Administrator

Administrator

               በሩትገርስ ዩኒቨርሲቲና በሚቺጋን ዩኒቨርሲቲ በተካሄደ ጥናት፤ በትዳር ህይወት ውስጥ ከባልየው ይልቅ የሚስትየው ደስታ ለግንኙነታቸው ህልውና የበለጠ አስፈላጊ እንደሆነ ተረጋገጠ፡፡ ተመራማሪዎቹ በአማካይ ለ39 ዓመታት በትዳር የዘለቁ ጥንዶች ላይ ጥናት እንዳደረጉ ታውቋል፡፡ ጥንዶቹ የትዳር አጋሮቻቸው ያደንቋቸው፣ ይሞግቷቸው ወይም ያበሽቋቸው እንደሆነ የተጠየቁ ሲሆን በ24 ሰዓት ጊዜ ውስጥ በሚያከናውኗቸው የተወሰኑ ተግባራት - ለምሳሌ አስቤዛ መሸመት ወይም ቴሌቪዥን መመልከት … ምን ያህል ደስተኛ እንደሆኑ ተጠይቀዋል፡፡ አብዛኞቹ የጥናቱ ተሳታፊዎችም በትዳር ህይወታቸው ከፍተኛ እርካታ እንደሚሰማቸው ተናግረዋል፡፡ ሴቲቱ በባሏ ደስተኛ ከሆነች እሱም በአጠቃላይ ህይወቱ የበለጠ ደስተኛ ይሆናል - ስለትዳሩ የሚሰማው ስሜት ምንም ይሁን ምንም፤ ብሏል ጥናቱ፡፡
ከጥናት ፀሃፊዎቹ አንዷ የሆኑት ዲቦራህ ካር ለሩትገርስ እንደተናገሩት፤ “ሚስቲቱ በትዳሯ ስትረካ፣ ለባሏ የማታደርገው ነገር የለም፤ ይሄ ደግሞ በህይወቱ ላይ በጎ ተፅዕኖ ይፈጥራል ብዬ አስባለሁ፡፡ ወንዶች ስለትዳር ግንኙነታቸው ብዙም አያወሩም፤ ስለዚህም በትዳር ህይወታቸው ደስተኛ አለመሆናቸው ወደሚስቶቻቸው ላይጋባ ይችላል”
ሰውየው በትዳሩ ደስተኛ ካልሆነ፣ ሚስቱ ህይወቱን ብሩህ ለማድረግ የምታከናውናቸው ትናንሽ ነገሮች የደስታ እጦቱን ሊሸፍነው ይችላል፡፡ ወንዶች የጥናቱ ተሳታፊዎች ከሚስቶቻቸው ይልቅ ትዳራቸው መልካም ነው ብለው የሚያምኑ ሲሆን ትዳራቸው ከፍ ያለ ደረጃ ላይ እንደሆነ የሚያስቡ ተሳታፊዎች በሙሉ ግን በአብዛኛው የህይወት እርካታን የተጎናፀፉ ሆነው ተገኝተዋል - ያለምንም የፆታ ልዩነት፡፡

ተመራማሪዎቹ በጥናታቸው ያገኙት ሌላ ነገር ደግሞ ባሎች ሲታመሙ የሚስቶቻቸው ደስታ መጨመሩ ነው፡፡ ምክንያቱም ለባሎቻቸው እንክብካቤ የሚያደርጉት እነሱ በመሆናቸው ነው ተብሏል፡፡ በሌላ በኩል ሚስቶች ሲታመሙ ብዙ ጊዜ ለእርዳታ ፊታቸውን የሚያዞሩት ወደ ሴት ልጆቻቸው ነው፡፡ እናም የባሎች የደስታ መጠን ሳይለወጥ ባለበት ይቆያል፡፡ የትዳር ህይወት የጥራት ሁኔታና የደስታ መጠን ሰዎች ዕድሜያቸው እየገፋ ሲሄድ በጤናቸው ላይ ተፅዕኖ ያሳድራል፡፡ በዴቦራህ የጥናት ፅሁፍ  መሰረት፤ “ጥራት ያለው ትዳር አስፈላጊ ነው፤ ምክንያቱም በኋላ ዘመን ውጥረት ፈጣሪ ከሆኑ ጤና የሚያላሽቁ ተፅዕኖዎች መከላከያ ጋሻ ያጎናፅፋል፤ እንዲሁም ጥንዶች ጤናና ህክምናን የተመለከቱ አስቸጋሪ ውሳኔዎችን በቅጡ ለመወሰን ያግዛቸዋል፡፡”
በእናንተ የትዳር ግንኙነት በጥናቱ የተመለከተው ዓይነት ውጤት ገጥሟችኋል? ቢያንስ በግል ካስተዋልኩት፤ በትዳር ግንኙነታቸው ደስተኛ የሆኑ ሴቶች ለትዳር አጋሮቻቸው ተጨማሪ በጎ ነገር ለማድረግ ከመንገዳቸው እንደሚወጡ ተገንዝቤአለሁ፡፡ ይሄ ማለት ግን ወንዶች እንዲህ መሰሉን ነገር አያደርጉም ማለት አይደለም፡፡ ከዚህ ጥናት የምንረዳው አንድ ዋና ቁም ነገር፣ ሚስት ደስተኛ ስትሆን የትዳር ህይወት የሰመረ እንደሚሆን ነው፡፡ ንግስቲቷ ደስተኛ ስትሆን፣ መላው ቤተሰብ ደስተኛ ይሆናል እንደማለት!!

Monday, 06 October 2014 08:15

ማራኪ አንቀፅ

          ከአዋሳ እርሻ ኮሌጅ በዲፕሎማ ከተመረቅሁ በሁዋላ እዛው ከተማ 75 ዓመተምህረት ላይ በማውቀው ሰው እርዳታ ግብርና ሚኒስቴር ተቀጠርኩ፡፡ ‘አዲስ አበባ እንመድብሽ’ ቢሉኝም አልሄድም ነበር፡፡ አዲስአባን ጠላሁዋት፡፡ በቦዲ ሚሞሪ (የገላ ትውስታ ወይም የገላ ትዝታ) ይመስለኛል፡፡ ቦዲ ሚሞሪ (Body Memory) በአንጎል ውስጥ ብቻ ሳይሆን በሌላ የአካል ክፍል ውስጥም (በጡንቻ፣ በልፋጭ፣ በሞራ፣ በጉበት፣ በሳንባ ወዘተ) ትውስታ ሲከማች ማለት ነው፡፡ የፖለቲካ ጉዳዩ ከሽሮሜዳው አላዛር ጋር ተደርቦ አዲስአባን ስጠላ ትንሽ ልክ አይደለም፡፡ ባቡር ጣቢያ ምን አደረገኝ? በቅሎ ቤትና መካኒሳ ምን አደረጉኝ? እናቴ ለምን አዲስአባ እንደማልመጣ ስትጠይቀኝ  “እማመጃ ሙች መንግስት በእጣ ልመድብ እያለ አዋሳ ደረሰኝ፤ ገንዘብ ከፍዬ እንኳን የሚለውጠኝ አላገኘሁም፡፡ ምስክር ካስቸገረችሽ በደንብ ስቋቋም እወስዳታለሁ” አልኳት እማማ ‹ኸረ ለልጅቷ አይደለም፤ በሰራተኛ ከምታድግ ከእኔ ጋ ትሆናለች፡፡

ይሄን ደርግ የተባለ በጥባጭ ማን ላከብን እመቤቴ› ምናምን ምናምን፡፡ በልቤ የፈለግሽውን በይ እላለሁ፡፡ የአገራችን ምስክር መሃላ ነው፡፡ እንዋሽና እንምላለን፡፡ የማንምልበት የለም፡፡ ልብ ያልኩት እንዲህ ስገባበት ነው፡፡ በእግዚአብሔር እንምላለን፤ በሃይለስላሴ እንምላለን (ከንጉሠ ነገሥቱ የሚቀረው ጢማቸው ነው፣ እና ቀን ጠብቀንም ከተመቸን በጢማቸውም እንምላለን)፣ በመላእክት፣ በአባት፣ በእናት፣ በምንወደው ሰው፣ በደርጉ፣ በልባችን፣ በሳንባችን፣ በባላችንና በሚስታችን እንምላለን፡፡ በዚህ በዚህ ተለማምጄ ምናልባት በፋሲል እምላለሁ፤ በፋሲል ፔርሙስም እምላለሁ፡፡ ወደ አዋሳ ለመሄድ አንዳንድ እቃዎቼን በሻንጣ ስከት ያገኘሁዋቸውን የማርኪሲስት መፅሀፍት ለማድቤት እሳት ወረወርኩ፡፡ እስር ቤት ሙላት የሰጠኝን ያማረች ቅል እንዳትሰበርብኝ በጥንቃቄ በወረቀትና በላስቲክ ጠቅልዬ በልብሶቼ መሃል ወሸቅሁዋት፡፡ ድሮ አበባና ተክሎችን ከሰበሰብኩባቸው ሶስት አልበሞቼ አንዱን ብቻ አገኘሁ፡፡

ታስሬ ከተወሰድኩ በኋላ በበነጋታው ፈታሾች እኔን የሚወነጅሉበት ጸረ-አብዮት ወረቀት ሊያገኙ ሲበረብሩ እንደነበር ተነግሮኛል፡፡ የቀሩትን በርባሪዎቹ እንደወሰዱአቸው አውቃለሁ፡፡ ቢያበሳጭም ምን ይደረጋል? “ምን አውቃለሁ የሆነ ወረቀት ሰብስበው ሄዱ” አለች እማማ፤ ቀኑ ሲያልፍ፡፡
አላለፈም፡፡ በልጅነቴ የለፋሁበት ሲጠፋ ሃዘን አይገባኝም አሉ? ሃዘን ካለ የአልበሞቼ ትዝታ አለ ማለት ነው፡፡ ሁሉም አልበሞቼ ገና እኔ ውስጥ አሉ፡፡ ትንሽ ተቀምጬ ከትውስታዬ ሊጠፋ የጀመሩ አትክልቶችን እየገለጥኩ አየሁ፡፡ የመፅሀፉ ጠረን መስከረም ወር ውስጥ እንደሚያጋጥም የእንጦጦ ሸለቆ ነው፡፡ መጨረሻው ገፅ ላይ አንድ ጠጅ ሳር አገኘሁ፡፡ ገና በጣቴ ስነካካው ፈራረሰ፡፡ መደርደሪያዬ ላይ ደሞ ምናልባት ከሰባት አመታት በፊት አላዛር ለልደት ቀኔ የሰጠኝን አንድ ዳልሜሽያን የውሻ አሻንጉሊት አገኘሁ፡፡ ወደ ግድግዳ ገፋ ተደርጋለች፡፡ አቧራ ለብሳለች፡፡ በአዲስነቷ በጥቁር ነጠብጣቦች የተሸፈነች በረዶ ነጭ ነበረች፡፡ አይኖቿ ጥቁር ሆነው በዙሪያቸውን አረንጓዴ ናቸው፡፡ አፍንጫዋ ጥቁር ነው፡፡ ጅራተ ጎራዳ ናት፡፡ አልጋዬ ላይ በጀርባዬ ስሆን ሳታቋርጥ ታየኝ ነበር፡፡ አስተያየቷ ያባባል፡፡ ቆሻሻዋን አራግፌ ሻንጣዬ ውስጥ ከተተትኳት፡፡
አቶ አባይ አዋሳ አደርሳታለሁ ስላሉ ሳሎን ተቀምጬ እሳቸውን ስጠብቅ ቆይቼ፣ ሰልችቶኝ መኝታ ቤት ስገባ፣ እማማ ሻንጣዬን ስትበረብር አገኘሁዋት፡፡ በቀኝ እጅዋ ዳልሜሽያን አሻንጉሊቷን ይዛለች፤ ቀና ብላ በማዘን አየችኝና ምንም ሳትናገር እነበረችበት አመቻችታ አስቀመጠቻች፡፡ አፍሬ ወደ ሳሎን ተመለስኩ፡፡ አለሁበት መጥታ ምንም ነገር እንዳልሆነ፡፡
“አባይ የት ጠፋ? እያረጀ ሲሄድ ቀጠሮ መርሳት ጀመረ?” አለች፡፡ አልመለስኩላትም፡፡
አጠገቧ እግሮቿ ስር በጉዞዬ አውቶቡስ ውስጥ የምበላቸው ብርቱካኖች ሙዞች ተደጋግፈው ተቀምጠዋል፡፡ ብርቱካኑ ቅጠልያ ቀለሙ አልተወውም፡፡ ሎሚ አስተኔ ቆምጣጣ ሳይሆን አይቀርም፡፡ ፍራፍሬ ኮርፖሬሽን ቤመንገዱ ድንኩዋን ተክሎ ኪሎው በሁለት ብር ካምሳ ከሚሸጠው ከእማማ ገዝታ ነው፡፡ ከነዚህ ጎን ደሞ ገና አረንጓዴነቱ ያለቀቀው ጥሬ ሙዝ አለ፡፡ እማማ ከመስሪያቤቷ ስትወጣ፣ የስራ ጓደኛዋ ልጅሽን ደህና ግቢ በይልኝ ብላ የላከችልኝ ነው፡፡ ከሴትዬዋ አልቀራረብም፡፡ ሙዞቹ ጥሬ ከመሆናቸው የተነሳ እያንዳንዳቸው ሁለት ሁለት ጠንከራ ሰረሰሮች አሉዋቸው፡፡ ስድስቱም አንድ አንጓ ላይ እንደ ደራጎን ጥርስ ተደርድረዋል፡፡
እማማ የላስቲክ ቀረጢቱን በእግሯ እየነካካች ታስባለች፤ ስለ እኔ ጉዞና ሰፈር ስለመቀየር ይሁን ስለ አባይ እንጃ፡፡ እኔ መሄዴ ነው፡፡ እማማ ብቻዋን መኖር የምትችል አይመስለኝም፡፡ ከአባይ ጋር ለምን እንደማይጋቡ አይገባኝም፡፡ አሻንጉሊቴን ባታይብኝ ኖሮ ትዳር ስለመመስረት እጠይቃት ነበር፡፡ ግን፤“አንቺስ አሻንጉሊት ከመሰብሰብ አላዛርን ጠበቅ አታደርጊም ነበር” ብትለኝስ ብዬ ተውኩት፡፡ በየቀኑ በደም ስሬ፣ በልቦናዬ ደካማ የሚያደርገኝን ነገር የምሰበስብ ይመስለኛል፡፡----
(ከደራሲ አዳም ረታ
መረቅ የተሰኘ አዲስ ረዥም ልብወለድ
መጽሃፍ ውስጥ የተቀነጨበ፤2007 ዓ.ም)

Monday, 06 October 2014 08:13

እንቆቅልሽ?

ወደታች የሚወርድ፣ ወደላይ ግን የማይወጣ?
በወጣትነቴ ረዥም ነኝ፡፡ ሳረጅ አጭር እሆናለሁ፡፡ ማን ነኝ?
የሜሪ አባት አምስት ሴት ልጆች     አሏቸው፡፡ ናና፣ ኔኔ፣ ኒኒ፣ ኖኖ ይባላሉ፡፡ የአምስተኛዋ ልጃቸው     ስም ማነው?
ካለኝ ለሰው አላካፍለውም፡፡ ለሰውካካፈልኩት አይኖረኝም፡፡ ምንድነው?
ሰውየው ከባድ መኪና እየነዳ ነው፡፡ የፊት መብራት አላበራም፡፡ ጨረቃም አልወጣችም፡፡
ከፊት ለፊቱ አንዲት ሴት መንገድ ታቋርጣለች፡፡እንዴት አያት?

====================


መልስ
ዝናብ
ሻማ
ሜሪ
ምስጢር
ብሩህና ፀሐያማ ቀን ነበር

(የወላይታ ምሳሌያዊ አነጋገር)

ከዕለታት አንድ ቀን አንዲት ዶሮና አንድ አውራ ዶሮ ወደ አንድ ፍሬ ወደ ሚገኝበት ተራራ ይወጣሉ፡፡ አንድ ስምምነት እንዲያደርጉም መነጋገር ጀመሩ፡-
አውራ ዶሮ ---------- እመት ዶሮ
እመት ዶሮ ---------- አቤት አያ አውራ ዶሮ
አውራ ዶሮ ------- አንድ ነገር እንስማማ
እመት ዶሮ -------- ምን አሰብክ ወዳጄ?
አውራ ዶሮ -------- ምንም ዓይነት ፍሬ ብናገኝ አንዳችን ላንዳችን እናካፍል
እመት ዶሮ ----- በሃሳቡ እስማማለሁ፡፡ ድንቅ መርህ ነው!
በዚህ ስምምነት ፀንተው ያን ተራራ ተያያዙት፡፡ ከሰዓታት በኋላ እመት ዶሮ አንድ ትልቅ ፍሬ አገኘች፡፡ ግን ስለማግኘቷ አንዲትም ቃል ትንፍሽ ሳትል መንገድ ቀጠለች፡፡ አንድ አሳቻ ቦታ ስትደርስ፣ ዘወር ብላ ፍሬውን ልትበላ ሞከረች፡፡ ሆኖም ፍሬው በጣም ትልቅ በመሆኑ አልዋጥ አላት፡፡ አንቆ የሚገላት መስሎ ስለተሰማት፣ በጣም ደነገጠች
“አያ አውራ ዶሮ! አያ አውራ ዶሮ!” ስትል ጮኸች፡፡
አውራ ዶሮም፤ “ምነው? እመት ዶሮ ምን ሆንሽ?” አላት፤ ካለበት ሆኖ፡፡
“እባክህ ትን ብሎኝ ልሞት ነውና ውሃ ፈልገህ አምጣልኝ”
አውራ ዶሮው በአቅራቢያው ወደሚገኝ አንድ የውሃ ጉድጓድ ሄዶ፤ “ጉድጓድ ሆይ! እባክህ እመት ዶሮ ልትሞትብኝ ነውና ትንሽ ውሃ ስጠኝ?” ሲል ጠየቀው፡፡
ጉድጓዱም፤ “መስጠት እሰጥሃለሁ፡፡ ግን በመጀመሪያ ከዕለታት አንድ ቀን የአፌ መሸፈኛ የሆነውን ቀይ ሀር ጨርቅ፣ እመት ዶሮ ሰርቃ ወስዳብኛለችና ከጌታዋ ቤት ሄደህ አምጣልኝ” አለው፡፡
አውራ ዶሮው አሁንም የዶሮ ጌታው ዘንድ እየበረረ ሄዶ፤
“ጌታዬ፤ እመት ዶሮ በውሃ እጦት ልትሞት ቢሆን፤ ጉድጓድን ውሃ ስጠኝ ልለው ሄድኩ፡፡ እሱም ወደ ጌታዋ ዘንድ ሄደህ የሰረቀችኝን ሀር አምጣ አለኝ፡፡ እባክዎ ሀሩን ይስጡኝና ውሃ ላግኝላት?” ሲል ጠየቀው፡፡
ጌትዬውም፤ “በመጀመሪያ ከቤት ሰርቃ የወሰደችውንና ለዶሮ ጠባቂው የሰጠችውን ሰዓት አስመልስልኝ” አለው፡፡
አውራ ዶሮ ሲበር ሄዶ ዶሮ ጠባቂውን ለመነውና ሰዓቱን አስመልሶ ለጌትዬው መለሰ፡፡ ቀዩን ሀር ተቀብሎ ለጉድጓዱ ሰጠ፡፡ ውሃውንም ከጉድጓዱ ወስዶ ለዶሮዋ ሊሰጥ ወደ ተራራው ወጣ፡፡ እዚያ ሲደርስ ግን እመት ዶሮ ለአንዴም ለሁሌም አሸልባለች፡፡
                              *           *         *
አበው “ብቻውን የበላ ብቻውን ይሞታል” ይላሉ፡፡ አንድም ደግሞ “ሥራ ለሰሪው እሾህ ለአጣሪው” ይላሉ፡፡ የሰራነው ሥራ እስከ እለተ ሞታችን ድረስ ይከተለናል፡፡ እያንዳንዷ ዱካችን የማታ ማታ ተከትላ ታጋልጠናለች፡፡ የሙስና የመጨረሻ ፍፃሜ እንደዶሮይቱ በተያያዘ ጥፋት ዋጋ መክፈል ነው፡፡ Domino effect እንዲሉ ፈረንጆች፡፡ አይታወቅብኝ በሚል በአልጠግብ ባይነት በአሳቻ ቦታና ሰዓት የመነተፍነው የህዝብ ንብረትና ንዋይ፣ አንድ ቀን ክፉ ቦታ ላይ እንደሚጥለን እንገንዘብ፡፡ ቃልን ማፍረስ፣ የሀገርን ሀብት መበዝበዝ፣ የሀገርን ክብር ማዋረድ፤ ሁሉም ዓይነት ሙስናዎች የማታ ማታ ያስጠይቃሉ፡፡
የተጠርጣሪዎች መብዛት፣ ከስራ መባረሮች፣ የጥርጣሬና ፍርሃት መንገስ፣ ከተሾሙበት ስልጣን መባረር መብዛት ወዘተ ሁሉም የሙስና መገለጫዎች ናቸው፡፡ ስለሆነም የተገለጠ ዐይን ይፈልጋሉ፡፡ ይህንን ለማስተካከል አንጋረ ፈላስፋ የሚለንን ማዳመጥ መልካም ነው፡-
“ንጉሥ ሦስት ነገሮችን ገንዘብ ማድረግ ይገባዋል፡-”
1ኛ/ ዐዋቂዎቹን አክብሮ መያዝ
2ኛ/ ለተቸገሩት መስጠትና በማናቸውም መርዳት
3ኛ/ ህዝቡን በቅንነትና በርህራሄ ማስተዳደር፡፡”
    ቀጥሎም እንዲህ ይለናል፡-
“ብልህ ዐዋቂ ሰው፣ አንደበቱ የልቡ አማካሪ ነው፡፡ መናገር ሲያምረው አስቀድሞ በልቡ ያወጣ ያወርድና፣ ለመናገር መንገድ ሲያገኝ ይናገራል፣ ባያገኝ ግን ዝም ይላል፡፡ ቁም ነገሩ ይኸው በጎውንና ክፉውን ለይቶ መናገር ነው” ስለዚህም ነው የሙስናን ጣራ መንካት ደጋግመን ስንናገር የከረምነው፡፡ ዛሬም ያንኑ የሙስና መንገድ የሚከተሉ አያሌ ናቸው፡፡ የሌሎች መጠርጠር፣ የሌሎች መታሰር የማያስደነግጣቸው አያሌ ናቸው፡፡ የሚሰነዘረው በትር የማቀፍ ያህል ፈገግ የሚያሰኛቸው በሺዎች የሚቆጠሩ ናቸው፡፡
“ጉርሻ የለመደች ሴት በጥፊ ሊመቷት እጅ ሲያነሱ አፏን ትከፍታለች፡፡” የሚለው የወላይታ ተረት የሚነግረን ይሄንኑ ነው፡፡
ኢድ ሙባረክ!

  • በዋሺንግተን የኢትዮጵያ ኤምባሲ መሳሪያ የተኮሰው

 የፀጥታ ሰራተኛ ወደ ኢትዮጵያ ተመለሰ

በሳምንቱ መጀመሪያ ዋሺንግተን ዲሲ በሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ላይ በዳያስፖራ ተቃዋሚዎች የተደረገውን ጥሰት ተከትሎ፣ ባለፈው ረቡዕም በስዊድን የኢትዮጵያ ኤምባሲ ላይ በተቃዋሚዎች ተመሳሳይ የጥሰት ሙከራ መደረጉን ምንጮቻችን ለአዲስ አድማስ ገለፁ፡፡ በስዊድን ስቶክሆልም በሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ላይ ባለፈው ረቡዕ የዳያስፖራ ተቃዋሚዎች ተመሳሳይ የጥሰት ድርጊት ለመፈፀምና በስዊድን የኢትዮጵያ አምባሳደር ወይንሸት አሰፋ ላይ ለሁለተኛ ጊዜ ጥቃት ለማድረስ እንደሞከሩ የጠቆሙ ምንጮች፤ የፀጥታ ሃይሎች ደርሰው ሙከራውን እንዳከሸፉት ገልፀዋል፡፡
በአሜሪካ የኢትዮጵያ ኤምባሲን ቅጥር ግቢ  ጥሰው ከገቡ የዳያስፖራ ተቃዋሚዎች ጋር በተፈጠረ አተካሮ መሳሪያ ወደ ላይ የተኮሰው የኤምባሲው የፀጥታ ሰራተኛ ያለመከሰስ መብቱን ተጠቅሞ ወደ ኢትዮጵያ መመለሱን የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የፕሬስ ኃላፊ ጄን ሳኪ አስታወቁ፡፡
ባለፈው ሰኞ  የተወሰኑ ያለ የዳያስፖራ ተቃዋሚዎች የኢትዮጵያ ኤምባሲ ቅጥር ግቢ ጥሰው መግባታቸውን ተከትሎ በተፈጠረ አምባጓሮ ሰለሞን ገብረስላሴ (በቅፅል ስሙ ወዲ ወይን) የተባለው የኤምባሲው የፀጥታ ሰራተኛ መሳሪያ በመተኮሱ፣ የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የግለሰቡ ያለመከሰስ መብት ተነስቶ ጉዳዩ በአሜሪካ ፍርድ ቤት እንዲታይ ጥያቄ ያቀረበ ሲሆን ጥያቄው በኢትዮጵያ መንግስት በኩል ተቀባይነት ባለማግኘቱ ወደ አገሩ እንዲመለስ ተደርጓል ተብሏል፡፡ በተመሳሳይ ምክንያት ከአሜሪካ የወጣ ማንኛውም ዲፕሎማት ወደ አሜሪካ መመለስ የሚችለው ክሱ በፍርድ ቤት እንዲታይ ብቻ ነው፡፡
በዋሺንግተን ዲሲ በሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ላይ በዳያስፖራ ተቃዋሚዎች የተፈጸመውን ጥሰት እንዲሁም የኤምባሲውን ደህንነት ጉዳይ በተመለከተ በአዲስ አበባ ለሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ ላቀረብነው ጥያቄ፣ የኤምባሲው የኢንፎርሜሽንና ፕሬስ ኃላፊ ካትሪን ዲዮፕ በሰጡት ምላሽ፤ “በኢትዮጵያ ኤምባሲ ላይ በግለሰቦች በተፈፀመው ድርጊት በጣም አዝነናል፤ ነገር ግን ጉዳዩ በምርመራ ላይ በመሆኑ አስተየያየት መስጠት አንችልም፣ በዋሽንግተን ዲሲና በሌሎች ግዛቶች ለሚገኙ ኤምባሲዎች ደህንነት አሜሪካ ትኩረት እንደምትሰጥ እናረጋግጣለን” ብለዋል፡፡ የኢትዮጵያ መንግስት በአዲስ አበባ ለሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ የሚያደርገውን ጥበቃ በእጅጉ እንደሚያደንቁም ኃላፊዋ ተናግረዋል፡፡
ከትናንት በስቲያ የውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ በፅህፈት ቤታቸው ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፤ በአሜሪካ የኢትዮጵያ ኤምባሲ መጣስንና መሳሪያ ስለተኮሰው የሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ባልደረባ ተጠይቀው፣ “በአሁኑ ወቅት ጉዳዩን አስመልክቶ ሙሉ ስዕል የለኝም” በማለት ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ በጉዳዩ ላይ አስተያየት እንዲሰጡን ሌሎች የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር ሃላፊዎችን ለማግኘት ያደረግነው ተደጋጋሚ ሙከራ አልተሳካም፡፡  በሰሞነኛ አበይት ጉዳዮች ላይ ትንታኔ የሚሰጠው የሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ድረ ገፅም ማተሚያ ቤት እስከገባንበት ሰዓት ድረስ በጉዳዩ ላይ ያለው ነገር የለም፡፡

          በአሁን ወቅት ወደ 300 የሚሆኑ የአውሮፓ ኩባንዎች በኢትዮጵያ በተለያዩ የኢንቨስትመንት መስኮች የተሰማሩ ሲሆን የአውሮፓ ኩባንያዎችን ይበልይ ወደ ሃገር ውስጥ ለመሳብ ጥረት እተደረገ ነው ተብሏል፡፡ “የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንትና ቢዝነስ ማነቃት በሚል መርህ በአውሮፓ ህብረት ኢትዮጵያ ልኡክ እና በህብረቱ የቢዝነስ ዶርም አዘጋጅነት በአዲስ አበባ ሂልተን ሆቴል በትናንትናው እለት ኢግዚብሽንና ኮንፈረንስ የተካሄደ ሲሆን በሃገሪቱ ተፈትሸዋል፡፡
የኮንፍረንሱ ዋነኛ አላማ አውሮፓ ህብረት እና የኢትዮጵያ የቢዝነስ ባለድርሻ አካላት በኢትዮጵያ ስላለው የቢዝነስ እና ኢንቨስትመንት አማራጭ እና ለችግሮቹ መፍትሄ በሚሆኑ ጉዳዮች ላይ ለመወያየት የነበረ ሲሆን በእለቱም የመንግስት ከፍተኛ ባለስልጣናት ተገኝተዋል፡፡ በኮንፈረንሱ ላይም በሃገሪቱ ለአውሮፓ ባለሃብቶች ተግዳሮት ናቸው በተባሉት ታክስ፣ ንግድ ፍቃድ፣ ግብር እና የውጭ ምንዛሬ ጉዳይ ላይ ሰፊ ውይይት ተካሂዷል በእለቱ ኢትዮጵያ የውጭ ኢንቨስትመንትን ለመሳብ በምታደርገው ጥረት ላይ ሰፊ ውይይት የተካሄደ ሲሆን ከንግድ ፍቃድ ጋር ተያይዞ ይውጭ ባለሃብቶች የሚያጋጥማቸው ተግዳሮቶች በስፋት ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡

ወላጆች የጥርሳቸውን ጤንነት ሊከታተሉላቸው ይገባል

የእንግሊዝ የማህበረሰብ ጤና ተመራማሪዎች፤ 54ሺ ገደማ የሚሆኑ ህፃናትን ጥርሶች ከመረመሩ በኋላ 12 በመቶ በሚሆኑት ህፃናት ላይ የጥርስ መበስበስ ምልክቶችን እንዳገኙ ይፋ አደረጉ፡፡ ህፃናቱ በአማካይ ሶስት ጥርሶቻቸው አንድም በስብሰዋል አሊያም ወልቀዋል ወይም ደግሞ ተሞልተዋል ብለዋል ተመራማሪዎቹ፡፡ ከቦታ ቦታ የጥናት ውጤቱ ከፍተኛ ልዩነት ያሳየ ሲሆን በሌችስተር አካባቢ 34 በመቶ ያህሉ ህፃናት የጥርስ መበስበስ ሲስተዋልባቸው በሌሎች አካባቢዎች ደግሞ 2 በመቶ ያህሉ ብቻ የችግሩ ተጠቂዎች መሆናቸው ታውቋል፡፡
አንዳንድ ህፃናት ገና በለጋ ዕድሜ ላይ የሚከሰት የተለየ ዓይነት የጥርስ መበስበስ እንደተገኘባቸው ተመራማሪዎቹ ተናግረዋል፡፡
ይሄ ችግር የሚያጠቃው የላይኛውን የፊት ጥርሶች ሲሆን በፍጥነትም ወደ ሌሎች ጥርሶች የሚሰራጭ እንደሆነ ታውቋል፡፡
እንዲህ ዓይነቱ የጥርስ መበስበስ ችግር በጡጦ ወይም በኩባያ ጣፋጭ አሊያም ስኳር የበዛባቸው ፈሳሾችን በመውሰድ የሚከሰት ነው ተብሏል፡፡
የእንግሊዝ የማህበረሰብ ጤና ተመራማሪዎች፤ ወላጆች ለልጆቻቸው ጣፋጭ ምግቦችንና መጠጦችን አልፎ አልፎና በጣም በትንሹ መስጠት እንዳለባቸው ተናግረዋል፡፡ የእናት ጡት ያቆሙ ህፃናት በሚወስዷቸው ምግቦችና መጠጦች ላይም ስኳር እንዳይጨምሩ ለወላጆች ምክራቸውን ለግሰዋል፡፡
ወላጆችና ሞግዚቶች፤ ህፃናቱ የመጀመሪያ ጥርሳቸውን እንዳበቀሉ መቦረሽ መጀመር አለባቸው የሚሉት የህክምና ባለሙያዎች፤ ልጆቹ ሰባት ወይም ስምንት ዓመት እስኪሆናቸው ድረስም የጥርስ ንፅህና አጠባበቃቸውን መቆጣጠር እንዳለባቸው ጠቁመዋል፡፡

በእድሜያቸው የገፉ ሰዎችን የማሽተት ችሎታ በመለካት፣ በቀጣይ በህይወት የሚቆዩበትን ጊዜ ለመተንበይ እንደሚቻል በአሜሪካ የቺካጎ ዩኒቨርሲቲ ተመራማሪዎች የተሰራ ጥናት ማረጋገጡን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
ተመራማሪዎች ከ57 እስከ 85 አመት እድሜ ክልል ውስጥ በሚገኙ 3ሺህ ሰዎች ላይ ያደረጉትን ጥናት ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ ጥሩ የማሽተት ችሎታ ያላቸው ሰዎች፣ የማሽተት ችሎታቸው ዝቅተኛ ከሆኑ ሰዎች ጋር ሲነጻጸር ቀጣዮቹን 5 አመታት በህይወት የመቆየት ዕድላቸው ከፍ ያለ ነው፡፡
ጥናቱ በተከናወነባቸው ሰዎች ላይ የተመዘገበው ውጤት እንደሚያሳየው፣ ዝቅተኛ የማሽተት ችሎታ ካላቸው ሰዎች መካከል 39 በመቶ የሚሆኑት በአምስት አመት ጊዜ ውስጥ ሲሞቱ፤ ጥሩ የማሽተት ችሎታ ካላቸው ሰዎች መካከል በተመሳሳይ ጊዜ ውስጥ የሞቱት 10 በመቶው ብቻ ናቸው፡፡
ተመራማሪዎቹ ለግለሰቦቹ የአሳ፣ የብርቱካን፣ የጽጌረዳ አበባ፣ የቆዳና የናና መዓዛዎችን በእስክርቢቶ ጫፍ ላይ በማድረግ እንዲያሸቱና የምን መዓዛ እንደሆነ እንዲለዩ በመጠየቅ የማሽተት ችሎታቸውን መዝግበዋል፡፡ ከአምስት አመታት በኋላም፣ ጥናቱ ከተሰራባቸው ሰዎች፣ ምን ያህሉ በህይወት እንዳሉና ምን ያህሉ እንደሞቱ አረጋግጠዋል፡፡ በመቀጠልም የሞት መጠኑን ከማሽተት ችሎታ ጋር በማጣመር፣ በሁለቱ ነገሮች መካከል ያለውን ግንኙነት ለማጥናት ሞክረዋል፡፡
የማሽተት ችሎታ እየቀነሰ መምጣት በቀጥታ ለሞት እንደማይዳርግ የተናገሩት ተመራማሪዎቹ፣ ይሄም ሆኖ ግን ክስተቱ እንደማስጠንቀቂያ ሊወሰድ እንደሚችል ገልጸዋል፡፡
“የማሽተት አቅም መቀነስ በቀጥታ ለሞት አይዳርግም፡፡ ይሄም ሆኖ ግን በግለሰቡ ጤንነት ላይ ጉዳት እንደደረሰ የሚያመላክት ቅድመ ማስጠንቀቂያ ነው፡፡ በምርምሩ ያገኘናቸው ውጤቶች በጤና ምርመራ ላይ እገዛ የሚያደርጉ ናቸው፡፡ ለአደጋ የመጋለጥ እድላቸው ከፍተኛ የሆኑ በሽተኞችን ለይቶ ለማወቅ የሚያግዝ ፈጣንና ወጪ የማይጠይቅ የምርመራ ዘዴ ሆኖ ሊያገለግል ይችላል” ብለዋል የተመራማሪ ቡድኑ መሪ የሆኑት ፕሮፌሰር ጃያንት ፒንቶ፡፡
በህይወት የመቆየት ዕድልን የሚወስኑ እርጅና፣ የምግብ አወሳሰድ፣ የሲጋራ ሱሰኝነት፣ ድህነትና አጠቃላይ የጤና ሁኔታን የመሳሰሉ ጉዳዮች እንዳሉ ሆነው፣ የማሽተት ችሎታቸው በጣም ዝቅተኛ የሆኑ ሰዎች ለሞት የመዳረግ እድላቸው ከፍተኛ እንደሆነ ተመራማሪዎቹ ተናግረዋል፡፡
ይሄም ሆኖ ግን የማሽተት ችሎታ መቀነስ፣ በምን መንገድ በህይወት ላለመቆየት እድል አስተዋጽኦ እንደሚያበረክት በግልጽ ባይታወቅም፣ ተመራማሪዎቹ በሁለቱ መካከል ያለውን ግንኙነት በተመለከተ የራሳቸውን ሃሳብ ሰንዝረዋል፡፡
አነስተኛ የማሽተት ችሎታ መኖር፣ በግለሰቦች ሰውነት ውስጥ የሚገኙ ያረጁ ህዋሶች የሚታደሱበት መጠን አነስተኛ መሆኑን ሊያመላክት ይችላል ብለዋል ተመራማሪዎቹ፡፡ ጤናማ የማሽተት ችሎታ እንዲኖር ከሚያደርጉ ነገሮች መካከል፣ በአፍንጫ ውስጥ የሚገኙ ህዋሳት በየጊዜው መታደሳቸው ይጠቀሳል ሲሉም ተናግረዋል፡፡
ሰዎች ዝቅተኛ የማሽተት ችሎታ ስላላቸው መጨነቅ እንደሌለባቸው የመከሩት ፕሮፌሰር ፒንቶ፤ ጉዳዩ ከጉንፋን፣ ከአለርጂክና ሳይነስን ከመሳሰሉ የጤና ችግሮች ጋር የተያያዘ ሊሆን እንደሚችልም ተናግረዋል፡፡ የማሽተት ችግሩ እየተባባሰ ከመጣ ግን፣ ሃኪማቸውን ማማከር እንደሚገባቸው ገልጸዋል፡፡
የካርዲፍ ዩኒቨርሲቲ ባልደረባ የሆኑትና በጥናቱ ውስጥ ያልተሳተፉት ፕሮፌሰር ቲም ጃኮብ በበኩላቸው፤ በጥሩ ሁኔታ የተከናወነው ይህ ጥናት፣ የማሽተት ስሜትና ጤንነት በእጅጉ እንደሚቆራኙ ያመላከተ ነው ብለዋል፡፡
በሰውነት አጠቃላይ ሁኔታና በስነ-ልቦና መካከል ትስስር እንዳለ የጠቆሙት ጃኮብ፤ ለአብነትም ማሽተት አለመቻል ድብርት እንደሚፈጥር፣ ድብርትም በመስማት ችሎታ ላይ ተጽዕኖ ሊፈጥር እንደሚችል ገልጸዋል፡፡

             በዓለም ላይ ከሚገኙ አገራት የትኞቹ ዕድሜያቸው ለገፉ አዛውንቶች ህይወት ምቹ እንደሆኑ ለማወቅ በ96 አገራት ላይ በተካሄደ ጥናት፣ ኖርዌይ ለአዛውንቶች ጤናማ ህይወት ቁጥር 1 ተመራጭ አገር ስትሆን አፍጋኒስታን በመጨረሻ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች፡፡ የኸልፕኤጅ ኢንተርናሽናል ግሎባል ኤጅዎች ኢንዴክስ፤ ዕድሜያቸው ከ60 በላይ የሆናቸው አዛውንቶችን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ደህንነት (ዋስትና) በመለካት ነው የአገራቱን ደረጃ ያወጣው፡፡ በተባበሩት መንግስታት የአዛውንቶች ቀን መፅሄት ላይ በወጣው መረጃ መሰረት፤ አውስትራሊያ፣ ምዕራብ አውሮፓና ሰሜን አሜሪካ እድሜያቸው ለገፉ ዜጎች እጅግ ምቹ አገራት መሆናቸው የተረጋገጠ ሲሆን አፍጋኒስታን ግን ለአዛውንቶች ህይወት የማትመች መሆኗ በጥናቱ ተጠቁሟል፡፡

እ.ኤ.አ በ2050 ከዓለም ህዝብ ውስጥ 21 በመቶ ያህሉ ዕድሜያቸው ከ60 ዓመት በላይ የሆኑ አዛውንቶች እንደሚሆኑ ሪፖርቱ ተንብይዋል፡፡ የኑሮ ምቹነትን የሚጠቁመው ኢንዴክስ፤ አራት ዘርፎችን የሚመዝን ሲሆን እነሱም የገቢ ዋስትና፣ ጤና፣ ግለሰባዊ አቅምና ሰውየው ሴትየዋ የሚኖሩት በ“ምቹ አካባቢ” ነው አይደለም የሚሉት ናቸው፡፡ ለአዛውንቶች ምቹ የመኖርያ ሥፍራ በመሆን በቀዳሚነት ከተጠቀሰችው ኖርዌይ ቀጥሎ ስዊድን፣ ስዊዘርላንድ፣ ካናዳና ጀርመን ይከተላሉ፡፡ በጥናቱ ውስጥ ከተካተቱት አገራት በ40 ያህሉ በ2050 ዓ.ም 30 በመቶ የሚሆነው ህዝብ 60 እና ከዚያ በላይ ዕድሜ ያለው እንደሚሆን ሪፖርቱ ጠቁሟል፡፡ የተባበሩት መንግስታት መረጃ እንደሚያመለክተው፤ በ2030 ዓ.ም በዓለም ላይ ዕድሜው 60 ወይም ከዚያ በላይ የሚሆነው ህዝብ ቁጥር 1.4 ቢሊዮን ይደርሳል ተብሎ ይገመታል፡፡

የኮበለሉ ጋዜጠኞች ወደ አገራቸው እንዲመለሱ ጥሪ አቅርበናል
ሥልጠናው ከምርጫ ጋር የሚያገናኘው ምንም ነገር የለም
የአቅም ግንባታ እንጂ የርዕዮተ ዓለም ማስረጫ አይደለም

ከነሐሴ አጋማሽ ጀምሮ ለዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች እየተሰጠ ባለው ስልጠናና በአምስት የግል መጽሄቶችና በአንድ ጋዜጣ ላይ የተመሰረተውን ክስ ተከትሎ ከአገር በወጡት በርካታ ጋዜጠኞች ዙሪያ የአዲስ አድማስ  ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ፤ የመንግስት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ፅ/ቤት ሚኒስትር ዲኤታ አቶ እውነቱ ብላታን  ሰሞኑን በፅ/ቤታቸው አነጋግሯቸዋል፡፡

ለከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ተማሪዎች የተዘጋጀው ስልጠና ዓላማ ምንድን ነው?
የስልጠናው ዋና ዓላማ፣ አንደኛ በዩኒቨርሲቲዎች አካባቢ ሰላማዊ የመማር ማስተማር ሂደት በተቀላጠፈ መልኩ ማስቀጠል ነው፡፡ ሁለተኛ ሃገሪቱ በምትከተለው የልማት ስትራቴጂ ዙሪያ እስካሁን የደረስንበት፣ እንዲሁም ከፊታችን የሚጠብቁን ተግዳሮቶችና ስራዎች ምን እንደሆኑ የጠራ ግንዛቤ ማስያዝ ነው፡፡ ሀገሪቱ ባለፉት 23 ዓመታት የተጓዘችባቸውን መንገዶች በተለይ ወጣቱ ትውልድ በደንብ እንዲያውቀውና የበኩሉን ሃገራዊ የዜግነት ግዴታውን እንዲወጣ ጭምር ከየት ተነሳን ወዴት እየሄድን ነው የሚለውን ለማስጨበጥ ነው፡፡ ሌላው ሃገሪቱ እየተከተለች ባለችው ልማታዊና ዲሞክራሲያዊ ስርአት ግንባታ ላይ ያሉ ክፍተቶች ምንድን ናቸው? እንዴትስ ይቀረፋሉ? የመልካም አስተዳደር ትግላችን ምን ያህል ተጉዟል? ምንስ ይቀረዋል? በዚህ የመልካም አስተዳደር ጉዞ ውስጥ ከወጣቱና ከከተማው ህዝብ ምን ይጠበቃል? በአጠቃላይ ሃገሪቱ ለተያያዘቻቸው የሰላም፣ የልማትና የዲሞክራሲ ስርአት ግንባታ ወጣቱ ሚናውን መጫወት በሚችል መልኩ ግንዛቤ ለመስጠት ተፈልጎ ነው ስልጠናው እየተሰጠ ያለው፡፡ ይሄ ስልጠና ዘንድሮ የተጀመረ አይደለም፤ በየጊዜው በየትምህርት ተቋማቱ ሲሰጥ የቆየ ነው፡፡ የዚያው ቀጣይ ፕሮግራም ነው፡፡
ሥልጠናው በዩኒቨርሲቲዎች ብቻ የሚያበቃ ሳይሆን ለመንግስት ሰራተኞችም የሚሰጥ ነው፡፡ በህዝባዊ አደረጃጀቶች ውይይቶች እየተካሄዱ፣መንግስት በ5 ዓመቱ የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ አፈፃፀም ላይ የደረሰባቸው የእድገት ደረጃዎች የነበሩት ውጤታማ ተሞክሮዎች ምን ነበሩ? ከዚህ ምን ተምረን ለቀጣዩ እቅድ እንዴት እንሰራለን? የሚለውንና በአጠቃላይ ትልልቅ በሆኑ አገራዊ አጀንዳዎችና በህዳሴው ጉዞ ላይ  የሰፊውን ህዝብ  ተሣትፎ ለማጠናከር ታስቦ እየተካሄደ ያለ ስልጠና ነው፡፡ አሁን በዩኒቨርስቲዎች ለነባር ተማሪዎች ሁለተኛ ዙር ስልጠና እየተሰጠ ነው ያለው፡፡ ዩኒቨርሲቲ ማለት ይህቺን አገር የሚረከበው ወጣቱ ሃይል የሚገኝበት ነው፡፡ ይሄ በእውቀት የተካነው ወጣቱ ሃይል፣ ነገ ወደ ስራ ሲሰማራ የበኩሉን አስተዋጽኦ ማበርከት ይችል ዘንድ በአገሪቱ ነባራዊ ሁኔታ ላይ ግንዛቤ ለማስጨበጥ ተፈልጐ ነው ስልጠናው  የሚካሄደው፡፡ በዩኒቨርሲቲ ያለው የተማረ ሃይል ስለብዝሃነት፣ ስለመቻቻል፣ ስለመከባበር የጠራ ግንዛቤ እንዲኖረው ጭምር ነው ስልጠናው እየተሰጠ ያለው፡፡
ስልጠናው በተማሪዎቹ ፍቃደኝነት ሳይሆን በግዴታ ነው የሚካሄደው የሚሉ ቅሬታዎች ይሰማሉ፡፡  እውነት በግዴታ ነው ?
ስልጠናው ግዴታ አይደለም፡፡ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ወዶና ፈቅዶ የሚሳተፍበትና ግንዛቤ የሚያገኝበት ነው፡፡ ተማሪው በአጠቃላይ አገራዊ ፖሊሲዎችና ስትራቴጂዎች ላይ የሚወያይበት ስለሆነ በግዴታ ላይ የተመሠረተ ነው የሚያስብለው ነገር የለም፡፡ ስልጠናው በፍፁም በግዴታ ላይ የተመሰረተ አይደለም፡፡
ተማሪዎች በስልጠናው ተሳትፈው ሠርተፊኬት ካልተሰጣቸው ለትምህርት መመዝገብ እንደማይችሉ ተነግሯቸዋል ይባላል፡፡ ይሄ ውሸት ነው ማለት ነው?
የአንድ ወይም የሁለት ሣምንት የተለመዱ ስልጠናዎች ይሠጣሉ፡፡ ማንኛውም ስልጠና ሲካሄድ ለማንኛውም ሠልጣኝ ሠርተፊኬት ይሰጣል፡፡ ስልጠናው ምን ያህል ገብቶታል ወይም የተሳትፎ ብቃቱ ምን ያህል ነው የሚለውን ለመመዘን አይደለም፡፡ እንኳንስ ለ15 ቀን በተከታታይ ሰፊ ስልጠና ተሰጥቶ ይቅርና ለሁለትና ሦስት ቀናት ስልጠናም ሠርተፊኬት ይሰጣል፡፡ ተማሪዎችም በትላልቅ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ ነው የተወያዩት፤ በሀገሪቱ ውስጥ ስላለው መቻቻል፣ ህገ መንግስቱንና ህገ መንግስታዊ ስርአትን ተከትሎ መስራት ምን አንድምታ እንዳለው የሚዳስስ ሥልጠና ነው የወሰዱት፡፡ ትላልቅ አገራዊ አጀንዳ ላይ ለሠለጠነ አካል ሠርተፊኬት መስጠት አግባብ ነው፡፡ ሠርተፊኬቱ መሳተፉን ማረጋገጫ ነው፡፡ ከዚያ ውጭ የሚሰጠው ጥቅም የለም፡፡ ሠርተፊኬት መሰጠቱን እንደ ግዴታ ማሳያ ማድረግ ስህተት ነው፡፡ ማንም ተገዶ እንዲሰለጥን አይደረግም፡፡
የስልጠናው ውጤታማነትስ ምን ያህል ነው?
እኔም አሰልጣኝ ሆኜ ተሳትፌያለሁ፡፡ እንደውም አሁን ከመቱ መመለሴ ነው (ቃለምለልሱ የተደረገው ሃሙስ ከሰአት ነው) መጀመሪያ ላይ የተለያዩ ብዥታዎችን በማሠራጨት ስልጠናውን ለማደናቀፍ ጥረት ተደርጓል፡፡ በዚህ የተነሣ ተማሪውም ዘንድ በግንዛቤ ማጣት ከውጭ በሚነዙ አሉባልታዎች የመነዳት ችግሮች ነበሩ፡፡ እነዚህ ችግሮች የመጀመሪያዎቹ ቀናት አካባቢ ድረስ ብቻ ነው የዘለቁት፡፡ የስልጠናውን ጠቃሚነትና አስፈላጊነት ከተረዳና ጥቅሙ ለራሱ፣ ለማህበረሰቡና ትምህርት ቤት ለላኩት ወላጆቹ መሆኑን ከተገነዘበ በኋላ ግን ስልጠናውን በፍላጎትና በተነቃቃ ስሜት ነው የተሳተፈው፡፡
 ከአንዳንድ ወገኖች ስልጠናውን የማደናቀፍ ተልዕኮ ተቀብለው ወደ ስልጠናው የገቡት እንኳ መጨረሻ ላይ ራሳቸውን አጋልጠው “ይሄ የኔ ሃሳብ አይደለም፣ ይሄን ስልጠና ማዘግየታችሁ እኛን ለብዥታ እንድንጋለጥ አድርጐናል” ብለዋል፡፡ በስልጠናው ላይ መልካም መልካም ነገሮች  ብቻ አይደለም የቀረቡት፤የአገሪቱ ተግዳሮቶችና ማነቆዋች በሙሉ ተነስተዋል፡፡ በአፈፃፀም ሂደት የነበሩ ጉድለቶች፣ የስርአቱም ሆነ የዚህች አገር አደጋዎችና የአደጋ ስጋቶች ምን ምን እንደሆኑ ጎልተው ወጥተው ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡ ሁሉም ነገር ሳይደበቅ ግልጽ በሆነ አካሄድ ነው ስልጠናው የተሰጠው፡፡ እንደውም ወደ መጨረሻ ላይ ተማሪዎቹ በፍቅር እየወደዱት መጥተዋል፡፡
 እናም ውጤታማና በድል የተጠናቀቀ ስልጠና ነበር ማለት ይቻላል፡፡ አሠልጣኝም አስተባባሪም ስለነበርኩ በዚህ ረገድ ያየሁትን በሚገባ መመስከር እችላለሁ፡፡ ሌሎች አካባቢ ስለተደረጉት ስልጠናዎች አንደኛው ዙር ከተፈፀመ በኋላ ግምገማ ተካሂዷል፡፡ አፈፃፀማችን እንዴት ነበር? በቀጣይ የነበሩትን ጉድለቶች እንዴት እናስተካክል? የሚል አጠቃላይ ግምገማ ስለተካሄደ ውጤታማና ከጠበቅነው በላይ ነበር ማለት እችላለሁ፡፡ ከተማሪዎቹም ዘንድ ሥልጠናው በአመት አንድ ጊዜ ቢካሄድ-- የሚል ሃሳብ ሲቀርብ ስለነበር እጅግ ውጤታማ የሆነ ስልጠና ነው፡፡
ኢህአዴግ የመንግስት ሃብትና ገንዘብን ለራሱ ርእዮተ ዓለም ማስፈፀሚያ እያዋለ ነው የሚል ትችት ይሰነዘራል፡፡ በዚህስ ላይ ምን ይላሉ?
በመጀመሪያ መንግስት ይሄን ስልጠና የማከናወን ሙሉ መብትና ነፃነት አለው፡፡ አሁን ፓርቲውን በዚህ ለመክሰስ ተፈልጐ ከሆነ፣ ፓርቲው በምርጫ አሸንፎ ስልጣን ላይ እስከሆነ ድረስ በመንግስት የሚሠራው አሸናፊው ፓርቲ የቀረፃቸው ፖሊሲዎችና ስትራቴጂዎች ናቸው፡፡ እነዚህ የፓርቲው ፖሊሲዎች ከምርጫ በኋላ ወደ ስልጣን ሲመጣ፣ አገራዊ ፖሊሲ ሆነዋል፡፡ አገራዊ ፖሊሲና ስትራቴጂውን ደግሞ መንግስት በመላ አገሪቱ የማስፈፀም ግዴታ አለበት፡፡ በዚህ አስታኮ ገዥውን ፓርቲ ለመክሰስ የሚደረገው ጥረት ውሃ አይቋጥርም፤ምክንያቱም የአገሪቱን ፖሊሲና ስትራቴጂ የሚያስፈጽመው ፓርቲው ነው፡፡
 አሁን የተሰጠውና እየተሰጠ ያለው ስልጠና በመንግስት እንጂ በፓርቲው አይደለም፡፡ ስለዚህ የሀገሪቱን የአቅም ግንባታ፣ መሠረተ ልማት፣ የአዕምሮ ግንባታንም ጭምር የመስራት ሙሉ ነፃነትና መብት ያለው መንግስት ነው፡፡ ይሄ አንዱ የአቅም ግንባታችን አካል ነው፡፡ የአቅም ግንባታው የሚሰጠው ደሞዝ ተከፋይ ለሆነውና በመንግስት ስልጣን ላይ ላለው ብቻ ሳይሆን በአጠቃላይ ለአርሶ አደራችን፣ ለተማሪዎችና ለተለያዩ ህብረተሰብ ክፍሎች ነው፡፡ ይህ የአቅም ግንባታ እንጂ የርዕዮተ ዓለም ማስረጫ አይደለም፡፡ በአጠቃላይ ስለአገሪቱ እጣ ፈንታ የማወቅና የመወሰን ጉዳይ ነው፡፡ ይህን የማድረግ ደግሞ በስልጣን ላይ ያለው መንግስት ታሪካዊ ሃላፊነት ነው፡፡ ህገ-መንግስታዊ ግዴታውም ነው፡፡ መንግስታዊ ሃላፊነትንና ግዴታን የመወጣት ጉዳይ ነው፡፡
ስልጠናው መጀመሪያ የታቀደ ሳይሆን ድንገት የመጣ አጣዳፊ ፕሮግራም ነው፤ እንደውም የግንቦቱን ምርጫ ታሳቢ ያደረገ ነው፤ የሚሉ ወገኖች አሉ፡፡ እርስዎ ምን ይላሉ?
ይሄ የተለመደ ነው፡፡ ታስታውሱ እንደሆነ የህዳሴው ግድብ ራሱ ለምርጫ ተብሎ እንጂ የታሰበበት አይደለም ሲባል ነበር፡፡ ነገር ግን የሚሠራውን የሚያስበው በስራው ላይ ያለው አካል ነው፡፡ ከዚያ ውጭ ያለው አካል ከመሬት ተነስቶ የታሰበበት አይደለም፤ መታሰቡንም አላውቅም ብሎ ሊበይን አይችልም፡፡ እነዚህ ወገኖች በመንግስት ውስጥ እስካልሆኑ ድረስ የታሰበውን ነገር ሁሉ አስቀድመው የሚያውቁበት እድል ሊኖር አይችልም፤ነቢያቶች እስካልሆኑ ድረስ፡፡
 ስለዚህ ስልጠናው በመንግስት እቅድ ውስጥ የነበረ እንጂ በዱብ እዳ የተሠራ አይደለም፡፡ ከምርጫ ጋርም የሚያቆራኘው ምንም ጉዳይ የለም፡፡ “ኢህአዴግን ብቻ ምረጡ” የሚል አረፍተ ነገር በአንዲት ቦታ ተብሎ ከሆነ፣ ይሄን በማስረጃ አስደግፎ ማቅረብ ይቻላል፤ ነገር ግን እንዲህ የተባለበት ቦታ የለም፡፡ ከምርጫ ጋር ፈጽሞ ሊያያዝ አይገባም፡፡ ይሄ ጉዳይ ከአንድ ዙር ምርጫ በላይ የዘለለ ነው፡፡ ስለ አገር ህልውና፣ በቀጣይ አገሪቱን ስለሚረከብ ዜጋ ጉዳይ ነው፡፡
 ስለ አገሪቷ እጣ ፈንታ ቀጣዩ ትውልድ እንዲገነዘብ የማድረግ ጉዳይ ነው፡፡ ትውልድን የመቅረጽ ጉዳይ ነው፡፡
 እነዚህ ነገሮች የተለመዱ ናቸው፡፡ ከዚህ በፊት የስነ ዜጋ ትምህርት ሲጀመር ኢህአዴጋዊ ለማድረግ ነው ሲባል ነበር፤ስለዚህ አዲስ ነገር አይደለም፡፡ ይልቁንም “ይሄ ነገር ለአገር በጐ ከማሰብ የተደረገ ነው” ቢባል ኖሮ ነበር በጣም የሚገርመው፡፡ የአሁኑ ግን የተለመደና መሠረተ ቢስ እንደሆነ ላረጋግጥ እወዳለሁ፡፡
ከስልጠናው ምን ተገኘ? ወደፊትስ ምን  ታቅዷል  
በዩኒቨርስቲዎቹ ያሉ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመፍታት የሚያስችል ግብአት አግኝተናል፡፡ በቀጣይም ለአዲስ ገቢ ተማሪዎች፣ ለመምህራንና ለአስተዳደር አካላት የአስር ቀናት ስልጠና ይሠጣል፡፡
በቅርቡ ከአገር የተሰደዱ ጋዜጠኞች ወደ ሀገራቸው እንዲመለሱ ጥሪ እንዳቀረቡ ሰምቼአለሁ---
አዎ አቅርበናል፡፡
በምን መልኩ ነው ጥሪው የቀረበው?
በጋዜጠኞች ስልጠና ላይ የመክፈቻ ንግግር ሳደርግ አንዱ ያነሳሁት ጉዳይ ነበር፡፡
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በፍትህ ሚኒስቴር ከተከሰሱ 5 መጽሔቶችና 1 ጋዜጣ ጋር በተገናኘ የተሰደዱ ጋዜጠኞች አሉ የሚል ነገር በየቦታው ይወራል፡፡ እነዚህ ጋዜጠኞች በክሱ ተደናብረው ከሃገር ኮብልለው ከሆነ፤ እነሱን ሊያስጠይቅ የሚችል ነገር ስለሌለ መኮብለላቸው አግባብ አይደለም፡፡ ብዥታው አግባብነት ስለሌለው በአስቸኳይ ወደ ሀገራቸው ተመልሰው ስራቸውን እንዲቀጥሉ ነው ጥሪ ያስተላለፍነው፡፡
አሁንም ደግሜ የምለው፤ ጋዜጠኞቹ ከአገር የወጡት በጋዜጣውና መጽሔቶቹ ክስ ምክንያት ከሆነ፣አግባብ ስላልሆነ  ወደ ሀገራቸው ተመልሰው ስራቸውን እንዲቀጥሉ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡