Administrator

Administrator

አንድ ዛፍ የሚቆርጥ ጅል ሰው ነበረ፡፡
የሚቆርጠው ቅርንጫፍ ላይ ሆኖ ነው ዛፉን የሚቆርፈጠው፡፡፡ ይህን ያዩ አንድ አዛውንት፤
“አንተ ሰው ምን እያደረግህ ነው?”
“ለቤት መስሪያ እንጨት አንሶኝ ዛፍ እየቆረጥኩ ነው፡፡”
“አያ ያንተስ ቤት አልተሰራም ተወው” ብለውት መንገዳቸውን ቀጠሉ፡፡
ሰውዬው ከነከነውና ከዛፉ ወርዶ እየሮጠ ተከተላቸውና፤
“ለምንድነው ያንተ ቤት አይሰራም ያሉኝ?” ሲል ጠየቃቸው፡፡
“እየቆረጥክ የነበረውን እንጨትኮ የተቀመጥክበትን ነው፡፡ አብረህ ስለምትወድቅ ቤትህን ማን ይሰራዋል ብዬ ነው፡፡”
ሰውየው እኚህ ሰው ሞኝ ናቸው ብሎ መጥረቢያውን ወደተወበት ዛፍ ተመለሰና መቁረጡን ቀጠለ፡፡
ብዙም ሳይቆይ ከነእንጨቱ መሬት ወድቆ ተሰበረ፡፡
አዛውንቱ ሲመለሱ መሬት ላይ ወድቆ አገኙት፡፡
“እንዳልኩት መሬት ወድቀህ አገኘሁህ፡፡ የሰው ምክር አልሰማ ብለህኮ ነው” አሉት፡፡
ሰውዬውም፤
“አልተጎዳሁም፡፡ ትንሽ ግራ እግሬ ላይ ስብራት ነው የደረሰብኝ፡፡ ይልቁንም አንድ እርዳታ ቢያደርጉልኝ ጥሩ ነበር፡፡”
“ምን ልርዳህ?”
“እባክዎ የወደፊት እጣ ፈንታዬን ይንገሩኝ” አለና እግራቸውን ላይ ወደቀ፡፡
አዛውንቱም፤
“አህያ ሦስት ጊዜ ካስነጠሰ ትሞታለህ” አሉት፡፡ ስለትንበያቸው አመሰግኗቸው ወደ ቤቱ ሄደ፡፡ ቤቱ ደርሶ እከብት ጋጣ ጋ እንደቆመ አህያው አንድ ጊዜ አስነጠሰ፡፡
“ሰውዬው ያሉኝ ነገር ሊደርስብኝ ይሆን እንዴ?” ብሎ ስጋት ገባውና፣ አህያውን ሊያስነጥሰው ይችላል ያለውን የሚሸት ነገር ሁሉ ከአህያው አካባቢ ለማራቅ ሲያጓጉዝ አመሸ፡፡
ወደ እኩለ ሌሊት ላይ ግን አህያው ለሁለተኛ ጊዜ አስነጠሰ፡፡
ሰውዬው በጣም ተጨነቀ፡፡ ስለዚህ አህያ በሦስተኛ ጊዜ እንዳያስነጥስ ዘዴ መፈለግ ጀመረ፡፡ አንድ ዘዴ መጣለት፡፡ የአህያውን አፍንጫ በድንጋይ መድፈን፡፡
ድንጋይ አመጣና ምንም ቦታ ሳያስተርፍ የአህያውን አፍንጫ ደፈነው፡፡
በሰራው ስራ ተኩራርቶ አህያው ፊት ቆሞ ሳለ፣ አህያው ለመተንፈስ በመቸገር ጭምር አንዴ አምጦ ክፉኛ አስነጠሰ፡፡ ባፍንጫው የተጠቀጠቀው ድንጋይ ተፈናጥሮ ወጣና የሰውዬውን ደረት አጎነው፡፡ ሰውዬው ወደ ኋላው ተፈነቸረና ሞተ፡፡
***
በገዛ እጅ የገዛ ራስን መጥፊያ ማመቻቸት የሞኝነት ሁሉ ሞኝነት ነው፡፡ የሚነገረንን ምክር ልብ ብሎ መስማት ዋና ቁም ነገር ነው፡፡ ይደርሳል ተብሎ የሚታሰብን ችግር ለመፍታት ሌላ ችግር በራስ ላይ መጋበዝ የጥፋት ሁሉ ጥፋት ነው፡፡ ችግሮችን የባሰ ያወሳስባልና፡፡ አህያዋ እንዳታስነጥስ ብሎ ማስነጠሸዋን ለመዝጋት መሞከር የዋህነት ነው፡፡
በሀገራችን ካየነው የረዥም ጊዜ የትግል ጉዞ ሦስት ባህርያት ጎልተው ይታያሉ፡፡ አንደኛው ትግል የተመሰረተበትንና የቆመበትን መርህ እንደ ዛፍ ቆራጩ ላይ ላይ ተቀምጦ ገዝግዞ መቁረጥና አብሮ መንኮታኮት ነው፡፡ አደርገዋለሁ ያሉትን ሳያደርጉ በአጭር መቀጨት፡፡ ሩቅ አስቦ ቅርብ ማደር፡፡ ቶሎ ተስፋ መቁረጥ፡፡ ጨለማ ጨለማውን ብቻ ማየት፡፡ ሁለተኛው ዘላቂ ጎዳና ላይ ከወጡ በኋላ ከተለዋዋጩ የዓለም ሁኔታና ነፀብራቁ ከሆነው የሀገር ሁኔታ ጋር በአዲስ መልክ ራስን ለመለወጥና ለመጠንከር ዘዝግጁ አለመሆን ነው፡፡ ሦስተኛው ሌላውን በልጠው ካልታዩ ለመጠንከር ዝግጁ አለመሆን ነው፡፡፡ የራስ ማደግ አልታይ ማለት ነው፡፡ ይህ እውን ይሆን ዘንድ ሌላውን እስከመጥለፍ አልፎም እስከ ማጥፋት መሄድ ነው፡፡ ክፉ አባዜ፡፡


አንድ የሀገራችን ፖለቲከኛና ምሁር በፃፈው አንድ መጽሐፍ ላይ እንደጠቀሰው፤ “ጊዜው የጨለመ ይመስላል እንጂ የረጅሙ ጊዜ የኢትዮጵያ ተስፋ ብሩህ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ህዝብ በአንድ ድምጽ ሆኖ በነፃነት ብቻ ነው መኖር የምንፈልገው፤ በፍርሃት ማህበረሰብ ውስጥ መኖር በቅቶኛ ብሏል፡፡ አንዴ ይህን የወሰነ ህዝብ በጉልበት ተመልሶ የፍርሃት ጨለማ ውስጥ አይኖርም፡፡ ትልቁ የአሁን ጊዜ የፖለቲካ ሃይሎች ፈተና፣ ይህንን የረጅም ጊዜ ብሩህ ተስፋ የሚጎዱ እንዳይሆን መጠንቀቅ ነው፡ ለዚህ ነው የተቃውሞ ሀይሎ በአጭር ጊዜ በተወሰደባቸው የሀይል ርምጃ በመገፋት የቂምና የጥላቻ ጨለማ ውስጥ ላለመግባት መጠንቀቅ ያለባቸው፡፡ ይህ ማለት ጨቋኞችን ማባበል አለባቸው ማለት አይደለም፡፡ ይልቁንም ማንዴላ እንዳሉት፤ በጉልበት የሌላውን ነፃነት ለመውሰድ የሚፈልጉ እነዚህ ሰዎች ራሳቸው በጥላቻና በትእቢት እስር ቤት ውስጥ የሚገኙ ናቸውና፣ ከጥላቻ ይልቅ ሀዘኔታችንን ነው ልንሰጣቸው የሚገባው፡፡ የሌሎቻችን ነፃ መውጣት እነሱንም ነፃ የሚያወጣቸው መሆኑን ሁልጊዜ ልንነግራቸው ይገባል፡፡ ይህን ለማድረግ የሚያስችል ጠንካራ መንፈስ ሲኖረን እኛም ለእውነተኛ ዴሞክራሲ የተዘጋጀን መሆናችንን እናስመሰክራን” ይላል፡፡


ተስፋን ከጨለማ ውስጥም ቢሆን ማውጣት ይቻላል፡፡ ሆኖም ተስፋ በመጀመሪያ ከየራሳችን የልብ ብሩህነት የሚመነጭ መሆኑን አለመዘንጋት ነው፡፡ ከየራሳችን የእለት የሰርክ የህይወት ሂደት ውስጥም ጨላማና ብርሃን መኖሩን ማስተዋል ነው፡፡ እያንዳንዱ የመስተዋት ጡብ የፀሀይ ብርሃን በሌለበት ወገን ጨለማ አለው፡፡ ጡቡን ወደ ፀሀዩ ወገን ለማዞር መሞከር ነው ዋናው፡፡ ይህም ቢሆን ዋጋ ይጠይቃል፡፡ አልፎ ተርፎ መስዋዕትነትም ይጠይቃል፡፡ ይህንን እሳቤ በፖለቲካ መልኩ ስናጤነው፣ በትግል ውስጥ መቼም ቢሆን መቼ አቀበትና ቁልቁለት፣ ማሸነፍና መሸነፍ፣ መውደቅና መነሳት ሁሌም አለ፡፡ ካያያዝ ይቀደዳል፤ ካነጋገር ይፈረዳል፡፡ ትግል የስልትና የስትራቴጂ የማሕበራዊ መስተጋብርና የልምድ አጠቃቀም ግብዓት ውጤት ነው፡፡ ግትርነት፣ እልህ ቂምና አለሁ - አለሁ ባይነት ተስፋ ሳይሆን፣ ግንፍል ስሜትን፤ ፍሬያማነትን ሳይሆን መጨንገፍን ነው የሚወልደው፡፡ ሌላው ትኩረት የሚሻው ነገር የጊዜ አጠቃቀም ነው፡፡ የረዥም ጊዜ ትግል ጽናት መያዝን ይጠይቃል፡፡ ሳይታክቱ መጓዝን ይጠይቃል፡፡ የነዚህ ሁሉ መጠቅለያ የሰው ነገር መስማት ነው፡፡ የሰሙት ጥሩ ሆኖ ሲገኝ ስራ ላይ ለማዋል መድፈር ነው፡፡ ለመለወጥም ለመለወጥም (ለ ትጠብቃለች) ዝግጁ መሆን ነው፡፡ አዳዲስ ሀሳብን መቀበል ከችግር መውጣት ነው፡፡ ከህመም መፈወስ ነው፡፡ አላዋቂ ከሚስምህ አዋቂ ያስታምህ የሚባለው ለዚህ ነው፡፡

• 10 ታዋቂ የቡና አምራች ኩባንያዎች በፌስቲቫሉ ይሳተፋሉ

• የኢትዮጵያ ቡና በጃዝ ሙዚቃ ይደምቃል ተብሏል

• 3ሺ ገደማ ጎብኚዎች እንደሚታደሙበት ይጠበቃል

 

በኢትዮጵያ የመጀመሪያ ነው የተባለለት የቡና ፌስቲቫል (ኮፊ ፌስት) የፊታችን ቅዳሜና እሁድ በሸራተን አዲስ ሆቴል የሚካሄድ ሲሆን፤ በፌስቲቫሉ ላይ አሥር የሚደርሱ ታዋቂ የቡና አምራችና ላኪ ኩባንያዎች ይሳተፉበታል፡፡


የቡና አምራች ኩባንያዎቹ የተለያዩ ዓይነት የቡና ምርቶቻቸውን የሚያቀርቡ ሲሆን፤ ለኤክስፖርት የተዘጋጁ የቡና ምርቶችን ጨምሮ ለሸያጭ ይቀርባሉ ተብሏል፡፡ የቡና ቀመሳ ሥነስርዓትም ይካሄዳል፡፡


ለሁለት ቀናት የሚካሄደውን የመጀመሪያውን የቡና ፌስቲቫል አስመልክቶ የኹነቱ ጠንሳሾችና አዘጋጆች ዛሬ ጠዋት ረፋዱ ላይ በሸራተን አዲስ ሆቴል ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡


ከፌስቲቫሉ ግንባር ቀደም ስፖንሰሮች አንዱ የሆነው ሸራተን አዲስ ዋና ሥራ አስኪያጅ - በመግለጫው ላይ የተገኙ ሲሆን፤ በኢትዮጵያ የመጀመሪያው የቡና ፌስቲቫል በሆቴሉ መዘጋጀቱ ልዩ ደስታና ጉጉት እንደፈጠረባቸው ገልጸዋል፡፡

የኢትዮጵያ ቡና ፌስቲቫል የመካሄድ ዓላማን ያብራሩት አዘጋጆቹ፤የኢትዮጵያን ቡና በሚገባው ልክ ለማክበርና ለማጉላት ነው ብለዋል፡፡ ”እኛ ኮፊ ፌስትን እንደ በዓል ነው የምንቆጥረው፤ቡናችንን የምናከብርበትና የምናጎላበት ታላቅ በዓል፡፡” ሲሉም አስረድተዋል፡፡

እንደ ጀርመን ያሉ አገራት በኦክቶበር ፌስት (ዓመታዊ የቢራ ፌስቲቫል) እንደሚታወቁ የጠቀሱት አዘጋጆቹ፤ ኢትዮጵያም በቡና ፌስቲቫል (ኮፊ ፌስት) መታወቅ አለባት ብለው እንደሚያምኑ ተናግረዋል፡፡

በአገራችን በየዓመቱ የተለያዩ የቡና ቀመሳ ዝግጅቶች እንደሚካሄዱ ያወሱት አዘጋጆቹ፤ ኮፌ ፌስትን ለየት የሚያደርገው ለአምራቾችና ለላኪዎች ብቻ የተዘጋጀ ሳይሆን ለሁሉም ኢትዮጵያዊ ነው ብለዋል፡፡

”ለዚህም ነው መግቢያውን በነጻ ያደረግነው፤ ማንኛውም የቡና ወዳጅና አፍቃሪ የፊታችን ቅዳሜና እሁድ በሸራተን አዲስ መታደም ይችላል” ሲሉም ጋብዘዋል፡፡


በሁለቱም ቀናት ፌስቲቫሉ በታዋቂ የጃዝ ሙዚቀኞች የሚታጀብና የሚደምቅ ሲሆን፤ ይህም ኹነቱን አይረሴ እንደሚያደርገው ታምኗል፡፡ የመጀመሪያውን የኢትዮጵያ የቡና ፌስቲቫል፤ ዳሸን ባንክና ሸራተን አዲስን ጨምሮ ሌሎች ስመጥር ድርጅቶች ስፖንሰር ያደርጉታል፡፡


ፌስቲቫሉን ያዘጋጁት ፕሮሎግ ማርኬቲንግ፣ ዩቦራ ኮሙኒኬሽን እና ቢዮንድ ቡና በመተባበር መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡

በአደራ ከቆመበት የመኪና መሸጫ ግቢ ውስጥ በጥበቃ ሰራተኛው አማካኝነት የተሰረቀው መኪና ከአንድ አመት በኋላ ተገኘ።

ጥበቃው መኪናውን ለመስረቅ አስቦና አልሞ፣ ሥራ ፈላጊ መስሎ በመኪና መሸጫው መቀጠሩንም አምኗል።

ሰኔ 15 ቀን 2015 ዓ.ም፣ ለሰኔ 16 አጥቢያ፣ በአዲስ አበባ ቡልጋሪያ አካባቢ ከሚገኘው ታዋቂ የመኪና መሸጫ ግቢ ውስጥ ተሰርቆ የነበረው፣ 2022 Rava 4 መኪና ህዳር 18 ቀን 2017 ዓ.ም በኦሮሚያ ክልል ዱከም ከተማ ተገኝቷል።

በተለያዩ ስሞች የሚንቀሳቀሰውና በመኪና መሸጫው ጌታነህ ብርሃን በሚል ስም የተመዘገበው ተጠርጣሪው ቀደም ብሎ ተይዞ የነበረ ሲሆን፤ ወደ መኪና መሸጫው በጥበቃ ሰራተኝነት ተቀጥሮ የገባው መኪናውን ለመስረቅ በማሰብ መሆኑን የእምነት ክህደት ቃሉን በሰጠበት ወቅት ተናግሯል።
ተጠርጣሪው እስካሁን በዚህ አይነት ከባድ የስርቆት ወንጀል ከ80 በላይ መኪኖችን የሰረቀ ሲሆን፤ በተመሳሳይ ቡልጋሪያ አካባቢ በሚገኘው መኪና መሸጫ ውስጥ አብረውት ይሰሩ የነበሩ የጥበቃ ሰራተኞችን በጠላ ውስጥ አደንዛዥ መድሃኒት በመጨመርና እንዲጠጡ በማድረግ መኪናውን እንደሰረቀ ታውቋል።

በዚህም ከአንድ አመት ከስድስት ወር የፀጥታ አካላት ፍለጋና ርብርብ በኋላ፣ የተሰረቀው መኪና ሻንሲ ቁጥሩ ተቀይሮ ተገኝቷል።

መኪና ሻጮቹ በጓደኝነት ለመተባበር በቅን ልቦና በማሰብ ግቢያቸው ውስጥ ያስቀመጡት መኪና ጣጣ ይዞባቸው መምጣቱ ቢያሳዝናቸውም፣ በፖሊስ አባላትና በመኪና ሻጮቹ ጥረት በስተመጨረሻ የመኪናው መገኘት እንዳስደሰታቸው ገልጸው፣ ፖሊስን አመስግነዋል።

Monday, 25 November 2024 07:46

ባየሽኝ ግዜ

ላይሰናስል ሳዳውር፤
ላይጠረቃ ሳጋብስ፤
አለሁ እንዳጋሰስ።
ላይከትም ከአቦል ጀምሬ፣
በረካ አልባ ቡን ሳንቃርር፣
የማይፈፀም ሩጫ ገጥሜ፣
በባእዳን ውርጭ ጠይሜ፣
ስኳትን ቅስሜን ቀልጥሜ፣
“ቃል” ላይወጣኝ ተለጉሜ፣
“ኖሯል” ካልሽው ፥ ይኸው አለሁ።
የቅኔ ቆሌዬ በኖ፤
ዲዳነት ቋንቋዬ ሆኖ፤
ደስታ ጣእሙ ጠፍቶ፤
በአልጫ ኑሮ ተተክቶ፤
ከተማ ሳለሁ ድብርት፤
ከአሸን መሃል ብቸኝነት፤
አየሽ ጉዴን የኔ እናት!
ነጠላ ነብሴ ጤዛሽን ሲሻ፣
ሐሞቴ በጥምሽ ሲደብን፥
አለመጣራትሽ ይነደኛል፤
ዝምታሽ ያበሳጨኛል፤
ለምን ፥ ግን ለምን ይለኛል፤
ልቀጣሽ ፥ ልቆጣሽ ወጥናለሁ፣
ቀን ያማይወልድ ፥ ቃል አሰናዳለሁ፤
ኩርማን ምናቤን አዋክቤ፣
ቃል ከሃሳብ አናብቤ፣
የምትጎጂበትን ባልጩት ጠርቤ፣
የምወግርበት ደንግያ ፡ ለስድቤ፣
አጫለሁ ፥ እሰደራለሁ፤
አፌን ከፍቼ አንቺን ልቆጣ፣
የብሶትን ትንፋግ ፡ ጮኬ ላስወጣ፣
የቃላት ሳማ ቀነጥባለሁ፤
ጭካኔሽን ልዘረዝር፥
ስንክሳሬን አዘጋጃለሁ፤
ንጋት ጠብቅና ቀና እላለሁ፤
ማልጄ ወደ ምስራቅ አያለሁ፤
ከማትጠፊበት አማትራለሁ፤
ያኔ ትወጫለሽ፤
ጨለማን ገሰሽ ትፈነጥቂያለሽ፤
ባየሁሽ ፥ ባየሽኝ ግዜ. . . .
የወጠንኩትን ፥ ቃል ጥያቄዬን ዘነጋዋለሁ፤
ሁሉ ይጠፋና ትሁት ሆናለሁ፤
ሳይሽ ፥ ሳይሽ... ውላለሁ፤
በምትሄጂበት እከተላለሁ።
(ያሬድ ይልማ)

፨ ኢትዮጵያ የብዙኀን ሀገር ናት። የአንድ ጎሳ፣ የአንድ ሰው፣ የአንድ ሃይማኖት፣ የአንድ ወገን ሀገር ኾና አታውቅም፤ አትኾንምም። ኢትዮጵያ የብዙ ዘመን ታሪክ የኖራትም ኾነ አሁን ድረስ ከነ’ክብሯ’ ያለችው በተለያዩ አለላዎች የተሰፋች ስለኾነች ነው። ፕሮፌሰር ላጲሶ ጌ. ዴሌቦ በ1991 ‹እፎይታ› መጽሔት ላይ ‘ታሪካዊ ትንታኔ’ በሚል ርዕስ እንደጻፉት፦ ‹‹ከ330 እስከ 615 ድረስ በ285 ዓመታት ውስጥ ኦሪት፣ ክርስትናና ኢስላም ቤተ-መንግሥት ውስጥ ገቡ። ሃይማኖቶቹን ያመጧቸው ግሪኮች፣ ሮማውያን እና የአረብ ስደተኞች ናቸው።[...] ከክርስትና ከኦሪትና ከእስልምና መካከል አንዳቸውን ብንቀንስ ኢትዮጵያ የሚባል ነገር አይኖርም፤ ይላሉ። ይህ እውነታ በሀገራችን ለረዥም ዘመን የነበረ ቢሆንም አሁንም ድረስ በ’አንዳንድ’ ሰዎች ዘንድ ተቀባይነት ያለው አይደለም። ‹‹መጤ ነው›› የሚል የኋላቀር አስተሳሰብ በአዕምሯቸው ያቆሩ ሰዎች አሉ። መጀመሪያ የነበረችው ኢትዮጵያ ናት፤ ከዛ አስተማሪዎች እና ስደተኞች መጡ። አስተማሩ ተመለሱ። ኢትዮጵያ ውስጥ የነበሩ ሕዝቦች አምነው ተቀበሏቸው። ተቀባዮቹ ኢትዮጵያውያን ናቸው። ስለዚህ ማንም መጤ የለም። ከእነዚህ ሰዎች አንዱ ቢጎድል “ኢትዮጵያ” የምንላት ሀገር አትኖረንም። ፕሮፌሰሩ ሲቀጥሉ ‹‹...ግጭት ሳይኖር ማዋሃድ የኢትዮጵያ ልዩ ባህሪ እንደኾነ ያሳያል። ክርስትናን እስልምናን እና ኦሪትን መንግሥቱና ሕዝቡ በፈቃደኝነት ነው የተቀበላቸው።››
፨ ሰው ሳይፈልገው በኾነው ነገር ማንም አይወቅሰውም፤ ማንም አይሸልመውም። “ነጭ ስለኾነ ጥቁር ስለኾነ፣ እዚህ ጎሳ ወይ እዚያ ጎሳ ስለተወለደ” ብሎ አንድ ሰው ሌላውን መውደድ ወይ መጥላት አላዋቂነት ነው። አሁንም ድረስ፤ የተዋለደ፣ አብሮ የኖረ፣ የተዋደደ፣ አብሮ ያደገን ማኅበረሰብ፤ በውስጡ ‹ወገኔ አይደለም› ብሎ የሚያስብ ሰው መኖሩ ያስገርማል። ‹‹የኢትዮጵያን ታሪክ ሲጽፉ የኖሩት ደብተራዎች ናቸው።›› ይላሉ ፕሮፌሰሩ ‹‹በጽሑፋቸው ውስጥ ሕዝቡን ጠላትና ወገን ብለው ነው የሚፈርጁት።›› ከዕውቀት ማነስ አልያም በልብ አምኖ ‹ጠላቴ ነው፣ አረመኔ ነው› ብሎ ማሰብ የሀገራችን እድገት እንቅፋት ኾኖ የኖረና በዚሁ የሚቀጥል ከኾነም ለአገራችን ጎጂ መሆኑን መረዳት ተገቢ ነው፡፡
፨ በ2008፣ በሁለተኛ እትም ተሻሽሎ የታተመው፣ በአለቃ ተክለኢየሱስ ዋቅጅራ የተጻፈውን ‹የኢትዮጵያ ታሪክ› መጽሐፍ አንድ ምዕራፍን እንቃኛለን፡፡ መጽሐፉ በዶክተር ሥርግው ገላው ተዘጋጅቶና ተስተካክሎ (አርትዖት ተደርጎ) የታተመ ነው። የምናየው ምዕራፍ ፯(7) ‹‹ከዐፄ ገብረመስቀል በኋላ በኢትዮጵያ ስለ ነገሡት ነገሥታት፣ ስለ እስልምና ሃይማኖት›› የሚለውን ነው።
፨ ያለ አንዱ ጎሣ፣ ያለ አንዱ ሃይማኖት ኢትዮጵያ የምትባል ሀገር የለችም። የብዙኀን ደሴት እንጂ ለይቶ ‹‹የእንቶኔ›› ደሴት ናት ማለት ጭፍንነት ነው። አለቃ ተክለኢየሱስ ዋቅጅራ በዚህ መጽሐፋቸው (ከላይ በጠቀስነው ርዕስ) የተለየ ወገንተኝነት አንጸባርቀዋል። መነሻ መረጃ በሌለው ትርክት ‘ታሪክ’ ብለው ጽፈዋል። የራሳቸው ‘ሃይማኖት’ ላይ የሚያተኩር መጽሐፍ ጽፈው ቢኾንና እንዲህ ዓይነት ነገር ቢጽፉ ተቀባይነት ሊኖረው ይችላል፤ ግን ‹የኢትዮጵያ ታሪክ› ብለው ራሳቸውን አሞግሰው ሌላውን አኮስሰው ማቅረብ ስህተት ነው። ምክንያቱም ሀገሪቷ ኢትዮጵያ ራሷ አስማምታ ያኖረችውን እሳቸው ሊሽሩ አይችሉም። በመረጃ እጦት ወይ በዕውቀት ማነስ ከኾነ እልፎች ታሪኩን የሚያውቁ በአቅራቢያቸው ማግኘት ይችሉ ነበር። ስህተቱ ደግሞ በጸሐፊው ብቻ ሳይኾን በአርታዒውም ጭምር ነው፤ ‹‹አለቃ ተክሌ እንዲህ ብለው ጽፈዋል ግን ታሪኩ እንዲህ ነው›› ብለው በኅዳግ ማስታወሻም ቢኾን ማቅረብ ይችሉ ነበር። ሁለቱም ለፍተው ለሕዝቡ ትክክለኛ ‘ታሪክ’ን ለማድረስ ጥረዋል፤ በዚህ ይመሰገናሉ። ኾኖም እንደው ሰዎችን ባያገኙ ቢባል እንኳ በሚፈልጉት ቋንቋ የተጻፉ በርካታ መጻሕፍት ነበሩ። በ’ሀገራችን ታሪክ’ ሥም ጥላቻ እና ወገንተኝነት ማንጸባረቅ የ ‘አዋቂ’ ሰው ተግባር አይደለም። የጸሐፊውን ስህተት በዘመናቸው የነበረውን የ’አግላይነት ፖሊሲ’ ተከትለው ነው በሚል ማስተባበያ ብናቀርብ አርታዒው ግን ቢያንስ ትክክለኛውን መረጃ ማቅረብ ነበረባቸው።
፨ ገጽ 10 ላይ መጽሐፉን የጻፉበትን ምክንያት ‹‹ታሪክ ጸሐፊዎች በአድርባይነት ሚዛናዊነት የጎደለው ታሪክ ጽፈው በማንበቡ ይህንን ስህተት ለማረምና ሚዛናዊ የሆነ ታሪክ ለመጻፍ ነው።›› ብለው የጠቀሱትን ተቃርነዋል። (የማተኩረው በሌሎች ታሪኮች ሳይኾን ከላይ በተጠቀሰው ርዕስ ላይ ብቻ ነው፡፡)
፨ እንቀጥል፤ ገጽ 116 ላይ እንዲህ ይላሉ፦ ‹‹... ክርስቶስ በተወለደ በ፮፻፳፪(622) ዘመን መሐመድ ተወለደ።›› ብለው ያስቀምጣሉ። በየትኛውም የታሪክ መዝገብ ብናይ፣ የትኛውንም የ‹ሲራ› (የነብዩ ሙሐመድ(ሰ.ዐ.ወ) ታሪክ) መጻሕፍት ብናነብ፣ የነብዩ ሙሐመድ ውልደት በ570 ወይ 571 እ.ኤ.አ እንደኾነ እናረጋግጣለን። ለምሳሌ አንድ መጽሐፍ ልጥቀስ፦
‹‹ነብዩ ሙሐመድ(ሰ.ዐ.ወ) በመካ ከተማ በ570(ድ.ል) ተወለዱ።››(የተረሳው ኢስላማዊ ታሪካችን፣ 13)
አለቃ ተክለኢየሱስ ስለ ነብዩ ሙሐመድ (ሰላም በርሳቸው ላይ ይሁን) መወለድ ከነገሩን በኋላ ‹‹የመሐመድ ታሪክ እንዲህ ነው።›› ብለው ቀጥታ ስለ ፋርስ ንጉሥ፣ እሳቸው ከስርይ ወይም ከስሪ ስለሚሉት ወደ ኪስራ ታሪክ ይገባሉ፤ ከውልደታቸው ወዲያው ዘለው ወደ ሥድስተኛው አመተ ሂጅራ ወይም ወደ 628 (እ.ኤ.አ)። ምክንያቱም በነብዩ ሙሐመድ መልዕክተኛ አብደላህ ቢን ሁዘይፋ ሳህሚ የኢስላም ጥሪ የኪሥራ ቤተ-መንግሥት የገባው በዚህ ዓመት መኾኑን የታሪክ መጻሕፍት ያስረዳሉ። ቀጥለው ‹‹እስላም ገባበት። ሥሙም እስጥንቡል[እስታንቡል] ይባላል።›› ይላሉ። የቱርክ ከተማ የኾነችው ኢስታንቡል ወይም ቆስጠንጢኒያ የተከፈተችው ከነብዩ ሙሐመድ ኅልፈት ከ850 ዓመት በኋላ ነው። በ21 ዓመቱ ወጣት ሙሐመድ አል-ፋቲህ በሜይ 29, 1453(ጁማደል ዑላ፣ 15፣ 857 አመተ ሂጅራ) ነው - የተከፈተችው። ኢስታንቡል የሚለው ሥሟም የተሰየመው ያን ጊዜ መኾኑን ታሪክ ዘግቧል። እኛ አማን አሰፋን እንጥቀስ፦ ‹‹የከተማዋን ሥምም ቀየረ። አዲስ ሥም አወጣላት። ኢስላም ቡል አላት። የኢስላም ከተማ (መዲነቱል ኢስላም) ማለት ነው።›› (በሠይፎች ጥላ ሥር፣ 104)
፨ ቀጥሎ ‹‹ከክርስቶስ ልደት በኋላ ፮፻፴ ዘመን ነው። በዚያም እስላሞች ዓለሙን ሁሉ አሰለሙት። እጅግ በረቱ። በኢየሩሳሌም በጌታ መቃብር መስጊድ ሠርተዋል።››(116-117) ይላሉ። በእሳቸው አጻጻፍ ካየን ነብዩ ሙሐመድ በ622 ተወልደው በ630 ደግሞ ዓለሙን ካሰለሙት፤ በሥንት ዓመታቸው ነብይ ኾኑ? በሥንት ዓመታቸው አስተማሩ? በ8 ዓመታቸው ዓለምን መቆጣጠር የሚያስችል ጉልበት አገኙ? ስለዚህ ራሳቸው በጻፉት ስህተት መኾናቸውን ገለጹ። በ630 ነብዩ በመዲና ነበሩ። ያኔ ዓለምን ሙሉ የተቆጣጠሩበት ጊዜ አልነበረም። ወደ መላው ዓለም በስፋት ‹ኢስላምን ለማስተማር› የተሄደው በአራቱ ኸሊፋዎች ማለትም በአቡበከር፣ ዑመር፣ ዑስማን እና ዐሊይ ዘመን ነበር። ‹‹በኢየሩሳሌም በጌታ መቃብር መስጊድ ሠርተዋል።›› የሚለውም በ630 በነብዩ ዘመን ሳይኾን በዑመር ዘመን በ637(638) ነው(17 ወይም 16 አመተ ሂጅራ) ነው። ታሪክ ስናነብ እንደምናየው ዑመር ያን ጊዜ ኢየሩሳሌምን እየጎበኙ የሰላት ወቅት ደርሶ ቄሶች ‹‹ግባ እና ቤተ-ክርስቲያን ስገድ›› ቢሏቸው ‹‹ወደፊት የሚመጡት ህዝቦች ‘ዑመር ሰግዶበታል’ ብለው እንዳይወስዱባችሁ እፈራለሁ›› ብለው ሌላ ቦታ ሰገዱ፤ እንጂ አስገድደው ወሰዱ የሚል የለም።
፨ የአንድ ሐገር ሰው ኾነው ‹ይኸው የሐገራችንን ታሪክ ነው የጻፍኩት› እያሉ ግን በአግላይነት፣ በ‹አላውቅህም› ባይነት ‹‹ያንተ ሃይማኖት እኮ የጌታዬ እርግማን ነው።›› ዓይነት ማለት ጭፍን ወገንተኝነት ነው። እንዲህ ዓይነት “አሻሚ” ሃሳቦችን የሃይማኖት መጽሐፍ አዘጋጅተው በተዓማኒ ማስረጃ ላይ ማስተማር እንጂ በ‹ኢትዮጵያ ታሪክ› ሥም ማስፈር ስህተት ነው።
ይቀጥሉና፤ ‹‹የመሐመድ ታሪክ እንዲህ ነው። መሐመድ በመዲና በዓረብ ሀገር ተወለደ።››(117) ይላሉ፤ ይሄ ፍጹም ስህተት ነው። ከመረጃ እጦት አይመስለኝም፤ ምክንያቱም ዝቅ ብለው አባታቸው ገና ነብዩ ሳይወለዱ(ተረግዘው ሳሉ) እንደሞተ ይናገራሉ። ይህን ታሪክ የሰሙበት ወይ ያነበቡበት ቦታ ላይ ነብዩ በመካ እንደተወለዱ ያሳያቸዋል። እናታቸው የሞተችው 7 ዓመታቸው እያሉ(117) ሳይኾን 6 በሚል ይስተካከል። ቀጥሎ ‹‹በተወለደ በ፲፭(15) ዓመቱ ከመካ ታላቅ ሴት ባለጸጋ አገባ።›› ብለው ኸዲጃን፤ ህድጅ፣ ከዲቻ ብለው ይጠቅሳሉ። ይህም ትልቅ ስህተት ነው፤ ይህም ካነበቡበት ወይ ከሰሙበት ቦታ 25 እንጂ 15 የሚል አይኖርም።
፨ ትልቁ እና ዋነኛው ስህተታቸው የሀገራቸውን ሰው ከድተው ወገንተኝነታቸውን ያሳዩበት ‹ነብዩ ሙሐመድ በረኃ ለበረኃ ሲንከራተት ቆይቶ ራሱን ነብይ አደረገ፤› ብለው ከዕውነታው የራቀ እርሳቸውንም የሚያስገምት ጽሑፍ መጻፋቸው ነው፡፡ በጉዳዩ አለማመን መብታቸው ነው፤ ግን ‹የሀገር ታሪክ› ብለው እስከጻፉ ድረስ የሀገራቸው ሰው የኾነው የሚያምንበትን ጠይቆ እና ተረድቶ መጻፍ አዋቂነት ነው። ዘመዶቹ ስለሆኑ አመኑለት ለማለትም ‹‹ምሽቱና አሽከሮቹ፣ ሰይድ ባሪያው በርሱ አመኑ። የቅርብ ዘመዶቹ ዓሊና መሐመድ ያቡበከርን ልጅ አግብቶ ነበርና...›› ብለው ‘ያመኑለት ለዝምድናው ነው’ን ያስተላልፋሉ። አንደኛ ነገር ሰይድ የሚባል ባሪያ አልነበረም። አቡበከርም የሰለመው ልጁን ስላገባለት የሚለውም ልክ አይደለም። ዓዒሻ የአቡበከር ልጅ እና ነብዩ ሙሐመድ የተጋቡት እርሷ 18(ወይም 20) ዓመት ሲሆናት በ2ኛው አመተ ሂጅራ፣ ነብይ ከኾኑ በ15ኛው ዓመት ማለት ነው።
፨ ‹‹ከዚያ በኋላ የመካ ሰዎች ከነደቀ መዛሙርቱ አባረሩት። መዲና ተመለሰ። በሐምሌ ፲፭(15) ቀን ከክርስቶስ ልደት በኋላ በ፮፻፴፬(634) ዘመን ነው። ነገር ግን ኤድስከሬ የሚባል የመዲና ሰው በክብር ተቀብሎት ነበረ። በነዚያ ኃይል መካን ወግቶ ተመለሰ። ከዚያ ወዲያ ወደ ዕስጥንቡል ንጉሥና ወደ ፋርስ ንጉሥ ይልክ ጀመረ። ነብይነቱን እንዲያውቁለት።›› እዚህ ላይ ብዙ ልክ ያልኾኑ ነገሮችን መልቀም እንችላለን። የመጀመሪያው፦ “የመካ ሰዎች ከነደቀመዛሙርቱ አባረሩት። መዲና ተመለሰ።” ይላሉ፤ እዚህ ጋ የ‹ኢትዮጵያን ታሪክ› የሚጽፉ ከኾነ ተሰደው ወደ ኢትዮጵያ መጥተው ስለነበሩት ሰሀቦች ታሪክ አልጻፉም። የሀገራቸውን ትልቅ ታሪክ ዘለዋል። ሁለት፦ ቅድሚያ መዲና ይኖሩ እንደነበር አርገው ‹ተመለሱ።› ይላሉ። ሦስት፦ ‘በ634 ነው’ ይላሉ፤ ይህም በሳቸው ሂሳብ በ622 ተወልደው፣ ነብይ ሆነው፣ አሳዳጅ ተሳዳጅ የኾኑት በ12 ዓመታቸው ነው። ኸዲጃን ደግሞ ያገቡት በ15 ዓመታቸው፤ በየትኛው የሂሳብ ህግ እንዲህ እንደሚመጣ አላውቅም። አራት፦ ‘ኤድስከሬ የሚባል ሰው’ ይላሉ። ይህን ከየትኛው መዝገብ አግኝተው እንደጻፉት እኔ አላውቅም፤ የነብዩን ዝርዝር የሕይወት ታሪክ የጻፉ(ሁሉም) እንዲህ የሚባል ግለሰብ አልጠቀሱም። ‘መካን ወግቶ ተመለሰ’ ብለውም፤ ነብዩ ሙሐመድ መዲና ከተሰደዱ ከ8 ዓመት በኋላ(ማለትም በDecember 629 ወይም በJanuary 630) የተከናወነን ጉዳይ ይጠቅሳሉ፤ ደግሞም በጦርነት እንደተከፈተ ነገር ‘ወግቶ ተመለሰ።’ ይላሉ፤ ‹ረሒቀል መኽቱም› የሚለው የነብዩ ሙሐመድን ሕይወት የያዘው መጽሐፍ ስለዚያን ጊዜ ገጽ 316 ላይ እንዲህ ይላል፦ ‹‹በተለምዶ በጉዞ ወቅት ከሚያዘው የነፍስ ወከፍ መሳሪያ፣ ማለትም ሰይፍ ከነአፎቱ ካልሆነ በቀር የጦር መሳሪያ አልያዙም። ምክንያቱም የመዋጋት ሐሳብ አልነበራቸውምና።›› እናም ወግተው ገቡ የሚለው መሰረት የሌለው ተረክ ነው። አምስት፦ ከላይ እንደተገለጸው የኢስታንቡል ጉዳይ ነው።
፨ ቀጥሎ እስከ መጨረሻው(ገጽ 118) ድረስ ያለው በጥቂት መነሻ ላይ ራሳቸው ጨምረው የጻፉበት፣ ለ‹ኢትዮጵያ ታሪክ›ነት የማይበቃ ወገንተኝነት ያንጸባረቁበት ጽሑፍ ነው። በአርታዒው(?) የኅዳግ ማስታወሻ ላይ ቢስተካከልም ‹‹በትንሣኤ ሙታን ግን አያምንም።›› ብለው የዕምነቱ መሠረት የኾነውን ክደው፤ የሃይማኖቱ ትዕዛዛትንም እንደ ማናናቅ አድርገው (‹‹የመሐመድ ሃይማኖት ትዕዛዙ ይህ ነው።[...] አካልን ሁል ጊዜ መታጠብ።››) ሲሉ ጽፈዋል። ‹‹ክፉ የሠራ በገሃነም መልካም የሠራ በገነት እንዲኖር ያውቃል።›› እያሉ “ትንሣኤን አያውቁም” ማለት ከ’አዋቂ’ ሰው የማይጠበቅ ነው።
፨ በመጨረሻ፣ ‹‹መሐመድ ማስተማር በጀመረ በ፲፰(18) ዘመኑ ሞተ። በሞተ በ፳፫(23) ዘመኑ የሕግ መጽሐፋቸው መጽሐፈ ቁራናቸው ተጻፈ።[...] ከርሱ በኋላ የመሐመድ ሃይማኖት በዓለሙ ሁሉ ደርሶ አሁን መካ መዲና ተመለሰ።›› (118) ይላሉ። ‹‹ኢየሱስ ክርስቶስ እንደመሰከረለት እንዲህ ሲል ከኔ በኋላ መንፈሴን ጵራቅሊጦስን እልክላችኋለሁ። እርሱም ሁሉን ያስተምራችኋል። ያለው ቃል እርሱን መስሎት ነበረ።›› በማለት ታሪካዊ ስህተት ፈጽመዋል። ነብዩ ሙሐመድ ማንበብም ኾነ መጻፍ አይችሉም፣ ስለዚህ ይህን የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅስ አላነበቡትም። ሰው አነበበላቸው ቢባል እንኳ የብሉይ ኪዳን በአረብኛ ቋንቋ የተተረጎመው አርሳዲያስ በሚባል ግለሰብ እ.ኤ.አ በ900 ነው። እሳቸው ከሞቱ ከ300 ዓመታት በኋላ፤ ሐዲስ ኪዳን ደግሞ አርፔኒየስ በተባለ ግለሰብ እ.ኤ.አ በ1616 ነው። ስለዚህ መጽሐፉን አግኝተው የማንበብም ኾነ የመስማት እድል እንዳልነበራቸው ይህ ማሳያ ነው።
“በ18 ዓመታቸው ሞቱ” የሚለው ማስረጃም ከባድ ስህተታቸው ነው፤ ሁሉም ታሪክ ላይ የተዘገበው በ63 ዓመታቸው እንደሞቱ ነው። “በሞተ በ23 ዘመኑ ቁርዓን ተጻፈ።” የሚለውም ታሪኩን ሲሰሙ ወይ ሲያነቡ በሥርዓት አለመስማታቸውን የሚያረጋግጥ ነው። ቁርዓን በ23 ዓመት ከሰማይ ወርዶ አለቀ እንጂ በሞቱ በ23 ዓመቱ ተጻፈ የሚለው መሠረት የለሽ ነው። ከዚያም ወገናቸውን ክደው “በዓለም ደርሶ መካ መዲና ተመለሰ” ማለት፤ የሀገራቸውን ህዝብ ‘ወገኔ አይደለህም’ ማለት ነው።
፨ አርታዒውም ኾነ ጸሐፊው እንዲህ ዓይነት ወገንተኝነት ያረበበበት ጽሑፍ መጻፍና ማስተላለፋቸው ከባድ ስህተት ነው።

 

   በአንድ ሀገር ላይ የሚከሰት የገበያ አለመረጋጋት እና የዋጋ ንረት በዜጎች ላይ የኑሮ መወደድ እና የገበያ መናር በማስከተል የመሸመት አቅምን ይፈታተናል፡፡ እንደ ሀገር የተከሰተው የኑሮ ውድነትን አለማቀፋዊ የሆኑ መነሻ ጉዳዮችን ተንተርሶ በተፈጠረ የውጪ ምንዛሬ መጨመር በአንድ በኩል የአቅርቦትና ፍላጎት አለመጣጣም በሌላ መልኩ እየፈተነ ስለመሆኑ ይነገራል። በአሰራርና ቁጥጥር ሊመለሱ የሚገባቸው ተግባራት በአግባቡ ባለመሰራታቸው ምክንያት የኑሮ ውድነቱ የተፈጠረ ስለመሆኑም ይገለጻል፡፡
ይሄን ችግር ከመፍታት አኳያም በመንግስት በኩል ገበያ ማረጋጋት፣ ገቢ መሰብሰብ፣ ህገ-ወጥ ንግድ ቁጥጥር እና የኢትዮጵያ-አዲስ አበባ ታምርት ንቅናቄ በመፍጠር በከፍተኛ የከተማው አመራሮች በጥበብ እንዲመራ በማድረግ ዜጎች በከፍተኛ ሁኔታ ተጋላጭ እንዳይሆኑ ዘርፈ ብዙ ተግባራት ሲከናወኑ፤ የማሻሻያ እርምጃዎችም ሲወሰዱ ቆይተዋል፡፡ ለዚህም፣ በምርትና አገልግሎቶች ላይ የዋጋ ድጎማ የማድረግ፤ የቀረጥ ነጻ አገልግሎት መፍቀድ እና አቅርቦትን ማሳደግ የመሳሰሉ ርምጃዎች ተወስደዋል፡፡


ከተማችን አዲስ አበባ በሃገሪቱ የንግድ እንቅስቃሴ ከሚካሄድባቸው ከተሞች በዋነናነት የምትጠቀስ ስትሆን የምርት ዕጥረት በመፍጠርና ፣ ዋጋ በማናር ፣ ህብረተሰቡን ለምሬት የሚዳርግ ሁኔታ ይስተዋላል፡፡ በንግድ ስርዓቱ ውስጥ አርቴፊሻልና ሰው ሰራሽ የሆኑ ሆን ተብል ምርትን ያለአግባብ በማከማቸት ዕጥረት መፍጠር፤ ከደረሰኝ ውጭ ግብይት ማካሄድ፤ የድጎማ ምርቶችን ስኳር፣ ዘይት፣ ነዳጅ በህገወጥ መንገድ መሸጥ፤ በመኪና ሊይ ሽያጭ ማካሄድ በእህል ምርት፣ ሲሚንቶ ምርት፣ አትክሌትና ፍራፍሬ ምርት ወዘተ ያልተገባ የዋጋ ጭማሪ ማድረግ፤ የአስገዳጅ ጥራቱ የወጣላቸው ምርት ገበያ ዋጋ፤ የሚዛን ጉድለት በመኖሩ ታይቷል፡፡
ሌላው የመሰረታዊ ፍጆታ ምርቶችን አቅርቦት ከመጨመር አኳያ፣ የግብርናውን ምርትና ማርታማነት ማሳደግ የሚያስችሉ ተግባራት ተከናውነዋል፡፡ በዚህም የግብርና ምርቶችን በስፋት ማቅረብ እና ቢያንስ የምርት እጥረት እንዳይኖር ማድረግ ተችሏል፡፡
በጅምር ላይ ያለውን የዋጋ መረጋጋት ውጤት ማስቀጠል የሚያስችል ተጨማሪ አቅም ተደርጎ የሚወሰደው ደግሞ፣ የገበያ ሰንሰለትን መቀነስና የደላሎችን ጣልቃ ገብነት መግታት የሚያስችሉ ርምጃዎችም መወሰዳቸው ሌላው የችግሩ መቃለል ምክንያት ናቸው፡፡
በከተማችን አዲስ አበባ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየናረ የመጣውን የኑሮ ውድነት ለማረጋጋት የከተማው አስተዳደር የተለያዩ የኑሮ ውድነት ማቅለያ አማራጮች እየተጠቀመ ይገኛል፡፡ ከነዚህ አማራጮች መካከል አንዱ በህብረት ስራ ማህበራት በኩል የሚሰጠው አገልግሎት አንዱ ሲሆን ለከተማው ነዋሪ የፍጆታ ምርት አቅርቦት በሚፈለገው መጠን ማግኘት እንዲችልና በተሻለ ዋጋ እንዲሸምት እየተደረገ ይገኛል፡፡
እንደ ከተማ የአዲስ አበባ ገቢዎች ቢሮ የኑሮ ውድነትን ለማቅለልና ህገወጥ ንግድን ለመከላከል በ2017 በጀት ዓመት የተለያዩ ተግባራት እያከናወነ የሚገኝ ሲሆን በተለይም ከመስከረም 2017ዓ.ም ጀምሮ በከተማች ከደረሰኝ ግብይት ጋር በተያያዘ የሚስተዋሉ ችግሮችን ለመቅረፍ ሰፊ ዘመቻ በማካሄድ ላይ ይገኛል፡፡
በዚህም የዋጋ ማረጋጋትን የሚፈጥሩ 164 መሰረታዊ የሸማቾች ህብረት ስራ ማህበራት ዩኒዬን እንደ ከተማ፤ በ800 የመቸርቸሪያ ሱቆች የሸማቹን አቅም ባመጣጠነ ዋጋ የገበያ ማረጋጋት ስራዎችን በማከናወን ላይ የሚገኙ ሲሆን 19 ፋብሪካዎች ፣ 63 የክልል አርሶ አደሮች ፣ 282 ኢንተር ፕራይዞች እንዲሁም በ3 ግብርና ምርት ማዕከላት 195 ቸርቻሪና አከፋፋዮች የኑሮ ውድነትን በማቃለል ረገድ ከፍተኛ ሚና እየተጫወቱ ይገኛሉ፡፡
የምርት አቅርቦትን በማሳደግ የዋጋ ግሽበትና የኑሮ ውድነትን ለማቃለል በመንግስት በኩል ከተከናወኑ ተግባራት መካከል የሰብል ምርት በገበያ ማዕከላት 108,481ኩንታል፤ የአትክልትና ፍራፍሬ ምርት 486,765፤ በገበያ ማዕከላት የገበያ ትስስር መፍጠር የተቻለ ሲሆን በእንስሳት ግብይት ዘርፍ 120,879 የዳልጋ ከብት አቅርቦት ትስስር መፍጠር ተችሏል፡፡ 635,722 በግና ፍየሎችን በገበያ ማዕከላት ማቅረብም ተችሏል፡፡
ሌላው የነዋሪውን አቅም ባገናዘበ መልኩ መንግስት በተለያዩ ቦታዎች የእሁድ ገበያዎችን ተደራሽነትን በማስፋትና ጥራትን በማስጠበቅ የተከናወኑ ተግባራት የተከናወኑ ሲሆን የእሁድ ገበያ መዳረሻዎች ላይ 969 የሰንበትና የእሁድ ገበያዎችን ተደራሽ ማድረግ ተችሏል፡፡
በተጨማሪም 106,261 ኩንታ በእሁድ ገበያ የሰብል ምርት ትስስር የተፈጠረ ሲሆን በአትክልትና ፍራፍሬ ምርትም እንደዚሁ 488,255 ትስስር መፍጠር ተችሏል፡
መንግስት ለህረተሰቡ የኢንዱስትሪ ምርቶች ላይ ድጎማ በማድረግ የኑሮ ውድነቱን የማቃለል ተግባራትን በፍትሃዊነት እያከናወነ ይገኛል፡፡ በዚህም 90,663 ኩንታል ስኳር የምግብ ዘይት 1,009,404 በሌትር በድጎማ በትስስሩ መሰረት ማሰራጨት ተችሏል፡፡ ዝቅተኛ ገቢ ላላቸው የህብረተሰብ ክፍሎችም እንዲሁ በተለየ ሁኔታ 98,869,238 የሸገር ዳቦ ማሰራጨት የኑሮ ጫናን ማቃለል ተችሏል፡፡
ህጋዊ የንግድ ስርአት ተዘርግቶ በሚገኝባት ከተማችን ህገ-ወጥነትን ለመከላከል የከተማ አስተዳደሩ የተለያዩ አሰራሮችን በመዘርጋት 1200 የክትትልና ቁጥጥር ባለሞያዎችን በማሰማራት አመራሩን በመጨመር ህገ-ወጥ ንግድን የመከታተልና የመቆጣጠር ስራ እየተሰራ ይገኛል፡፡ በዚህም በ147‚334 የንግድ ድርጅቶች የበር ለበር ክትትልና ቁጥጥር በማድረግ የንግድ ህገ-ወጥነትን ለመከላከል ተችሏል፡
በተጨማሪም የከተማችን አስተዳደር ዜጎች የተሻለ ተጠቃሚ ይሆኑ ዘንድ በተለያዩ መድረኮች የግንዛቤ ማስጨበጥ ተግባራትን እያከናወነ ነው፡፡
የግንዛቤ ማስጨበጫ መድረኮቹም በተመለከተ በከተማው ሁሉም አከባቢዎች የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ሃላፊ አቶ ጃንጥራር አባይ እና ሌሎች የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የስራ ሃላፊዎች በከተማው የሚስተዋለውን የኑሮ ውድነት ከመከላከል እና አጠቃላይ የንግድ ህገ ስርአት ላይ ከነጋዴው ህብረተሰቡ ጋር ውይይት እየተደረገ ሲሆን የንግዱ ማህበረሰብ እና ያለ ህጋዊ ግብይት የሚገነባ ከተማም ሆነ ሃገር የሌለ በመሆኑ የነጋዴውን ህይወት ለማሻሻል እና የታክስ አሰባሰቡን ዘመናዊ እንዲሆን ሁሉም ወደ ህጋዊ መስመር እንዲገባ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን ገልፀዋል፡፡
በሌላ በኩል ነጋዴዎች የሚያነሳው ህጋዊ ጥያቄ መስማትና ማዳመጥ የከተማዋን እድገት ማፋጠን በመሆኑ መንግስት ጥያቄዎችን ለማዳመጥ ዝግጁ ሲሆን ፍትሃዊ የንግድ ስርአት ለመፍጠር እየተሰራ ነው ፡፡ ነጋዴዎችንም ወደ ህጋዊ መረቡ መግባት እንዳለባቸው ተግባብተን ወደ ተግባር ስንገባ ያልተገቡ ምልክቶች እየታዩ መሆናቸው ተገቢ እንዳልሆነም በውይይቶቹ የጋራ ተደርገዋል፡
የገቢ ዘርፍ ተቋማት ዘመኑን የሚመጥን የታክስ አሰባሰብና አስተዳደር ስርዓትን በመከተል የግብር ስወራና ማጭበርበርን የመግታት ኃላፊነት የሁሉም ዜጋ በመሆኑ የገቢ መጠንን ለማሳደግ ከተለምዷዊ አሰራር የተላቀቀና በቴክኖሎጂ የሚመራ ዘመኑን የሚመጥን የገቢ አሰባሰብ ስርአት መከተል አስፈላጊ ነው።
በመሆኑም መንግስት የገቢ አሰባሰብ ሰርአትን ለማዘመንና ተገቢውን የገቢ አሰባሰብ ስርአት ለማስጠበቅ የተለያዩ ተግባራትን በማከናወን ገቢ እያደገ መጥቷለ። የሚሰበሰበው ገቢ እያደገ ቢመጣም ከከተማችን የመልማት አቅም እና ከሀገራዊ ምርት አንጻር ያለው ድርሻ ሲታይ ውስን መሆኑ ታምኖበት በቴክኖሎጂ የታገዘ የታክስ አሰባሰብን በማጠናከርና የታክስ አስተዳደርን በማጠናከር እንዲሁም የታክስ መሰረትን የማብዛትና የማስፋት ስራ ተከናወኗል፡፡
ግብር በአግባቡ ካልተሰበሰበ በተገቢው መንገድ ለህብረተሰቡ የመልማት ጥያቄ ምላሽ መስጠት አይቻልም የታክስ አሰባሰብና አስተዳደር ስርዓትን በማዘመን ያሉትን ፀጋዎች በመለየት ገቢ የመሰብሰብ አቅምን ማሳደግ ይገባል፡፡
ግብር የሚሰበሰበው ከማሕበረሰቡ ስለሆነ የሻጭም ሆነ የሸማቹ ደረሰኝ የመስጠትና የመጠየቅ ባህሉ ደካማ መሆን እና ነጋዴው ደግሞ የራሱ ጥቅም ከማግኘት አኳያ ደረሰኝ የመስጠት ችግሮች የሚስተዋል ችግር ነው፡፡ ችግሮቹን በሁለት ከፍሎ ማየት ይቻላል፡፡ አንደኛው ደረሰኝ በትክክል ባልተቆረጠበት ቦታ ፍትሐዊ የግብር አከፋፈል አይኖርም፡፡ ፍትሐዊነት ግብር ከፋዩ መክፈል ያለበትን እንዲከፍል የሚያስችል ሲሆን ሁለተኛው ለመንግሥት መግባት ያለበትን ታክስና ግብር በአግባቡ ገቢ አለመደረጉ ፍትሐዊነትን ከሚያጎድል ጉዳይ መሆኑ ግልጽ ነው፡፡
ያለደረስኝ በሚደረግ ግብይት ከሸማቹ አንጻር ቢታይ የሚጠቀመው ነገር የለም፤ ሸማቹ በደረሰኝም ሆነ ያለደረሰኝ ቢገዛ መክፈል ያለበትን ሒሳብ ይከፍላል፡፡ ነጋዴው የሚቀበለው ቫትንም ጨምሮ ሲሆን በሀገር ልማት ላይ የሚፈጠረው ጫና ደግሞ ቀላል የሚባል አይደለም፡፡ በሌላ አነጋገር ደረሰኝ በመስጠትና በመቀበል መካከል የሚኖር ክፍተት ሻጭም ገዢም ሊጠቀሙባቸው የሚገባቸውን የመሰረተ ልማት ጥያቄዎች በፍጥነት ለመመለስ እንዳይቻል አዳጋች ይሆናል፡፡ ስለዚህ የማሕበረሰቡ ንቃተ ህሊና እየጨመረና ግንዛቤ እያደገ ሲሄድ ደረሰኝ የመስጠትና የመጠየቅ ባህል እያደገ ይሄዳል፡፡ የሚሰበሰበውም ግብር ከፍ እንደሚል አጠያያቂ አይደለም፡፡
በተጨማሪም የከተማ አስተዳደሩ ገቢዎች ቢሮ በከተማችን ዘመናዊ፣ ፍትሃዊና ተደራሽ የገቢ አሰባሰብ ስርዓት በመዘርጋትና ከተማዋ የምታመነጨውን ገቢ በላቀ ደረጃ በማሰባሰብ የከተማዋን የወጪ ፍላጎት ለማሟላት በደረሰኝ ግብይትና በብልሹ አሰራሮችና በሌብነት ድርጊቶች ላይ የተጀመሩ ተግባራት እንዲሳኩና የህብረተቡ ተጠቃሚነት እንዲረጋገጥ ጥረት እያደረገ ነው፡፡
በአጠቃላይ የከተማ አስተዳደሩ በቀጣይ የነዋሪውን ሸክም የሚያቃልሉና ጫና የሚቀንሱ ተግባራትን አጠናክሮ የሚያስቀጥል ሲሆን ምርት ደብቀው የምርት እጥረት እንዲፈጠር የሚያደርጉ የገበያ ተዋናዮችም እድል እንዳያገኙ እና ተፅእኖ እንዳይፈጥሩ ለማድረግ ከፍተኛ ጥረት ያደርጋል፡፡ ህብረተሰቡም ከመንግስት ጎን በመሆን ህገ-ወጦችን በማጋለጥ በመሰረታዊ የድጎማ ምርቶች ላይ የሚፈጠሩ አሻጥሮችን በመከታተልና በማጋለጥ ያለ አግባብ እያሻቀበ የመጣውን የዋጋ ንረት ለማረጋጋት የከተማ አስተዳደሩ፣ ነጋዴው፣ አቅራቢውና ነዋሪው በጋራ ተቀራርበው ሊሰሩ ይገባል፡፡

የ“ENJOY AI” አገር አቀፍ የመጨረሻ ውድድር አሸናፊዎች ተሸለሙ

• አሸናፊዎቹ በቻይና በሚደረግ ውድድር ኢትዮጵያን ወክለው ይሳተፋሉ


ቦሌ መድሃኒያለም ወረድ ብሎ በሚገኘው ቤስት ዌስተርን ፐርል አዲስ ሆቴል፣ 11ኛ ፎቅ ላይ በተሰደረው አዳራሽ፣ ከወትሮው ለየት ያሉ እንግዶች ታድመዋል፡፡ አህጉራዊ ጉባኤ ላይ ለመካፈል የመጡ እንግዶች አይደሉም፡፡ ኢትዮ ሮቦቲክስ ባዘጋጀው የ2024 “ENJOY AI” አገር አቀፍ የመጨረሻ ውድድር ላይ ለመሳተፍ የተገኙ ታዳጊዎች ናቸው - የዲጂታል ኢትዮጵያ ተስፋዎች የሚለው ይገልጻቸዋል፡፡

የሮቦ ሮቦቲክስ መሥራችና ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ሰናይ መኮንን ለአዲስ አድማስ እንደገለጹት፤ታዳጊዎቹ በዛሬው ዕለት ከሰዓት በኋላ በኮዲንግ ስኪልስ ቻሌንጅ ነው የተወዳደሩት፤ በውድድሩ አሸናፊ የሚሆኑት በቅርቡ በቻይና በሚደረገው ዓለማቀፍ ውድድር ኢትዮጵያን ወክለው ይሳተፋሉ ብለዋል፡፡

በውድድሩ ላይ ከተሳተፉት የታዳጊ ቡድኖች መካከል ቲም ናይል፣ ቲም አልፋ፣ ቲም ዊነርስ፣ ቲም ላየንስ፣ ቲም ኤግል፣ ቲም አቢሲኒያና ሌሎችም ይገኙባቸዋል፡፡

የውድድሩን አሸናፊዎች ለመለየት በታዳጊ ቡድኖቹ መካከል እልህ አስጨራሽ ፍልሚያና ፉክክር መደረጉን በአካል ተገኝተን ታዝበናል፡፡ ታዳጊዎቹ ስፔስ ትራቭሊንግ፣ ጋላክቲክ ዲፌንስ ባትል እና ክሎዚንግ ሰረሞኒ ኦቭ ስፖርትስ በተሰኙ ውድድሮች ለሦስት ዙር ተወዳድረዋል፡፡

በመጨረሻም፣ ከየዘርፉ ከ1ኛ እስከ 3ኛ የወጡ አሸናፊዎች የወርቅ፣ የብር፣ የነሓስ ሜዳልያና የተሳትፎ ምስክር ወረቀት ተሸልመዋል፡፡ የወርቅ ተሸላሚዎቹ ሦስት ቡድኖች ከዚህ በታች ቀርበዋል፡-

• ቲም ኤግል -በ120 ነጥብ በክሎዚንግ ሰረሞኒ ኦቭ ስፖርትስ

• ቲም ስፓርታ - በ630 ነጥብ በስፔስ ትራቭሊንግ ዘርፍ

• ቲም ናይል - በ100 ነጥብ በጋላክቲክ ዲፌንስ ዘርፍ

ለአሸናፊዎቹ የወርቅ ሜዳልያ የሸለሙት የቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን ሚኒስትሩ ተወካይ አቶ ሰላምይሁን አደፍርስ ባደረጉት ንግግር፤ ኢትዮ ሮቦቲክስ ከወትሮው ውድድር በተለየ የኤአይ እና ዲጂታል ስኪል አቀላቅሎ መምጣቱን ጠቅሰው፤የድርጅቱ መሥራች አቶ ሰናይ ላደረገው ወደር የለሽ ጥረትና ትጋት አመስግነዋል፡፡

አክለውም፤ ውድድሩ ሰፋ ብሎ እንዲካሄድና ተደራሽ እንዲሆን ለኢትዮ ሮቦቲክስ እገዛችንን አጠናክረን እንቀጥላለን ብለዋል፡፡

 

 

አንድ ንጉሥ ከሦስት ልጆቻቸው ለአንደኛው መንግሥታቸውን ለማውረስ አስበዋል፡፡
ልጆቹ ግን “እኔ ልውረስ፣ እኔ ልውረስ” እያሉ አስቸገሯቸው፡፡ ስለዚህ አውጥተው አውርደው ካጠኑ በኋላ ልጆቻቸውን ጠርተው፤
“ከሦስታችሁ ማንኛችሁ በትረ ሥጣኔን ይውሰድ?” ሲሉ ጠየቁ፡፡ በመጀመሪያም በትምህርቱ፣ በዕድሜው ትልቅ የሆነው የበኩር ልጃቸው እንዲመልስ ዕድል ሰጡ፡፡
የመጀመሪያ ልጅም፣
“ለእኔ ይገባኛል”አለ፡፡
“ለምን?”
“እኔ የበኩር ልጅ ስለሆንኩና፤
በመጀመሪያ ት/ቤት እንዲከፈት አድርጌአለሁ፡፡ አገሬን ጠቅሜአለሁ” አለ፡፡ ቀጥለው ሁለተኛውን ልጅ ጠየቁት፤ እሱም፤
“ለእኔ ይገባኛል፡፡ ምክንያቱም ባለፈው ጠላት አገራችንን ሲወር ሰበብ ፈልጎ በብዙ መንገድ ሲተነኩስ ዝም ማለት ነው፤ ብዬ ምክር ለግሼዎ፤ ለማሸነፍ ችለናል፡፡ አገራችንን ያዳንኩ እኔ ነኝ” አለ፡፡
ሦስተኛው ልጅ እድል ተሰጠው፡፡ እሱም፤
“ባለፈው ጊዜ መንግሥታችን በዕዳ ተይዞ ሳለ የሀገራችንን ወርቅና የከበረ-ደንጊያ ሁሉ ልሸጠው ነው ሲሉ፣ እኔ ግዴለም የዘንድሮን አዝመራ በትዕግሥት እንጠብቀው” ብዬ፤ አዝመራችን ተሸጦ ዕዳችንን ከፈልን፡፡ ሀገሬን ያዳንኩ እኔ ነኝ” አለ፡፡
ንጉሡ የሦስቱንም በጥሞና ካዳመጡ በኋላ፤
“ልጆቼ ጥንት ልዑል ሳለሁ አንድ መምህር ነበሩኝ፡፡ የበሰሉ፣ አዋቂ የተባሉ ናቸው፡፡ አንድ ቀን ‹መምህር ሆይ፤ ዕድሜዬ እየጨመረ አባቴም እየደከሙ ናቸውና፣ ንጉስ ለመሆን የሚያስፈልጉኝን ሦስት ነገሮች ይንገሩኝ› ስል ጠየቅኋቸው”
መምህሩም ጥቂት ካሰላሰሉ በኋላ፤
“ልዑል ሆይ ከሁሉ አስቀድሞ፤ ሌላው የማይቀማዎን ንብረት ይስጥዎ” አሉኝ፡፡
እኔም፤ “ሌላው የማይነጥቀኝ ንብረት ምንድን ነው?” ስል ጠየቅኋቸው፡፡
መምህሩም፤ “ዕውቀት ነው” ሲሉ መለሱልኝ፡፡ ቀጠሉናም
“ሁለተኛው ደግሞ፤ ሁሉን የሚፈታ ኃይል ይስጥዎ” አሉኝ፡፡
“ሁሉን የሚፈታ ኃይልስ ምንድነው?” አልኳቸው፡፡
“ብልሃት፣ ዘዴ” አሉና መለሱ፡፡
“እሺ ሦስተኛው ምን እንደሆነ ይንገሩኝ?” አልኳቸው፡፡
መምህሩም፤ “አገሩን በሙሉ ለመግዛት የሚበቃ የማያጠራጥር አቅም ይስጥዎ፡፡”
እኔም፤ “ይህ የማያጠራጥር አቅም ምን ሊሆን ይችላል? ይግለጡልኝ?” አልኳቸው፡፡
መምህሩም፤ “ትዕግሥት፤ ትዕግሥት ነዋ!” አሉኝ፡፡
ይህን የመምህሩን ታሪክ ከተናገሩ በኋላ ንጉሡ ወደ ልጆቻቸው ዞረው፤
“አያችሁ ልጆቼ አገር ለማስተዳደር ዕውቀት፣ ብልሃትና ትዕግሥት ያስፈልጋል፡፡ እናንተ ደግሞ አንዳችሁ የዕውቀት፣ አንዳችሁ የብልሃት፣ አንዳችሁ የትዕግሥት፣ ባለቤት ናችሁ፡፡ ችሎታችሁን ካላስተባበራችሁ ሀገር አታስተዳድሩምና፣ አስቡበት” ብለው ሸኟቸው፡፡
***
ሀገራችን አዋቂ፣ ብልህና ታጋሽ መሪ ትፈልጋለች፡፡ ሁሉም ተሰጥዖዎች በአንድ መሪ ውስጥ ተሟልተው የማይገኙ ሊሆኑ ይችላሉና አቅምን አስተባብሮና አዋዶ መጓዝ ግዴታ ይሆናል፡፡ ህብረ-ኃይል መፍጠር ያስፈልጋል፡፡ ህብረ-ቀለም ቀለም መፍጠር ያስፈልጋል፡፡ ያለ ዕውቀት ከዓለም ጋር መጓዝ አይቻልምና አዋቂዎችን ማሰባሰብ የግድ ነው፡፡ ያለ ብልሃት እንኳን ማህበረሰብን ቡድንን መምራት አይቻልምና፤ የቅርብ የቅርብ ችግርን መፍቻና የሩቅ ኢላማን መምቻ ብልሃት ማዘጋጀት የዕለት-ሰርክ ተግባሬ ብሎ መያዝ ያሻል፡፡ ማናቸውንም ተግባር ዐይኑ ሊበራ ቃል- እንደተገባለት ሰው “ዛሬን እንዴት አድሬ” በሚል ለመከወን ማሰብ “ሩቅ አሳቢ ቅርብ አዳሪ” ያደርጋል፡፡ ከሚኬድበት መንገድ ሁሉ መድረሻ ላይ ሀገርና ህዝብ መኖሩን አለመርሳት፤ በሁሉም ወገን ልብ ላይ መታተም አለበት፡፡ “ከዚህ ሁሉ ትግልና ፍትጊያ በኋላ በሚዶው መጀመሪያ የሚያበጥርበት ማነው?” ተብለው እንደተጠየቁት መላጦች ላለመሆን፤ ዓላማንም ሆነ ዒላማን ልብ-ማለት መቼም ቢሆን ወሳኝ ነው፡፡
ወደ ሰላም የሚወስዱንን መንገዶች ሁሉ ከአውራ- ጎዳና እግር- መንገድ ድረስ እሾ ካማም ሆኑ ሣር-ሜዳ፤ በራስ ድርድርም ይለቁ በዓለም ሽማግሌ፤ በጥንቃቄና በብሩህ መነጽር ማየት በጣም አስፈላጊ ነው፡፡ በትዕግሥትም እስከ ኬላው ድረስ ለመጓዝ መቁረጥ መልካም ነገር ነው፡፡ ዲሞክራሲያዊ መንግስት ሲታሰብ፤ እንኳ እንደኛ በዳዴ ላይ ላሉ አገሮች፣ ብዙ በተለማመዱትም ዘንድ ከቀድሞው አስተሳሰብ መላቀቅና የቀድሞውን ጥቅም አጣለሁ የማለት ራስ-ወዳድነት፤ ያለ የነበረ ነገር ነው፡፡ ጉዞውን ረዥም የሚያደርገውም የአዲሱ አለመለመድና ከአሮጌው ለመላቀቅ ያለመቻል አባዜዎች ናቸው፡፡ ከዚህ አልፎ ተርፎ ለየፖለቲካ ተግባሩ የሚለጠፍ ቅጽል ስም ነገሮች ከማወሳሰብና ከማክረር ያለፈ ጠቀሜታ አይኖረውም፡፡ ይህን ስላልክ ወይም ስላደረግህ የዚህ ወይም የዚያ የፖለቲካ ፓርቲ ወይም አመለካከት ደጋፊ ነህ የሚል አስተሳሰብ ጎጂነቱ አያጠያይቅም፡፡ የቅርብ ጊዜ ትዝታችን ነው፡፡ ነገሮች እልባት ባላገኙ ቁጥር አገር፤ እንደ ጃርቷ “ የጃርት- እናት፤ ልጆችሽን እንዴት አድርገሽ ትልሻቸዋለሽ?” ስትባል፤” እንደየዕድሜያቸው” ከማለት ያለፈ መልስ የላትም፡፡ ሀገርን ለማገዝ አሁንም ዕውቀት፣ አሁንም ብልሃት፣ አሁንም ትዕግሥት ያስፈልጋል፡፡

የኢትዮጵያ አገራዊ ምክክር ኮሚሽን በሚቀጥሉት ሦስት ሳምንታት በኦሮሚያ የሚያከናውነውን ሥራ እንደሚያጠናቅቅ አስታውቋል። ኮሚሽኑ የቀረው የሥራ ዘመን ሦስት ወር ቢሆንም የተቋሙ የቆይታ ጊዜ እንዲራዘም መጠየቅ እንደማይፈልጉ ኮሚሽነሩ ተናግረዋል፡፡
የአገራዊ ምክክር ኮሚሽን ኮሚሽነር ፕሮፌሰር መስፍን አርአያ ባለፈው ማክሰኞ ሕዳር 10 ቀን 2017 ዓ.ም. ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ባቀረቡት የስራ አፈጻጸም ሪፖርት፤ በአገሪቱ ካሉ 1 ሺህ 400 ወረዳዎች ውስጥ በ615 ወረዳዎች ሙሉ በሙሉ የአጀንዳ ማሰባሰብ ሥራ መጠናቀቁን ገልጸዋል፡፡ ነገር ግን በኦሮሚያ ወደ 360 ገደማ ወረዳዎች፣ በአማራ ወደ 264 ወረዳዎች፣ እንዲሁም በትግራይ ሙሉ በሙሉ ሥራው በቀጣይ የሚከናወን መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
በኦሮሚያ የአጀንዳ ማሰባሰብ ሥራው በሦስት ሳምንት ውስጥ ይጠናቀቃል ብለው እንደሚጠብቁ የገለጹት ኮሚሽነሩ፤ በአማራ ክልል አስቻይ ሁኔታ እስከተፈጠረ ድረስ ሥራው ይቀጥላል ብለዋል፡፡ በክልሉ ግጭት ከመነሳቱ በፊት በርካታ መሰረታዊ ሥራዎች ተሰርተው እንደነበር በማውሳት፣ ከግጭቱ መቀስቀስ በኋላም ሥራዎችን ለመስራት ኮሚሽኑ እንዳልከበደው አስረድተዋል።
በተመሳሳይ መልኩ፣ የፌደራል ተቋማት በተለይም የመንግሥት ሕግ አውጪ፣ አስፈጻሚ፣ ተርጓሚ፣ እንዲሁም በፌደራል ደረጃ ያሉ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ የሃይማኖት ተቋማትና የዳያስፖራ አባላትን አጀንዳ የማሰባሰብ ሥራ በአጭር ጊዜ ውስጥ እንደሚቀጥል ተናግረዋል፡፡
አጀንዳው ተሰብስቦ እንደተጠናቀቀ በሚከናወነው የአገራዊ ምክክር ጉባዔ የሚሳተፉ 4 ሺህ ተወካዮች እንደሚኖሩ ዋና ኮሚሽነሩ ገልጸዋል፡፡
ኮሚሽኑ ወደ መቐለ ተጉዞ ከጊዜያዊ አስተዳደሩ ፕሬዚዳንት አቶ ጌታቸው ረዳ ጋር መወያየቱን ያነሱት ፕሮፌሰር መስፍን፤ ፕሬዚዳንቱ የኮሚሽኑን አጠቃላይ እንቅስቃሴ በመርህ ደረጃ እንደሚቀበሉ መናገራቸውን አብራርተዋል። ነገር ግን ኮሚሽነሩ ለመግለጽ ባልፈለጓቸው ምክንያቶች የተነሳ ኮሚሽኑ ሙሉ በሙሉ ወደ ትግራይ ገብቶ ሥራውን እስካሁን አልጀመረም።
እስካሁን በተከናወነው የአጀንዳ ማሰብሰብ ስራ በርካታ አጀንዳዎች እየመጡላቸው መሆኑን የገለጹት ዋና ኮሚሽነሩ፤ ባለፉት ሁለት ዓመታት ሥራውን እያከናወነ ያለው ከ100 ባልበለጡ የተቋሙ ሰራተኞች መሆኑን አመልክተዋል፡፡ መንግሥት ከመደበው በጀት በተጨማሪ ከውጭ ድጋፍ አድራጊዎች 13 ነጥብ 5 ሚሊዮን ዶላር መገኘቱንም ተናግረዋል፡፡
የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) ተወካይ ዶ/ር አበባው ደሳለው፤ “ኮሚሽኑ የታጠቁ ሃይሎችን እንዴት ለማሳተፍ አቅዷል? በሰላማዊ መንገድ ተሳትፎ እያደረጉ ያሉ ፓርቲዎች አመራሮቻቸውና አባሎቻቸው በመንግስት እየታሰሩ የምክክር ሒደቱ እንዴት ውጤታማ ይሆናል?›› ሲሉ ጠይቀዋል፡፡
በተጨማሪም በርካታ የምክር ቤቱ አባላት፤ በአማራ፣ በኦሮሚያና በትግራይ ክልሎች ያሉ ሥራዎች ባልተጠናቀቁበት ሁኔታ የምክክሩ ውጤታማነት ምን ሊመስል ይችላል? ሲሉ ጥያቄ አቅርበዋል፡፡
የኮሚሽኑን ገለልተኝነት በተመለከተ ከፖለቲካ ፓርቲዎችና ከታዋቂ ሰዎች፣ እንዲሁም ከሌሎች አካላት ጥያቄ የሚነሳ መሆኑን በመጥቀስ፣ የፓርላማ አባላት ኮሚሽኑን ማብራሪያ ጠይቀዋል፡፡
ፕሮፌሰር መስፍን በበኩላቸው፤ “የውክልና ጉዳይን በሕዝብ ቁጥር ‘እናምጣ’ ካልን፣ አሁንም እንደሚነሳው የአንድ አካል የበላይነት እንዲኖር ሊያደርግ የሚችል በመሆኑ፣ ይህ የምክክር ሂደት በእጅ ማውጣት የሚሰራ ሳይሆን የተመረጡ ሰዎች የሕዝቡን ጥያቄ አምጥተው በአጀንዳ መልክ የሚያቀርቡበት ሂደት ነው›› ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡
ዋና ኮሚሽነሩ ፕሮፌሰር መስፍን አርዓያ፤ ኮሚሽኑ የቀረው የሥራ ዘመን ሦስት ወር ቢኾንም የቆይታ ጊዜው እንዲራዘም መጠየቅ እንደማይፈልጉ አስታውቀዋል፡፡ ከታጠቁ ሃይሎች ጋር የሚደረግ ምክክር መኖሩን በተመለከተ ለተነሳው ጥያቄ ወደ ኮሚሽኑ ለውይይት የመጣ የታጠቀ ሃይል አለመኖሩን ያመለከቱ ሲሆን፤ ከኮሚሽኑ ጋር አብሮ ለመስራት በተፈራረሙ ማግስት አባሎቻቸው የሚታሰሩባቸው ፓርቲዎች አቤቱታ እንደሚያቀርቡ ገልጸዋል።

ኢትዮጵያ የአፍሪካ ነጻ ንግድ ቀጣና ስምምነትን ለመተግበር ዝግጅቷን አጠናክራ ካልቀጠለች፣ ተጎጂ ከሚሆኑ አገራት አንዷ ልትሆን ትችላለች ተብሏል። የፓን አፍሪካ ንግድ ምክር ቤት ዋና ዳይሬክተር አቶ ክቡር ገና፤ አገሪቱ ለአፍሪካ ነጻ ንግድ ቀጣና ራሷን ዝግጁ ካላደረገች፣ አነስተኛ ኢንዱስትሪዎች የመጥፋት አደጋ ሊጋረጥባቸው እንደሚችል ስጋታቸውን ገልጸዋል።


ኢትዮጵያ የውጭ አገር የንግድ ማሕበረሰብን የሚስብ የሕዝብ ብዛት ቢኖራትም፣ የአፍሪካ ነጻ ንግድ ቀጣናን ተግባራዊ ለማድረግ የሚስተዋሉ ችግሮች እንዳሉ አቶ ክቡር ገና ተናግረዋል፡፡ “አንድን ምርት ከአንድ የአፍሪካ አገር ወደ ሌላኛው ከማጓጓዝ ይልቅ ወደ ቻይና መላክ ቀላል የሆነበት ሁኔታ ተፈጥሯል” የሚሉት ዳይሬክተሩ፤ የፖለቲካ፣ የመሰረተ ልማት፣ የቢሮክራሲና የፋይናንስ ችግሮች ለንግድ የማይመቹ ስለሆኑ መስተካከል እንዳለባቸው ጠቁመዋል።


ኢትዮጵያ የነጻ ንግድ ቀጣናውን ለመተግበር ዝግጅት እያደረገች አለመሆኗን የሚገልጹት አቶ ክቡር፤ “ከሌሎች የአፍሪካ አገራት ጋር እስከዛሬ ድረስ ንግድ እካሂደናል ለማለት አይቻልም” ብለዋል። ከኢትዮጵያ ወደ ሌሎች የአፍሪካ አገራት የሚላኩ ምርቶች ቢኖሩም፣ በመጠን ግን በጣም አነስተኛ መሆናቸውን አቶ ክቡር አልሸሸጉም።
“አምራች ድርጅቶች የምርት መጠናቸውን እንዲያሳድጉ የሚያግዝ አቅም ሊኖር ይገባል” ያሉት ዳይሬክተሩ፤ ኢትዮጵያ ለነጻ ንግድ ቀጣናው ስምምነት ዝግጅቷን አጠናክራ ካልቀጠለች፣ ተጎጂ ከሚሆኑ አገራት አንዷ ልትሆን እንደምትችል ስጋታቸውን ገልጸዋል፡፡ በዚሁ ስምምነት ሳቢያ አነስተኛ ኢንዱስትሪዎች የመጥፋት አደጋ ሊጋረጥባቸው እንደሚችልም ጠቁመዋል፡፡


“የንግዱ ማሕበረሰብ እንደዚህ ዓይነት -- የነጻ ንግድ ቀጣና ስምምነት -- አጋጣሚ ሲፈጠር ‘እንዴት ነው የምጠቀምበት?’ ብሎ ራሱን መጠየቅ ይኖርበታል። ራሱን ማዘጋጀትም አለበት። ለመንግስት የሚያቀርባቸው ጥያቄዎችም ካሉ፣ እንዲፈጸሙለት መጠየቅ ይኖርበታል” ብለዋል። ይሁንና ጥያቄ ከማቅረብ አንጻር ከንግዱ ማሕበረሰብ ብዙም እንቅስቃሴ እንደማይታይ አመልክተዋል።
መንግሥት ተግባራዊ እያደረገ በሚገኘው አጠቃላይ የኢኮኖሚ ሪፎርም መሰረት፣ “የኤክስፖርት ንግድን ማሳደግ ይገባል” ተብሎ በተደጋጋሚ እንደሚገለጽ እና የአፍሪካ አህጉር ደግሞ ለኤክስፖርት ንግድ እጅግ አመቺ መሆኑን የገለጹት አቶ ክቡር፤ በአንጻራዊነት ከሌሎች የአፍሪካ አገራት ጋር ስንመዘን፣ ተመሳሳይ አቅም ላይ በመሆናችን፣ ያንን አጋጣሚ በመጠቀም ኤክስፖርትን ማሳደግ ይገባል ብለዋል።