Administrator

Administrator

በአዲስ አበባ ወሎ ሰፈር ጎርጎሪዮስ አደባባይ ፊት ለፊት የተገነባው ባለ 15 ፎቅ ዓለማቀፍ ሆቴል፤ የፊታችን ቅዳሜ  የካቲት 23 ቀን 2016 ዓ.ም እንደሚመረቅ ተገለጸ፡፡
ለግንባታ 7 ዓመት የፈጀውና የኩራዝ ወንዝ ኃ.የተ.የግ. ድርጅት አጠቃላይ ፕሮጀክት አንደኛው እህት ኩባንያው ነው የተባለው ሽታዬ ስዊት ሆቴል፤ አባት አርበኞች፣ የመንግሥት ባለሥልጣናትና አምባሳደሮች በተገኙበት ይመረቃል ነው የተባለው፡፡
በ600 ካ.ሜ ቦታ ላይ ያረፈው ሆቴሉ G†15 ከአንድ ቤዝመንት ጋር ያለው ሲሆን፤ በቂ የመኪና ማቆምያ ቦታም ያካተተ መሆኑ ተጠቁሟል፡፡
ሆቴሉ የራሳቸው ማብሰያ ክፍሎች ያላቸው ሰፋፊ ምቹና ዘመኑ ያፈራቸውን መገልገያዎች የያዙ መኝታ ክፍሎች ያሉት ሲሆን፤ ለየት የሚያደርገውም የፔንት ሃውስ ክፍል ምርጫ ያለው ነው ተብሏል፡፡
የባህል ምግብ አዳራሽ፣ የመዋኛ ሥፍራና የሰርግ ስብሰባ አዳራሾች ያካተተው ሽታዬ ስዊት ሆቴል፤ ከ200 በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የሥራ ዕድል እንደሚፈጥር ተነግሯል፡፡
በሆቴሉ የምረቃ ሥነስርዓት  ላይ ለአባት አርበኞች ምስጋናና ዕውቅና እንደሚሰጥ ታውቋል፡፡

አንድ ንጉሥ አንድ ብልህ አጫዋች ነበራቸው። በየጊዜው ከሚመክራቸው ምክር መካከል ሰሞኑን የነገራቸውን ለመቀበል ከብዷቸዋል። ሰሞኑን የመከራቸው “ከወዳጆችዎ ይልቅ፣ ስለርስዎ ድክመት ዕውነቱን የሚነግሩዎ ጠላቶችዎ ናቸውና አዳምጧቸው” የሚል ነበር። ንጉሡ አላመኑበትም። ስለዚህ ለማረጋገጥ መዘዋወር ጀመሩ።
ንጉሡ በጣም የሚፈሩና አይበገሬ ነኝ የሚሉ ናቸው። በሄዱበት ቦታ ሁሉ የሚያገኟቸውን መኳንንቶች “እስቲ ስለ እኔ ጉድለት ንገሩኝ?” ይሉና ይጠይቃሉ።
“ንጉሥ ሆይ! እርስዎ ላይ እንዴት አይነት ሰው ነው ጉድለት ሊያገኝ የሚችለው። ደግሞ እርስዎ ምን ይወጣልዎታል!” ይሏቸዋል።
ቀጥለው ወደ ሠራዊታቸው ይሄዱና፤
“ምን እንከን አለብኝ? እስቲ ስለራሴ ንገሩኝ?” ይላሉ።
ከሠራዊታቸው ታማኙ ባለሟል ብድግ ብሎ፣
“ንጉሥ ሆይ! እርስዎ ከቁመናዎ ጀምሮ፣ ለጀግንነትዎ፣ ለዕውቀትዎ፣ ለዓለም ተደማጭነትዎ ምን የሚቀነስ የሚወጣልዎ ነገር አለብዎ!” ይላቸዋል። እንዲህ ከርመው አንድ ቀን በአጋጣሚ ከጠላቶቻቸው ጋር በሚሲዮን ይቀመጣሉ። አጠገባቸው የተቀመጠው ቀንደኛው ባላንጣቸው ቀስ ብሎ፤
“ስሙ ንጉሥ፤ ሲናገሩ አፍዎት መጥፎ ጠረን ያመጣል” ይላቸዋል።
ንጉሱ ይናደዳሉ። “እንዴት እስከዛሬ አንድ ወዳጄ ይሄን አልነገረኝም? እንዲህ በአደባባይ እንድጋለጥ ያደረጉኝ ወዳጆቼ ናቸው! ቆይ ግድ የለም! ባልሰራላቸው!” ይላሉ በሆዳቸው። ስብሰባውን እንደጨረሱ ሲገሰግሱ ወደ ቤተ-መንግስታቸው ይሄዱና ንግስቲቱን አስጠርተው፤
“አፌ ጠረን እንዳለው እስከዛሬ ያልነገርሽኝ ለምንድን ነው?” ሲሉ በቁጣ ጠየቁ። ንግስቲቱም፤ በንፁህ ልቦናና በቀናነት፤
“ንጉሥ ሆይ! የሁሉም ንጉስ አፍ እንደ እርስዎ አፍ አይነት ሽታ ያለው መስሎኝ ነው” ሲሉ መለሱ።
ንጉሡም እጅግ የቅርባቸው የሆነችው የገዛ ባለቤታቸው ጉድለታቸውን ሳትነግራቸው፤ ሩቅ የሚኖሩት ጠላቶቻቸው ማወቃቸውን ልብ ሲሉ፤ ያ አስተዋይ አጫዋቻቸው የነገራቸው ቁም ነገር እውነት መሆኑን ተገነዘቡ።
***
ማንኛውም መሪ፣ በማንኛውም ደረጃ ያለ ቢሆን፤ አንድ ሀቅ ልብ ማለት አለበት። ራሱን ብቻ የሚያዳምጥ መሪ፤ ከወዳጆቹ የሚጠብቀው ምንጊዜም ምስጋናን ስለሆነ ጉድለቶቹን የማየትም የመስማትም እድል አያገኝም። ወገኖቹም አይደፍሩትም። እሱም ራሱን አይደፍርም። ይህ ሁሉ የሚሆነው ሁሌ በሰላም ጊዜ በሆነ ባልከፋ። ሁኔታዎች በውጥረትና በችግር በሚሞሉበት ሰዓት ሲመጣ ነው አደጋው። ምክንያቱም የሁኔታዎች መወሳሰብን ተከትለው ሰዎችም ይለወጣሉና ነው። ችግሩ ግን በዚህ ብቻ አያቆምም። መሪውን መስለውና አክለው ማደግ ሲመኙ የቆዩ ባለሟሎቹና ተከታዮቹ አለማዳመጥ ሰናይ ስነምግባር እየመሰላቸው እነሱም እኩዮቻቸው የሚሉትን አልሰማ ይላሉ። በዚህ ምክንያት ካለመደማመጥ አልፎ፣ የሚፈጠረውን ጩኸት ለመገደብ ካለመቻል ደረጃ ይደረሳል። በየመንበራቸው እንደተቀመጡ በየራሳቸው ደሴት ውስጥ ይዋጣሉ። ውለው አድረውም የታችኞቹ በላይኞቹ ላይ ቅያሜን ያጠነክራሉ። ቀስ በቀስ በተለይ የመረረ የመከፋት ስሜት ውስጥ በገቡ ጊዜ፤ እንደ ሮማው ካሽየስ፣ ባለቃው ላይ ማሴርን፣ ራስን እንደማዳን ሲቆጥሩ፤ ከላይ ወደ ታች ይወርዱ የነበሩ ትእዛዛት ወደ ጎንም፣ ወደ ይም እንዲያመሩ ሲፈለግ፣ ለወትሮው የአለቃውን ድክመት ሁሉ የእኔ ነው እያለ አሜን ይል የነበረው ሁሉ፣ ድርሻ ድርሻችንን እንውሰድ በሚል፤ ሌላውን ማነሳሳትና ብሶቱን ሌላው ላይ ማጋበቱን ይያያዘዋል። ይሄኔ እንደ ሮማው ብሩተስ ያለው በትዕግስት የሚያገኘውን ስልጣን ቄሳርን በማስወገድ ሊፈጽመው እንዲሻ ሲተነኮስ፣ ወይም ሲወነባበድ፣ ነገር የተገላቢጦሽ ይሆናል። ቄሳር በመሞቻው “አንተም ብሩተስ?” ያለበት ሰዓት የሚመጣ እንግዲህ ያኔ ነው።በተለይ ስልጣንን በዲሞክራሲያዊ መንገድ የመጋራት ልምድ በሌለበት እንደ እኛ ባለው አገር ብርቱ ጥንቃቄ የሚጠይቀው፣ በወንበሩ ዙሪያ አስፈላጊ ትዕግስትና መቻቻል አለመኖር ነው። መተማመን እንዲኖር ሀሳብን መግለጽ ያስፈልጋል። ለዚህ ደግሞ ነጻነቱ አስፈላጊ ነው። ሀሳብን የመግለጽ ነጻነት በሀቅና ከልብ ካልታመነበት፤ “ለብ ለብ ዲሞክራሲ” “ገባ ያለው ዲሞክራሲ” እና “ስፔሻል ዲሞክራሲ” እያልን እንድንከፋፍል ልንገደድ ነው። “አካሄዱ ፍጻሜውን ያሳያል” እንዳንል፤ አባይን ጭብጦዬን ከቀማኝ ወዲህ አላምነውም፤ የሚሉ ወገኖች ይሟገቱናል። የለም “ግቡ አካሄድን ያሳያል” - የትም ፍጪው ዱቄቱን አምጭው ነው ነገሩ- ለሚሉት ደግሞ ካልታዘልኩ አላምንም፣ ስንቱ ሥልጣን ላይ ከወጣ በኋላ አይደል ወይ መላው የጠፋው የሚሉ ይኖራሉ። ሁኔታዎችን አጣጥመን መጓዝ የሚያስፈልገን ለዚህ ነው። የሚያግባባንን መንገድ ከንፍቀ-ክበባችን ውጭም ቢሆን ማዳመጥ፣ ከባላንጣዎቻችንም ቢሆን መማር፣ ሁሌ ከመተላለፍ አንዳንዴ “ምን ይሆን?” ብሎ ለሌሎች ሀሳብ ትንሽ እድሜ መለገስ፤ ቀስ በቀስ ግትርነታችንን ሊያረግበው ይችላል።
አለንልህ ያልነውንና በእርሱም ትከሻ ለስልጣን የበቃንለትን፣ ከቀን በኋላ ከእርሱ እጅ የማንወጣውን ህዝብ ማዳመጥ እንደሚኖርብን እንድናስብም ፋታ ይኖረናል።
ስለሌላው ውሸት እንጂ እውነት በተናገርን ቁጥር፣ ስለሌላው ድክመት እንጂ አንድ አንኳር ጥንካሬ እንኳን ባነሳን ቁጥር፣ እኛ ብቻ ሀቀኛ፣ እኛ ብቻ ጠንካራ እያልን እንገበዛለን። ይህ ደግሞ ስለራሳችን እውነተኛ ገጽታ እናዳናውቅ ያደርገናል። የእኛኑ ቅኝት የሚያዳምጡ ወገኖቻችንና ደጋፊዎቻችን እውነተኛ ይዘትና ቅርጻችንን አይነግሩንም።
ስለዚህ ከእኛ ውጭ የማዳመጥ ባህል ማዳበር ደግ ነገር ነው- ከ”ጥላትም” ሰፈር ቢሆን። አበው “ክፋትህና ውሸትህ ሲጠፋብህ፤ ጠላትህን አስታውሰኝ በለው” የሚሉት ይሄንኑ ሊያስገነዝቡን ነው፡፡

ኢትዮጵያ የአገራቱ ስምምነት እንቅልፍ እንደማይነሳት ገልፃለች
- በሶማሊያ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች አደጋ ተጋርጦባቸዋል ተባለ

ሶማሊያ በቅርቡ ከቱርክ ጋር የፈፀመችውና የሶማሊያ ፓርላማ ሰሞኑን  ያጸደቀው ወታደራዊ ስምምነት፣ ለአጎራባች አገራት በተለይም ለኢትዮጵያ ትልቅ ስጋት እንደሚጋርጥ ምሁራን ገለፁ። በሁለቱ አገራት መካከል ስምምነቱ የተፈረመው ኢትዮጵያ ከሶማሊላንድ ጋር የመግባቢያ ሰነድ መፈራረሟን ተከትሎ፣ ከሶማሊያ ጋር ውዝግብ ውስጥ በገባች  ማግስት መሆኑ ደግሞ ስጋቱን የባሰ ያደርገዋል  ተብሏል።
ለ10 ዓመታት እንደሚዘልቅ በተነገረለት በዚህ ወታደራዊ ስምምነት፣ ቱርክ ለሶማሊያ የባህር ሃይል ሥልጠናና የቁሳቁስ ድጋፍ እንደምታደርግ ተዘግቧል።
የሶማሊያው ፕሬዚዳንት ሀሰን ሼክ መሀመድ የተፈረመውን ስምምነት አስመልክቶ በሰጡት መግለጫ፤ በሚቀጥሉት አስር ዓመታት ቁጥራቸው በውል ያልተገለጹ የቱርክ የባሕር ኃይል መርከቦችና ወታደሮች በሶማሊያ የባሕር ጠረፍ ውስጥ ሆነው ለአገሪቱ ድጋፍ የሚያደርጉ ሲሆን፤ የሶማሊያ ባሕር ኃይልን መልሶ የማደራጀት ሥራም እንደሚያከናውኑ ጠቁመዋል።
 “የቱርክ ወንድሞቻችን በስምምነቱ መሰረት፣ ባህሮቻችንን ለ10 አመታት ይጠብቃሉ፤ ከ10 አመት በኋላ ጠንካራ የባህር ሃይል እንፈጥራለን” ብለዋል-ፕሬዚዳንቱ።
የስምምነቱ ዝርዝር ይፋ ባይደረግም ቱርክ የሶማሊያን ባህል ሃይል በማሰልጠን የምታስታጥቅ ሲሆን የሶማሊያን የባህር ጠረፍም ለመጠበቅም የራሷን ባህር ሃይል በአካባቢው ታሰማራለች ተብሏል። ስምምነት   በቅርቡ ከአገሪቱ ጋር ውዝግብ ለገባችው ኢትዮጵያ ትልቅ ስጋት እንደሚፈጥር የፖለቲካ ምሁራን ይገልጻሉ። የፖለቲካል ሳይንስ መምህሩ ዶክተር አንተነህ ተስፋዬ ለአዲስ አድማስ በሰጡት አስተያየት፤ ኢትዮጵያ ከተለያዩ ወገኖች ጋር ያለባትን  ውስጣዊ ችግሮች ለመፍታት ዕድል ባላገኘችበት በዚህ ወቅት   ሌላ ግጭት ሊቀሰቅሱ የሚችሉ ጉዳዮች ውስጥ መግባቷ ኃላፊነት የጎደለው ተግባር ነው ሲሉ ተችተዋል።  በተለይ  በሁለቱ አገራት መካከል ግጭት ሊፈጠር ይችላል የሚል ስጋት ባጠላበት በአሁኑ ወቅት፣  አገሪቱ ከቱርክ መንግስት ጋር የፈጸመችው ወታደራዊ ስምምነት ስጋቱን ይበልጥ የሚያባባስ እንደሚያደርገው ተናግረዋል።
ለኢትዮጵያ የባሕር ጠረፍ ያስገኛል የተባለው የመግባቢያ ሠነድ መፈረሙን ተከትሎ፣ በሶማሊያና በሶማሊላንድ በሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ላይ ከፍተኛ የደህንነት ስጋት እንደተጋረጠባቸው የጠቆሙት ዶ/ር አንተነህ፤    በተለይም  የሶማሊላንድ  ሁለተኛ  ትልቋ   ከተማ በሆነችው ቦርኦ በሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን ላይ   የአካል ጉዳት ለማድረስ፣ ንብረት ለመዝረፍና፣ ቤታቸውን በእሳት ለማቃጠል ሙከራ ተደርጓል  ብለዋል። በሶማሊኛ ቋንቋ “ኢትዮጵያዊ ላይ በተገኘበት እርምጃ ይወሰድበት” የሚል አደገኛ በራሪ ጽሑፍ በሐርጌሳ ከተማ እየተበተነ መሆኑን ተናግረዋል-ወቅቱ  በሶማሊላንድ ለሚገኙ ወደ 50 ሺ የሚጠጉ  ኢትዮጵያውያን እጅግ አደገኛ መሆኑን በመግለፅ።ይህ በእንዲህ እያለ፣  የሶማሌላንድ ፕሬዝዳንት ሙሴ ቢሂ፣ ሶማሊላንድ ከኢትዮጵያ ጋር የተፈራረመችው የባሕር በር የመግባቢያ ስምምነት ተፈጻሚ መኾኑ እንደማይቀር ለአገራቸው መገናኛ ብዙሃን ተናግረዋል። “ሶማሊያ ቱርክን ወይም ግብጽን አጋሯ አድርጋ ብታመጣም፣ ስምምነቱን ተግባራዊ ከመሆን የሚያግደው ነገር የለም” ብለዋል ፕሬዚዳንቱ።
ሰሞኑን በወቅታዊ ጉዳዮች ዙሪያ መግለጫ የሰጡት የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር መለሰ ዓለም፤ “ሶማሊያና ቱርክ የተፈራረሙት ወታደራዊ ስምምነት ኢትዮጵያ ከሶማሊላንድ ጋር ያደረገችውን መግባቢያ ስምምት ሊጎዳ አይችልም” ብለዋል።
“ሶማሊያም ሆነች ቱርክ ሉአላዊ አገር ናቸው፤ የፈለጉትን ስምምነት ከየትኛውም አገር ጋር የማድረግ መብት አላቸው” ያሉት ቃል አቀባዩ፤ “ኢትዮጵያ ከቱርክ ጋር ጥሩ የሚባል ግንኙነት አላት፤ ይህ ወታደራዊ ስምምነት እንቅልፍ አይነሳንም” ብለዋል።

ወመዘክር አዲስ ያስገነባውን ህንፃ የፊታችን ቅዳሜ ያስመርቃል

•  የተቋሙ የ80ኛ ዓመት ክብረ በዓልም ይከበራል ተብሏል

የኢትዮጵያ ቤተ-መዛግብትና ቤተ-መጻሕፍት አገልግሎት ያስገነባውን ባለ 13 ወለል የቤተመዛግብት ሕንጻ የፊታችን ቅዳሜ የካቲት 16 ቀን 2016 ዓ.ም እንደሚያስመርቅ ተገለጸ።

ከህንፃው ምርቃት ጎን ለጎንም ተቋሙ የተመሰረትበት የ80ኛ ዓመት ክብረ በዓልም በአንድ ላይ ይከበራል ተብሏል፡፡

እነዚህን ሁነቶች ምክንያት በማድረግ በተቋሙ ተመዝግበውና ተጠብቀው የሚገኙና በሌሎች ተባባሪ ተቋማት እጅ የሚገኙ የጽሑፍ ቅርሶች አውደርዕይና ሌሎች ተቋሙን ሊያስተዋውቁ የሚችሉ ክንውኖች እንደሚካሄዱ ለማወቅ ተችሏል፡፡

ዝግጅቶቹ ከእሁድ የካቲት 17 ቀን 2016 ዓ.ም ጀምሮ ለእይታ ክፍት እንደሚሆኑ ተነግሯል፡፡

አንጋፋው ድምፃዊ ጌታቸው ካሳ ህልፈተ ህይወት የተሰማንን ጥልቅ ሀዘን እየገለፅን ለወዳጆቹ እና ቤተሰቦቹ እንዲሁም አድናቂዎቹ መፅናናትን እንመኛለን።

Tuesday, 20 February 2024 00:00

"ዶቃ" አሸነፈ !!

በቅድስት ይልማ ተዘጋጅቶ በማህደር አሰፋ ፕሮዲዩስ የተደረገው ዶቃ ልብ አንጠልጣይ ፊልም "Los Angeles”ከተማ ውስጥ በተዘጋጀው በፓን አፍሪካን ፊልም ፌስቲቫል ላይ ተሳትፎ በ" Audience Choice Awards” አሸናፊ መሆን ችሏል::

በአፍሪካዊያን የጥበብ ስራዎች ላይ ትኩረትን ያደረገው ፓን አፍሪካ ፊልም ፌስቲቫል ከ32 ዓመታት በፊት የተመሰረተ ነው።

ቅድስት ይልማ ከአሁን ቀደም "ረቡኒ" ፣ "ታዛ" ፊልሞችንና "እረኛዬ" ድራማን ጨምሮ ከአስር በላይ ስራዎችን ለተደራሲያን ማቅረቧ ይታወሳል::


• በአማራ ክልል ትራክተር እንጂ ጥይት አያስፈልግም

• ይቅርታም ብለን ካሣም ከፍለን ቢሆን፣ እንታረቅ እንስማማ

• በምርጫ የሰጣችሁንን ሥልጣን በምርጫ ውሰዱት

-ሪፖርታዥ-

በትላንትናው ዕለት ከአማራ ክልል ተወካዮች ጋር በጽ/ቤታቸው የተወያዩት ጠ/ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ፤ በአማራና በኦሮምያ ክልል ነፍጥ አንግበው ከሚንቀሳቀሱ ወገኖች ጋር በጠረጴዛ ዙሪያ በመወያየት ሰላም ለማምጣት እንደሚፈልጉ ተናገሩ፡፡

አዲሱ ምክትል ጠ/ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህና የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳደር አረጋ ከበደ በተገኙበት በተካሄደው በዚህ ውይይት ላይ ጠ/ሚኒስትር ዐቢይ፣ ለሃይማኖት መሪዎችና ለአገር ሽማግሌዎች ባስተላለፉት ጥሪ፤ ”እባካችሁ በሰላማዊ መንገድ ገብቶ መነጋገር የሚፈልግ ሰው ካለ --ከየሰፈሩ አምጡ አወያዩና ይቅርታም ብለን ካሳም ካስፈለገ ካሳ ከፍለን እንታረቅ፤ እንስማማ፡፡” ብለዋል፡፡

“ሰው መግደልና መዝረፍ የትም አያደርስም፤ መክራችሁ የሚመለስ ሰው ካለ በመመለስ እርዱን፤እኛ የምንፈልገው ሰላም ነው” ሲሉ ጠ/ሚኒስትሩ ለአማራ ክልል ተወካዮች መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡

ከአማራ ክልል የተለያዩ ዞኖች ተወክለው በውይይቱ ላይ የታደሙ ተሳታፊዎች በክልሉ የሰላምና ጸጥታ ጉዳይ፣ በመሰረተ ልማቶች ችግር፣ በግብርና ግብአቶች አለመሟላት፣ በመልካም አስተዳደር እጦትና በሌሎችም ዙሪያ ጥያቄዎችና አስተያየቶችን ሰንዝረዋል፡፡

ከተወካዮቹ ለተሰነዘሩት ጥያቄዎችና አስተያየቶች ምላሽና ማብራሪያ የሰጡት ጠ/ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ፤ ስለ ታጣቂዎች፣ ስለ አማራ ተወላጆች የሥልጣን ድርሻ፣ ስለ ሃይማኖትና መንግስት ሚና፣ ስለ አንድነት ቤተ መንግሥት ፒኮክ ጉዳይ፣ ስለ ልማትና ሌሎች ሰፊ ጉዳዮች ተናግረዋል፡፡

የአማራ ተወላጆች ባለፉት 5 ዓመታት በአዲስ አበባ ላይ ያገኙት የሥልጣን ድርሻ ባለፉት 30 ዓመታት ኖሯቸው እንደማያውቅ የገለጹት ጠ/ሚኒስትሩ፤ ከለውጡ በኋላ የትኛውም ሥልጣን ለሁሉም ክፍት መሆኑን ተናግረዋል፡፡

“ድሮ የአዲስ አበባ የሥልጣን ድርሻን በተመለከተ 25 ፐርሰንት ለኦህዴድ፣ 25 ፐርሰንት ለብአዴን፣ 25 ፐርሰንት ለህወኃት እና 25 ፐርሰንት ለደህዴን ነበር” ያሉት ጠ/ሚኒስትሩ፤ የፈለገ ቢያብጥ በአዲስ አበባ ላይ የአማራ የሥልጣን ድርሻ 25 ፐርሰንት ብቻ እንደነበር አስታውሰዋል፡፡

“ዛሬ ግን ካላጋነንኩት አማራ በአዲስ አበባ ላይ ከ33–35 ፐርሰንት የሥልጣን ድርሻ አለው” ብለዋል፡፡

ከምክትል ጠ/ሚኒስትር ጀምሮ ደህንነት፣ መከላከያ፣ ውጭ ጉዳይ፣ አየር መንገድና ብዙ ተቋማት በአማራ ተወላጆች ሥልጣን ሥር መሆናቸውንም ጠ/ሚኒስትሩ አብራርተዋል፡፡

የመንግሥት ሥልጣንን አስመልክቶ ያብራሩት ጠ/ሚኒስትሩ፤ “ሥልጣን በምርጫ ነው የሰጣችሁን፤ ስትፈልጉ በምርጫ ውሰዱት፤ ከኛ የተሻለ ካገኛችሁ ምረጡ፤ደሞ ታዩታላችሁ በምርጫ ህዝብ ሲወስን እንዴት እንደምናከብር፤ ጊዜው ሲመጣ ታዩታላችሁ” ብለዋል፡፡

ሥልጣን በአፈሙዝ ግን በፍጹም አይሞከርም ያሉት ጠ/ሚኒስትሩ ፤ “እኛ ወታደሮች ነን፤ የአድዋ አርበኞች ልጆች ነን፤ ማንም በጉልበት ሊያሸማቅቀን አይችልም” ሲሉ ተናግረዋል፡፡



በአማራና ኦሮምያ ክልል ነፍጥ አንግበው የሚንቀሳቀሱ ወገኖችን በተመለከተ ጠ/ሚኒስትሩ ሲናገሩ፤ “የኛ ፍላጎት በአማራ ክልል ያለውም ሸኔ በኦሮምያ ያለውም ሸኔ ህዝብ ከማገድ፣ ከማገት፣ ከመግደል፣ ከመጥለፍና ከመዝረፍ ወጥቶ በሰላማዊ መንገድ ተነጋግሮ፣ ትጥቁን አስቀምጦ፣ ምርጫ ተወዳድሮ በሃሳብ አሸንፎ፣ እነሱ እዚህ መጥተው (ሥልጣን ላይ) እኛ እዚያ ብንቀመጥ ምንም ችግር የለብንም፡፡” ብለዋል፡፡

በአማራ ክልል ጥይት አያስፈልግም፤ ትራክተር ነው የሚያስፈልገው ያሉት ጠ/ሚኒስትር ዐቢይ፤ እኛ ከናንተ ጋር በፍቅር ብቻ ነው መኖር የምንፈልገው፤ ከዚህ የተለየ አጀንዳ የለንም ብለዋል፡፡

ጠ/ሚኒስትሩ ከአማራ ክልል የተለያዩ ዞኖች ከተወከሉ ተሳታፊዎች ጋር ያደረጉትን ውይይት ሲቋጩ፤ “በትብብር እንሥራ፤ በምክክር እንስራ፤ አንናናቅ፤ እንተባበር፤ የሚሻለው እሱ ነው፤ከዚያ ውጭ ያለው ሃሳብ ጥፋት ነው፡፡” የሚል መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡

የቴሌግራም ቻናልችንን በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…
https://t.me/AdissAdmas

87ኛውን የካቲት 12 የሰማዕታት መታሰቢያ ቀንን በማስመልከት በሰማእታት ሀዉልት የአበባ ጉንጉን አኑረናል።
ዘላለማዊ ክብር ለጀግኖች ሰማእታት!
የ87ኛው የየካቲት 12 የሰማዕታት መታሰቢያ ቀንን ለማሰብ ነው የአበባ ጉንጉን ያኖሩት።
ከንቲባ አዳነች በዚህ ወቅት ባደረጉት ንግግር፤ኢትዮጵያ የዛሬ መልክና ቅርፅ የያዘችው የቀደምት አባቶቻችን በከፈሉት በደምና አጥንት ዋጋ ነው ብለዋል ።
ልጅ ዳንኤል ጆቴ መስፍን በበኩላቸው፤ ከ87 ዓመት በፊት በፋሽስት ጣሊያን በግፍ በተፈፀመው ጭፍጨፋ ሕይወት ያጡ ሰማዕታትን ስናስብ፤ የባለፈውን ታሪክ ብቻ በመዘከር ሳይሆን ያሁኑ ትውልድ ከጀግኖች አባቶች እንዲማር ለማድረግ ጭምር ነው ሲሉ ተናግረዋል ።

• የአበባ ዘርፉ ከ50 ሺ በላይ የሥራ ዕድል ፈጥሯል
• ኢትዮጵያ የዓለም 4ኛዋ ትልቋ የአበባ አምራች ናት
• የፍቅረኛሞች ቀን ለአበባ አምራቾች የውጥረት ጊዜ ነው


ባለፈው ረቡዕ ፌብሯሪ 14 ቀን 2024 ዓ.ም በመላው ዓለም የቅዱስ ቫላንታይን ቀን (የፍቅረኛሞች ቀን) ተከብሮ ውሏል- በፅጌረዳ አበባና በሌሎች የፍቅር መግለጫ ስጦታዎች ደምቆና ፈክቶ። በአበባ ምርትና ሽያጭ ላይ ላሉ ወገኖች ግን ከበዓሉ ጥቂት ቀናት ቀደም ብሎ አንስቶ ያሉ ጊዜያትን ጨምሮ በውጥረት የተሞላ ነው- የአበባ ምርቶች በብዛት ለገበያ የሚቀርቡበት ወቅት በመሆኑ፡፡ በአዲስ አበባ ዳርቻ ላይ ለሚገኘው የጋሊካ አበባ ኩባንያም ከዚህ የተለየ አይደለም - ወቅቱ፡፡ ይህን ባለፈው ረቡዕ  በሰፊው የጋሊካ የአበባ እርሻ ግቢ ውስጥ በአካል ተገኝቶ የቃኘው የፈረንሳዩ የቴሌቪዥን ጣቢያ ፍራንስ 24 ነው፡፡ የጣቢያው ዘገባ እንደሚያመለክተው፣ በዕለቱ ከጠዋቱ 1 ሰዓት ላይ 300 የሚሆኑ የኩባንያው ሠራተኞች በእርሻው ሥፍራ ላይ ደርሰው ነበር፡፡  
በየዓመቱ የኩባንያው 8 ሄክታር የቤት ውስጥ ማልሚያ (ግሪንሃውስ)፣ በመላው ዓለም የሚላኩ 5 ሚሊዮን ገደማ የፅጌረዳ አበቦችን እንደሚያመርት ዘገባው ይጠቁማል፡፡
የቅዱስ ቫላንታይን ቀን መቃረቢያ ጊዜያት ግን ከዓመቱ  ሁሉ እጅጉን ሥራ የሚበዛበት ወቅት ነው። ዛሬ ብቻ (ባለፈው ረቡዕ ማለት ነው) ከ20ሺ በላይ አበቦች ይሰበሰባሉ- ብሏል ዘገባው፡፡
“እዚህ ኡደቱ 80 ቀናት ገደማ ነው” ሲል ያስረዳው  የእርሻው ስራ አስኪያጅ አቶ ግዛቸው ወንድሙ፤ “ፅጌረዳዎቹን የዛሬ 80 ቀን ከተከልካቸው ዛሬ ደርሰው ታገኛቸዋለህ። እናም በተለይ አንዳንዶቹ የፅጌረዳ ዓይነቶች እንዲደርሱ ለማዘጋጀት እንሞክራለን፤ በዋናነት ቀያይ ጽጌረዳዎቹን፡፡ እኛ ሁልጊዜም ከሚፈለገው ያነሰ ነው የምናመርተው።” ብለዋል።
ባለፉት 12 ዓመታት በኢትዮጵያ የአበባ ምርት በከፍተኛ ሁኔታ ማደጉን የጠቆመው ፍራንስ 24፤ እ.ኤ.አ በ2013 ዓ.ም ኢትዮጵያ ከምንም ተነስታ 212 ሚ.ዶላር የሚገመት 2 ቢሊዮን ቶን አበባ ለውጭ ገበያ መላኳን ያስታውሳል።
ይኼም አሃዝ ኢትዮጵያን የዓለም አራተኛዋ ትልቋ የአበባ አምራች ሲያደርጋት፤ በአፍሪካ ደግሞ ከኬንያ ቀጥሎ በሁለተኛ ደረጃ ላይ አስቀምጧታል- ይላል ዘገባው።
50ሺ የሥራ ዕድሎች
ምንም እንኳ አብዛኞቹ የአበባ ኩባንያዎች በውጭ ዜጎች ባለቤትነት የተያዙ ቢሆኑም፣ የኢትዮጵያ የአበባ ዘርፍ ከ50ሺ በላይ ለሚሆኑ ሰዎች የሥራ ዕድል የፈጠረ ሲሆን፤ ከ70 በመቶ የሚልቁት ሠራተኞች ደግሞ ሴቶች ናቸው።
“የምኖረው እዚሁ ጎረቤት ነው፤ ነገር ግን የራሴ መሬት የለኝም። እዚህ  ለመሥራትና በቆጠብኩት ገንዘብ የራሴን ንግድ ለመጀመር ነው ያቀድኩት።” ትላለች፤ በጋሊካ እርሻ ላይ ከሚሰሩት አንዷ የሆነችው ብርቱካን ሚልኬሳ፤ ለፍራንስ 24 ቴሌቪዥን።
“እዚህ በመሥራታችን ትልቅ ጥቅም አለን። ለምሳሌ፡- በየቀኑ ምሳችንን በነጻ እንመገባለን።” ስትልም አክላለች-ብርቱካን።
የኢትዮጵያ አበባ ገበሬዎች ጥብቅ የስነ-ምግባር መመሪያ የሚከተሉ ሲሆን፤ እጅግ ውድድር በበዛበት ገበያ ውስጥ እንደሚሰሩም ይገነዘባሉ።
በጋሊካ እያንዳንዱ ፅጌረዳ በጥንቃቄ ይመረጣል፤ ይደረደራል፤ ከዚያም  ይታሸጋል።
“ወደ መዳረሻቸው ከመላካቸው በፊት ፅጌረዳዎቹ ይታሸጋሉ፤ ውሃ ይጠጣሉ፤ ከዚያም በቀዝቃዛ ክፍል ውስጥ ለአንድ ሌሊት ይቀመጣሉ።” ሲል የጋሊካ ባለቤት ስቲፌን ሞቲየር አስረድቷል፡፡
እርሻው ከ60 በላይ የፅጌረዳ ዝርያዎችን ያመርታል። አዲስ ዲቃላ ቀለማት ሲፈጠሩ ልዩ ስሞች ይወጣላቸዋል።
“የተለያዩ አገራት የተለያዩ ዓይነት ፅጌረዳዎችን ይፈልጋሉ። ይኄኛው ምናልባት ወደ ጃፓን ወይም ደቡብ አፍሪካ ይላካል” አለ ስቴፋን ወደ ነጭ ፅጌረዳ እየጠቆመ፤ “የተቀሩት በተለይም ቀይ ፅጌረዳዎቹ ደግሞ  ወደ ፈረንሳይ ይላካሉ።”
በመጨረሻም አበቦቹን ለመውሰድ ትልቅ መኪና ይመጣል። ከዚያም አበቦቹ በአውሮፕላን ተጭነው በቀጥታ በዓለም ዙሪያ ወደሚገኙ የአበባ መሸጫ ሱቆች በሰዓታቸው ይደርሳሉ - ለፍቅረኛሞች ቀን!!

ፖርቹጋል ገናና በነበረችበት ወቅት የነበሩ የአንድ ንጉሥ አፈ-ታሪክ አለ፡፡
ለዘመናት በወራሪነት የኖሩ ንጉሥ፣ በምርኮ የያዙዋቸውን አገሮች አቀናለሁ እያሉ ብዙ ብር ያፈሱባቸዋል፡፡ ከዚያም በዓመት አንድ ጊዜ ህዝቡን ሰብስበው፤
“ዕድሜ ለእኔ በሉ ነፃ አወጣኋችሁ” ይላሉ፡፡ህዝቡ በጭብጨባ ስለንግግራቸውና ስለቸርነታቸው ያለውን አድናቆት ይገልፃል፡፡
ቀጥለውም ንጉሡ፤ “ዛሬ በገዛ ደግነቴ፤ ለሀገራችሁ ዕድገት፣ ለህዝባችሁ ደህንነት ስል አንድ ተጨማሪ በጎ-አድራጎት እፈፅማለሁ፡፡ ይኸውም፤ ነፃ የወጣችሁበትን ቀን በዓመት አንድ ቀን ታከብሩ ዘንድ ፈቅጄላችኋለሁ፡፡”
ህዝቡ በጭብጨባ አድናቆቱን ይገልፃል፡፡፡
ከዚያ እንደተለመደው፤
“ጥያቄ ካላችሁ መጠየቅ ትችላላችሁ” ይላሉ፡፡
ከሰው መካከል በተራ በተራ እየተነሱ ተወካዮች ጥያቄ ይጠይቃሉ፡፡ የህፃናቱ ተወካይ፤ “ንጉሥ ሆይ! መዋዕለ - ህፃናት ይሰራላችኋል ከተባልን ብዙ ዓመት አለፈን፡፡ በጦርነቱ እናት አባታቸውን ያጡ አያሌ ህፃናት የሚኖሩበት አላገኙም፡፡”
ቀጥሎ የወጣቱ ተወካይ ይነሳል፡፡
“ንጉሥ ሆይ! ከሁሉም በጦርነቱ የተጎዳው ወጣቱ ነው፡፡ ወጣቱ የሚያነብበት ቤተ -መፃሕፍት፣ የሚዝናናበት ኳስ ሜዳ፣ የሚወያይበት አዳራሽ የለውም፡፡ ስለዚህ የእርሶን እርዳታና ረድኤት እንሻለን” ንጉሥ- “መልካም፡፡ የእናንተም በጣም አሳሳቢ ጉዳይ ነው፡፡ በቀጣይ የተያዘ ስለሆነ ይፈፀማል” አሉ፡፡
በተከታታይ የሴቶች ተወካይ፣ የሽማግሌ ተወካይ፣ የሠራተኛ ተወካይ፣ የተማሪ ተወካይ ወዘተ…. ጥያቄያቸውን አቀረቡ፡፡
ንጉሡም “በቀጣይ ተይዟል” ሲሉ መለሱ፡፡
በመጨረሻም የምርኮኞቹ ወታደሮች ተወካይ፤
“ንጉሥ ሆይ! ከሁሉም የተጎዳን እኛ ወታደሮች ነን፡፡ ይኸው ያለ ጦርነት ተቀምጠን ስንትና ስንት ዓመት  ተሰቃየን፡፡ ወይ ከእንግዲህ ጦርነት የለምና ተበተኑ በሉን፡፡ አለበለዚያ ደግሞ በአስቸኳይ ጦርነት ይፈጠርልንና በቶሎ ተግባር ላይ እንሰማራ፡፡ ንጉሥ ሆይ! ቃታ እንስብበታለን ያልነው ጣታችን ለስልሶ የወርቅ ቀለበት ማሰሪያ ሆነ፡፡ ለሬዲዮ መገናኛ የተሠጠን መሳሪያ የሙዚቃ ማዳመጫ ሆኖ ሰነበተ፡፡ ስንት ዳገት ቁልቁለት ይወጣል ይወርዳል፤ የት ይደርሳል የተባለው ሰውነታችን በተጠረገ መንገድ መምነሽነሽ፤ በሚሞቅ አልጋ ላይ መተኛት የሁልጊዜ ፀባዩ ሆነ፡፡ ምቾት በዛ ንጉሥ ሆይ? ያ በሥልጠና ላይ የተነገረን ጦርነት የታለ?  እንደ-ምጽዓት ቀን ራቀብን’ኮ፡፡ ኧረ አንድ መላ ይፈጠርልን ንጉስ ሆይ!” ሲል ተማጠነ፡፡
ንጉሡም፤ “እኔም ይህን ችግራችሁን በጣም አስቤበታለሁ፡፡ ሥቃያችሁ ያሰቃየኛል፡፡ ህመማችሁ ያመኛል፡፡ ስለዚህም የናንተ ጉዳይ ከማንም በፊት በቀዳሚነት በቀጣይ ተይዟል” አሉ፡፡
እኒያ ንጉሥ ከዚያን ጊዜ አንስቶ እስከ እለተ - ሞታቸው ድረስ መጠሪያ ስማቸው “ንጉሥ በቀጣይ” የሚል ሆነ፡፡
አገራቸውም፤ ከዓመት ዓመት ጦርነት በቀጣይ እያስተናገደች፤ አያሌ ቅኝ-ግዛቶቿን እስክታጣ ድረስ ስትዋጋ ኖረች፡፡
***
ህዝቦችን በተስፋ ብቻ በማሰር ለመሰንበት  የሚሞክር እንደ ፖርቹጋሉ ንጉሥ ያለ መሪ፤ ህዝቦቹ የለበጣ የሚገዙለት፤ በሀሳዊ-ጭብጨባ እንዲገበዝ የሚያደርጉት ነው፡፡ ከቶውንም ምርኮኞቹን ነፃ እንዳወጣቸው ማሰቡና፤ እንዲያስቡም ለማስገደድ መሞከሩ፤ ጊዜያዊ የአሸናፊነት ስሜትን እንጂ ዘላቂ ሥርዓትን ለመገንባት የሚፈይደው ነገር አይኖርም፡፡
ህዝብ የተታለለ ሲመስል የእድር አለቃውም፣ የቀበሌ ሹሙም፣ የቢሮ ኃላፊውም፣ የቢሮክራሲ አባ-ወራውም፣ የፖለቲካ ፓርቲ መሪውም…. አዕምሮውን ሰብሰብ አድርጎ፣ ማናቸውንም ዕርምጃ ከመውሰዱ በፊት ሁለት ሶስቴ አስቦ፤ ከምወስደው እርምጃ ጠቀሜታና ህዝቡ ከሚያገኘው ፋይዳ የትኛው ሚዛን ይደፋል? ብሎ ሁኔታዎችን ማውጠንጠን እጅግ ወሳኝ ጉዳይ ነው፡፡ የገባሁት የተስፋ ቃል ከታጠፈ ካፌ የሚወጣው ሁሉ ወደ አለመታመን ማምራቱ አይቀርም ብሎ የማያስብ የበላይ፤ የኮቴውን ድምፅ ያህል እንኳ የሚታወስ ፍሬ የሌለው ነው፡፡
የኒውዚላንድ ህዝቦች ሲተርቱ “አሮጌ ቃል - ኪዳን ወደ ኋላ ይቀራል” እንደሚሉት፤ በአዲስ ቃል-ኪዳን ወይም እንደ ፖርቹጋሉ የአፈ -ታሪክ ንጉስ በቀጣይ ቃል-ኪዳን ይተካል ብንል፤ ጊዜን መሸጋገራችን እንጂ ረብ ያለው ድርጊት አልፈፀምንም፡፡
ጆርጅ ፓድሞር የተባለው ትሬኒዳዳዊ የምርጫ ተወዳዳሪ “አፍሪካውያን በቃል--ኪዳን በመተማመን ረዥም ጊዜ ኖረዋል፡፡ አሁን ማየት የሚፈልጉት ጥቂት ተጨባጭ ተግባራትን ብቻ ነው፡፡ አንገታቸው ላይ የሎሌነት ሰንሰለት አጥልቀውም ስለ “ዲሞክራሲ” እና ስለ “ነፃነት” የሚሰበኩ ሃይማኖት አከል ውዳሴዎችን ማዳመጥ ደክሟቸዋል፤ ታክቷቸዋል” ያለው በከንቱ አይደለም፡፡ የብዙ ፖለቲካዊ ቀውሶች መንስዔዎች የታጠፉ ቃሎች ናቸው፡፡
ሌት ተቀን አውጥተን አውርደን፣ አዋቂ ጠይቀን፤ የውጪ አጥኚ አሰማርተን ይሄን ችግር በቅርቡ እንፈታዋለን ብለን ስናበቃ፣ መልሰን በቅርቡ ያልነውን ላልተወሰነ ጊዜ አሸጋግረነዋል ካልን፣ ከቃል ማጠፍ የማይተናነስ ተግባር ፈፅመናልና ችግሩን አዘገየነው እንጂ የመፍታት ሙከራ አላደረግንም፡፡ የሚዋዥቀውን ወይም ትርጉም ባለው መልኩ ለውጥ ያልታየበትን ኢኮኖሚ፣ አድጓል ተመንድጓል፣ነገ ደግሞ የእጥፍ-እጥፍ ያድጋል ብለን ቃል-ብንገባ፣ በኑሮ ውድነቱ ሳቢያ ሰልፍ አስመርሮኛል የሚለውን ሰው በቅጡ ማሳመን የሚቻል አይሆንም፡፡ ነባራዊውም ሆነ ህሊናዊው ሁኔታ የማያግዙት ሙግት፤ አፍአዊ እንጂ ልባዊ ብሎም ተግባራዊ ለመሆን ይሳነዋል፡፡
የላይኛው እንዳፈተተው ሲናገር የታችኛው ለማስተጋባት የበለጠ መጮሁ አግባብ ያለው ሥርዓት በሚመስልበት፣ እንደ ውሃ በመሬት ስበት ኃይል ከላይ ወደታች እንደሚወርድ የዕዝ-ሠንሠለት የተዋቀረ በሚመስል አካሄድ ውስጥ፤ “አሳታፊ ዲሞክራሲ”፣ “የውድድር ኢኮኖሚ”፣ “ልማት-ተኮር ራዕይ”፣ “ፍትሕ-ርትዕ የሰፈነበት ማህበራዊ መርሕ” እያልን ብናንቆለጳጵሰው፤ ለስልት እንጂ ለስሌት አያግዘንም፡፡  ዞሮ ዞሮ  ከላይ ወደታች የሚወርድ አንድ አሸንዳ ውስጥ ያለ ፍሰት የመሰለ ፖለቲካዊ ሥርዓት፤ “ታላቅየው ሲመቸው፣ ታናሽየው ሳይድህ በእግሩ ይሄዳል” እንደሚባለው ያለ ነው፡፡

Page 11 of 700