት በወጣው አዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ ..ሚኒስትሩ የዩኒቨርስቲ ምሁራንን ክፉኛ ተቹ.. የሚለውን ዘገባ     አንብባችኋል? የፖለቲካ ፓርቲ መሪና የዩኒቨርስቲ መምህር የሆኑት ዶ/ር መራራ ጉዲና ለትችቱ መልስ የሰጡት በተረት ነበር - ጅራፍ ራሱ ገርፎ ራሱ ይጮሃል በማለት፡፡ የእኔ ትኩረት ግን በዋናው ትችት ላይ እንጂ በመልሱ ወይም በማስተባበያው ላይ አይደለም፡፡ የሲቪል ሚኒስቴር ሚኒስትሩ አቶ ጁነዲን ሳዶዩኒቨርስቲውና በምሁራኑ ላይ በሰነዘሩት ነቀፌታ ዩኒቨርስቲ ከኤኮኖሚውና ከማህበረሰቡ ተነጥሎ ብቻውን ደሴት ሆኖ ሊቀጥል አይችልም.. ብለዋል፡፡ በእርግጥ ሚኒስትሩ የተናገሩት ይሄን ብቻ አይደለም፡፡

ኧረ ገና ብዙ አለ፡፡ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ አስተዳደሩን ተቆጣጥሮ የያዘ የለውጥ ፀር የሆነ፣ ከፊውዳላዊ አስተሳሰብ ያልተላቀቀና በቡድናዊ አሠራር የተዋቀረ የምሁር ክምችት አለ ብለዋል - ሚኒስትሩ፡፡ የዩኒቨርስቲW ፕሮፌሰሮች ሸምድደው ፈተና ለመመለስ ነው የተማሩት ሲሉ ወቀሳ የሰነዘሩት ሚኒስትሩ፤ ዩኒቨርስቲãÒCN ለቴክኖሎጂ ዳተኛ ሆነዋል፤ እግራቸውን እየጐተቱ ነው ብለዋል፡፡ አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ እያንቀላፋ ነውም ይላሉ - ሚኒስትሩ ጁነዲን ሳዶ፡፡ የሚኒስትሩን ወቀሳ አንብቤ ስጨርስ በጥሞና ማሰብ ጀመርኩ፡፡ ይህችን አገር የሚመራት ማን ነው አልኩኝ - ለራሴ፡፡ ኢህአዴግ የሚል ምላሽ አገኘሁኝ - ከራሴ፡፡ አዎ 20 ዓመት ሙሉ ሲያስተዳድራት የቆየው ኢህአዴግ ነበር፡፡ ታዲያ እንዴት ድንገት ተነስቶ በራሱ ላይ ይሄን ሁሉ ነቀፋ ይሰነዝራል? ይሄን መመለስ የሚችለው ኢህአዴግ ብቻ ነው፡፡   
ለነገሩ ኢህአዴግ ሁሌ እንዲህ ያለች መላ ያውቅበታል፡፡ ድንገት ተነስቶ የነቀፋ ውርጅብኙን ሲያወርደው ግን የሌላ አገር መንግሥት እንጂ 20 ዓመት ኢትዮጵያን ያስተዳደረ ፈጽሞ አይመስልም፡፡ እኔማ አንዳንዴ ሌላ የሚመራው አገር ኖሮት ኢትዮጵያን በተጋባዥነት ወይም በፓርትታይም የሚያስተዳድራት ይመስለኛል፡፡ግራግብት የሚለኝ ደግሞ የት ከርሞ እየመጣ ነው ፊውዳል... ኪራይ ሰብሳቢ...ጥገኛ.. እያለ  የሚዘልፈን፡፡
እንግዲህ ዩኒቨርስቲውም ሆነ ምሁሩ እንዲህ ከተነቀፉ ኢህአዴግም አይቀርለትም ማለት ነው፡፡ ለምን ቢሉ. . . ላለፉት 20 ዓመታት ሌላ ገዢ ፓርቲ አናውቅማ - ከኢህአዴግ  ሌላ ለዚህም ይሆናል ዶ/ር መረራ የችግሩ ምንጭ ራሱ ኢህአዴግ ነው ያሉት፡፡
አለበለዚያ ደግሞ ..ተጋባዥ መንግሥት.. (ተጋባዥ ሌክቸረር ምናምን እንደሚሉት) ከሆነ በግልጽ ይንገረን፡፡ ዩኒቨርስቲውና ምሁራኑ እንዲህ እስኪሆኑ ኢህአዴግ የማንን ጐፈሬ እያበጠረ ነበር? በሌሎችም ጉዳዮች እንዲሁ ዓይነት ጥያቄ ስላለኝ ነው፡፡ አሁን ወደሌላ አጀንዳ ከመሄዳችን በፊት ከዚህ ቀደም የነገርኳችሁን ቀልድ ላስታውሳችሁ፡፡
ልጅ ወደ ት/ቤት ለመሄድ ደብተሩን ሸክፎ አባቱ ወዳሉበት በመሄድ 2 ብር እንዲሰጡት ይጠይቃል፡፡ በኑሮ ውድነቱ ናላቸው የዞረው አባት ..2 ብር? ለምን.. ሲሉ ቁጣ ባዘለ ቃና ይጠይቁታል - ልጃቸውን፡፡ ልጅም ገንዘቡን ለምን እንደፈለገው ሲያስረዳ ..ት/ቤት የሚታይ የአስማት ትርኢት ስላለ. . ... ይላል፡፡ አባት ልጃቸው በነገራቸው ነገር ከልክ በላይ ተገርመው ..እና 2 ብር የፈለከው አስማት ለማየት ነው.. አሉት ረጋ ብለው እያዩት፡፡ እርጋታቸው የጤና እንዳልሆነ የጠረጠረው ልጅም አንገቱን በአዎንታ ነቀነቀ፡፡
አባትም ..ይሄን ሁሉ ቤተሰብ በዚህች ደሞዝ ከማስተዳደር የበለጠ አስማት አለ እንዴ?.. አሉትና ድምፁን አጥፍቶ ወደ ት/ቤቱ ሄደ፡፡ ይህቺን ቀልድ የደገምኳት ባልተለመደ ሁኔታ የቀልድ ድርቅ መከሰቱን በመስማቴ ቀልድ የመፍጠር ተሰጥኦ አለን የሚሉ ወገኖችን ለመነሸጥ (inspire ለማድረግ) ነው፡፡ ሌላው ምክንያት ደግሞ ሰሞኑን አንዲት ከአሜሪካ ለእረፍት የመጣች ወዳጃችን አዲስ ቀልድ ንገሩኝ ብላን ዓይናችን ፈጥጦ ስለነበር ነው፡፡ እውነት ግን ለምን አዳዲስና ወቅታዊ ቀልዶች ከጆሯችን ራቁብን? የዚህ ዓይነት ቀልዶች የኑሮ ውድነቱ በተከሰተ ሰሞን እንሰማ እንደነበር ያስታወሰን አንድ ወዳጃችን፤ የኑሮ ወድነቱ የዕለት ተዕለት ህይወታችን ሲሆንና እየተላመድነው ስንመጣ ቀልድ መፍጠሩንም ተውነው በማለት ሊያስረዳን ሞከረ፡፡ ሌላኛው ጓደኛችን ደግሞ እንዲህ አለ ..አያችሁ አሁን ሁላችንም የምንኖረው እንደ እኚያ አባት በአስማት ነው. .  ስለዚህ የአስማቱን ዓይነት ቀልድ መፍጠር አንችልም.. የመጀመሪያውን አስተያየት የሰነዘረው ወዳጃችን ሌላ ሃሳብ አከለ ..ህዝብ ሲቀልድ ጥሩ ነው፤ ምሬቱንና ጭንቀቱን ያስተነፍስበታል.. በማለት፡፡ የአሜሪካዋ እንግዳችን ሃሳቡን በመደገፍ ማጠናከሪያ የሚመስል ነገር ተናገረች፡፡ ..ህዝቡ በኑሮ ውድነትና በሌሎች የተለያዩ ችግሮች ተወጥሮ እንደሌላው ጊዜ ከምሬቱ ውስጥ ቀልድ አለመፍጠሩ ጥሩ ምልክት አይደለም. . . በቀልድ እኮ በውስጡ ያመቀው ነገር ሁሉ ይወጣለታል.. እንግዲህ እነዚህ በወቅታዊው የቀልድ ድርቀት ዙሪያ የተሰነዘሩ አስተያየቶች ተራ ዜጎች የሰጡት መላ ምት እንጂ በሳይንስና በጥናት የተደገፉ አይደሉም፡፡ በተለይ መንግሥትና የፖለቲካ ፓርቲዎች ግን በፖለቲካው፣ በኤኮኖሚውና በሌሎች ማህበራዊ ጉዳዮች ላይ በየጊዜው በህዝቡ የሚፈጠሩ ቀልዶችን አሰባስበው በባለሙያ ቢያስጠኑ ብዙ ሊጠቀሙ እንደሚችሉ አምናለሁ፡፡ ህዝቡ የፖለቲካ ቀውስ ሲፈጠር፣ የተቃዋሚ አመራሮች ወህኒ ቤት ሲገቡ፣ ምርጫ ሲካሄድ፣ ፖለቲከኞች ቃል የገቡለትን ሲክዱት፣ በዋጋ ንረት በቅጡ መኖር ሲያቅተው. . . ሌላ ምንም ማድረግ ባይችል እንኳ ራሱ ምርጥ ቀልድ ፈጥሮ፣ ስቆና ሌላውንም አስቆ ከችግሩ ወይም ከችጋሩ ጋር ይላመዳል፡፡ እናላችሁ ያቺ የአሜሪካዋ እንግዳችን የቀልድ ያለህ እንዳለች አንድም አዲስ ቀልድ ሳንነግራት የዋጋ ጭማሪ የተደረጉባቸውን ምግቦችና መጠጦች ዝርዝር ብቻ ስትሰማ ሰንብታ ..የማርና ወተት አገር.. እያሉ ወደ¸ያቆላምጧት አሜሪካ ተመልሳ ሄደች፡፡
የሚገርማችሁ ታዲያ እንግዳችንን ኤርፖርት ሸኝቼ ወደ ቢሮዬ ስመለስ አንድ ጋዜጠኛ ወዳጄ ጮማ የሆነ ቀልድ ነገረኝና ወደ ቦሌ አየር መንገድ ልመለስ ምንም አልቀረኝም ነበር፡፡ ሆኖም አውሮፕላኑ ተነስቶ እንደሚሆን ገመትኩና ተስፋ ቆርጬ የቀልዱን ጮማ ራሴው አጣጥመው ገባሁ፡፡ ህዝብ መቀለድ ሲተው ጥሩ ምልክት አይደለም በሚል ከዳያስፖራዋ የሰማሁት አስተያየት ከንክኖኝ ነበርና አዲስ ቀልድ መስማቴ ትንሽ የመረጋጋት ስሜት እንደፈጠረብኝ አልሸሽጋችሁም፡፡ እንዴ ለምን አልረጋጋም? በአንድ በኩል የኑሮ ውድነት፣ በዚያ ላይ እንደ ድሮ ሳቅ የለ (በቀልድ ድርቀት የተነሳ). . . እልም ያለ ድብርት አይደለም እንዴ?
እውነት እኮ የፓርላማውም ድራማ (ይቅርታ ቀልድ ለማለት ነው) ቀረ እኮ የፓርላማ መቀመጫዎች በሙሉ በኢህአዴግ ቁጥጥር ስር ከዋሉ ይኸው ሁለት ዓመት ገደማ መሆኑ አይደል ሁለት ዓመት ያለ ቀልድ አይከብድም? ከምር ነው የምላችሁ. . . ተቃዋሚዎች ለፓርላማው ለዛና ውበት አጐናጽፈውት እንደነበር የገባኝ ከምክር ቤት ከወጡ በኋላ ነው ..ሰው ካልሄደና ካልሞተ አይመሰገንም.. የሚል ተረት አለ ልበል. . . ባይኖርም እንኳ የግድ መፈጠር አለበት፡፡ የተረት ድርቅስ ፈጽሞ አይመታንም! እኔ የምለው በተረት ብዛት ከዓለም አንደኛ ነን አይደል? በቀልድም ይሄን የመሪነት ደረጃ ማስጠበቅ አለብን የሚል ጠንካራ አቋም አለኝ፡፡ እናንተስ?
ፓርላማውን ሳስታውስ ምን ትዝ እንደሚለኝ ታውቃላችሁ? yጠ/ሚኒስትሩÂ የአቶ ቡልቻ ክርክር፣ yጠ/ሚኒስትሩÂ የአቶ ልደቱ በተረብ የተሳለ ሙግት ወዘተ፡፡ ያ ደግ ዘመን ግን ተመልሶ የሚመጣ አልመሰለኝም፡፡ (ተስፋ ቆረጥኩባችሁ እንዴ?) አሁን ፓርላማውን የሞሉት የኢህአዴግ አባላት ደግሞ ወይ የተለየ ሃሳብ አያመጡ፣ ወይ ተረት አይችሉ. . . ወይ ደግሞ በተረብ አይሸነቋቆጡ. . . ደረቅ ፖለቲካና የተጠና የሚመስል ንግግር ድጋፍ፣ አቋም፣ መርህ. . . ምናምን ብቻ ነው የሚችሉት፡፡ ራሳቸውን ተቃዋሚዎቹን ሳይቀር ያስፈግጉ የነበሩት ጠ/ሚኒስትሩ እንኳን ቀልድና ተረብ እርም አሉ እኮ! ምን ያድርጉ. . . የኢህአዴግ አባላት ለቀልድና ለተረብ አይመቹማ! እርግጠኛ ነኝ ጠ/ሚኒስትሩ ከአሁኑ ፓርላማና ከቀድሞው (ተቃዋሚዎች የነበሩበት) የትኛው እንደሚሻል ቢጠየቁ ..አንዳንዴ ስለሚገግሙ እንጂ ተቃዋሚዎች የነበሩበት ይሻለኝ ነበር.. የሚል ምላሽ ይሰጣሉ፡፡ ለምን መሰላችሁ. . . እንኳን እሳቸው አገር በማስተዳደርና በፖለቲካ ሥራዎች የተጠመዱት ቀርቶ እኛም እንኳ ሳቅና ጨዋታ ይናፍቀናል፡፡ እኔ የምለው ሌላ ሌላውን ስቀባጥር ጋዜጠኛ ወዳጄ የነገረኝን ጮማ የሆነች ቀልድ ሳልነግራችሁ ረሳሁት አይደል እንግዲህ አደራ ይህችን በስንት ፀሎትና እግዚኦታ የተገኘች ቀልድ በጥሞና ስሙኝ፡፡
የቀድሞው የፓርላማ አፈ ጉባኤ አዲሱን አፈ ጉባኤ ተቀብለው ኃላፊነታቸውን ሲያስረክቡ ነው አሉ፡፡ የቀድሞው አፈ ጉባኤ ስለሥራው ሁኔታ ለምሳሌ ለም/ቤት አባላት ስለተመደበው የንግግር ሰዓት፣ ስለ ምክር ቤቱ ደንብና ሥርዓት ማብራሪያ ሰጥተው ካጠናቀቁ በኋላ የፓርላማውን መዶሻ ለአዲሱ አፈ ጉባኤ ያስረክባሉ፡፡ አዲሱ አፈ ጉባኤ መዶሻውን እያገላበጡ ሲመለከቱ ቆዩና ጥያቄ አቀረቡ፡፡ ..መንቀያው የታለ?.. ወደ መዶሻው እያዩ፡፡ የቀድሞ አፈ ጉባኤም ፈጠን ብለው ..ነቅለን ጨርሰናቸዋል. . . የቀረው አንድ ብቻ ነው እሱንም በዚህ ቀጥቅጠው.. አሏቸው አሉ፡፡ (ነቅለን ጨርሰናቸዋል ያሉት ተቃዋሚዎችን መሆን አለበት) አዲሱ አፈ ጉባኤ የቀድሞው አፈ ጉባኤ ለሠሩላቸው ትልቅ ውለታ (ነቅለው ስለ=rsù§cW) ከልባቸው አመስግነው እሳቸውም ጊዜው ሲደርስ ውለታ እንደሚመልሱ ቃል ገብተውላቸው ተሰነበባቱ፡፡ አንዳንድ አክራሪ ኢህአዴጐች በዚህች ቀልድ በስጨትጨት ሊሉ ይችላሉ፡፡ ግን አንፈርድባቸውም፡፡ ቀልድ እንደ ስኳርና ዘይት ጠፍቶ እንዴት መከራችንን እንደበላን ስለማያውቁ ነው፡፡ እኔ እንደውም ኢህአዴግን ብሆን ምን አደርግ ነበር መሰላችሁ. . . ቀልድ ፈጣሪዎችን በማህበር ተደራጁ እልና በወቅታዊ የፖለቲካና ኤኮኖ ጉዳዮች ላይ ቀልድ እንዲፈጥሩና ለህዝቡ እንዲረጩ (እንደ ስንዴው ማለት ነው) አደርግ ነበር፡፡ ለምን ቢባል. . . የተቆጣውን፣ የተከፋውን፣ የተማረረውን፣ ተስፋ የቆረጠውን፣ ያኮረፈውን ወዘተ ከታመቀና ከታጨቀ መራር ስሜቱ በቀልድ ዘና እንዲል፡፡. . . ይሄ ነገር ግሩም የህዝብ አስተዳደርና የአገር አመራር ብልሃት አይመስላችሁም?
በነገራችን ላይ ስፖንሰር አፈላልጌ የ..ቀልድ ባንክ.. የመክፈት ሃሳብ አለኝና በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ቀልድ አለን የምትሉ ቀልዶቻችሁን እንድታቀርቡ ተጋብዛችኋል፡፡
ማሳሰቢያ- በኢህአዴግ ላይ የተቀለዱ ቀልዶችን አልቀበልም (ከራሱ ከኢህአዴግም ቢሆንም) በሉ የቀልድ ቆሌን መለማመኑን አትዘንጉ! የነገ ሰው YblN       

 

Read 4394 times Last modified on Saturday, 20 August 2011 10:45