Administrator

Administrator

   የሩሲያ ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን በተከሰተው የኢኮኖሚ ቀውስ ምክንያት ሚኒስትሮቻቸው የአዲስ ዓመት እረፍት እንደማይወስዱ ሰሞኑን አስታወቁ፡፡ በሩሲያ ትልቁ በዓል እንደሆነ በሚነገርለት የፈረንጆች አዲስ ዓመት፤ በመላ አገሪቱ የሚገኙ የሩሲያ ኩባንያ ሰራተኞች ለበዓሉ የ12 ቀናት እረፍት ይወስዳሉ፤ ከጃንዋሪ 1 እስከ 12፡፡
ፑቲን ባለፈው ሐሙስ በቴሌቪዥን በተሰራጨ የመንግስት ኃላፊዎች ስብሰባ ላይ፣ በዚህ ዓመት የካቢኔ ሚኒስትሮቻቸው እረፍት መውሰድ እንደማይገባቸው ተናግረዋል፡፡ “ቢያንስ ለዚህ ዓመት መንግስት ይሄን ረዥም የበዓል ዕረፍት መስጠት አይችልም - መቼም የምለው ይገባችኋል” ብለዋል - ፕሬዚዳንቱ፡፡
የአገሪቱ ጠ/ሚኒስትር ዲሚትሪ ሜድቬዴቭ በበኩላቸው፤ በበዓሉ ወቅትም ጭምር (ከዓመቱ የመጀመሪያ ቀናት አንስቶ) የኢኮኖሚውን ሁኔታ እንዲከታተሉላቸው እንደሚፈልጉ ለሚኒስትሮቹ ነግረዋቸዋል፡፡
በነዳጅ ዋጋ መቀነስና በምዕራብ አገራት ማዕቀብ ክፉኛ የተጎዳው የሩሲያ ኢኮኖሚ፤ ከስድስት ዓመታት ወዲህ ለመጀመሪ ጊዜ በቀጣዩ ዓመት “ድቀት” ውስጥ የሚገባ ሲሆን፣ የአገሪቱ ገንዘብ ሩብልም በአሁኑ ሰዓት ከዋጋው ግማሽ በታች ወርዷል፡፡ ከያዝነው ወር መጀመሪያ አንስቶ አንድ ዶላር በ80 ሩብል ሲመነዘር የቆየ ሲሆን፣ ባለፈው ሐሙስ የ2 በመቶ መጠነኛ መሻሻል አሳይቶ አንድ ዶላር በ52 ሩብል መመንዘሩ ታውቋል፡፡
የሩሲያ ማዕከላዊ ባንክ የአገሪቱ መጠባበቂያ ገንዘብ ከ2009 ዓ.ም ወዲህ ለመጀመሪያ ጊዜ ከ400 ቢሊዮን ዶላር በታች መውረዱን አስታውቋል፡፡ ዋጋው እጅግ ያሽቆለቆለውን የአገሪቱን መገበያያ ሩብል ማረጋጋት፣ የሩሲያ የገንዘብ ኃላፊዎች ተቀዳሚ ስራ ይሆናል ተብሏል፡፡ ከዩክሬን ጋር በተያያዘ በአገሪቱ ላይ የተጣለው ማዕቀብ፣ በርካታ የሩሲያ ኩባንያዎችን ከምዕራብ አገራት የፋይናንስ ገበያ እንዳስወጣቸው ተዘግቧል፡፡

የትንፋሽ ማጠር ገጥሟቸው ባለፈው ማክሰኞ ሂዩስተን ሜቶዲስት ሆስፒታል የገቡት የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት  ጆርጅ  ኤች ደብሊው ቡሽ፤ ከትላንት በስቲያ የተከበረውን የፈረንጆች የገና በዓል በሆስፒታል አሳለፉ፡፡
የፕሬዚዳንቱ ቃል አቀባይ ጂም ማክግራዝ፤ ቡሽ በጥሩ ጤንነት ላይ እንደሚገኙና የገና በዓልን በሆስፒታል ያሳለፉት በሽታው ከፍቶባቸው ሳይሆን ለጥንቃቄ ሲባል እንደሆነ ገልፀዋል፡፡ የዛሬ ሁለት ዓመት በተመሳሳይ ጊዜ ብሮንካይትና በሃይለኛ ሳል ይዟቸው ሆስፒታል ከገቡ በኋላ የገና በዓልን ጨምሮ ለሁለት ወራት እዚያው መቆየታቸውን ያስታወሱት ቃል አቀባዩ፤ የአሁኑ ግን ከቀድሞው በጣም ይለያል ብለዋል - የፕሬዚዳንቱን ጤናማነት ሲገልፁ፡፡
የፕሬዚዳንቱ ሆስፒታል መግባት ላሳሰባቸው በርካታ ወዳጆችና አድናቂዎቻቸው የቡሽ ዋና ኃላፊ በሰጡት መግለጫ፤ “የቡሽ ቤተሰብ፤ ለጭንቀታችሁ፣ ለፍቅራችሁና፣ ለፀሎታችሁ በእጅጉ ያመሰግናል፡፡ ይሄ የዛሬ ሁለት ዓመት እንደሆነው ዓይነት አይደለም፡፡ የትንፋሽ ማጠር ነው፡፡ በጥቂት ቀናት ውስጥ ወደ ቤታቸው ይመለሳሉ” ብለዋል፡፡ ቡሽ ሆስፒታል መግባታቸውን የሰሙት ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ እና ባለቤታቸውም ለቀድሞው ፕሬዚዳንትና ለመላው የቡሽ ቤተሰብ የመልካም ጤንነት ምኞታቸውን ልከዋል፡፡
ሪፐብሊካኑ የ90 ዓመቱ ቡሽ፤ 41ኛው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት በመሆን አገራቸውን ያገለገሉ ሲሆን የ43ኛው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ጆርጅ ደብሊው ቡሽም አባት ናቸው፡፡ የዊልቸር እስረኛ ባደረጋቸው ከፍተኛ የነርቭ ህመም ሲሰቃዩ የቆዩት ቡሽ፤ በቅርቡ ግን ነቃ ነቃ ማለት ጀምረው ነበር ተብሏል፡፡ ባለፈው ሰኔ ለ90ኛ ዓመት የልደት በዓላቸው ከሄሊኮፕተር ላይ በፓራሹት የዘለሉ ሲሆን የዛሬ ወር “41፡ A Portrait of My Father” የተሰኘ አዲስ መፅሃፋቸው የምረቃ ስነስርዓት ላይ ከልጃቸው ጋር ተገኝተው ነበር፡፡
ፕሬዚዳንት ሆነው የተመረጡበትን 25ኛ ዓመት በዓል በቅርቡ ያከበሩት ጆርጅ ቡሽ፤ በፕሬዚዳንት ሮናልድ ሬገን ዘመን ምክትል ፕሬዚዳንት ሆነው አገልግለዋል፡፡
በሁለተኛው የዓለም ጦርነት በባህር ኃይል አብራሪነት የተሳተፉ ሲሆን ወደ ፖለቲካው ዓለም ከመግባታቸው በፊት በቴክሳስ የነዳጅ ኢንዱስትሪ ውስጥ እንደሰሩ የህይወት ታሪካቸው ያወሳል፡፡

መኪና ሲያሽከረክሩ የተያዙ ሁለት የሳኡዲ ሴቶች ለአንድ ወር ገደማ ከታሰሩ በኋላ ባለፈው ሳምንት ጉዳያቸው ሽብርተኝነትን ለሚመለከት ልዩ ፍ/ቤት እንደተላለፈ ተገለፀ፡፡
የ25 ዓመቷ ሎዩጄይን አል ሃትሎል እና የ33 ዓመቷ ማይላ ይሳ አል - አሙዲ ጉዳይ ወደ ልዩ ፍ/ቤት የተላለፈው በማህበራዊ ሚዲያ ላይ በሰጡት አስተያየት ነው ብለዋል - የመብት ተሟጋቾች፡፡ ሳኡዲ በዓለም ላይ ሴቶች መኪና እንዳያሽከረክሩ የምትከለክል ብቸኛ አገር ናት፡፡
ሴቶች መኪና እንዳያሽከረክሩ በፅሁፍ የተቀመጠ ህግ ባይኖርም የመንጃ ፈቃድ የሚሰጠው ግን ለወንዶች ብቻ ነው፡፡ ሴቶች በአደባባይ ሲያሽከረክሩ ከተገኙም በፖሊስ ተይዘው ከመታሰርም ባሻገር ይቀጣሉ፡፡
የሳኡዲ ሴቶች መኪና እንዳያሽከረክሩ የተጣለባቸው እገዳ እንዲነሳላቸው ማህበራዊ ሚዲያን ጨምሮ የተለያዩ ተከታታይ እንቅስቃሴዎች ሲያካሂዱ ቆይተዋል፡፡
አዣንስ ፍራንስ ፕሬስ የዜና ወኪል እንደዘገበው፤ ሚስ ሃትሎል የተያዘችው ከጐረቤት አገር፣ ዩናይትድ አረብ ኢምሬትስ እያሽከረከረች ወደ ሳኡዲ ለመግባት ስትሞክር ነው፡፡
ነዋሪነቷን በዩናይትድ አረብ ኢምሬትስ ያደረገችው የሳኡዲ ጋዜጠኛ ሚስ አላሙዲም የተያዘችው ሚስ ሃትሎልን ለመርዳት ድንበር ላይ ስትደርስ ነው ብሏል - የዜና ወኪሉ፡፡
ሁለቱም ሴቶች በትዊተር እጅግ በርካታ ተከታይ ያሏቸው ሲሆን ሚስት ሃትሎል ወደ አገሪቱ ለመግባት አንድ ቀን ሙሉ ያችውን ውጣ ውረድ በትዊተር ገጿ ላይ እንዳሰፈረች ተዘግቧል፡፡ ባለፈው ሐሙስ በአገሪቱ ምስራቃዊ ክፍል የሚገኘው አል - አህሳ ፍ/ቤት፤ የሁለቱ ሴቶች ጉዳይ በሪያድ የሽብርተኝነት ክሶችን ለመከታተል በተቋቋመው ልዩ ፍ/ቤት እንዲዳኙ በይኗል፡፡ የሴቶቹ ጠበቆች ግን ይግባኝ ለመጠየቅ ማሰባቸውን የመብት ተሟጋቾች ለአዣንስ ፍራንስ ፕሬስ ጠቁመዋል፡፡

     በደራሲ ሐማቱማ “The case of the Socialist witchdoctor” በሚል ርዕስ ተፅፎ በህይወት ታደሰ “የሶሻሊስቱ ጠንቋይ ጉዳይ” በሚል ወደ አማርኛ የተመለሰው መፅሃፍ ለንባብ በቅቷል፡፡ የተለያዩ በርካታ ታሪኮች ስብስብ የሆነው ይሄው መፅሃፍ፤ በአንድ ሶሻሊስት ጠንቋይ ላይ ያተኮረ ታሪክ የያዘ ሲሆን ሌሎችም አስገራሚ ፖለቲካዊ ታሪኮችን አካትቷል፡፡ መፅሃፉ በ307 ገፆች የተቀነበበ ሲሆን በ50 ብር ከ65 ሳንቲም ለገበያ ቀርቧል፡፡

 “የዘንድሮ ትዳሮች” በሚል ርዕስ በመቅደስ በቀለ (ማክዳ) ተፅፎ በእርከን ቢዝነስ ዲቨሎፕመንት አሳታሚ የታተመው መፅሐፍ በገበያ ላይ ውሏል፡፡ በቅርቡም ይመረቃል ተብሏል፡፡
በመፅሀፉ የዘንድሮ ትዳሮችን ጨምሮ ሌሎች እውነተኛ ታሪክ ላይ የተመሰረቱ ከ15 በላይ አጫጭር ልቦለዶች እንደተካተቱበትና በ200 ገፆች ተሰናድቶ በ60 ብር ለገበያ እንደቀረበ ለማወቅ ተችሏል፡፡
የመፅሃፉ ደራሲ መቅደስ በቀለ (ማክዳ) የበርካታ ፊልሞች ደራሲና ዳይሬክተር ስትሆን “የዘንድሮ ትዳሮችና ሌሎች” ሁለተኛ መፅሃፏ መሆኑ ታውቋል፡፡ ደራሲዋ ከዚህ ቀደም “የፍቅር መስዋዕት” የተሰኘ መፅሃፍ አሳትማለች፡፡

የገጣሚ የሺመቤት ካሳ “አመሻሽ” የግጥም መድበል ሰሞኑን በ25 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡
የግጥም መድበሉ 62 አጫጭርና ረጃጅም ግጥሞች የተካተቱበት ሲሆን ገጣሚዋ ማስታወሻነቱን ለቀደምት ደራሲያንና ለነገው ደራሲያን ማድረጓን አስታውቃለች፡፡

የደራሲ ስንዱ አካልነህ “ኤል-ማጐት” የተሰኘ የረዥም ልቦለድ መፅሃፍ እየተነበበ ነው፡፡
በጐንደር ማተሚያ ድርጅት ታታሞ ለገበያ የቀረበው መፅሃፉ መቼቱን በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገር ያደረገ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡ መፅሃፉ በ75 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

በጋዜጠኛና ደራሲ አሰግድ ሀምዛ ተፅፎ የታተመው “በህይወት መስኮት” የተሰኘ መፅሃፍ ዛሬ በሀዋሳ ከተማ ይመረቃል፡፡ መፅሃፉ፤ ወጎችና የፍቅር ደብዳቤዎችን ያካተተ ሲሆን ደራሲው በመምህርነት ባገለገለበት ሙርሲ ብሔረሰብ ውስጥ የታዘበውንና የኖረውን እውነታ በሚጥም ቋንቋና ውበት ፅፎታል፡፡
141 ገፆች ያሉት መፅሀፉ ዛሬ ሲመረቅ፣ የዘርፉ ምሁራን አስተያየት የሚሰጡ ሲሆን በስነ ስርዓቱ ላይ የጥበብ አፍቃሪዎችና ቤተሰቦች እንደሚታደሙ ታውቋል፡፡ መፅሃፉ አገር ውስጥ በ40 ብር፣ በውጭ አገር በ8 ዶላር እንደሚሸጥ ተገልጿል፡፡

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
ሰውየው አእምሮ ሀኪም ዘንድ ይሄድና…“ዶክተር፣ መጥፎ ተግባራት እየፈጸምኩ ህሊናዬ እየረበሸኝ ነው…” ይለዋል፡፡
ዶክተሩም… “እና መጥፎ ድርጊት ከመፈጸም የሚከላከል ህክምና እንዳደርግልህ ነው የምትፈልገው?” ይለዋል፡፡ ሰውየውም… “አይደለም…”  ይላል፡፡
ዶክተሩም… “ታዲያ ምን ፈልገህ መጣህ?” ይለዋል፡፡
ሰውየው ምን ቢል ጥሩ ነው…“ህሊናዬን ከሥሩ ነቅለህ አውጣልኝ!”
‘አልሰሜን ግባ በለው’ አሉ…እኛ ዘንድ ቢመጣ ህሊና እያለም እንዴት ‘ህሊናቢስ’ መሆን እንደሚቻል ‘በስምንተኛ ዲግሪ’ ደረጃ እናሰለጥነው ነበር፡፡ የምር ግን የህሊና ነገር እኮ እኛ አገር የሆነች ተረስታ ከአሮጌ አንሶላ ጋር የተጠቀለለች ነው የምትመስለው፡፡  
እናላችሁ…“ትንሽ ህሊና እንኳን የለህም!” ብሎ አማረኛ ቀረ፡፡ ህሊና የሰው ስም ብቻ የሚመስለን እየበዛን ነዋ! (“ህሊና ቢኖረኝ እዚህ አገር ታገኙኝ ነበር ወይ…” ያልከን ወዳጃችን በእግርህ አስነካኸው እንዴ!)
እኔ የምለው…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…ነገርየው እንዴት ነው…‘ጉልቤ’ ነገሮች በዙብና! ልክ ነዋ…ጉልቤነት ማለት እኮ የግድ ‘አገጭ ማጣመም’፣ ጥርስን ‘በመሀረብ ማስቋጠር’ ምናምን ማለት ብቻ አይደለም፡፡ የዘንድሮ ‘ጉልቤነት’… አለ አይደል…መአት መልክ አለው፡፡
እንግዲህ ጨዋታም አይደል…ይቺን ስሙኝማ…የሆነ ሚኒባስ ታክሲ ላይ ያየነው ‘ጥቅስ’ ነው…‘ጥቅሱ’ ምን ይል መሰላችሁ… (ምንም ደስ ባይልም መነገር አለበት፣) “አፍህን ከምትከፍት ሱቅ ክፈት” ይላል፡፡
እናላችሁ…እንዲህ አይነት በህዝብ መገልገያ ላይ ከእግር ጥፍር እስከ ራስ ጸጉር ‘ሙልጭ የምንደረግበት ዘመን ላይ ደርሰንላችኋል፡፡ የምር ግን… እንደዚህ አይነት ነገር መጀመሪያ ስናይ ፈገግ እንደ ማለት ይቃጣናል፡፡ ግን… እኛም ተሰዳቢዎች መሆናችን ሲገባን…
“የበጎቹ ጠባቂ ሆይ፣ ‘ወየት’ ነህ!” እንላለን፡፡  
ምን መሰላችሁ…‘የቤትሽን ዓመል እዛው’  ‘አትንጣጪ’ ምናምን ሲባል ዝም ተብሎ ተከረመና አሁን ደግሞ “አፍህን አትክፈት…” ወደ መባል ደርሰናል፡፡
የምር እኮ…ነገርየው በዚሁ ከቀጠለ …ቀስ ብሎ…በአንድ ወቅት እዚች ዋና ከተማችን ጎራ ያለ የገጠሩ ሰውዬ… “አዲስ አበባ ገዳይ ጠፋ እንጂ ሟች ብዙ ነበር!”  ያለበት አይነት ስድብ ነገ ተነገ ወዲያ የማይለጠፍበት ምክንያት የለም፡፡ እነማ…እንደዚህ አይነት ነገር ሲበዛብን፣
“የበጎቹ ጠባቂ ሆይ፣ ‘ወየት’ ነህ!” እንላለን፡፡  
የምር አስቸጋሪ ጊዜ ነው፡ የደንብ ልብስ የለበሱ በከተማው ጎዳናዎች በበዙበት ጊዜ፣ ማስቲካና መፋቂያ ሻጮች ሲሯሯጡ በምናይበት ጊዜ… አንዳንድ አካባቢ ተረጋግቶ መገበያየት እንኳን እያስቸገረ ነው፡፡ እኔ የምለው… እግረ መንገዴን…የገበያተኛ መዋከብ ‘የደንብ ጥሰት’ ለመሆን ያንሳል እንዴ!
በቀደም መርካቶ ዕቃ ቢጤ ለማየት ወጣ ብለን… “አይ መርካቶ!”  ብለን ተመለስን እላችኋለሁ፡፡ የምር እኮ… የምንጣፍ ሱቆች በበዙበት አካባቢ መራመድ እስኪያቅታችሁ ድረስ ትከበባላችሁ፡፡  ‘የደላላው’ ብዛት! የሆነ ሱቅ ውስጥ ለመግባት ስታስቡ ወጣት ደላሎች እየተከተሉ… “መጋዘኑ እዛ’ጋ ነው፣ ቅናሽ አለው…” “እዛ ሱቅ ያለው አሪፍ ነው…” ምናምን እየተባለ እስኪሰለቻችሁ ድረስ የሚቀባበሏችሁ ወጣቶች ብዛታቸው… አለ አይደል… ያበሳጫል ብቻ ሳይሆን ‘ያስፈራል’ ቢባል ማጋነን አይሆንም፡፡
እንግዲህ ይህ ሁሉ ሲሆን በአካባቢው የደንብ ልብስ የለበሱ ሰዎች ውር፣ ውር ይታያሉ— የሚያስጥል የለም እንጂ፡፡ እናላችሁ… ገበያተኛ ሲጉላላ፣ ደንብ አስከባሪውም ዝም፣ ነጋዴውም ዝም፣ ሁሉም ዝም ሲሆን… አለ አይደል…
“የበጎቹ ጠባቂ ሆይ፣ ‘ወየት’ ነህ!” እንላለን፡፡  
ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…እዚህ አገር መድረክ ላይም ‘ሙልጭ’ ተደርጎ መሰደብ እየተለመደ ነው፡፡ መጀመሪያ ሰብሳቢው…“መሀላችን የተሰገሰጉ የራሳቸው ዓላማ ያላቸው…” ምናምን እያለ ‘ሆረር’ ምናምን ነገር ይለቅባችኋል፡፡
‘አስተያየት ሰጪው’ ተነስቶ… “በተባለው ላይ የምጨምረው የለኝም…” ይልና  “ዕድገታችንን ለመግታት የሚፍጨረጨሩ አንዳንድ የስብሰባው ተካፋዮች ላይ እርምጃ ለምን እንደማይወሰድ…” በቁጭት ይጠይቃል፡፡ ይህ ሁሉ ሲሆን እከሌ፣ እከሌ ተብሎ እስካልተጠቀሰ ድረስ አንዳንድ “…የስብሰባው ተካፋዮች…” የሚለው ሁላችንንም ስለሚመለከት…አለ አይደል…
“የበጎቹ ጠባቂ ሆይ፣ ‘ወየት’ ነህ!” እንድንል ያደርገናል፡፡
አሀ… ማን በበላው ማን ‘ራዳር’ ውስጥ ይገባል! ልጄ ዘንድሮ ‘…ሁሉም እንደ የሥራው…” ምናምን የሚል አባባል፣ ‘ጥቅስ’…ነገር አይሠራም፡፡ ልጄ…ዘንድሮ ሰው ‘ባልሠራው’ የሚበላበት፣ ‘ባልሠራውም’ የሚበላውን የሚያጣበት ዘመን ነው፡፡
ይቺን ስሙኝማ…የመንገድ ግንባታ ሥራ ላይ ነው አሉ፡፡ እናላችሁ…አንዱ ሠራተኛ አካፋ አልነበረውም፡፡ ታዲያ…አለቃውን፣ “አካፋ የለኝም…” ይለዋል፡፡ አለቅየውም…“ታዲያ ምን ያነጫንጭሀል! አካፋ ከሌለህ ሥራ አትሠራ!” ይለዋል፡፡ ሰውየው ምን ብሎ ቢመልስ ጥሩ ነው… “ታዲያ እንደ ሌሎቹ ሠራተኞች ምን ተደግፌ ልቁም?” ብሎ አረፈላችሁ፡፡
እናማ…በየቢሮው፣ በየሥራ ቦታው ‘አካፋ ተደግፈን’ የምንቆም መአት ነን፡፡
ይቺን አሪፍ ነገር ስሙኝማ…ሰውየው ለጓደኛው ሲደውል ከጀርባ ድምጽ ይሰማል፡፡ “የምን ጫጫታ ነው የምሰማው?” ይለዋል፡፡ ጓደኝየውም… “የእህቴን ልደት ዓመታዊ በዓል እያከበርን ነው…” ይለዋል፡፡ ሰውየውም ግራ ይገባዋል፡፡ “የእህቴን ልደት ዓመታዊ በዓል ብሎ ነገር ምንድነው? ወይ ልደት ታከብራለህ፣ ወይ ዓመታዊ በዓል ታከብራለህ፡፡ ሁለቱ የሚገናኙ አይደሉም…” ይለዋል፡፡
ጓደኛየው ምን ብሎ ቢመልስ ጥሩ ነው…“አይ ሞኞ…የእህቴን አሥራ ስምንተኛ ዓመት ልደት አሥራ አምስተኛ ዓመታዊ በዓል እያከበርን ነው…” ብሎት አረፈ፡፡ አሪፍ አይደል!
የዕድሜ ነገር ከተነሳ… ይቺን ስሙኝማ…“በቀደም ሀያ ዘጠነኛ ዓመቴን ሳከብር ለምንድነው ስጦታ ያልሰጠኸኝ?”  ብትለው እሱዬው… “ረሳሽው እንዴ! የዛሬ አምስት ዓመት ሀያ ዘጠነኛ ልደትሽን ስታከብሪ ሽቶ አልሰጠሁሽም?” ብሏት አረፈ፡፡
እናላችሁ…ጉልቤነት መልኩን እየለዋወጠ መከራችንን እያበላን ነው፡፡ ቤት አከራይ በቀን ሁለት ባሊ ውሀ ብቻ እየፈቀደ፣ መብራት በሦስት ሰዓት ላይ እያጠፋ፣ “ከአንድ ሰዓት በኋላ ማምሸት ክልክል ነው…” አይነት ክፉ ሚስት እንኳን የማታስበው ‘ህግ እያረቀቀ’ ይቆይና አንድ ቀን ማታ በር ይንኳኳል፡፡ እናንተም ስትከፍቱ አከራያችሁ ተኮሳትረው ቆመዋል፡፡ እናንተም…“ደህና አመሹ፣ ምነው ደህና!” ስትሉ ምን ትባሉ መሰላችሁ…“ኪራዩ ላይ ከሰኞ ጀምሮ አንድ ሺህ ብር ጨምረናል፡፡
 ካልተስማማችሁ በሁለት ቀን ውስጥ ቤቱን ልቀቁልን፡፡” የምር ያበሳጫል፡፡ ስሙኝማ…የብስጭት ነገር ከተነሳ … “እንትናዬው ምን ያህል ብታበሳጨው ነው ሴቶችን እንደዚህ ጠምዶ የያዛት!” የሚያሰኝ ንግግር ገጥሟችሁ አያውቅም!
ሰውየው ጓደኛውን… “ሬድዮ ለመጀመሪያ ጊዜ የተፈጠረው በገነት ውስጥ ነው ሲሉ ሰማኋቸው፡፡
ምን ማለታቸው ነው?”  ሲል ይጠይቀዋል፡፡ ጓደኝዬውም ምን ብሎ መለሰ መሰላችሁ…“እሱን የነገሩህ ሰዎች ፈጣሪ አዳምን ፈጠረ፡፡ ከዚያም ከጎኑ የጎድን አጥንት አወጣና የመጀመሪያውን ድምጽ ማጉያ ፈጠረ ማለታቸው ነው፣”  ብሎት አረፈ፡፡‘ጉልቤነትን’… አለ አይደል… ሲሆን ያስወግድልን፣ ካልሆነም የምንሸከምበትን ትከሻ ያደንድንልን፡፡
“የበጎቹ ጠባቂ ሆይ፣ ‘ወየት’ ነህ!” የምንልበትን ጊዜ ያሳጥርልን፡፡  
ደህና ሰንብቱልኝማ!

   ከዕለታት አንድ ቀን አንዲት የውሃ ኤሊ የመውለጃዋ ጊዜ ደርሶ ኖሮ ከውሃው ወጥታ ወደ ባህሩ ዳርቻ ትሄዳለች፡፡ይቺ ኤሊ ቀስ እያለች በረጅሙ የአሸዋ መንገዷ ስታዘግም ሁለት ጓደኛሞች ያዩዋታል፡፡
አንደኛው ፤ “ይቺ ዔሊ ወዴት ነው የምትሄደው?” ይላል፡፡
ሁለተኛው፤ “የመውለጃ ጊዜዋ ደርሶ ይሆናል”
አንደኛው፤ “የመውለጃዋ ጊዜ ቢደርስ ወደ አሸዋው ምን ያስኬዳታል? መኖሪያዋ ውሃ ውስጥ ነው፡፡ እዚያው ወልዳ ተገላግላ እርፍ አትልም እንዴ?”
ሁለተኛው፤ “ለምን ውሃ ውስጥ እንደማትገላገል አላውቅም፤ የማውቀውና ሰዎች ሲሉ የሰማሁት ግን፤ ኤሊ የመውለጃዋ ጊዜ ሲደርስ ወደ ባሕሩ ቅርብ ዳርቻ አይደለም የምትጓዘው፡፡ ከውሃው እጅግ እርቃ ወደማይታይ አቅጣጫ ነው የምትሄደው”
“ልጆችዋን እሩቅ ቦታ ሄዳ የምትገላገል ከሆነ፤ በኋላ እንዴት አድርገው ልጆችዋ ከሷ ጋር ይገናኛሉ? እናታቸው በባሕሩ ውስጥ መሆኗንስ እንዴት ያውቃሉ?”
ይህ ጥያቄ በጣም ውስብስብና በቀላሉ የሚፈታ ስላልሆነላቸው በአቅራቢያው ወደሚገኝ አንድ ጠቢብ ዘንድ ሄደው ሊጠይቁ ይስማማሉ፡፡
ጠቢቡ ቤት ሄደውም፤ “ጠቢብ ሆይ! አንዲት የውሃ ኤሊ አየን፤ ከውሃው ወጥታ ወደ አሸዋው ዘልቃ እርቃ ሄደች፡፡ በኛ ግምት የመውለጃዋ ቀን ደርሶ ይሆናል ተባባልን፡፡ ግን አንድ ጥያቄ አነሳን፡፡ ወልዳ ወደ ባሕር ስትመለስ ልጆችዋን ማን ያመጣላታል? መቼም ህፃናት ናቸውና አውቀው ወደ ባሕሩ አይመጡም፡፡ ደግሞስ ያን ያህል ሰፊ ባሕር ውስጥ እናታቸው የት ትኑር የት እንደምን ያውቃሉ” ሲሉ ጠየቁት፡፡ ጠቢቡም “የአምላክን ተአምር የምታደንቁት እነዚህን አይነት ጉዳዮችን ለመመርመር ስትችሉ ነው፡፡ ኤሊዋ ልጆችዋን የምትወልደው እንዳላችሁት ከባሕሩ ራቅ ያለ ቦታ ሄዳ ነው፡፡ እንዳላችሁትም ከተገላገለች በኋላ የባሕሩ ዳርቻ አሸዋ እንዲሞቃቸው እዚያው ትታቸው ነው ወደ ባሕሩ የምትመለሰው፡፡ ልጆችዋ እስኪጠነክሩ ድረስ እዚያው አሸዋው ላይ ይቆዩና ሰፊውን አሸዋ አቋርጠው ወደ እናታቸው ይመለሳሉ፡፡ የተፈጥሮ ህግ ስለሆነ ያለ ጥርጥር በባሕሩ ውስጥ እናታቸው የቱ ጋ እንዳለች ያውቃሉ፡፡ ዋና አስገራሚ ነገር ግን ወደ ባሕሩ በሚመጡ ጊዜ መንገድ ላይ አደጋ መኖሩ ነው፡፡ በባሕሩ ዳርቻ ላይ የኤሊ ጫጩት እየተመገቡ የሚኖሩ ወፎች አሉ፡፡ ከጫጩቶቹ መካከል በወፎቹ ከመበላት ተርፈው እናታቸው እቅፍ ውስጥ ለመግባት የሚችሉት ጥቂቶቹ የታደሉቱ ናቸው፡፡ ይህ የአምላክ ስርዓተ ተፈጥሮ ነው፡፡ ትላንት እንደዚያ ነበረ፤ ዛሬም አለ፤ ነገም በአግባቡ ይቀጥላል፡፡” አላቸው፡፡
የፍጥረታትን ተዓምር እያደነቁ ወደመጡበት ተመለሱ፡፡
***
በዓለም ላይ በዚህም ቢሉት በዚያም ከመሆን የማይቀር ነገር አለ፡፡ መንግስታት ይለወጣሉ፤ አገሮች ባሉበት ይቆያሉ፡፡ የሚሠሩ ያገኛሉ፡፡ ዳተኞች ባዶ እጃቸውን ይቀራሉ፡፡ የሚጥሩ ዳር ይደርሳሉ፡፡ የተኙ ወደ ኋላ ይሄዳሉ፡፡ ይሄ ተፈጥሮአዊ የሆነው ነገር አይቀሬ ነው፡፡ ከኤሊ ጫጩቶች መካከል ተርፈው ለእናታቸው የሚኖሩ ጥቂቶቹ ይሁኑ እንጂ ይኖሩ ዘንድ የተፈቀደላቸው የታደሉ ናቸው፡፡ ያልታደሉት ባጭር ይቀጫሉ፡፡ ይህ ህግ ሁሌም የሚኖር ነው፡፡ ሰው የሚሰራው ነገር ተጨማሪ ነው፡፡ ያም ሆኖ
“አለ አንዳንድ ነገር
በዚህ ቢሉት በዚያ ከመሆን የማይቀር”  ይላሉ ደራሲ ከበደ ሚካኤል፡፡ በዚህ ውስጥ የተቃራኒዎች አንድነትና ትግል ሁሌም አይቀሬ ነው፡፡ ገዢው ፓርቲ መግዛቱን ለመቀጠል ተገዢዎች የኛም ፓርቲ የገዢነት ቦታ ሊኖረው ይገባል በማለት እስኪሸናነፉና እስኪለይላቸው ጉዞአቸውን ይቀጥላሉ፡፡
“ልምድን ከሩቅ ሆነህ አታየውም፤ ሲከሰት ግን መኖሩን ታውቃለህ” ይላሉ ፈረንጆች፡፡ ለመማር ዝግጁ የሆነ ባወቀው ይጠቀማል፡፡ አትማር ያለው ባወቀውም ይደነቁራል፡፡ በሀገራችን ብዙ ፓርቲዎች ተወልደዋል፡፡ ብዙዎች ሞተዋል፡፡ አንዳንዶች ቀንቷቸዋል፡፡ አንዳንዶች በአጭር ተቀጭተዋል፡፡ የሁሉም የጋራ ሀብት ግን ከኖሩት አለመማር ሆኖ ታዝበነዋል፡፡ አሸናፊው ድሉን ከማሸብረቅ በቀር የሄደበትን መንገድ ዳግመኛ ለመመርመር አይቃጣውም፡፡ ተሸናፊው ቂም በቀሉን ከማመንዠክ እና ጊዜ ከመጠበቅ በቀር ያለፈውን ሁኔታ አጥንቶ በወጉ ለነገ ለመዘጋጀት ከቶም ልቦና የለውም፡፡ ይህ ሀቅ ሁሌም ምርጫ በመጣ ቁጥር የሚያጋጥመው እውነታ ነው፡፡ ትላንት በምርጫው አሸናፊ ነኝ የሚለው ወገን ለአሸናፊነት ሁሌም የታጨሁና ሁሌም የሚሳካልኝ ነኝ የሚለውን አስተሳሰብ የማይለወጥ እውነታ አድርጐ መውሰዱን አይን ካለን እናያለን፡፡ በአንፃሩ ትላንት በምርጫው ተሸናፊ የሆነው ወገን ደግሞ በመጭበርበር ተሸነፍኩ እንጂ ልክ ነበርኩ የሚለውን ሃሳቡን ሳይለውጥ አምስት አመት ይኖራል፡፡ በኢትዮጵያ ሠርጉ ካልደረሰ በርበሬ አይቀነጠስም ይባላል፡፡ አድፍጦ፣ አሳቻ ጊዜ መርጦ ለማነቅ ጀግና መባል አንዱና ዋነኛው የትግል ዘዴ በሆነበት ሀገር፣ የዲሞክራሲ እውንነት ሁሌም ጥያቄ ውስጥ ነው፡፡
ያለ ዲሞክራሲያዊ መስተጋብር ህይወት የአዘቦት መንገዷን እንጂ የተለወጠ ጐዳና ወይም እግረ መንገድ እንኳ ልትቀዳጅ አይቀናትም፡፡ የትግሉን ሂደት ከማየት ይልቅ ስወለድም እንዲህ ነበርኩ ማለትም አጉል መመካት ነው ይሉናል አበው ጠበብት፡፡ እኛ ብቻ ነን ለዚህ ስልጣን የተቀባን የሚለው ሃሳብ ግዘፍ ነስቶ የምናየው ለዚህ ነው፡፡ ከዚህ ይሰውረን ብለን እናማትብ፡፡ አንድ የፖለቲካ ድርጅት በእውነትም ሆነ በውሸት ምርጫ ሲያሸንፍ “ፍፁም ስለሆንኩ አሸነፍኩ” የሚል አስተሳሰብ ውስጥ መዋኘቱ አይገርሜ ነው! ግቡን መምታቱ ያላጋጠሙትን አሊያም አጋጥመውት ያልዘገባቸውን መንሸራተቶችና መሰናክሎች ወይም ሰንካላ እድሎች እንዲረሳ የደረሰበት ወንበር ክፉ ንቀት ይሰጠዋል! ዛሬ እዚህ የደረስከው በሠራኸው ጥሩም፣ መጥፎም ነገር  ነው፡፡ የሚለውን ልብ አይልም፡፡ “መሠላል ያላንሸራተተው ሁሌ ጫፍ የሚወጣ ይመስለዋል” የሚለው ተረት ከላይ የተጠቀሰውን ሁሉ ያጠቃልላል፡፡
“ጥሩው ብቻ አይደለም እዚህ ያደረሰህ
መጥፎም ነው እኮ ያንተ ማንነትህ” እንደማለት ነው በግጥም ሲለገጥ፡፡