Administrator

Administrator

ህንዳዊው ዝዮና ቻና ከ39 ሚስቶች 94 ልጆችን አፍርቷል፡፡ ከ100 በላይ የልጅ ልጆችም አይቷል፡፡
ከሁሉም በላይ የሚገርመው ደግሞ ሁሉም እ.ኤ.አ በ2021 ዓ.ም በሞት እስኪለይ ድረስ ከ100 በላይ ክፍሎች ባሉት የተንጣለለ መኖሪያ ቤት ውስጥ በአንድ ላይ ነበር የሚኖሩት፡፡
ዘይገርም ነው!!
የቴሌግራም ቻናልችንን በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…
May be an image of one or more people and text that says 'had FB: MR AR SCIENTIFIC A man in India named Ziona Ziona Chana 39 wives, 94 children, and over 100 grandchildren, all living together in in a 100-room mansion until his death in 2021.'
 
 
 
 
የፊታችን ሰኞ ነሐሴ 5 ቀን 2017 ዓ.ም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ከአፍሪካ የልማት ባንክ ግሩፕ ፕሬዚዳንት አኪንዉሚ አዴሲና ጋር ለኢትዮጵያ አየር መንገድ አዲስ የአውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ ፕሮጀክት የሚውል 7.8 ቢሊዮን ዶላር ፋይናንስ ለማፈላለግ የፊርማ ሥነሥርዓት እንደሚያከናውኑ ይጠበቃል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ በቢሾፍቱ ለሚያስገነባው በአፍሪካ ትልቁ የአውሮፕላን ማረፊያ 10 ቢሊዮን ዶላር የሚያስፈልገው ሲሆን፤ ከዚህ ውስጥ 7.8 ቢሊዮን ዶላር ፋይናንስ የማፈላለግ ሃላፊነቱን የአፍሪካ ልማት ባንክ ወስዷል። ቀሪው 20 በመቶ የግንባታ ወጪ በኢትዮጵያ አየር መንገድ በኩል የሚሸፈን እንደሚሆን ኦልአፍሪካ ዘግቧል፡፡
የአውሮፕላን ማረፊው ግንባታ በመጪው ህዳር ወር ገደማ የሚጀመር ሲሆን፤ በአራት ዓመት ውስጥ ግንባታው ሙሉ ለሙሉ ይጠናቀቃል ተብሎ ይጠበቃል።
ግንባታው ሲጠናቀቅም በዓመት በትንሹ 100 ሚሊዮን መንገደኞችን የማጓጓዝ አቅም ይኖረዋል ተብሏል፡፡
የቴሌግራም ቻናልችንን በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…
ከወርቅ ማዕድን አውጪዎች 7 ቢ. ብር ገቢ ቢጠበቅም
የተገኘው 24 ሚ. ብር ብቻ ነው
የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዝዳንት ጀኔራል ታደሠ ወረደ፣ የውጭ አካላት የትግራይን ማዕድናት እየበዘበዙ ይገኛሉ በማለት ዛሬ መቀሌ ውስጥ በዘርፉ ዙሪያ በተካሄደ መድረክ ላይ መናገራቸውን የክልሉ የዜና ምንጮች ጠቅሳ ዋዜማ ዘግባለች፡፡
ጀኔራል ታደሠ፤ "የውጭ አካላት" ያሏቸውን ማዕድን መዝባሪዎች ማንነት ለይተው እንዳልጠቀሱ ግን ተነግሯል።
ጊዜያዊ አስተዳደሩ የማዕድናት ምዝበራን ለመከላከል ያቋቋመው ግብረ ኃይል፣ ከሰሜን ምዕራብ ዞን ብቻ 440 የወርቅ ማውጫ ማሽኖችን ከሕገወጥ የማዕድን ቦታዎች መያዙን በመድረኩ ላይ ባቀረበው ሪፖርት መናገሩን ዘገባዎቹ ጠቅሰዋል።
ትግራይ በተያዘው ዓመት ከወርቅ ማዕድን አውጪዎች 7 ቢሊዮን ብር ገቢ ትጠብቅ እንደነበር የጠቀሰው ግብረ ሃይሉ፣ በዓመቱ የተገኘው ግን 24 ሚሊዮን ብር ብቻ እንደሆነ መገለጹን ዘገባው ያመለክታል፡፡
የቴሌግራም ቻናልችንን በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…
 
 
 
 
 
 
 
 
የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከአስርተ አመታት በላይ ሲጠቀምበት የኖረውን የንግድ ምልክት (Logo) በአዲስ የንግድ ምልክት ለመቀየር 600 ሚሊዮን ብር በጀት መድቦ ሲሰራ ነበር:: በዚህም መሰረት ባንኩ አዲሱን የንግድ ምልክት ይፋ የማድረጊያ ሰዓት ላይ ዕቅዱን ሰርዟል::
ምክንያቱ ደግሞ ጠቅላይ ሚንስትሩ አዲሱ ሎጎ የፈጠራ እና የኢትዮጵያዊነት ገጽታ ጎድሎታል በሚል ባቀረቡት ትችት እንደሆነ ዛሬ ሪፖርተርስ ዘግቧል:: ከዚህ ጋር ተያይዞ ለፕሮጀክቱ የተመደበው በጀት ብዙዎችን ሲያነጋግር ውሏል:: እኔ ግን እንደ ማርኬቲንግ እና ብራንዲንግ ባለሙያ ከገንዘቡ መነጋገሪያነት ባሻገር በሚከተሉት ጉዳዮች ላይ የግሌን ምልከታ እና ጥያቄ ማስፈር ፈለግኩ::
በመጀመርያ ደረጃ የንግድ ምልክት (Logo) ምንድነው? ሎጎ ማለት የድርጅትን ብራንድ ማንነት (Brand Identity) ፣ እሴት (Values) እና ራዕይ (Vision) በአንድ ምስል ወይም ምልክት የሚያጠቃልል የምስል መታወቂያ (Visual Identity) ነው። በቀላል አገላለጽ ሎጎ የአንድ ድርጅት ምርት ወይም አገልግሎት መለያ የሆነ ምልክት ነው። እንደ ሰው ስም ሎጎም አንድ ድርጅቱ በሌሎች ድርጅቶች ወይም ምርቶች መካከል በቀላሉ እንዲታወቅ ያደርገዋል።
ከዚህም ባሻገር ሎጎ የአንድ ድርጅት እና ደንበኛን ስነ-ልቦና የሚያስተሳስር፣ በማስተሳሰር በደንበኞች አዕምሮ ውስጥ የሚገነባ ስሜት ነው:: ይሄም በጊዜ ሂደት በደንበኞች ዘንድ እምነት እና ታማኝነት (Trust and Loyalty) ይገነባል። ደንበኞች አንድ ሎጎን ሲያዩ ከምስሉ ባለፈ የተለያዩ ስሜቶችን ፣ ትውስታዎችን እና ልምዶችን ያስታውሳሉ::
ለምሳሌ “Just Do It” የሚል ቃልን ድንገት ብንመለከት ወደ አዕምሯችን ጓዳ በፍጥነት ብቅ የሚለው Nike ጫማ ነው:: እንዲሁ ደግሞ የተጎመጠ የአፕል ፍሬ ምስል ብናይ ወደ አዕምሯችን በፍጥንት ብቅ ሊል የሚችለውን ብራንድ እና ምርትም ግልፅ ነው::
በዚህም መሠረት የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ (CBE) ለረዥም ጊዜ ሲጠቀምበት የኖረው ሎጎ ከህዝቡ ጋር ጥልቅ የስነ-ልቦና ትስስር የፈጠረ የብራንድ ካፒታል (Brand Equity) መገንባቱ የማይካድ ሃቅ ነው። ይህ ሎጎ ባንኩን ለሚያውቁት ሁሉ የረጅም ጊዜ ግንኙነት ምልክት ሆኖ አገልግሏል። እንደየደንበኛው ማንነት ሁሉም የራሱ የሆነ የስነ-ልቦና ትስስር ይኖረዋል:: (ቁጠባ ፣ የሲስተም ችግር ፣ መጉላላት ፣ የደህንነት ስሜት ፣ ሽልማት ፣ ወለድ ፣ ዕዳ ፣ ቦታ ጠቋሚነት ወዘተ) እነዚህ በሙሉ ባንኩ ከደንበኞቹ ጋር በሎጎው የሚፈጥረው ስነ-ልቦና ትስስር ናቸው:: ታዲያ ንግድ ባንክ አሁን ይሄን ሎጎ ለምን ሊቀይረው ፈለገ?
የዘርፉ ባለሙያዎች እንደሚሉት አንድ ድርጅት ሎጎውን ለመቀየር ወይም Rebrand ለማድረግ እጅግ አሳማኝ ምክንያት ሊኖረው ይገባል ብለው ይስማማሉ:: ለምሳሌ ወደ አዲስ የገበያ ዘርፍ የሚገባ ከሆነ:: የንግድ አቅጣጫ የሚቀይር ከሆነ:: ያለበትን አሉታዊ ምስል ለመቀየር ከፈለገ ወዘተ ብለው ያስቀምጣሉ:: ታዲያ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሎጎውን ሊቀይር የፈለገው ከእነዚህ አሳማኝ ምክንያቶች በአንዱ ምክንያት ነው? ወይስ በኢ-ምክንያታዊ በፋሽን እና በውድድር መንፈስ ብቻ? ባንኩ የዘመናዊነት ገጽታን ለማላበስ ቢፈልግም ደንበኞቹ የለመዱትን ማንነት ችላ ማለቱ ትክክል ነው ወይ?
ንግድ ባንክ ድንገተኛ የሎጎ ለውጥ ማድረጉ ወደፊት የሚያመጣበት አሉታዊ ተፅዕኖዎችም አሉት:: ይኼም የደንበኞችን የረጅም ጊዜ የስነ-ልቦና ትስስር ማፍረስ ነው። ይህን ነገር ከዚህ በፊት የሞከሩ ድርጅቶችም ከፍተኛ ዋጋ ከፍለዋል። ለአብነት ያህል:-
ታዋቂው የልብስ ድርጅት Gap ቀድሞ ሲጠቀምበት የነበረውን ሎጎ በድንገት በመቀየሩ ደንበኞቹ በንዴት ዘመቻ ከፍተውበት በአንድ ሳምንት ውስጥ ወደ ቀድሞው ሎጎ እንዲመለስ አስገድደውታል። ሌላው የብርቱካን ጭማቂ አምራች ድርጅት የሆነው Tropicana ነው:: ትሮፒካና በ2009 ሎጎውንና ማሸጊያውን ሲቀይር ሽያጩ በ20% በመውረዱ በወር ውስጥ ወደ ነበረበት ተመልሷል።
እነዚህ ምሳሌዎች የሚያሳዩት ሎጎ የድርጅቱን ማንነት ብቻ ሳይሆን የደንበኞችንም ስሜት የሚወክል መሆኑን ነው። የንግድ ባንክ ሎጎውን በመቀየሩ ከላይ ከተጠቀሱት አሉታዊ ተፅዕኖዎች በተጨማሪ በህዝቡ ዘንድ የተገነባውን Emotional Attachment ሊያሳጣው ይችላል::
በብራንድ ማኔጅመንት ዘርፍ ታዋቂው ምሁር ማርቲ ኒውማየር (Marty Neumeier) “Your brand isn’t what you say it is. It’s what they say it is.” ይላሉ። "የእርስዎ ብራንድ እርስዎ የሚሉት አይደለም። ብራንድዎ ህዝቡ የሚለው ነው" የሚል ነው።
ይህ ንግግር የሎጎን ወሳኝነትና ከደንበኞች ጋር ያለውን ትስስር ያጎላል። ሎጎን በገንዘብ ብዛት መቀየር የሚሞከር ከሆነ የብራንድ ማንነት ሊሸረሸር እንደሚችል ይናገራሉ።
በመጨረሻም የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሎጎ ለመቀየር ከ600 ሚሊዮን ብር በላይ በጀት ማውጣቱ ስትራቴጂያዊ ውሳኔ ቢሆን እንኳ የህዝብን ስሜት እና የረጅም ጊዜ ታሪክን ካለማገናዘብ አንፃር ትክክል ነው ወይ??? ሎጎ የድርጅት ምልክት ቢሆንም እውነተኛው ማንነቱ ግን በህዝብ ልብ ውስጥ ነው። ታዲያ የህዝብን ልብ የሚነካውን ምልክት መቀየር የገንዘብ ወጪ ብቻ ሳይሆን የደንበኛን ልባዊ እና ታሪካዊ ትስስር ስሜትን ማጣትስ አይደለምን?
“A logo is not what the company says it is. It's what the people feel it is.”
Via ዮአኪን በቀለ
የቴሌግራም ቻናልችንን በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…
May be an image of lighting, skyscraper and text that says '☬ SF CBE Always reliable Alwaysrellablebank bank'
 
 
 
 
• "ከፍተኛ" ታሪፍ እጥላለሁ ብለዋል
የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በ24 ሰዓታት ውስጥ "ከፍተኛ" ያሉትን ታሪፍ በህንድ ላይ እንደሚጥሉ አስታወቁ።
የደልሂ ፖለቲከኞች ከሩሲያ የነዳጅ ምርት መግዛታቸው ያባሳጫቸው ትራምፕ፣ ህንድ ታማኝ የንግድ አጋር አልሆነችልንም በሚልም ወቅሰዋል።
ህንድ ኢኮኖሚዋን ለመታደግና ብሄራዊ ጥቅምን ታሳቢ በማድረግ፣ ከሞስኮ አሁንም ነዳጅ ማስገባት መቀጠል እንደምትችል ሊታወቅልኝ ይገባል ብላለች።
አውሮፓ ህብረትና አሜሪካ አመክንዮ የሌለው ክስ አቅርበውብኛል በሚልም ኒው ደልሂ ትከራከራለች።
"ባለከፍተኛ ታሪፍ አገር " በሚል ትራምፕ ህንድን ሲጠሩ፣ በ24 ሰዓታት ውስጥ ከ25 በመቶው በተጨማሪ ከፍተኛ የተባለ ታሪፍ ሊጥሉባት እንደሆነ ይጠቁማል።
“ብዙ ቢዝነስ ከእኛ ጋር ይሰራሉ። ነገር ግን አንፈልጋቸውም።" በሚልም እንዲሁ አጣጥለዋል ትራምፕ።
የሩሲያን ነዳጅ በመግዛት የሞስኮን የጦር መሳሪያ ካዝና እየሞላ ነው፤ ሲሉም የጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲን መንግስት መውቀሳቸውን ኤንቢሲ አስነብቧል፡፡
የቴሌግራም ቻናልችንን በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…
በ2025 የመጀመሪያ 6 ወራት ዉስጥ በተለያዩ ሐገራት የደረሱ የተፈጥሮ አደጋዎች በሰዉ ሕይወትና አካል ላይ ካደረሱት ጉዳት በተጨማሪ ዓለምን 135 ቢሊዮን ዶላር አከሰሩ።
ለኢንሹራስ ኩባንዮች የጠለፋ ዋስትና የሚሰጠዉ ስዊስ ሪ የተሰኘዉ ኩባንያ እንዳስታወቀዉ፤ ዘንድሮ በግማሽ ዓመት ዉስጥ የተፈጥሮ አደጋ ያደረሰዉ ኪሳራ ከዚህ በፊት ታይቶ አይታወቅም።
መቀመጫውን ሱሪሽ-ስዊትዘርላንድ ያደረገዉ ኩባንያ እንደሚለው፤ ቃጠሎ፣ የዉኃ ሙላት፣ ርዕደ መሬትና መሰል አደጋዎች ካወደሙት ሐብትና ንብረት ዋስትና ወይም ኢንሹራስ የነበራቸዉ 80 ቢሊዮን የሚያወጡት ብቻ ናቸዉ።
ኢንሹራንስ ከተገባላቸዉ ንብረቶች ወይም የተፈጥሮ ሐብቶች ከፍተኛ ጥፋትና የኢንሹራስ ወጪ ያስከተለዉ ጥር ላይ ሎስአንጀለስ-ዩናይትድ ዉስጥ የደረሰዉ ቃጠሎ ነዉ - 40 ቢሊዮን ዶላር።
በተያያዘ ዜና፤ ትናንት ፈረንሳይና ስጳኝ ዉስጥ የተቀጣጠለዉ እሳት በፍጥነት እየተዛመተ ነዉ። ደቡብ ፈረንሳይ ዉስጥ አንዲት ሴት በቃጠሎው ሞተዋል፤ 12 ቤቶች፣ 12ሺ ሔክታር መሬት የሸፈነ ሰብልና ደን ዉድሟል።
ደቡባዊ ስጳኝ ታሪፋ በተባለች በሐገር ጎብኚዎች የምትዘወተር አካባቢን ያጋየዉ እሳት ደግሞ 1500 ሰዎችና 500 መኪኖችን ወደ ሌላ አካባቢ እንዲሸሹ አስገድዷል።
አሜሪካ ሎስ ፓደሬስ የተባለዉ አካባቢ የተነሳዉ ቃጠሎም የአካባቢዉን ደን እያጋየ መሆኑ ተዘግቧል፡፡
DW
የቴሌግራም ቻናልችንን በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…
አሊባባ ኩዋርክ ኤ.አይ (Quark AI) የተሰኘ ስማርት መነጽር አስተዋወቀ፡፡ ተቋሙ ባበለጸገዉ ኩዌን በተባለ የቋንቋ ሞዴል እና በኩዋርክ ምናባዊ ረዳት ታግዞ የሚሰራ ይሆናል፡፡
መነጽሩ አሁናዊ ትርጉምን ለማግኘት፣ የስብሰባ ንግግሮችን ወደ ጽሁፍ ለመቀየር፣ ከእጅ ንክኪ ነጻ የሆኑ የስልክ ጥሪዎችን ለማድረግ እና ሙዚቃዎችን ለማዳመጥ የሚያስችል አቅምን የተላበሰ ነው፡፡
መነጽሩ እ.ኤ.አ በ2025 መጨረሻ ለቻይና ገበያ ይፋ ይደረጋል የተባለ ሲሆን እስካሁን ስለዋጋው የተገለጸ ነገር እንደሌለ የሲ.ኤን.ቢ.ሲ ድረ ገጽ መረጃ ያሳያል፡፡
ስማርት መነጽሮቹ ከአሊባባ መተግበሪያዎች ጋር በመናበብ የሚሰሩ ናቸው፡፡
በዚህም ተጠቃሚዎች በድምጽ ትዕዛዝ ከመተግበሪያዎቹ የመንገድ አቅጣጫዎችን ለመጠየቅ ብሎም በአሊፔይ አማካኝነት ክፍያ እንዲከፍሉ ያስችላሉ፡፡
የተጠቃሚዎች ልምድ ማነስ፣ አጭር የባትሪ ቆይታ እና የተገደበ የኤ.አይ መስተጋብር የስማርት መነጽሮችን ከዚህ ቀደም የሚያጋጥሟቸው ችግሮች ናቸው፡፡ አሊባባ ይህን መሰል ችግሮች በኩዋርክ ኤ.አይ መነጽር መቅረፍ መቻሉ ተገልጿል፡፡
የቴሌግራም ቻናልችንን በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…
'አቢሲኒያ ሌግዠሪ ኮች' የተሰኘ የትራንስፖርት አገልግሎት አቅራቢ ድርጅት ከኬንያ ዋና ከተማ ናይሮቢ ወደ አዲስ አበባ በአውቶብስ ተጓዦችን ማመላለስ መጀመሩን አስታወቀ።
ድርጅቱ ባለፈው ሳምንት እሁድ በይፋ አገልግሎት መስጠት መጀመሩን 'አቢሲኒያ ሌግዠሪ ኮች' ዳይሬክተር ሚካኤል ጄምስ ማቺዮ ለቢቢሲ ተናግረዋል።
በአንድ ጉዞ 7 ሺህ 500 የኬንያ ሽልንግ እንደሚያስከፍል የተናገሩት ዳይሬክተሩ ለደርሶ መልስ ጉዞ ዋጋ 15 ሺህ የኬንያ ሽልንግ (16 ሺህ የኢትዮጵያ ብር ገደማ) መሆኑን ገልጸዋል።
አቶ ሚካኤል ከ'አቢሲኒያ ሌግዠሪ' በፊት 'ሮያል አላይድ' ተሰኘ ከናይሮቢ ሞያሌ እና ሞምባሳ የሕዝብ ማመላለሻ ትራንስፖርት አገልግሎት ላይ የተሰማራ ድርጅት መኖሩን ጠቁመዋል።
ከአራት ዓመታት በፊት የተመሠረተው 'ሮያል አላይድ' እስከ ሞያሌ ብቻ ይሠራ እንደነበር የጠቀሱት ዳይሬክተሩ በአውሮፕላን ቲኬት መወደድ ሳቢያ የአውቶብስ ትራንስፖርት ፍላጎት መኖሩን እና ይህንን ፍላጎት ሊያሟላ የሚችል አገልግሎት አቅራቢ አለመኖሩን "በጊዜው ክፍተት ነበር" ይላል።
ይህን ክፍተት ለመሙላት ነው "ለምን ቀጥታ [ከናይሮቢ- አዲስ አበባ] ጉዞ አንጀምርም ብለን አቢሲኒያን ጀመርን" ሲሉ ያክላሉ።
"ስምንት ባስ ነው ያለን የእኛ ዕቅድ 16 መሆን አለበት የሚል ነው። ከ16ቱ ስድስት ባስ እዚያው ኢትዮጵያ እንዲሆኑ ነው የምንፈልገው [እነሱን] በጂቡቲ በኩል እናስገባለን" ሲሉ ቀጣይ የድርጅቱን ዕቅድ ለቢቢሲ ገልጸዋል።
እንደ አቶ ሚካኤል ገለጻ አቢሲኒያ ሌግዠሪ በየቀኑ ወደ በናይሮቢ እና በአዲስ አበባ መካከል የሕዝብ ማመላለስ ሥራዎችን ይሠራል።
ባለፈው ዕሁድ ሥራውን በይፋ ሲጀምር ሰባት ተሳፋሪዎች ከናይሮቢ ወደ አዲስ አበባ ለመሄድ ትኬት ቆርጠው ነበር።
"እሁድ የሙከራ ጉዞ ነበር፤ነገር ግን በደንብ ማስታወቂያ ስላልተሠራ ቀጥታ የሚጓዙ ተሳፋሪዎች አልተገኙም" የሚሉት አቶ ሚካኤል "ባሱ 46 ሰዎች የመያዝ አቅም ቢኖረውም ቀጥታ አዲስ አበባ የሚሄዱት ሰባት ሰዎች ብቻ ነበሩ" ብለዋል።
አብዛኞቹ ተሳፋሪዎች ሞያሌ ድረስ የሚሄዱ እንደነበሩ ያስታወሱት ዳይሬክተሩ፤ "ሰባቱን ሰዎች በሰላም ባስ ወደ አዲስ አበባ ሸኘናቸው" ሲሉ ተናግረዋል።
ነገር ግን ሐሙስ ወደ አዲስ አበባ የሚጓዘው አውቶብስ ትኬት ተሽጦ ማለቁን ለቢቢሲ ገልጸዋል።
አውቶብሱ 46 ሰዎችን ብቻ እንዲጭን የተደረገበት ምክንያት ወንበሮች መካከል ክፍተት እንዲኖር እና ሰፋፊ ወንበሮችን ለመጠቀም መሆኑን አክለዋል።
አቶ ሚካኤል አውቶብሶቹ አስተናጋጆች፣ ራሳቸውን የቻሉ የሴቶችን እና የወንዶች መጸዳጃ፣ በውስጣቸው የኢንተርኔት እና 'ስክሪንን' ጨምሮ የመዝናኛ አግልግሎት እንዳላቸው ገልጸዋል።
የጉዞ መስመር እና ሰዓትን በተመለከተ አውቶብሱ ከቀኑ 10 ሰዓት ከናይሮቢ ሚነሳ ሲሆን፣ በማግስቱ ጠዋት ሞያሌ ይደርሳል።
ኢሚግሬሽን እስከሚከፈት ተሳፋሪዎች እንደሚያርፉ የጠቆሙት አቶ ሚካኤል ኢሚግሬሽን ከጠዋቱ ሁለት ሰዓት ያልቃል ብለዋል።
ከጠዋቱ ሁለት ሰዓት ተኩል ከሞያሌ፤ በያቤሎ፣ ቡሌ ሆራ፣ ዲላ፣ ሐዋሳ አድርጎ ከምሽቱ 1 ሰዓት ገደማ አዲስ አበባ እንደሚገባ ገልጸዋል።
የፀጥታ ሁኔታውን በተመለከተ ጥያቄ የቀረበላቸው አቶ ሚካኤል "ይህ መስመር ከመጀመሩ በፊት በራሴ ከ10 ጊዜ በላይ ተመላልሻለሁ፤ በመንገዱ ላይ የፀጥታ ስጋት በእኔ ጉዞ አጋጥሞኝ አያውቅም። ከዚህ በተጨማሪም የመንገዱን ደኅንነት በተመለከተ ከሞያሌ መረጃ ወስደን ነው የምንሄደው። እንዲሁም በኢትዮጵያ ድንበር ውስጥ በምሽት ጉዞ አናደርግም ቀን ብቻ ነው የሚጓዘው" ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል።
ድርጅቱ ከተመሠረተ ስድስት ወራት እንዳስቆጠረ የጠቆሙት አቶ ሚካኤል በስምንት የሕዝብ ማመላለሻ አውቶብሶች ሥራውን እንደጀመረ እንዲሁም ይህን ቁጥር ወደ 16 የማሳደግ ዕቅድ እንዳለው አስረድተዋል።
"[ድርጅቱ] መጀመሪያ ኬንያ ነው የተቋቋመው እዚህ ስንጨርስ እዚያ ሄደን ንግድ ፈቃድ ለማውጣት ጠይቀን ነበር ግን ዘገየ" ሲሉ ለቢቢሲ ተናግረዋል።
በኬንያ የኢትዮጵያ ኤምባሲ ምክትል አምባሳደር አቶ ደመቀ አጥፎ ከሦስት ሳምንት በፊት ከድርጅቱ ኃላፊዎች ጋር መነጋገራቸውን ኤምባሲው አስታውቆ ነበር።
አምባሳደር ደመቀ ለኩባንያው አመራሮች ስለ ማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው ገለጻ ማድረጋቸውን የጠቆመው ኤምባሲው "የኩባንያው አመራሮች ይህንን ዕድል ተጠቅመው ቅርንጫፉን በኢትዮጵያ እንዲከፍቱ አበረታተዋል" ብሏል።
የቴሌግራም ቻናልችንን በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…
 
 
 
 
 
 

በስመ ኣብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ኣሓዱ ኣምላክ ኣሜን፤

 

በሀገራችን በኢትዮጵያና በመላው ዓለም የምትገኙ ሕዝበ ክርስቲያን በሙሉ፡-

 

የክብር ባለቤት እግዚአብሔር ኣምላካችን እንኳን ለሁለት ሺሕ ዐሥራ ሰባት ዓ.ም የቅድስት ድንግል ማርያም ጾመ ፍልሰታ በሰላም ኣደረሳችሁ!

‹‹ታዓብዮ ነፍስየ ለእግዚአብሔር፣ ነፍሴ እግዚአብሔርን እጅግ ታከብረዋለች›› (ሉቃ.፩÷፵፮)፤

 

ይህንን ዐረፍተ ነገር የተናገረችው ማኅደረ መንፈስ ቅዱስ የሆነችው ቅድስት ድንግል ማርያም ናት፤ ቅድስት ድንግል ማርያም እግዚአብሔር ዓለምን ለማዳን በሰራው ስራ ሰውነታችንን ለመዋሓድ የመረጣት ምርጥ የፍጥረት ወገን ናት፤ፍጥረት ሁሉ በእግዚአብሔር ለእግዚአብሔር ተፈጥሮኣል፤የእግዚአብሔርም ነው፤ የቅድስት ድንግል ማርያም መመረጥም በእግዚአብሔር ለሰው የተደረገ ምርጫ ነው፤

 

የሰው መዳን ከጥንቱ ከጠዋቱ በእግዚአብሔር ልዩ ኣሰራር እንደሚከናወን በነቢያት የተገለጸ ነበረ፣‹‹ኣኮ በተንባል ወኣኮ በመልኣክ ኣላ ለሊሁ እግዚእ ይመጽእ ወያድኅነነ፤ በኣማላጅም ኣይደለም፤ በመልኣክም ኣይደለም እሱ ራሱ ጌታ መጥቶ ያድነናል እንጂ›› የሚለው የነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስ ትንቢትም ይህንን ያስረዳል፤ ቃለ ትንቢቱ ድኅነታችን በጌታ ቤዛነት እንደሚከናወን ያረጋግጣል፤ይህም ሊሆን የቻለው ከፍጡራን ወገን በደሙ ቤዛነት ፍጡራንን የሚያድን ስለሌለ ነው፤

 

ከዚህ ኣንጻር የሰው መዳን በእግዚአብሔር ኣሰራር በደም ቤዛነት ከሆነ፣ በደሙ ቤዛነትም ዓለምን ማዳን የሚችል ከፍጡር ወገን ከሌለ፣ መዳናችን በእግዚአብሔርና በእግዚአብሔር እጅ ብቻ የተንጠለጠለ ነበረ፤ እግዚአብሔር በደሙ ቤዛ ሆኖ ዓለምን ለማዳን ደግሞ ደም ሊኖረው ይገባ ነበር፤ በመሆኑም እግዚአብሔር በክዋኔው ደም የሌለው ስለሆነ ለቤዛ ዓለም የሚፈስ ደምን ገንዘብ ማድረግ ነበረበት፤ይህንን ደም ለመዋሓድ ቅድስት ድንግል ማርያምን መረጠ፤ ለዚህ ብቁ እንድትሆንም በእስዋ ላይ ስራውን ሰራ፤በምርጫውም መሠረት ከቅድስት ድንግል ማርያም ደማዊ ሥጋንና ነፍስን ተዋሕዶ ለቤዛዊ መሥዋዕት መንገዱን ኣመቻቸ፤

 

ቅድስት ድንግል ማርያም በነገረ ድኅነት መሰላል ለመሆን በእግዚአብሔር የተመረጠች በመሆኗ ኣንቀጸ ኣድኅኖ ወይም የድኅነት በር ትባላለች፤ቅድስት ድንግል ማርያም ለዚህ ታላቅ ነገረ ድኅነት መመረጥዋ እጅግ ታላቅ ዕድል መሆኑን ስለተገነዘበች ‹‹ታላላቅ ስራዎችን ሰርቶልኛልና›› በማለት እግዚአብሔርን በመዝሙር ኣመስግናለች ኣክብራለችም፤

 

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት!

 

የቅድስት ድንግል ማርያም የምስጋና እና የኣምልኮ መዝሙር የኛም መዝሙር ነው፤ እግዚአብሔር ለቅድስት ድንግል ማርያም ታላላቅ ስራዎችን እንደሰራ ለኛም ብዙ ታላላቅ ስራዎችን ሰርቶልናል፤ እየሰራልንም ነው፤ ለሰራልን ኣምላክም እንደ ቅድስት ድንግል ማርያም ታላቅ ክብርን መስጠት ይገባናል፤ ለእግዚአብሔር የምንሰጠው ክብርም በቃል ብቻ የሚገለጽ ሳይሆን በተግባር የሚታይ ሊሆን ይገባል፤ የድንግል ማርያም መንፈሳዊ ሕይወት በማስተዋል በትሕትና፣

በትዕግሥት በርኅራኄ በመታዘዝ በንጽህና በቅድስና በክብርና በበረከት የተሞላ እንደሆነ በቅዱስ መጽሓፍ ከተጻፈው ሥነ-ሕይወቷ መረዳት እንችላለን፤

ታድያ በእርሷ ክብርና ተማሕፅኖ የምንተማመን ልጆቿም የእሷን ያህል እንኳ ባንችል ወደእርስዋ የሚጠጋጋ መንፈሳዊ ሕይወት ሊኖረን ይገባል፤ ይህም የምናደርገው ለእግዚአብሔር ክብርና ለእኛ መዳን ሲባል ነው፤ እኛ እግዚአብሔርን ስናከብር እንከብራለን እንድንማለን፤ ለእግዚአብሔር ክብር የማንሰጥ ከሆነ ግን ውጤቱ መክበር ሳይሆን ሌላ ነው የሚሆነው፤

 

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት!

 

እኛ በየጊዜው ጾምን እንድንጾም ያስፈለገበት ዋናው ምክንያት ፈቃደ ሥጋችንን በመግራት ለእግዚአብሔር ታዛዦች እንድንሆን ነው፤ ጾም የኃጢኣት መግቻ መሳሪያ በመሆኑ ‹‹ልጓመ ኃጢኣት›› ተብሎ ይታወቃል፤ በዚህም ሰውነታችንን ለግብረ ኃጢኣት ከሚያጋግሉ ምግቦች ኣርቀን በሰከነ መንፈስ እግዚአብሔርን እያሰብን ኃጢኣታችንንም እያስታወስን በንስሓ ወደ እርሱ ለመቅረብና ለሱ ለመታዘዝ እንጾማለን፤

 

የጾም ጥቅም ከጥንት ጀምሮ የታወቀ በእግዚአብሔርና በሰውም ተቀባይነት ያለው ነው፤ እግዚአብሔር ከመሥዋዕት ይልቅ መታዘዝን ይወዳልና በጾምና በጸሎት ለሱ ልንታዘዝ ይገባል፤ እግዚአብሔር በቅድስት ድንግል ማርያም ማሕፀን ሊያድር የቻለው ‹‹እንዳልኸኝ ይሁንልኝ›› ብላ ታዛዥነትዋን በገለጸች ጊዜ ነው፤ እኛም እንዳልከን ይሁንልን እያልን እንደእስዋ ታዛዥ መሆን አለብን፤

 

ዛሬ በዓለማችን ያለው መተረማመስ ለእግዚአብሔር ያለመታዘዝ ያመጣው ጣጣ እንደሆነ ማንም ኣይስተውም፤ መታዘዙ ቢኖር ኖሮ የሰው ልጅ ሰውን የሚያድን ብቻ እንጂ ሰውን የሚገድል መሳሪያ ኣያመርትም ነበር፤ ምክንያቱም እግዚአብሔር ወንድምህን እንደራስህ ኣድርገህ ውደድ ኣለ እንጂ ግደል ብሎ ኣላዘዘምና ነው፤ኣሁንም በዚህ ባለንበት ዓለም በጣም ተባብሶ የሚገኘው የመጠፋፋት ዝንባሌ ለእግዚአብሔር በመታዘዝ በሰላምና በሰጥቶ መቀበል ካልተቋጨ ዳፋው ኣስከፊ መሆኑ ኣይቀርም ፤

 

ከዚህ አንጻር ዛሬም ለሰው ልጆች ሁሉ የምናስተላልፈው መልእክት ‹‹በፍቅር ከሆነ ትንሹም ለሁሉ ይበቃልና ያለውን በጋራ በመጠቀም በፍቅርና በሰላም እንኑር›› የሚል ነው፤ ‹‹ፍትሕና ርትዕም ለሰው ልጅ መነፈግ የበለትም፤ ሰው በምድር ላይ ሰርቶ የመኖር መብቱ ሊከበርለት ይገባል፤ይህንን ማድረግ ማለት ለእግዚአብሔር መታዘዝ ማለት ነው፤ስለሆነም ለእግዚአብሔር ክብርና ለራሳችን መዳን ስንል ለእርሱ በመታዘዝ በሕይወትና በሰላም እንኑር፡፡

 

በመጨረሻም፡-

 

በጾመ ማርያም ሱባዔ ስለሀገር ሰላምና ስለሕዝብ ደኅንነት በመጸለይ፣ በልዩ ልዩ ምክንያት በመከራ ላይ ወድቀው የሚገኙ ወገኖቻችንን በሚያስፈልጋቸው ሁሉ በመርዳት ሱባዔውን እንድናሳልፍ ኣባታዊ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም ለመላው ሕዝበ ክርስቲያን እናስተላልፋለን፤

መልካም የሱባዔ ወቅት ያድርግልን እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ!

 

ወስብሓት ለእግዚአብሔር ኣሜን!!

 

አባ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣

 

ነሐሴ 1 ቀን 2017 ዓ.ም

 

ዋሽንግተን ዲሲ

 

"የወዲያነሽ"መጽሐፍ የፊታችን ቅዳሜ ነሐሴ 3 ቀን 2017 ከቀኑ 8:00 ጀምሮ በብሔራዊ ቤተመዛግብትና ቤተመጻሕፍት አገልግሎት (ወመዘክር ) ይመረቃል።