Administrator
Friday, 05 September 2025 10:25
ግብፅና ሱዳን የሕዳሴው ግድብ "ዘላቂ ስጋት" ደቅኖብናል አሉ
ግድቡ ዓለም አቀፍ ሕግን የጣሰ ነው ሲሉ ከሰዋል
ግብፅና ሱዳን ኢትዮጵያ የገነባችው ታላቁ የሕዳሴ ግድብ በምሥራቅ የናይልተፋሰስ አገራት ላይ ዘላቂ ስጋት ደቅኗል አሉ።
ኢትዮጵያ የግድቡን ግንባታ አጠናቅቃ ለምረቃ እየተዘጋጀች ባለችብት ጊዜ፣ የሁለቱ አገራት የውጭ ጉዳይና የመስኖ ሚኒስትሮች በካይሮ ተገናኝተው ከመከሩ በኋላ ባወጡት መግለጫ ነው ስጋታቸውን የገለጹት።
ሚኒስትሮቹ ትላንት ረቡዕ በጋራ ባወጡት መግለጫ፤ ግድቡ "በዓለም አቀፍ ሕግ መሠረት በምሥራቅ ናይል ተፋሰስ መረጋጋት ላይ ቀጣይነት ያለው ስጋት" መደቀኑን አመልክተዋል።
የሁለቱ አገራት ሚኒስትሮች በካይሮ ባደረጉት በዚህ ስብሰባ ላይ፣ ግድቡ ዓለም አቀፍ ሕግን የጣሰና በታችኛው ተፋሰስ አገራት ላይ ከፍተኛ ስጋት የሚፈጥር መሆኑን አስታውቀዋል።
ኢትዮጵያ ግድቡን በውሃ ለመሙላት የወሰደችውን የተናጠል እርምጃ የተቃወሙት አገራቱ፤ የውሃ ደኅንነታቸው ጉዳይ አንድና የማይነጣጠል መሆኑን መግለጻቸውን ቢቢሲ ዘግቧል።
አክለውም፤ "ኢትዮጵያ ትብብርን ዳግም ለማጠናከር በምሥራቃዊ የናይል ተፋሰስ አገራት ላይ የምትከተለውን ፖሊሲ መቀየር አለባት" ብለዋል።
ግብፅና ሱዳን በዚህ መግለጫቸው፣ ሌሎች የናይል ተፋሰስ አገራትን ተሳትፎ ውድቅ አድርገው፣ ጉዳዩ በኢትዮጵያ፣ በግብፅና ሱዳን መካከል ብቻ መታየት እንዳለበት አስታውቀዋል።
የኢትዮጵያ ውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር አቶ ሀብታሙ ኢተፋ ከቀናት በፊት ከቢቢሲ አፍሪካ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ፣ ኢትዮጵያ በሕዳሴ ግድብ ዙሪያ ለመነጋገር አሁንም ዝግጁ መሆኗን አስታውቀዋል። ነገር ግን ግብፅና ሱዳን የግድቡን ውሃ ሙሌትና ቀጣይ ሥራን በሚመለከት የቅኝ ግዛት ዘመን ስምምነትን መሠረት በማድረግ፣ ኢትዮጵያ አስገዳጅ ስምምነት እንድትፈርም ይፈልጋሉ ብለዋል።
በኢትዮጵያ በኩል ግን ይህ ተቀባይነት የሌለው መሆኑንና ሁሉንም የተፋሰሱ አገራትን ተጠቃሚ የሚያደርግ ስምምነት እንዲደረስ እንደምትፈልግ ሚኒስትሩ ገልጸዋል፡፡
የቴሌግራም ቻናልችንን በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…


Published in
ዜና
Tagged under
Thursday, 04 September 2025 11:18
"ወይ አዲስ አበባ"ን በአዲስ ዓመት ዋዜማ
“ወይ አዲስ አበባ” መጽሔት .. በኅትመት ዋጋ መናር ምክንያት ከተቋረጠች በኋላ በአዲስ ዓመት ዋዜማ፣ የፊታችን ቅዳሜ .. ዳግም ለኅትመት በቅታ ከእጃችሁ ትገባለች።
"ምነው ጠፋችሁ?!" የሚለው ጥያቄ ላለፉት ዓመታት ከብዙ አንባቢዎቻችን ለዝግጅት ክፍላችን የቀረበ ጥያቄ ነበር። "ተመለሱ" ያሉንም ብዙዎች ናቸው። .. እነሆ ለቀረቡልን የ"ተመለሱ" ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት ያደረግናቸው ጥረቶች ተሳክተው በአዲስ መንገድ፣ በአዲስ መንፈስ፣ ከቀደመው በተሻለ ጥራት መጥተናል። ከአሁን በኋላም በየሁለት ወሩ እየታተመች ለንባብ ትበቃለች።
"ወይ አዲስ አበባ"ን በአዲስ ዓመት ዋዜማ! ...
Published in
ኪነ-ጥበባዊ ዜና
Tagged under
Thursday, 04 September 2025 10:51
ግጥም ሲጥም በብሔራዊ ቤተመንግስት AHOC
'እንዲህ ያለም የለ!' የተሰኘ ጥዑም የግጥም ስብስብ መጽሐፉን እንዘክራለን።
በሰዓቱ ተገኙና በሀብታሙና በጓደኞቹ በሚቀርቡ ጥዑም ግጥሞች ሰላምን ሸምቱ፤ ጎበዝ ገጣሚያንን ተዋወቁ!
በፍል ውሃ በኩል ባለው የብሔራዊ ቤተመንግስት መግቢያ (5ኛ በር) ቢገቡ አዲስ ሃውስ ኦፍ ካልቸርን በቀላሉ ያገኙታል።
Published in
ኪነ-ጥበባዊ ዜና
Tagged under
Thursday, 04 September 2025 10:45
"የብሌን አንዳች
''የብሌን አንዳች'' የተሰኘው የጋዜጠኛ ዋለልኝ አየለ መጽሐፍ አርብ፣ ነሐሴ 30 ቀን 2017 ዓ.ም ይመረቃል።
ቦታ፡ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት የስብሰባ አዳራሽ፣ አራት ኪሎ፣ ከብርሃንና ሰላም ማተሚያ ድርጅት ፊት ለፊት
ሰዓት፡ ከቀኑ 10 ሰዓት
Published in
ኪነ-ጥበባዊ ዜና
Tagged under
Wednesday, 03 September 2025 18:37
1500ኛው የነቢዩ መሐመድ መውሊድ (ልደት) ነገ ይከበራል
ነገ የሚከበረውን የመውሊድ በዓል አስመልክቶ የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ሥራ አስፈፃሚ አባልና የወጣቶችና ሴቶች ዘርፍ ተጠሪ ሼህ አብድልሃሚድ አህመድ፤ መውሊድ ሲከበር የአካባቢን ሰላም በማስጠበቅና የተቸገሩ ወገኖችን በመርዳት ሊሆን እንደሚገባ ገልፀዋል፡፡
የታላቁ አንዋር መስጊድ ኢማም ሼህ ጠሃ መሐመድ ሃሩን በበኩላቸው፤ " ነቢዩ መሐመድ ለዓለም ሰላምና ለሰው ልጆች እዝነት የተላኩና የሰሩ በመሆናቸው ሙስሊሙ ማህበረሰቡ አርዓያነታቸውን ሊከተል ይገባል" ብለዋል።
በመውሊድ በዓል አከባበር ወቅት የተለያዩ ዝግጅቶች እንደሚካሄዱና በዓሉ የእስልምና አስተምህሮን ለእምነቱ ተከታዮች ለማስረፅ እንደሚረዳም ገልጸዋል፡፡
በዓሉ ነገ ሐሙስ በመላው ኢትዮጵያ የሚከበር ሲሆን፤ በአዲስ አበባም በታላቁ አንዋር መስጊድ በልዩ ልዩ ዝግጅቶች እንደሚከበርም ተጠቁሟል፡፡


See insights and ads
Boost post
All reactions:
1010
Published in
ዜና
Tagged under
Wednesday, 03 September 2025 18:30
የብሔራዊ ባንክ ገዢ ከሃላፊነታቸው ለቀቁ
"ለምንወዳት ሀገራችን ማገልገል ትልቅ እርካታ የሚሰጥ ነገር ነው"
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ 10ኛው ገዥ የሆኑት አቶ ማሞ ምህረቱ፣ ከኃላፊነታቸው በገዛ ፈቃዳቸው መልቀቃቸውን አስታወቁ፡፡
አቶ ማሞ ምህረቱ፣ ለሰባት ዓመታት ያገለገሉበትን የመንግሥት የሥራ ኃላፊነት መልቀቃቸውን በዛሬው ዕለት በይፋዊ የኤክስ ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት መልዕክት አስታውቀዋል፡፡
"ከ7 ዓመታት የሕዝብ አገልግሎት በኋላ ሌሎች ሥራዎችን ለማከናወን ከመንግሥት ኃላፊነት ለመልቀቅ ወስኛለሁ" ያሉት አቶ ማሞ፤ "ለምንወዳት ሀገራችን ማገልገል ትልቅ እርካታ የሚሰጥ ነገር ነው" ብለዋል፡፡
በተለይም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በመሩት የቤት-አስተዳደር ኢኮኖሚ ማሻሻያ ፕሮግራም ውስጥ በመስራታቸው እንዲሁም፤ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክን በገዥነት በመምራታቸው ከፍተኛ እርካታ ማግኘታቸውን በመግለጽ፣ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ አመራርም ምስጋናቸውን አቅርበዋል።
አክለውም፤ "የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥ እንደመሆኔ፣ በሀገሪቱ ውስጥ ከ50 ዓመታት ወዲህ ትልቁ የሚባለውን የኢኮኖሚ ማሻሻያ መርቻለሁ" ብሏል፡፡
"በእነዚህ ማሻሻያዎች ምክንያት የውጭ ምንዛሪ ከሦስት እጥፍ በላይ ጨምሯል፤ ይህም በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ በታሪክ ከፍተኛ ደረጃ ላይ ደርሷል" ያሉት አቶ ማሞ፤ የዋጋ ግሽበት በሰባት ዓመታት ውስጥ ዝቅተኛ ደረጃ ላይ መድረሱን እንዲሁም የዲጂታል ክፍያዎች ከ10 እጥፍ በላይ መጨመራቸውን አስረድተዋል፡፡
አክለውም፤ "የብሔራዊ ባንክ ቡድንና የሥራ ባልደረቦቻችን ወደር ለሌለው ሙያዊ ብቃትና ከራስ ወዳድነት ነፃ የሆነ የሥራ ሥነ ምግባር ምስጋና ይግባውና፤ በዘመናዊ የገንዘብ ፖሊሲ ማዕቀፍ ወደ ገበያ ተኮር የምንዛሪ ተመን ሥርዓት በመሸጋገር የባንኩን የራስ ገዝ አስተዳደር በአዲስ ሕግ እንዲቋቋም አግዘናል" ብለዋል፡፡
የፋይናንስ ዘርፉ በከፍተኛ ሁኔታ ተጠናክሮ በመስፋፋቱ ከ5 ትሪሊየን በላይ ሀብት መድረሱን በመግለጽ፤ እነዚህና ሌሎችም የመንግሥት ታሪካዊ ክንዋኔዎች አስደናቂ መሆናቸውንም ተናግረዋል።
አቶ ማሞ በመጨረሻም፤ "ዛሬ ብሔራዊ ባንክን ለቅቄ ስወጣ የዘመናዊ ማዕከላዊ ባንክ ዓላማና ራዕይ ሊደረስበት እንደሚችል እርግጠኛ በመሆን ነው" ሲሉ መልዕክታቸውን ቋጭተዋል፡፡

Published in
ዜና
Tagged under
Wednesday, 03 September 2025 18:25
ሆስፒታሉ የዓለም ጤና ድርጅትን ዕውቅና ማግኘቱን ገለጸ
"ላንድማርክ ኑሮውም ጉዞውም ከህብረተሰቡ ጋር ነው"
ላንድማርክ አጠቃላይ ሆስፒታል "የአዲስ ዓመት ስጦታ" በሚል ከነሃሴ 26 ቀን ጀምሮ እስከ ጳጉሜ 1 ቀን 2017 የሚዘልቅ የነጻ የጤና ምርመራ መርሃ ግብር እያካሄደ መሆኑ ተገለጸ፡፡
የሆስፒታሉ አመራሮች ዛሬ ጠዋት ረፋዱ ላይ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፤ በእነዚህ ቀናት ለ300 ያህል ሰዎች ነጻ የጤና ምርመራ እንደሚሰጥ አስታውቀዋል፡፡ በዚህ መርሃ ግብርም የደም ግፊት፣ የስኳር፣ የጡት ካንሰር፣ የኤችአይቪና የአባላዘር በሽታዎች ነጻ ምርመራ የሚሰጥ ሲሆን፤ ወጪው በገንዘብ ሲሰላ ሩብ ሚሊየን ብር እንደሚደርስ አመራሮቹ ጠቁመዋል፡፡
በሌላ በኩል፤ ላንድማርክ አጠቃላይ ሆስፒታል የዓለም ጤና ድርጅት "የታካሚ ደህንነትና ወገንተኝነት" መስፈርቶችን በማሟላት ዕውቅና እንደተሰጠው አመራሮቹ አስታውቀዋል፡፡
የሆስፒታሉ ዋና ሥራ አስኪያጅ ፕ/ር ከበደ ኦሊ በሰጡት ማብራሪያ፤ "ላንድማርክ በዓለም ጤና ድርጅት መስፈርት በአንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ላይ የሚገኝ ብቸኛ ሆስፒታል ነው" ብለዋል፡፡
"ላንድማርክ ኑሮውም ጉዞውም ከህብረተሰቡ ጋር ነው" ያሉት ዋና ሥራ አስኪያጁ፤ የሆስፒታሉ የማስፋፊያ ግንባታ የማጠናቀቂያ ምዕራፍ ላይ እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡ በቅርቡም ተጠናቆ አገልግሎት እንደሚጀምር ተነግሯል፡፡
ላንድማርክ አጠቃላይ ሆስፒታል ላለፉት 17 ዓመታት የህክምና አገልግሎት ሲሰጥ የቆየ የግል ተቋም መሆኑ ይታወቃል፡፡
የቴሌግራም ቻናልችንን በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…
Published in
ዜና
Tagged under
Wednesday, 03 September 2025 18:15
ሚድሮክ በየወሩ እስከ 600 ሚ. ብር ደሞዝ ለሠራተኞቹ ይከፍላል
"ኢትየጵያን ከድህነት መንጋጋ ፈልቅቆ ማውጣት ግዴታዬ ነው"
የሼህ አል-አሙዲ ንብረት የሆነው ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ፣ ከ74 ሺህ ለሚልቁ ሰራተኞቹ በየወሩ ከ500 - 600 ሚሊዮን ብር ደሞዝ እንደሚከፍል ምን ያህሎቻችን እናውቃለን?
ኢትዮጵያም የእናታቸው አደራ ሆናባቸው አል-አሙዲ በኢንቨስትመንት ለመሳተፍ በኢትዮጵያ ከተሰማሩበት ጊዜ አንስቶ በሶስት ምዕራፍ የፖለቲካ ትርጓሜ እየተሰጠባቸው ብዙ ውጣ ውረድ ገጥሟዋል፤ ሸራተን ሆቴል እስኪዘጋ ድረስ፡፡
አል - አሙዲን ከሳኡዲ ስለመጡ “ወሀቢያን ወደ ኢትዮጵያ ሊያስፋፋ ነው፤ የእስልምና አክራሪነትን ሊያመጣ ነው” በሚለው ጥርጣሬ ሸራተን ለጊዜው እንዲዘጋ ተወስኖ እና ሆቴል ሳይሆን መስጊድ ነው የሚል ወሬም ተናፍሶ ሆቴሉ ተዘግቶ ከተፈተሸ በኋላ ተረጋግጦ እንደገና ተፈቅዶ መከፈቱንስ እናውቅ ነበር?
ያኔ የኢህአዲግ መንግስትን ይቃወሙና ተችተው ይጽፉ የነበሩ እንደ እነ ጋሽ ጻውሎስ ኞኞ ያሉትን ሼሁ ጀርመን ልከው ማሳከማቸው፤ ቀጥሎም አርቲስቶቹን እነ ታማኝ በየነና ፀሀዬ ዮሀንስ ላይ ከመንግስት ሹሞች ጫና ሲበዛባቸው አላሙዲን አሜሪካ ወስደው መደገፋቸውን ተከትሎ፣ በመንግስት በኩል ጥርጣሬው መባሱን፤ በዚህ ሳያበቃም - አፍቃሬ ደርግ ተብለው እንደነበርም በሚድሮክ በጣም መረጃ ሰጪ ዶክመንተሪ ላይ ተጠቅሷል፡፡
“አፍሪካ ከልቤ ብትሆንም - ኢትዮጵያ ግን የእናቴ አደራ ናት አሉ” - ቢሊየነሩ ሼህ መሀመድ አላሙዲን፡፡
ለኢህአዲግ መንግስት ሼህ አላሙዲን በ1997 ምርጫ ድጋፍ ሁነት ላይ መገኘታቸውን ተከትሎ ብዙ ሰው ሚድሮክ የህወሀት ነው፣ የወያኔና የአዜብ መስፍን ነው እስከሚለው ድምዳሜ ድረስ የዘለቀው ነቆራ ሚድሮክን ከፖለቲካ ፓርቲ ጋር አላጥፎ በባለሀብቱና በድርጅቶቹ ላይ ከፍተኛ ፈተና ደቅኖም ማለፉን ዶክመንተሪው ከትቦታል፡፡
በሚድሮክ ዶክመንተሪ ላይ እንደ ወግ በጣም ቀልብን በሚገዛ ሁነት ማብራሪያውን የሚሰጡት አቶ ጀማል አህመድ እንዲህ ሲሉ በአጽንኦት ያነሳሉ - “አላሙዲ ለኢትዮጵያ ስላላቸው በጎ ሕልም በህዝቡ ዘንድ በቂ ግንዛቤ አልተያዘውም፤ እናም አሁንም ድረስ ፈተና ሆኖ የቀጠለው አብዛኛው የሼሁን የሀገር ወዳድነት ውስጠታቸውን አልተረዳውም”
መንግስት በደንብ ያመናቸው በኢትዮ ኤርትራ ጦርነት ነው ይሉና የሚድሮኩ ዋና ስራ አስፈጻሚ ሲያብራሩ - “በዚህ ወቅት ሀገሪቱ ከባድ የፋይናንስ ማጥ ውስጥ ነበረችና አልአሙዲ የተጠየቁትን ድጋፍ ሁሉ በደስታ በማድረግ ከኢትዮጵያ ህዝብ ጎን በቁርጠኝነት ቆመዋል”፡፡
የሚያደርጉት ድጋፍ ሼህ አላሙዲን የማህበራዊ ግዴታቸውን ለመወጣት የሀገር ውለታ የዋሉ ሰዎችን መደገፍ መውደዳቸው ግን በአንዳንድ ፖለቲከኞች በበጎ ጎን አለመታየቱ ፈተና አመጣባቸው በማለት በቁጭት የሚያነሱት ስራ አስፈጻሚው አቶ ጀማል፤ ለካ ደግነትም ፈተና መሆኑን ያወቅሁት በእሳቸው ነው በማለት በአግራሞት በምልሰት ሄደው ያወሱታል፡፡
ሌላው በሚድሮክ የውስጥ ድርጅት የአስተዳደራዊ ልቅ አሰራር ችግርና ሙስና ብሎም የገንዘብ ብክነትና ስርቆትን ተከትሎ ኩባንያዎቹ የመውደቂያ ቀናቸውን የሚቆጥሩ ነበሩና ከግራ አጋቢ ሁኔታ የገባው ሚድሮክ የራሱን customized መዋቅር አበጅቶ በስሩ ያሉ 45 ድርጅቶች በ6 ዘርፎች ተጣምረው በ2012 ዓ.ም መጨረሻ ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ መፈጠሩ ይነገራል፡፡
ከወሎዋ ወልዲያ ትውልዳቸውን አድርገው ደሴ ወ/ሮ ስህን ት/ቤት ተከታትለው - የስራን ልምድ ከአንድ ስዊድን ካለ ትልቅ ኩባንያ ተቀጥረው ስለቢዝነስ ተሞክሮ ጨብጠዋል፡፡ አውሮፓ ላይ ሀብት ቢያፈሩም፣ ወደ ኢትዮጵያ ግን መጥተው አያውቁም ነበር፡፡ ይሁንና አንድ ቀን ግን እናታቸው የጤና አያያዛቸው አላምር አላቸው፤ እንግሊዝ ሀገር ለህክምና ከመሄዳቸው በፊት ግን ኢትዮጵያ ውሰዱኝ አሉ፡፡
ኢትዮጵያ መጥተው መርካቶን ጭምር ጎበኙ እና “ልጄ አደራህን!” አሉ ለሼህ አላሙዲን - “አደራ ሀገርህን ኢትዮጵያን አግዝ!” የሚል አደራ ተቀበሉ - ይህ የእናቲቱ አደራ አላሙዲንን ከበዳቸው፡፡
ለምን መንግስት ብቻ - የግል ባንክ ለምን አይኖርም፣ ኢኮኖሚው እንዲያድግ መንግስት መደገፍ አለበት የሚለው ሌላ የተሳሳተ የፖለቲካ ስሌት አስነስቶባቸው - ስማቸውንም የጠለሸበት አጋጣሚ ተፈጥሮ ነበር - ከበጎ ምክር ይልቅ ጥርስ አስነከሰባቸው - በዚህ መዘዝ የስራቸው ቀዳሚ የነበረው የመጀመሪያውን ሼራተን ሆቴል ታሽጎባቸው ነበር፤ የተሳሳተ ስሌቱም ስማቸውን አጠለሸባቸው፡፡
እኔ የተሸለምኩት መንግስት ኢትዮጵያ ሀገርህ ናት - ናና አልማ ስባል ነው - ለነገሩ የተወለድኩባትን እናት ሀገሬን እንዴት ነው የምረሳው ብለው ነበር፤ በአንድ ሽልማት ስነ ስርአት ላይ ባደረጉት ንግግር፡፡
ለበርካታ ወገኖች ስራ እድል በመፍጠር ኢትየጵያን ከድህነት መንጋጋ ፈልቅቆ ማውጣት ቅድሚያ ግዴታዬ ነው ይላሉ ዛሬም ድረስ ሼህ አል-አሙዲን፡፡
የሻይና ቡና ተክል ልማት ላይ በመሰማራት ኢትዮጵያን በዚህ ዘርፍ በአለም ቀዳሚ ረድፍ ላይ ማሰለፍ ህልማቸው ነበር፡፡
ሁሌም በተስፋ ይስተካከላል፤ የጊዜ ጉዳይ ነው ይሉኝ ነበር በማለት አቶ ጀማል የሼሁን ጨለምተኛ አለመሆን ይገልፁና፣ አሁን ያለው ፈተና ደግሞ ሳኡዲ ውስጥ ካለ ችግር ጋር የተያያዘ እና ከዛ ሀገር እንዳይወጡ በመደረጉ ድርጅቶቻቸውን ተከታትለው እንዳይመሩ እንደሆነ በቅሬታ ያነሳሉ፡፡ ይሁንና አሉ አቶ ጀማል - “አልአሙዲን ሁሌም ይፈተናሉ፤ አላህምዱሊላሂ ሁሌም ግን ፈተናውን ያልፉታል”፡፡
መንግስት ትኩረት የሰጣቸው የሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያ መዋቅር (home grown economic reform pillars) ከሚባሉት ከአይቲ በስተቀር በአራቱ ስለምንሳተፍ ትኩረቱ ለእኛ ጠቃሚ ነው ባይ ናቸው ከፍተኛው አመራር፡፡
ለ22 አመታት በኪሳራ የኖረው ኤልፎራ በዶሮ ዝርያ ከምስራቅ አፍሪካ ቀዳሚውን ስፍራ ስለመያዙ ተጠቅሷል፡፡ ጫጩትን ከውጭ ለምታስመጣው ኢትዮጵያ መድህን ሊሆን ጥረት ላይም ይገኛል፡፡ የሻይ ቅጠል ምርትን ከኬንያ እያስመጣች የነበረችው ኢትዮጵያ አሁን በሚድሮክ ፍላጎቷን የሚሞላ አቅርቦትና የውጭ ምንዛሪ ገቢም እየተገኘበት ነው፡፡
የአፍሪካ ቢዝነስ ሊደርሺፕ ኦርጋናይዜሽን የአመቱ ምርጥ ዋና ስራ አስፈጻሚ “CEO of the Year” በሚል ሚድሮክ የእውቅና ሽልማት እና በቅርቡም እንዲሁም የአፍሪካ መሪዎች በተገኙበት ሌላ የእውቅና ሽልማት አንስቷል፡፡
ፋብሪካዎቹ ጋ ሲኬድ - እኛ የዚህ ድርጅት ባለቤቶች ነን - የዚህ ድርጅት እድገት በእኛ ይወሰናል - የሚል አባባል አለ - ሆራይዘን ጋ የነበሩ ሰራተኞች የፈጠሩት መሪ ቃል ነው - ሌሎቹም ተጋሩትና ቀጠሉ - ጀማል አዝዞት የሆነ አይደለም፡፡
ሚድሮክ ባለፉት አስር አመታት ሰርቶ አምርቶ ካመጣው የሽያጭ ገቢ በላይ የዘንድሮ አንድ አመቱ ውጤት እጅግ ያስከነዳልም ተብሏል፡፡
በውጭ አልሚነት የተመዘገቡት ሼህ አላሙዲን ብዙ ሚሊዮን ዶላር ወደ ኢትዮጵያ ይዘው መጥተው ድርጅቶች ከፍተው አምርተው በውጭ ምንዛሪም ሸጠው ከፍተኛ ገቢም አግኝተዋል፤ ግን አንድ ዶላር ከሀገር አውጥተው አያውቁም ተብሎላቸዋል፡፡
የዚህን እውነትነት ለማረጋገጥ አሉ አቶ ጀማል በዶክመንተሪው - “የኢትዮጵያ ብሄራዊ ባንክም ጋ ሄዶ ማረጋገጥ ይቻላል፤ ከእኛ ብር ይወስዱ ስላልነበር፤ ማበረታቻ ቲፕ የሚሰጡት እንኳ በዩሮ ነበር፡፡
(Via:- ጋዜጠኛ እሸቱ ገለቱ)
የቴሌግራም ቻናልችንን በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…
Published in
ህብረተሰብ
Tagged under
Wednesday, 03 September 2025 18:14
የሴቶች የመሬት ባለቤትነት ሽፋን 60 በመቶ ደርሷል ተባለ
በኢትዮጵያ የሴቶች የመሬት ባለቤትነት ሽፋን 60 በመቶ መድረሱ ተገለጸ፡፡
የሴቶችን የመሬት ባለቤትነት ለማረጋገጥ ከግብርና ሚኒስቴርና ከሚመለከታቸው ተቋማት ጋር በቅንጅት እየተሠራ እንደሆነ የሴቶችና ማሕበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ኤርጎጌ ተስፋዬ ተናግረዋል።
ሚኒስትሯ በግብርናው ዘርፍ የሴቶችን ተጠቃሚነት የሚያሳድግ ፕሮግራም በአዲሱ ዓመት ይፋ እንደሚደረግም አስታውቀዋል።
በጋምቤላ ክልል ሙከራው ተጀምሮ ወደ ሌሎች ክልሎች የሚስፋፋው ይህ ሮግራም፤ የአምስት ዓመት ቆይታ ይኖረዋል፡፡
ሚኒስትር ኤርጎጌ ተስፋዬ 90 በመቶ የሚሆኑ የገጠር ሴቶች ከቀበሌ ጀምሮ ባሉ አደረጃጀቶች የራሳቸውን ሃብት እያፈሩ እንደሆነም ለሀገር ውስጥ ሚዲያ መግለጻቸውን ስፑትኒክ ዘግቧል፡፡
የቴሌግራም ቻናልችንን በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…

Published in
ዜና
Tagged under
Wednesday, 03 September 2025 18:12
ትራምፕ የቻይናን ፕሬዚዳንት በአሜሪካ ላይ በማሴር ወነጀሉ
• ክሬምሊን የትራምፕን ውንጀላ አጣጥሎታል
የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ፣ የቻይና አቻቸው ሺ ጂንፒንግ ከሩሲያና ሰሜን ኮሪያ መሪዎች ጋር በጥምረት በአሜሪካ ላይ እያሴሩ ነው ሲሉ ወንጅለዋል፡፡
ትራምፕ ይህንን ያሉት ቻይና በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወቅት በጃፓን ላይ ድል የተቀዳጀችበትን 80ኛ ዓመት መታሰቢያ አስመልክቶ ታላቅ ወታደራዊ ትዕይንት ዛሬ ረቡዕ ማካሄዷን ተከትሎ ነው።
በዚህ ታላቅ የወታደራዊ በዓል ላይ የሩሲያ ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን፣ የሰሜን ኮሪያው መሪ ኪም ጆንግ ኡንን ጨምሮ 26 መሪዎች ተገኝተዋል።
ትራምፕ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ላይ ለሺ ጂንፒንግ፤ "በአሜሪካ ላይ በጋራ እያሴራችሁ ላላችሁት ለቭላድሚር ፑቲንና ለኪም ጆንግ ኡን ሞቅ ያለ ሰላምታ አቅርብልኝ" ሲሉ መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡
ትራምፕ አክለውም፤ አሜሪካ በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወቅት ለቻይና የሰጠችውን ከፍተኛ "መስዋዕትነት" አውስተዋል።
"በርካታ አሜሪካውያን ለቻይና ድልና ክብር ሲሉ ሞተዋል። ለጀግንነታቸውና መስዋዕትነታቸው በትክክል እንደሚከበሩና እንደሚታወሱ ተስፋ አድርጋለሁ" ብለዋል፤ ባሰፈሩት መልዕክት፡፡
ክሬምሊን በበኩሉ፤ የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ያቀረቡትን የማሴር ክስ ውድቅ አድርጎታል፡፡
ዶናልድ ትራምፕ የሩሲያ፣ የቻይናና የሰሜን ኮሪያ መሪዎች በአሜሪካ ላይ እያሴሩ ነው በማለት የሰነዘሩትን ውንጀላ ያጣጣለው ክሬምሊን፤ በአሜሪካ ላይ የማሴርን ጉዳይ "ያሰበ እንኳ ማንም የለም” ሲል ምላሽ ሰጥቷል፡፡
የቴሌግራም ቻናልችንን በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…


Published in
ዜና
Tagged under

