Administrator

Administrator

”ይህን ሳያዩ ቤት እንዳይገዙ” በሚል መሪ ቃል የተዘጋጀ አርኪ የሪል እስቴት ኤክስፖ፤ ከየካቲት 15- 17 ቀን 2016 ዓ.ም በሚሊኒየም አዳራሽ  እንደሚካሄድ ተገለጸ፡፡ በዚህ ኤክስፖ ላይ ሪል እስቴት

አልሚዎች ቤት በማቅረብ ሲሳተፉ፣ ባንኮች ደግሞ ፋይናንስ በማቅረብ እንደሚሳተፉ አዘጋጆቹ ጠቁመዋል፡፡በኢንቴርየር ዲዛይን (ቤት የማስዋብ አገልግሎት) የተሰማሩ እንዲሁም የእንጨት ሥራ ውጤቶችን የሚያቀርቡ

ፈርኒቸር ቤቶችም በኤክስፖው ላይ እንደሚሳተፉ ታውቋል፡፡ ዘርፉ በቴክኖሎጂ እንዲታገዝም በዚህ ሥራ ላይ የተሰማሩ ድርጅቶች ሌሎች የኤክስፖው ድምቀት ናቸው ተብሏል፡፡ በዚህ ኤክስፖ አቅምን ታሳቢ በማድረግ

ታላቅ ቅናሽ ያደረጉ ሪል እስቴቶችም እንደሚሳተፉ የኤክስፖው አዘጋጆች ጠቁመዋል፡፡ኤክስፖው ይህን ሁሉ በአንድ ቦታ በማካተት የቤት ፈላጊውን ራስ ምታት ያቀላል የሚሉት አዘጋጆቹ፤ ቤት መግዛት የሚፈልግ

ዋጋንና ጥራትን እንዲሁም ሌሎች መረጃዎችን ለማሰባሰብ የሚያባክነውን ጊዜና ጉልበትም ይቆጥባል ባይ ናቸው፡፡  ከ70 በላይ ድርጅቶች የሚሳተፉበትን ይሄን ኤክስፖ እስከ 10ሺ የሚደርሱ ሰዎች እንደሚጎበኙት

ይጠበቃል ብለዋል፤ አዘጋጆቹ አርኪ ኤቨንት ኦርጋናይዘር፡፡ አርኪ ኤቨንት ኦርጋናይዘር ”አርኪ ሆምስ“ ኤክስፖን ሲያዘጋጁ፣ የዘንድሮው ለሁለተኛ ጊዜ መሆኑ ታውቋል፡

የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባዔ፣ መንግስት ከኢትዮጵያ ህዝብ የሃይማኖትና የባህል እሴቶች ጋር የሚፃረር ፅንሰ ሃሳቦችና ትርጓሜዎች ያላቸውን ይዘቶች ያካተተውን መንግስት ስምምነት መፈረሙን በጥብቅ

እንደሚቃወም አስታወቀ፡፡ በአውሮፓ ህብረትና በአፍሪካ፣ በካረቢያንና በፓስፊክ አገራት ለቀጣዮቹ 20 ዓመታት እንዲዘልቅ ታሳቢ ተደርጎ የተከናወነው የንግድና ኢኮኖሚ ትብብር በሚል ሽፋን የቀረበውና ሰሞኑን

የተፈረመው ስምምነት፣ ከግብረ ሰዶማዊነት መብቶች፣ ከፆታ መቀየር፣ ከውርጃና ሁሉን አቀፍ ግልሙትናዎችን ህጋዊ ማድረግ ይገኝበታል ተብሏል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም እጅግ አደገኛ ይዘት ያለው ለአህጉሪቱ ልጆችና

ታዳጊዎች ሁሉን አቀፍ የወሲብ ትምህርት አስገዳጅ ትምህርት ሆኖ እንዲሰጥ የሚያደርግ እንደሆነም ተገልጿል፡፡በኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባዔ የበላይ ጠባቂ አባቶች ሰሞኑን የተሰጠው ይኸው መግለጫ፣

መንግሰት ከሰሞኑ የፈፀመውን ይህንኑ ስምምነት በጥብቅ እንደሚቃወሙትና እንደማይቀበሉት በመጥቀስ፣ ጉዳዩን መንግስት በአንክሮ እንዲመለከተው ጠይቀዋል፡፡


Saturday, 10 February 2024 09:49

ጥል ያጣ ጠጅ ያድላል

በፈረንሳይ አገር፤ የውበት እንብርት በምትባለው በፓሪስ በጣም ተደናቂ ከሚባሉት እይታዎች መካከል የ”ኤፍል ታወር” (የኤይፍል ሰማይ-ጠቀስ ሀውልት እንደማለት  ነው) አንዱ ነው፡፡ ይህ ልዩ ቅርፅ ያለው የብረት አፅመ - ሀውልት የተሰራው ለ1889 ዓ.ም (እ.ኤ.አ) የፓሪስ ኤግዚቢሽን እንዲሆን ተብሎ ነበር፡፡ ቁመቱ 320 ሜትር ነው፡፡ ዋነኛው መሀንዲስና መሰረታዊው የዲዛይን ነዳፊ ኤይፍል ጁስታቭ (1832-1923) ይባላል፡፡ “ኤይፍል ታወር” የሚለው ስያሜ እንግዲህ ከሰውዬው ስም የመነጨ ነው ማለት ነው፡፡ አሜሪካን አገር በኒውዮርክ የሚገኘውን የነፃነት ሐውልት (Statue of Liberty) ዲዛይን የነደፈውም ይሄው መሀንዲስ ነው፡፡
የ”ኤፍል ታወር”ን ሐውልት ዲዛይን ለማውጣት መጀመሪያ በፓሪስ ያሉ ዲዛይን አውጪዎች በሙሉ እንዲወዳደሩ ማስታወቂያ ወጥቶ ነበር፡፡ ከተወዳደሩት መካከል በወቅቱ ታላቅ ነው የሚባለው አንድ ሰዓሊም ይገኝበታል፡፡ ይህ ሰዓሊ ማንም የሚበልጠኝ የለምና የማሸንፈው እኔ ነኝ ብሎ በእርግጠኝነት ኮርቶ የተቀመጠ ነበር፡፡
ውጤቱ ግን እንደጠበቀው አልሆነም፡፡ ያልገመተው ዲዛይነር አሸነፈ፡፡ ሰዓሊው በጣም ተበሳጨ፡፡ ከቤቱ መውጣት ሁሉ አስጠላው፡፡ ከቀን ቀን የኤፍል ታወር በፓሪስ ሰማይ ግዙፉን ቅርፁን ሽቅብ መዝዞ እየተንጠራራ ይታይ ጀመር፡፡ በመጨረሻም ሀውልቱ እጅግ አምሮ ከየአቅጣጫው ጎልቶ እንደሚታይ ሆኖ ቆመ፡፡
ታዲያ ሁሌ ጠዋት ጠዋት፣ ያ ተሸናፊ ሰዓሊ ከቤቱ ሲወጣ “ኤፍል ታወር” ገዝፎ ቆሞ ያየዋል፡፡ ይናደዳል፡፡ ስለዚህ አቅጣጫ ይቀይራል፡፡ ያ የብረት ኃውልት ግን ከተቀየረው አቅጣጫም ሆኖ ሲያየው በዚያም በኩል አፍጥጦ ያየዋል፡፡ በቆመበት አቅጣጫ ሁሉ የ”ኤፍል ታወር” ይታየዋል፡፡ “ይህንን ሐውልት የማላይበት የት ልድረስ?” ይላል፡፡ በድፍን ፓሪስ በተለያየ አቅጣጫ ለመዝናናት በሄደ ቁጥር “ኤፍል ታወር” ብቅ ይላል፡፡ ሰዓሊው ጨነቀው፡፡ በየትም አቅጣጫ ቢዞር ሀውልቱን ያየዋል፡፡ ስለሆነም የመሸነፍ ህመሙን ያስታውሰዋል፡፡ ለህሊናው ሁከት ይሆንበታል፡፡ ቡና እንኳን ለመጠጣት ወጥቶ የ”ኤፍል ታወር”ን ሳያይ ቡና ቤት መቀመጥ አልቻለም፡፡
አንድ ቀን አንድ ሀሳብ መጣለት፡፡ “ለምን ከሰማይ - ጠቀሱ ሀውልት ስር ያለው ካፌ ሄጄ ቡና አልጠጣም?” አለ፡፡ ፈጥኖ ወደዚያች ካፌ ሄደ፡፡ ቡናውን አዝዞ እየጠጣ ሳለ፣ በሁሉም አቅጣጫ ቢመለከት የ”ኤፍል ታወር” ጨርሶ የለም፡፡ ለመጀመሪያ ጊዜ እፎይ ብሎ ደስ እያለው ቡናውን ጠጣ! እነሆ በመጨረሻ ከጠላው እውነት ሥር መቀመጡ የተሻለ ሆኖ አገኘው፡፡
***
መሸነፍን አለመቀበል ለህሊና ውጋት ይዳርጋል፡፡ አንድ ወቅት ትልቅ ነበርኩና የሚበልጠኝ አይፈጠርም ብሎ ማሰብም ከፍተኛ ችግር ላይ ይጥላል፡፡ ያፈጠጠውን እውነት አልቀበልም ማለትና ከእውነት ለመሸሽ መሞከር፤ መከራ ማየትን ያስከትላል፡፡ ላያመልጡ ነገር ቁም-ስቅል ማየትን ያመጣል!
በተደጋጋሚ የሚሰሩ ስህተቶች ከአንዴ ከሁለቴ በላይ እርምት ይደረግባቸዋል ተብሎ ተመልሰው እዚያው የሚገኙ ከሆነ ወይ ከአራሚ፤ ወይ ከታራሚው፣ አሊያም ከስርዓቱ አንዳች መሰረታዊ ጉድለት አለ ማለት ነው፡፡ ይሄን ያልመረመረ እስከ ፍፃሜ ውድቀቱ ድረስ ከችግር ወደ ችግር ሲሸጋገር እንዲኖር ይገደዳል፡፡ ዕጣ-ፈንታው የሽግግር ዘመን ብቻ ይሆናል፡፡ አንዳንድ የሹመት ወንበሮች በተደጋጋሚ ሰው ተመድቦባቸው በተደጋጋሚ ፈጣን ሽረት ይደርስባቸዋል፡፡ ወንበሮቹም የሽግግር ወንበር ይመስላሉ ለማለት ይቻላል፡፡ ለመፍትሄው ሌላ ሰው የመመደብን ችግር እንጂ የአሰራሩን አሊያም የስርዓቱን እንከን የማየት ባህል ገና አልተለመደም፡፡ ይሄ የግድ መለመድ አለበት፡፡
ስብሰባ በተባለ ቁጥር “የመኖር ወይም አለመኖር” ጥያቄ የሚደቀንባቸው አያሌ ሹማምንት ናቸው! እንደ እውነቱ ከሆነ ለጊዜው ነው እንጂ እውነቱ የታወቀ እለት እርቃን መቅረት አለ- “የአይጥ ጧፍ ድመት ሲገባ ይጠፋል” ነዋ ነገሩ!
አንዳንዱ የራሱ ሳያንስ የሩቅና የቅርብ የስጋም፣ የድርጅትም ዘመዶቹን በዙሪያው ሰብስቦ ሌላ የሙስና፣ የኢ-ዲሞክራሲያዊነት፣ የኢ-ፍትሀዊነት፣ የአስተዳደር ደካማነት ማዕከል ለመፍጠር የሚውተረተር ይመስላል፡፡ እንዲህ መሰሉን ጉልበተኛ ተጠልሎ በማን አለብኝነት ዘራፍ ሲል ይውላል፡፡ “የጠገበ ሌባ ቃጭል ያንጠለጥላል” እንዲሉ ቀኑ ደርሶ “ከተከበረ” መንበሩ እስኪወርድ በአደባባይ ግነን በሉኝ ማለት የሙጥኝ ይላል፡፡ የማታ ማታ ከነዘመድ አዝማዱ የወረደ እለት ጉዳዮች ሁሉ ወደ መጀመሪያው እርከን ይመለሳሉ፡፡ (Back to Square one) ነገራችን ሁሉ የእንቧይ ካብ የእንቧይ ካብ ማለት እንግዲህ ይሄ ነው፡፡ሌላም ብርቱ ችግር አለ፡፡ እንደ ቅዱስ መፅሐፍ ቃል የሚደረደሩ ቃላት የስብሰባ አሸንክታብ ሆነው እንዳይቀሩ ልብ ብሎ ማየት ያስፈልጋል፡፡ የተሳሳተ የእድገት ስዕል ይሰጣልና መጠንቀቅ ይበጃል፡፡ ጧት ማታ የሚነበነቡት ቃላት የወረት ፀሎት እንዳይሆኑ ተግባራዊነታቸውን ማጤን ያስፈልጋል፡፡ አለበለዚያ የገዛ ራስን ጥላ እስከመሸሽ፣ ደረቁን እውነት የማላይበት የት ልድረስ እስከማለት የደረሰ ጥፋት ውስጥ መዘፈቅ ይከተላል፡፡ በየቢሮው ስብሰባ ተካፍሎ መመለስ፣ ልዩ ማዕረግ ያስገኘላቸው የሚያስመስሉ አያሌ አለቆች አሉ፡፡ የስብሰባዎቹን ቃላት መደጋገምን እንደ እውቀት መለኪያ መውሰድም እጅግ አደገኛ ህፀፅ አለው፡፡ መተግበር ዋና ነገር ነው፡፡ እንዴት መተግበር እንዳለበት ማውጠንጠንም ቁልፍ ጉዳይ ነው፡፡ በተከታታይ በታዩ ኢትዮጵያዊ ለውጦች ውስጥ ሁሉ የቃል-ጥናት ዋና መሳሪያ ሆኖ ታይቷል፡፡ የካድሬ ደቀ - መዛሙርትና የቢሮ ንቃት-ሃዋርያት ድግምት እስኪመስሉ ድረስ እንዲያንገፈግፉ መደረጋቸው አሌ አይባልም፡፡  የቢሮክራሲው ቁንጮ ቢሮክራሲውን እየረገመ ለሌላ አገር ቢሮክራሲ የቆመ ያስመስላል፡፡ አንዳንዴ ከናካቴው የሚወቀስ የጠፋበት ጊዜም ይፈጠራል፡፡ ነብሱን ይማረውና ሌኒን “ጠላቶቻችን ቋንቋችንን ወስደውብናል፣ ቅያሬ ቋንቋ ሊኖረን ይገባል” ያለው እንዲሁ ተቸግሮ ሳይሆን አይቀርም፡፡ ዛሬም ያንኑ ፈለግ የያዘ ይመስላል፡፡
የሚገርመው ግን ዋናው ትኩረት የሚደረገው የወቅቱ አንገብጋቢ ጉዳዮች ማለትም-የማያቋርጠው ድርቅ ላይ፣ የተፈጥሮአዊና ሰው ሰራሽ ጥፋቶች ላይ፣ ዞሮ-ገጠም የዕዳ ጣጣ ላይ፣ ስራ አጥነት፣ በሽታና ርሀብ ላይ አይደለም፡፡ ወደፊት እነሱን የሚፈቱ የሚመስሉ ነባቤያዊ ልፈፋዎች (theoretical rhetorics) የጥንትና ያሁኖቹ፣ የሩቅ ያሁኖችና የቅርብ ያሁኖች፣ ያደባባይ ቃላት ሽመናዎች (coinages) አስገራሚ ነው፡፡ አንዱ “ሂስና ግለሂስ” ሲል ሌላው “ግምገማ፤” አንዱ “ኅብረት” ሲል፣ ሌላው “ውህደት”፣ አንዱ “ግንባር” ሲል ሌላው “ቅንጅት” ወዘተ… መድብለ ፓርቲና የብዙሃን ፓርቲ፣ ኮንፈረንስና ጉባዔ፣ ውጤት - ተኮርና አመርቂ ውጤት፣ ዕሳቤና ግንዛቤ፣ አንጃና ውሁዳን፣ ማንቃትና ማስረጽ፣ በመዋቅር ማውረድና መመደብ፣ ሰብሳቢና ጠርናፊ፣ ምዝበራና ሙስና፣ ታክቲክና ስትራቴጂ፣ ሚሽንና ቪዥን፣ ፓርቲሲፔሽንና ህብረ-ሱታፌ፣… እነዚህን መሰል ቃላት እንደየአመራሩ ይፈበረካሉ፣ ይፈለፈላሉ፡፡ መረሳት የሌለበት ግን ይሄን ሁሉ ለመረዳት የሚችልና በተግባርም ማራመድ ያለበት ህዝብ ወሳኝ መሆኑን ነው፡፡ ህዝብ ያልተረዳው ነገር የፖለቲከኞች መሻኮቻ እንጂ መሬት - የያዘ (terre a terre) እና ረብ-ያለው ጉዳይ አይሆንም፡፡ የፒራሚዱ አናት ላይ ያሉ ኅሩያን ህዳጣን (ጥቂቶች ምርጦች) ብቻ ለውጥን የትም አያራምዱትም፡፡
እያንዳንዱ ድርጅት ወይም ፓርቲ በህዝብ አኗኗርና በሀገር እድገት ላይ ምን ያስከትላል ሳይል “ወቅታዊው መፈክር ያታግላል አያታግልም”፣ “ሀሳቡ ባይተገበርም ሰውን ካነጋገረ ተሳትፎን ያጎለብት የለም ወይ?” “በጉዳዩ ላይ አባላት ይተጋገላሉ አይተጋገሉም፣…” በሚል አይነት የራስን መንገድ ብቻ ባማከለ አካሄድ መጓዝ፣ ዞሮ ዞሮ ለግራ-መጋባትና ለአተካሮ ሊዳርግ፣ ኋላም ጥላቻን ሊፈጥር እንደሚችል መገንዘብ ከብዙ ውዝግብ ያድናል፡፡ አለበለዚያ ግን “ጥል ያጣ ጠጅ ያድላል” እንደተባለው ወቅታዊ አቧራ በማስነሳት ብቻ ላያቆም ይችላልና መጠንቀቅ ደግ ነው!! እንደ ሰዓሊው እውነቱ ስር ለመደበቅም ቢሆን ጊዜው መርፈድ እንደሌለበት አለመዘንጋት ነው!

የኢትዮጵያ የውጭ ግንኙነት ታሪክ ተመራማሪው የታሪክ ምሁሩ እና በቅርቡ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ለመጀመሪያ ጊዜ ያሳተመው''  የዘመናዊት ኢትዮጵያ የውጭ ግንኙነት እና ዲፕሎማሲ ከ1900-2015 ዓ.ም.'' መጽሐፍ ላይ አስተያየት በመስጠት ሞያዊ ድጋፍ ያበረከቱት ዶ/ር በለጠ በላቸው በሳይንስ ሙዚየም በመገኘት የዲፕሎማሲ ሳምንት አውደ ርዕይን ጎብኝተዋል።



የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ፣ ለሀገር አቀፍና ክልላዊ ፖለቲካ ፓርቲዎች የምዝገባና የህጋዊ ሰውነት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀት መስጠቱን አስታወቀ።
ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የምዝገባና የህጋዊ ሰውነት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀት የሰጠው ለወሎ ህዝቦች ዲሞክራሲያዊ ፓርቲና ለብሔራዊ ባይቶ ዓባይ ትግራይ ለተሰኙ ሀገር አቀፍ የፖለቲካ ፓርቲዎች እንዲሁም ለኩሽ ህዝቦች ብሔራዊ ንቅናቄ ለተሰኘ ክልላዊ የፖለቲካ ፓርቲ መሆኑን በማህበራዊ ትስስር ገጹ ያሰፈረው መረጃ ያመለክታል።
ቦርዱ ጥር 21 ቀን 2016 ዓ.ም ያከናወነው የምዝገባና የህጋዊ ሰውነት ማረጋገጫ በኢትዮጵያ የምርጫ፤ የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባና የምርጫ ሥነ-ምግባር አዋጅ ቁጥር 1162/2011  በተሰጠው ሥልጣን መሠረት መሆኑ ተገልጿል።

 ባለፉት 6 ወራት ሀብታቸውን ካስመዘገቡ 41 ከፍተኛ የመንግስት አመራሮች ውስጥ ትክክለኛ ሆኖ የተገኘው አንዱ ብቻ ነው
መታሰቢያ ካሣዬ
ባለፈው  የፈረንጆች 2023  በኢትዮጵያ የሙስና ወንጀሎች በእጅጉ  መጨመራቸውንና   የመንግሥት ስልጣንን ያለከልካይ ለግል ጥቅም ማዋል መባባሱን  ትራንስፓረንሲ ኢንተርናሽናል አስታወቀ።  አገሪቱ በ2023 በሙስና ነክ ወንጀሎች መንሰራፋት ልኬት 37  ነጥብ ከ100 ተሰጥቷት ከዓለም በ98ኛ ደረጃ ላይ እንደምትገኝ ተቋሙ  ይፋ አድርጓል።
የ180 የዓለም አገራትን  የሙስና ነክ ወንጀሎች  በየዓመቱ  እየመዘነ ደረጃ የሚያወጣው ትራንስፓረንሲ ኢንተርናሽናል  ከትናንት በስቲያ ይፋ ባደረገው የ2023 ሙሉ ዓመት ሪፖርት፣ ኢትዮጵያ በመመዘኛዎቹ 37 ከ100 ነጥብ በማግኘት 98ኛ ደረጃ ላይ መቀመጧን አስታውቋል፡፡ አገሪቱ በፈረንጆቹ  2022 ዓ.ም በሙስና ነክ ወንጀሎች መንሰራፋት ልኬት 38 ነጥብ ከ100 ተሰጥቷት ከዓለም 94ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣ እንደነበር ተቋሙ አስታውሷል።
በተቋሙ መለኪያ  ዓለም አቀፍ አማካይ የሙስና ውጤት 43 ነጥብ ሲሆን፤ ኢትዮጵያ ያገኘችው 37 ነጥብ  ከአማካይ በታች በስድስት ነጥብ ዝቅ ያለ መሆኑንም ተቋሙ በሪፖርቱ ጠቁሟል፡፡ በትራንስፓረንሲ ኢንተርናሽናል ነጥብ አሰጣጥ መሰረት፤ 100 ማለት ከሙስና ነጻ ማለት ሲሆን ወደ ዜሮ እየቀነሰ ሲሄድ የሙስና ወንጀሎች መጨመራቸውን አመላካች ነው።
ተቋሙ የሚፈትሻቸው የሙስና ዓይነቶች ጉቦ ፣ የመንግሥት ስልጣንን ያለከልካይ ለግል ጥቅም ማዋል፣ የመንግስት አካላት በመንግስት ዘርፍ ሙስናን የመቆጣጠር ችሎታ፣ በመንግስት ተቋማት ለሙስና አጋላጭ የሆኑ አሰራሮችን መተግበር፣ በጀትን ማዞር ፣ የመንግስት ባለስልጣናት ሃብታቸውንና ሊፈጠሩ የሚችሉ የጥቅም ግጭቶችን ከማሳወቅ አንጻር፣ የሙስና ጉዳዮችን ለሚያጋልጡ አካላት የህግ ከለላ መኖር እንዲሁም በሕዝባዊና መንግስታዊ ጉዳዮች ላይ የመረጃ ማግኘት መብትን ያካትታሉ።
የኢትዮጵያ ፌደራል ሥነ ምግባር እና ጸረ ሙስና ኮሚሽን  ሰሞኑን ይፋ ባደረገው መረጃ መሰረት፤ ባለፉት ስድስት ወራት  ሀብታቸውን ለኮሚሽኑ ካስመዘገቡ 41 ከፍተኛ የመንግሥት ባለስልጣናትና  አመራሮች መካከል ትክክለኛ ሆኖ የተገኘው አንዱ ብቻ መሆኑን ማስታወቁ ይታወሳል፡፡

-ድምጻዊ ዳዊት ጽጌ-
በአንጋፋዎቹ የአገራችን ድምፃውያን አሰፋ አባተ፣ ጥላሁን ገሰሰ እና እሳቱ ተሰማ ከዘመናት በፊት የተቀነቀኑና ከአድማጭ ጆሮ እርቀው የኖሩ ሦስት ተወዳጅ ሙዚቃዎች በወጣቱ ድምፃዊ ዳዊት ፅጌ ዳግም ተቀንቅነው፣ “የዘመን ቃናዎች ፩” በሚል ስያሜ የሙዚቃ ቪዲዮዎች እንደተሰራላቸው የተገለጸ ሲሆን፤ ትላንትና አርብ ጥር 24 ቀን 2016 ዓ.ም ሥራዎቹ በራሱ ዳዊት ፅጌ ዩቲዩብ እንደሚለቀቁ ተነግሯል፡፡
“የዘመን ቃናዎች ፩” የሙዚቃ ቪዲዮዎችን አስመልክቶ ከትናንት በስቲያ ሐሙስ  ረፋዱ ላይ ድምፃዊ ዳዊት ፅጌና አንጋፋው የሙዚቃ አቀናባሪ አበጋዙ ክብረወርቅ ሺዎታን ጨምሮ ሌሎች በሙዚቃ ሥራዎቹ የተሳተፉ ባለሙያዎችና የቀድሞ አርቲስቶች ቤተሰቦች  በተገኙበት በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ራስ መኮንን አዳራሽ ጋዜጣዊ መግለጫ ተሰጥቷል፡፡
ጋዜጣዊ መግለጫው በጥያቄና መልስ፤ በማብራሪያና አስተያየት የታጀበና ከወትሮው በተለየ መልኩ ቁምነገር የሚያስጨብጥና ጥበብ ጥበብ የሚሸት እንደነበር ታዳሚዎች ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡ ለዚህ ደግሞ መድረኩን በጥበብና በዕውቀት የመራው የመድረኩ ሞገስ  ተዋናይ ግሩም ዘነበ የአንበሳውን ድርሻ እንደሚወስድ ብዙዎች መሥክረዋል፡፡
 


ድምፃዊ ዳዊት ፅጌ የራሱን ዘፈኖችና አልበም ከመሥራት ይልቅ ለምን የነባር አርቲስቶችን ሙዚቃዎች በድጋሚ ለማቀንቀን እንደመረጠና ዓላማውንም ሲያስረዳ፤ “ትውልድ የራሱን ቀለም አስቀምጦ ማለፍ አለበት ብዬ አምናለሁ፡፡ ሌላውም እንዲሁ እንዲያደርግ እመክራለሁ፡፡ የዘመን ቃናዎች ቀደምት አርቲስቶችን የማክበር መንገድ--- መድረክ  መፍጠር ነው ዓላማው፡፡” ብሏል፡፡
የራሱንም ሙሉ አልበም ሰርቶ በማጠናቀቅ ላይ እንደሆነ የጠቆመው ድምጻዊው፤ በቅርቡ ለአድማጭ ጆሮ እንደሚደርስም በይፋ ቃል ገብቷል፡፡
አንጋፋው የሙዚቃ ሰው አበጋዝ ክብረወርቅ ሺዎታ የሙዚቃዎቹን ዳግም ማቀናበር አስመልክቶ ሲናገር፤ “እነዚህን ሥራዎች የተቀበልኩበት ምክንያት ከዚህ ቀደም የአስቴር አወቀንና የጥላሁን ገሰሰን ሥራዎች ተቀብዬ በድጋሚ ስለሰራሁ ነው፡፡ ሦስቱም ዳዊት ፅጌ የተጫወታቸው ሙዚቃዎች መሰረታዊው ጉዳይ ሳይነካ ወይም ሳይለወጥ ነው በድጋሚ የተቀናበረው፤ እኔ ብዙ የጨመርኩት ነገር የለም” ብሏል - ትህትና በተጫነው ድምፀት፡፡
በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ ከታደሙት ብዙዎቹ ግን በዚህ ትህትና በእጅጉ በተጫነው አስተያየቱ ጨርሶ አይስማሙም፡፡ ለዚህ ደግሞ በመግለጫው መጨረሻ ላይ ታዳሚው የተጋበዘውን ዳግም የተቀነቀነና የተቀናበረ ሥራ ይጠቅሳሉ፡፡ ልዩነቱ በግልጽ የሚታይ ነው ይላሉ - አስተያየት ሰጪዎች፡፡
የሙዚቃ ቪዲዮዎቹ የተቀረፁት ከትላንት በስቲያ ጋዜጣዊ መግለጫው በተሰጠበት በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ራስ መኮንን አዳራሽ መሆኑም ተጠቁሟል፡፡ ይሄ ደግሞ ግጥምጥሞሽ ሳይሆን በዕቅድ ታስቦበትና ታልሞበት የተከወነ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ከሰሩ አይቀር እንዲህ ነው - ጥንቅቅ አድርጎ፡፡
የመድረኩ አጋፋሪ አርቲስት ግሩም ዘነበ በበኩሉ፤ የዘመን ቃናዎች ፩ የተሰራበትን ምክንያት  ሲያብራራ፤ ከዚህ ቀደም የነበሩ አርቲስቶች ለኢትዮጵያ ሙዚቃ ለከፈሉት መስዋዕትነት ዋጋ ለመስጠትና ለማክበር የተሰራ የሙዚቃ ስብስብ መሆኑን በአፅንኦት የገለፀ ሲሆን፤ ሌላው ምክንያት ደግሞ እነዚህን ሙዚቃዎች ሌላ ከፍታ በመጨመር አቀናብሮ ለዘመኑ  ጆሮ በሚጣጣም መልኩ ለአድማጭ ለማቅረብ ነውም ብሏል፡፡
የዘመን ቃናዎች ቀጣይ ክፍሎች ወደፊትም እንደሚወጡ በመግለጫው ላይ የተጠቆመ ሲሆን፤ ድምፃዊ ዳዊት ፅጌ በዚህ ጉዳይ ላይ በሰነዘረው አስተያየት፤ “ቀጣዮቹን ክፍሎች እኔም ላልጫወታቸው እችላለሁ፤ ግን ብዙ ሥራዎች አሉ፤ በቀጣይ  የሚወጡ፡፡” ሲል ጠቁሟል፡፡
“የዘመን ቃናዎች ፩” የሙዚቃ ቪዲዮዎች የህግና የሞራል ግዴታዎችን በአግባቡ ተወጥተው መሰራታቸውም በመግለጫው ላይ ተደጋግሞ ተጠቅሷል፡፡ ተወዳጁ ድምፃዊ ዳዊት ፅጌ በጋዜጣዊ መግለጫው መደምደሚያ ላይ ለአርቲስቶቹ ቤተሰቦች በሙሉ ምስጋናውን አቅርቧል፡፡ “የእናንተ ፈቃድ ባይኖር ኖሮ ሙዚቃዎቹን መሥራት አንችልም ነበር” ብሏል - ዳዊት ፅጌ፡፡


ድምፃዊው በሙዚቃ ስራዎቹ ላይ ለተሳተፉት ባለሙያዎችም ምስጋናውን ከመድረክ አቅርቧል - በይፋ፡


የጋዜጣዊ መግለጫውን ኹነት ያዘጋጀው የተለያዩ ኤቨንቶችን በማዘጋጀትና በመምራት የሚታወቀው አንጋፋው የህትመትና ማስታወቂያ ድርጅት ኢምር አድቨርታይዚንግ እንደሆነ ለማወቅ ተችሏል፡፡

Sunday, 04 February 2024 00:00

ሦስት መዓዘን

ምዕራፍ 1
-ኪሩቤል ሳሙኤል -
የሚተነፍሰው ትንፋሽ ከዛፎቹ ቅጠሎች ጋር እየተጋጨ ደግሞ ደጋግሞ ይሰማዋል፡፡ ትንፋሹ ከአፍንጫው ሲወጣ ጥሎት ላይመለስ እየኮበለለ ነው የሚመስለው፡፡ በጣም ደክሞታል፡፡ ወደ የት እየሄደ እንደሆነ የሚያውቀው ታሪክ የለም፡፡ በዚህ ጥቅጥቅ ያለ ጫካ ውስጥ የሚተነፍስና የሰው ፍጥረት የሆነው እሱ ብቻ ነው፡፡ እህል ባልጎበኘው ሆዱ ለግማሽ ቀን ያህል ነው በነዚህ ዛፎች መካከል መልስ ፍለጋ ሲኳትን የከረመው፡፡ ሆኖም ሁሉም ነገሮች ምንምን ብቻ ነው እያስረዱት ያሉት፡፡
ድንገት…
ካለበት አካባቢ በቅርብ ርቀት ድንገት አንድ ድምፅ ሰማ፡፡ የተቻለው ድረስ ድምፁን ወደ ሰማበት ቦታ በሀይል እየተራመደ ተመለከተ፤ ምንም ነገር የለም፡፡ አሁንም ሳያቋርጥ መራመዱን ቀጠለበት፡፡
በመንገዱም ላይ እያለ ያለምንም ተስፋ የፈጠረውን ፈጣሪውን በህሊናው ውስጥ ቅርፅ አበጅቶለት፣ ሊፀልይለትና አንዳች ተዓምር እንዲሰራለት ሊለምነው ተመኘ፤ ሆኖም ምኞቱ ሙሉ አልነበረም፡፡ ምኞቱ ውስጥ እውቀት የለበትም፣ ሀሳብ የለበትም፤ ስሜት የለበትም፡፡ ድካምን ለመካድ ከሚደረግ የአዕምሮ ውስጥ ጨዋታ ውጭ ይህ ሰው አላማ ብሎ ሊያስቀምጠው የሚችለው የህይወት ስርዓት አብሮት የለም፡፡ ብቻውን ነው፡፡
ሆኖም ይህ የተዘበራረቀ ስሜት ብዙም ሳይቆይ ሰብሳቢ የህይወት ገጠመኝ ይዞለት መጣ፡፡ ከርቀት አንዲት ደሳሳ ቤት ከወደ ፊቷ አጎንብሳ በዛፎች መካከል ተሰፍታ ተመለከተ፡፡ ማመን አቃተው፡፡ እንደምንም እየተንደረደረ ሄዶ የቤቱ በር ጋር ቆመ፡፡ ምን ማድረግ እንዳለበት ግራ ገባው፡፡ ዝም ብሎ እንዳይገባ እሱ ራሱ ያልተረዳው ህግ መጥቶ ድፍረቱ ላይ ተከመረበት፡፡ እዛው በሩ ላይ ተገትሮ አንድ እሱን የመሰለ ፍጥረት ከቤቱ ውስጥ እስኪወጣ ድረስ ቆሞ እንዳይጠብቅ፣ በምንም አይነት ታሪክ ትዕግስት መስጠት የማይችለው ረሀብ በሆዱ ውስጥ የአመፃ ድምፁን እያስተጋባበት ነበር፡፡ ህይወት በሁለት የተስፋ ገመዶች ተወጥራ ይህን ሰው የተምታታ ምስሎችን ብቻ በጭንቅላቱ እንዲፈለፍል እያስገደዱት ነው፡፡
አልቻለም፡፡ ረሀቡን አልቻለውም፡፡ ወደቤቱ ተጠግቶ የጨለማ ጥቀርሻ የተቀባውን የቆርቆሮ በር ዘመም አድርጎ ከፈተው፡፡ ቅጥሩ የተጣሰበት ይመስል በቤቱ ውስጥ ተደብቆ ተቀምጦ የነበረው የጨለማ ፀዳል ሲረበሽ ታወቀው፡፡ ካጠገቡ የመብራት ማብሪያና ማጥፊያ አግኝቶ መብራቱን ተጫነው፡፡ ክፍሉ ላይ ብርሀን ሰለጠነበት፡፡ የብርሀኑ ሰበብ የሆነው አምፖል ግን የት ጋ እንዳለ ለማየት አልቻለም፡፡
ክፍሉ ባዶ አይደለም፡፡ በውስጡ አንድ በላዩ ላይ በሸረሪት ድር ተጀቡኖ የመጻሕፍት ክምር ያለበት ጠረጴዛ፣  የእንጨት ወንበር፣ በግድግዳው ላይ የተለያዩ የተለጣጠፉ ፎቶዎች፣ በፎቶዎቹ ላይ የአቧራ ቂጣ ተለጥፎባቸው፣ ከቤቱ ሰጎጥ ስር ደግሞ አንድ ተለቅ ያለ በእንጨት የተበጀ ሳጥን ይዟል፡፡
ይህ ሰው በቅድሚያ ትኩረቱን የት ላይ ማድረግ እንዳለበት በቆመበት ትንሽ ካሰላሰለ በኋላ በቅድሚያ በግድግዳው ላይ ወዳለው የፎቶግራፎች ሰልፍ ጋር ሄዶ ቆመ፡፡ በላያቸው ላይ ያለውን ቆሻሻ በእጁ ካፀዳ በኋላ በተቻለው ጥረት አጥርቶ ለመመልከት ቀረብ ብሎ መመልከት ጀመረ፡፡ በመጀመሪያ የተገናኘው ከራሱ ፎቶ ጋር ነው፡፡ ግራ ገባው፡፡ እንዴት ሆኖ የእሱ ፎቶ እዚህ ለምድር የተሰወረ ደሳሳ ጎጆ ውስጥ ሊገኝ እንደቻለ ማመን አቃተው፡፡ በፍጥነት ሌሎች ፎቶዎችን እያፀዳ መመልከት ውስጥ ገባ…የራሱ ብዙ ፎቶዎች፣ ከአንዲት ሴት ጋርና አብሯቸው ደግሞ አንድ ወንድ ህፃን ልጅ ይዘው፣ በሌላ ቦታም የራሱ ፎቶ የወታደር ልብስ ለብሶ ከሌላ ሴት ጋር የተነሳው፣ በሌላ ቦታ መጀመሪያ ያየው ህፃን ልጅ አደግ ብሎ ብቻቸውን የተነሱት ፎቶና በከፊልም ቢሆን ከዚህ ቀደም ያለው ህይወቱን የሚናገርበት የፎቶ ክምር ተመልክቶ ነፍሱ ደርቃ ቀረች፡፡
ብዙ ነገር ተረጋግቶ ማሰብ ይችል ነበር፡፡ ሆኖም አሁንም ሊመለከታቸው የሚገቡ የቤት እቃዎች ባሉበት ሆነው እየጠበቁት እንደሆነ ሲረዳ፣ፊቱን አዙሮ መጻሕፍቶቹ ላይ ትኩረቱን አደረገ፡፡ በመጻሕፍቱ ላይ ያለውን የሸሪት ድር አንስቶ መመልከት ውስጥ ገባ፡፡ አብዛኞቹ በእጅ ፅሁፍ የተፃፉ ድርሳናት ይታያሉ፡፡ ከዛም ባለፈ የብራና ጥቅሎችም አልፎ አልፎ ይታያሉ፡፡
ድርሳናቱንና ጥቅሎቹን ለማንበብ ጊዜ አልሰጠም፡፡ ዞሮ ወደ እንጨት ሳጥኑ ቀርቦ ለመክፈት ሙከራ አደረገ፡፡ ሳጥኑ ተለቅ ባለ ቁልፍ የተከረቸመ ነው፡፡ አሁኑኑ ሳጥኑን ከፍቶ ማየት እንዳለበት ተገነዘበ፡፡ ጎጆውን ለቆ ወጥቶ ጋኑን የሚሰብርበትን ድንጋይ ማፈላለግ ጀመረ፡፡ ፍለጋ ላይም እያለ ጥቃቅን በትውስታ ውስጥ የሚንፀባረቁ ምስሎች ያለ እሱ ፈቃድ ድንገት እየመጡ ብልጭ ድርግም ይሉበታል፡፡
ከግድግዳው ላይ ተለጥፎ ያየው ህፃን ልጅ መልክ ድንገት ብልጭ ብሎ ይታየዋል…አብሮት ሲስቅ…አብሮት ሲሮጥ…አብሮት ከሶፋ ላይ ተጋድመው መፅሐፍ ሲያነብለት….እነዚህ ሶስት ምስሎች ልክ እንደ ልብስ መስፊያ የሲንጀር ባህሪይ እየተመላለሱ ጭንቅላቱን ይተከትኩት ጀመር፡፡ ሆኖም ምንም ሊያደርገው የሚችለው ትዝታ አይደለም፡፡ የራሱ ልጅ ይሁን የሌላ የሚያውቀው እውቀት ባዶ ነው፡፡ ሆኖም ከጭንቅላቱ ስውር ስፍራ ውስጥ አስቀምጦት እንደነበር ግን መጠርጠር ውስጥ ገብቷል፡፡
ተለቅ ያለ ድንጋይ አጋጠመው፡፡
በፍጥነት ወደ ሳጥኑ ጎጆው አመራ፡፡ በጎጆው ውስጥ ሰርጎ በጋኑ ላይ ድንጋዩን ያመላልስበት ጀመር፡፡ በሳጥኑ ውስጥ ምግብ ቢያገኝ በወደደ ነበር፡፡ የራበው ሰው የሚያደምጠው በጆሮው ነው እንዲል ካልሂል ጅብራን፣ ይህም ሰው ቀስ እያለ እያጨለመው ያለውን ድካሙን የሚያሸንፍበትን መሳሪያ ብቻ ነው የሚፈልገው፡፡ ምግብ፡፡
ከብዙ ድብደባ በኋላ ጋኑ እጅ ሰጥቶ ተከፈተ፡፡ ቀስ ብሎ ከፈተው፡፡ ባየው ነገር በጣም ደንግጦ በፍጥነት ወደ ኋላው አፈገፈገ፡፡ ክፍሉ እጅግ ነፍስን በሚያጎመዝዝ ሽታ ታወደ፡፡ ደንግጦ ለጥቂት ደቂቃዎች ከወደቀበት ሆኖ በሳጥኑ ላይ ሲያፈጥበት ከቆየ በኋላ፣ያየው ነገር እውነት መሆኑን ለማረጋገጥ በቀስታ መልሶ ተጠጋው፡፡ ደግሞም ሲመለከተው ነገርየው ራሱ ነው፡፡
ነገርየው… በሳጥኑ ውስጥ እየተመለከተው ያለው  ራሱን ነው፤ ራቁቱን እጥፍጥፍ ብሎ ተኝቶ በመበስበስ ላይ ያለውን የራሱን አስክሬን ነው ያየው….
      

"ኤልዛቤል?"
ጥያቄው ከእንቅልፏ አባነናት፡፡
"አቤት…"
"የምጠይቅሽን ጥያቄ በጥንቃቄ ለመመለስ ሞክሪ? አለበለዚያ ለሚደርስብሽ ስቃይ ተጠያቂ ማንንም እንዳታደርጊ፡፡ ሁሉም ውሳኔ ያንቺ ነው፡፡ ተግባባን?"
"አዎ…" አለች ኤልዛቤል፤ በጨርቅ የተሸፈኑት አይኖቿ ላይ የእንባ ድፍድፍ እያመረተች፡፡
"ስንት ሆናችሁ ነው ወደዚህ ቦታ የመጣችሁት?"
"አልገባኝም…እኛ እነማን ነን? "
ይህን እንደተናገረች ድንገት አንዳች የኤሌክትሪክ ንዝረት ሰውነቷን አነዘረው፡፡ በሀይል ጮኸች፡፡ አለቀሰች፡፡ ጠያቂው በተረጋጋ መንፈስ ጥያቄውን ቀጠለ፡፡
"ስንት ሆናችሁ ነው የመጣችሁት?"
ኤልዛቤል ትንፋሽ ሰብስባ ለማሰብ ሞከረች፡፡ እነዚህ ሰዎች ያለምንም ርህራሄ እያሰቃዩዋት እንደሚሰነብቱ እንዲሁ ገባት፡፡ እያሰቃያት ያለው ሰው ስለ ማን እና ስለ ምን እየጠየቃት እንደሆነ ልታውቅ አልቻለችም፡፡ አሁን ላይ ሆና ተረጋግታ አስባ ልትደርስበት የሚቻላት ታሪክ ከኋላዋ ሊታያት አይችልም፡፡ ማምለጥ ብቻ እንዳለባት ነው ህሊናዋ እየደጋገመ እየነገራት ያለው፡፡ ይህን እያሰበች ያለችበት ወቅት ላይ ድንገት የኤሌክትሪኩ ንዝረት መጥቶ አንድ ጊዜ በሀይል አስጮሀት፡፡
"እሺ ታገሰኝ…" አለችው ንዴትና እልህ በተቀላቀለበት አንደበት፡፡
"ስንት ሆናችሁ ነው የመጣችሁት?" ጠያቂው ድምፅ ላይ መጠነኛ የድል አድራጊነት ስሜት ይደመጥበት ጀምሯል፡፡
"አራት ነን…" መለሰች ኤልዛቤል፡፡
"ለምንድን ነው የመጣችሁት? አላማችሁ ምን ነበር?"
"መረጃ ይዞ ለመውጣት ብቻ ነው የመጣነው፡፡" ኤልዛቤል በጥንቃቄ ጥያቄዎቹን ማድመጥ እንዳለባት እየገባት ነው፡፡ ጥያቄው እስካለ ድረስ መልስ ስፍራዋን ፈልጋ መክተሟ ግድ ነው፡፡
"ምን አይነት መረጃ ነው መሰብሰብ የፈለጋችሁት?"
"የማህበራችሁን አጠቃላይ አላማ…ከተቻለ ሙሉ ማኒፌስቶዋችሁን ይዘን ለመውጣት ነው የተላክነው፡፡"
ድንገት ፀጥታ ሰፈነ፡፡ በድን ዝምታ ውስጥ ሆና ኤልዛቤል የጠያቂዋን ትንፋሽ ለማድመጥ ሞከረች፡፡ ጠያቂው በፍጥነት በመተንፈስ ላይ ነው፡፡ ትልቅ ሀላፊነት ይዞ ወደ እሷ እንደመጣ ገባት፡፡ የሚፈልገውን መረጃ ካላገኘ አለቃው በሰላም እንደማይቀበለው አውቃለች፡፡ ስለዚህ ከራሷ ውጭ የዚህንም ሰው ህይወት መታደግ እንዳለባት ነው እየገባት ያለው፡፡ ፍርሀቱን መጠቀም እንዳለባት ገባት፣ ስጋቱ ድረስ ሄዳ የልቡን አድምጣለት ከአለቃው ይልቅ እሷ ደህነቱ ሆና የመገኘት ሀላፊነት አለባት፡፡ በዛ ውስጥ ነው መዳን የምትችለው፡፡ በንቃት ውስጥ ሆና የጠያቂውን ቃላት መጠበቅ ጀመረች፡፡
"እንዴት እንደተያዥስ ታስታውሻለሽ?"
"ምንም አይነት ትውስታ የለኝም፡፡ ሰውነቴ በጣም ደክሟል፡፡ በትክክል ላስብ አልችልም፡፡ በዚህ ስቃይ ውስጥ ማንስ ትላንቱን ማስታወስ ይችላል፡፡ እንደምታየኝ ነኝ፡፡ አቅም የለኝም፡፡ እንደፈለክ ብታደርገኝ ራሴን የምከላከልበት መንገድ የለም…እንደፈለክ ልታደርገኝ ትችላለህ…እሱን ደግሞ ጠንቅቀህ ታውቀዋለህ፡፡ እንደፈለክ…."
ይህን ተናግራ ፀጥ አለች፡፡ የልብ ትርታው ጋር የነፍሷን ጆሮዎች ላከቻቸው፡፡ በሀይል እየደለቁ ናቸው፡፡ ምራቁን ሲውጥ እያንዳንዱን የጉሮሮውን ክርክር በማድመጥ ደረሰችበት፡፡ "እንደፈለክ ማድረግ ትችላለህ…" እያለች ደጋግማ ቃላቶቹን የተጠቀመችው የወሲብ ከፍታውን ለማናር ብቻ ነበር፡፡ ለዚህ ሰው ጉልበትና ወንድነቱን ሰጥታዋለች፡፡ ከዚህች ደቂቃ አንስቶ እስረኛው ሳትሆን የወሲብ መገልገያ ቁሱ እንደሆነች አድርጎ ማሰብ እንደሚጀምር ታውቃለች፡፡ አውቃ ነው ይህን ያደረገችው፡፡ ጠያቂው ጉሮሮውን ጠራርጎ ጠየቃት…
"እስካሁን ለምን እንዳልተገደልሽ ታውቂያለሽ?"
"አዎ…በምሰራበት የስለላ ድርጅት ውስጥ ቁልፍ ሰው ከሚባሉት ሰዎች ውስጥ ስለሆንኩ፣ የእውቀት ስፋቴ ከየትኛውም የድርጅታችን ሰራተኞች በላይ ከፍ ስለሚያደርገኝ እና ተፈላጊ ስላደረገኝ፣ ቆንጆ ስለሆንኩ፣ ያየኝ በሙሉ ስለሚመኘኝ….ለዛ ይመስለኛል ሞት ወዳጆቼን መቀማት ችሎ የኔ ደጅ ጋር መድረስ ያቃተው፣ የሚወዱኝም የሚጠሉኝም በእኩል አይን ነው የሚያዩኝ…ሁሉም የሚወዱኝ የሚያከብሩኝ ሰው ነኝ፡፡ ያልሞትኩት ኤልዛቤል ስለሆንኩ ነው፡፡"
 ያ ፀጥታ ተመልሶ መጣ፡፡ የጠያቂው ነፍስ ጋር ቀረብ ብላ ልታደምጥ ሞከረች፡፡ ትንፋሹ በሀይል ጨምሯል፡፡ መረቧ ውስጥ እያስገባችው እንደሆነ እየተረዳች ነው፡፡ ጊዜ ማባከን አልፈለገችም፡፡
"ይቅርታ…እኔን ከመግደልህ በፊት አንድ ጥያቄ ብቻ ልጠይቅህ?"
ጠያቂው ጥቂት ካንገራገረ በኋላ ፈቀደላት፡፡
"ትኩር ብለህ ስታየኝ አምራለሁ? ሌሎች ሰዎች ታምሪያለሽ እያሉ ያቆዩኝ ዘመኔን ከመርገሜ በፊት ይሄን ብቻ መልስልኝ….አምራለሁ…?"
ጠያቂው በቀስታ ሲጠጋት ተሰማት፡፡ ወደ ፊቷ እየተጠጋ መሆኑን ከርቀት እየጋለ በሚመጣው እስትንፋሹ ገባት፡፡ አንገቷ ስር ገብቶ ሲተነፍስ ተሰማት፡፡ ጊዜ ማባከን አልፈለገችም፤ አንገቷን በሀይል ወደ ጎን ስባ በሀይል መንጋጋው ስር በጭንቅላቷ አጎነችው፡፡ እዛው ታፋዋ ስር ወደቀላት፡፡
ኤልዛቤል…
ለመኖር ያላት እድል በደቂቃዎች ውስጥ እንደሚወሰን ደርሳበታለች፡፡
ነፃነቷ ታፋዋ ላይ ተጋድሞ እየጠበቃት ነው፡፡
                                     
የዘካሪያስ አይኖች ተገለጡ፡፡ አለመሞቱን ያወቀው ያኔ ነው፡፡ ተበሳጨ፡፡ እንዴት አድርጎ እንደዳነ ለማስታወስ ጊዜ አላገኘም፡፡ የአንዲት ሴት ድምፅ ሊሰደድ ያለው ሀሳቡን ስባ አሁኑ ላይ መለሰበት፡፡
"ወንድም ዘካሪያስ ….እንኳን ወደ ሰው ልጆች መንደር በሰላም ተመለስክ?"
የልጅቷን መልክ ለማየት ሲዞር አንገቱ ላይ የተሰማው ህመም አላዞር አለው፡፡ ልጅቱ ይህን ተመልክታ አጠገቡ መጥታ ቆመች፡፡ ዘካሪያስ አተኩሮ ተመለከታት፡፡ ያውቃታል፡፡ አዘውትሮ ቡናውን የሚጠጣበት ካፌ ውስጥ አስተናጋጅ ሆና ያውቃታል፡፡
"አስታወስከኝ?" አለችው ስስ ፈገግታ ለአይኑ እየሰጠችው፡፡
"አውቅሻለሁ…የት ነኝ ያለሁት?"
"ለጊዜው ምንም አይነት እውቀት ባልሰጥህ ደስ ይለኛል፡፡"
"ለምን አዳንሺኝ…ማነሽ አንቺ?"
"ራስህን ነው ያዳንከው ወንድም ዘካሪያስ፡፡ እኔ ምንም ያደረኩልህ ነገር የለም፡፡ ለማንኛውም አሁን ላይ በጣም የምትፈለግ ሰው ነህ፡፡ በኔም ሆነ በብዙዎች፡፡ በጣም የሚያስቅህ ነገር ምን ልሁን ብዬ እንደሆነ እንጃ በሁለት የተለያዩ ግለሰቦች ነው ተቀጥሬ ስከታተልህ የከረምኩት፡፡ አሁን ግን ግራ የገባኝ ለየትኛቸው አሳልፌ ልስጥህ የሚለው ሀሳብ ነው፡፡ እ….ምን ይሻላል ትላለህ?"
ዘካሪያስ በፍርሀት ነው እያያት ያለው፡፡ በመሰረታዊነት ለአመታት እያፈላለገው ያለ ሰው እንዳለ ያውቃል፡፡ ሆኖም ስለ ሁለተኛው ሰው ደግሞ የሚያውቀው ነገር የለም፡፡
"ስለ ምን እያወራሽ እንደሆነ ላውቅ አልቻልኩም፡፡ እኔ ሰላማዊ ሰው ነኝ፡፡ በማንም ላይ ጉዳት አድርሼ አላውቅም፡፡ እስከዛሬም ባለው ህይወቴ አንድም ጠላት ተነስቶብኝ አያውቅም…."
የለበጣ ሳቅ እየሳቀች አጠገቡ ተጠግታው ተቀመጠች፡፡
"እርግጠኛ ነህ ዘኪ? የምሬን ነው… ስለምታወራው ነገር በጣም እርግጠኛ መሆን አለብህ፡፡ ይሄን ያልኩህ ዋነኛው ምክንያት፣ አንተን አስሼ እንዳገኝህ የሚፈልጉ ሰዎች ከለመድኩት ወጣ ባለ ከፍተኛ ገንዘብ ነው የተደራደሩኝ፡፡ እና ሳሰላስለው ይሄ ሰው ማን ቢሆን ነው በዚህን ያህል ደረጃ እየተፈለገ ያለው ብዬ ነገሮችን እንድመረምር ሆንኩኝ፡፡
ከዛም ስላንተ ማጥናት ጀመርኩኝ፡፡ በጥንታዊ የአስማት ጥበቦች ላይ እውቀት ያለህ ሰው እንደሆንክ፣ ሚስትህ እንደሞተችብህ፣ አሁን ላይ የት እንዳለች የማታውቃት አንዲት ሴት ልጅ እንዳለችህ፣ የልቤ የምትላቸውጓደኞች እንደሌሉህ፣ ያላሳተምከው ሚስጥረ ራዛኤል የሚል መፅሐፍ እንደፃፍክ፣ ከዛም ባለፈ ማንም እጅ ላይ የሌለ… የመላው ሁለንታን ሚስጥር የሚያትት…ከምድር ሆድ እቃ ውስጥ ያሉትን ማዕድናት አስሶ የሚጠቁም የብራና ጥቅል ለብቻህ ደብቀህ እንደምትኖር እና አሁን ላይ የማልገልፅልህን የህይወትህን ክፍል በደንብ አድርጌ ደረስኩበት፡፡ "
"እና ምን ውሳኔ ላይ ደረሽ?" ዘካሪያስ ረጋ ብሎ ጠየቃት፡፡
"ማን እያሳደደህ እንደሆነ እንደምታውቅ አውቃለሁ፡፡ ማወቅ የምፈልገው ግን ለምን የምትለዋን ነው፡፡ ለምንድን ነው የሚፈልጉህ…? በዚህ ሀሳብ ላይ ያንተን እውቀት ሳትዋሽ ከነገርከኝ ነፃነትህን ምናልባት ልሰጥህ እችላለሁ፡፡"
የዚያን ሰዓት ላይ ነው ዘካርያስ ከተኛበት አልጋ ጋር የጥፍንግ እንደታሰረ የተረዳው፡፡
"የምፈለገው ለእውቀቴ ነው፡፡ በሰው ልጅ አይን ታይቶ የማይተረጎም እውቀትን ከነፍሴ ከትቤ በሚስጥራዊው እውቀት ውስጥ የምመላለስ ሰው ነኝ፡፡ ህይወቴ ሚስጥር ነው፡፡ እውቀቴ ሚስጥር ነው፡፡ እምነቴ ሚስጥር ነው፡፡ እዚህ እሳቤ ድረስ እንዳስብ ያደረገኝም ሀሳብ በራሱ ሚስጥር ነው፡፡ ምንም ልነግርሽ የምችለው እውነት የለም፡፡ ለማንም አሳልፈሽ ብትሰጪኝ መልሴ ተመሳሳይ ነው፡፡ የልቤን ተረድቶ መልስ ወደሚያሻኝ ስፍራ የሚሰደኝ ሞት ነበር …እሱንም አንቺ ቀድመሽ ቀማሺኝ፡፡  ከቻልሽ መልሰሽ ግደይኝ? አሁን በጭንቅላቴ ውስጥ የከመርኩት እውቀት እያሰቃየ እንደበረዶ አሟሙቶ በስቃይ ሳይጨርሰኝ በፊት አንቺው ግደይኝ?
”ራሱን ሊገድል ከሚሻ ልብ ውስጥ ምንም አይነት ተስፋ አትፈልጊ፡፡ የምታስፈራሪኝ እየመሰለሽ ከሆነ ደግመሽ ማሰብ ይጠበቅብሻል፡፡ ብለምንሽ …ውለታ ብጠይቅሽ፣ የምጠይቅሽ አንድ ነገርን ብቻ ነው፡፡ ግደይኝ እና እኔንም ሆነ ይህችን ምስኪን ሀገር ታደጊያት፡፡ "
ልጅቷ አሁንም ፈገግ ብላ ስታየው ከቆየች በኋላ ከተቀመጠችበት አልጋ ላይ ተነስታ በጠረጴዛ ላይ ያስቀመጠችውን ስልክ አንስታ የዘካርያስን አይኖች በጥናት እያየች ደወለች፡፡ ስልኩ ተነሳ፡፡
"መምጣት ትችላላችሁ--" ይህን ተናግራ ከዘካሪያስ አይኖች ተሰወረች፡፡

የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የባህል ማዕከል በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ የሁሉም ዩኒቨርስቲዎች ባህል ማዕከላት የሚሳተፉበትና የፊታችን ሰኞ ጥር 27 ቀን 2016 ዓ.ም የሚከፈት አገራዊ ፌስቲቫል ማዘጋጀቱ ተገለፀ፡፡
ፌስቲቫሉ ለተከታታይ ሦስት ቀናት  የሚቆይ ሲሆን፤ መክፈቻው ሰኞ ከአመሻሹ 11 ሰዓት እስከ ምሽቱ 2 ሰዓት ድረስ በዩኒቨርስቲው የፋውንቴይን መናፈሻ አውድ ፊት ለፊት ለዚሁ ዓላማ ታስቦ በተዘጋጀ መድረክ ላይ በልዩ ልዩ ዝግጅቶች እንደደመቀ የሚቆይ ነው ተብሏል፡፡
 “ከዚህ በኋላም ዩኒቨርስቲዎች በየተራ ሃላፊነት ወስደው የሚያዘጋጁት ክብረ-በዓል ሆኖ ይቀጥላል፡፡ በሂደትም ምስራቅ አፍሪካን፣ አፍሪካን፣ ሌሎች አህጉራትን… ደረጃ በደረጃ እያካተተ በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚከበር “ኢንተርናሽናል ፌስቲቫል” እንዲሆን ለማስቻል ታቅዷል” ብሏል፤ የባህል ማዕከሉ ከትላንት በስቲያ ሃሙስ ባሰራጨው መግለጫ፡፡
“ይህ ሲሆን የአገራችን ዓይነተ- ብዙ ባህላዊ እሴቶች፣ ኪነጥበባዊና ሥነጥበባዊ የፈጠራ ውጤቶች፣ ብሎም ደግሞ አገራዊ የቱሪስት መስህቦች በማስተዋወቅ ረገድ የሚጫወታቸው የገፅታ ግንባታ ሚናዎች በዓይነትም፣ በይዘትም፣ በቅርፅም እጅግ በርካታ እንደሚሆኑ ይታመናል” ብሏል የባህል ማዕከሉ፡፡
የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የባህል ማእከል በኢትዮጵያ ዩኒቨርስቲዎች ታሪክ አንጋፋውና ግንባር ቀደሙ እንደመሆኑ መጠን፣ አገራዊ ሃላፊነቱም የዚያኑ ያህል እጅግ በጣም ከባድ እንደሆነ እናምናለን ያለው ማእከሉ፤ ይህንኑ እምነታችንን መሰረት በማድረግም የሁሉንም ዩኒቨርስቲዎች የባህል ማዕከል ያቀናጀ “አገር - አቀፍ የዩኒቨርስቲዎች ባህል ማዕከላት ጥምረት”ን ለመመስረት የሚያስችለውን የፈር - ቀዳጅነት ሚና ሲጫወት ቆይቷል ብሏል፡፡
“በውጤቱም እነሆ ዛሬ በዓይነቱም ሆነ በግብሩ የመጀመሪያ በሆነው ታላቅ አገራዊ ፌስቲቫል ላይ በአንድነት ለመታደም ጫፍ ላይ ደርሰናል” ብሏል ማዕከሉ በመግለጫው፡፡



የካቲት
ወይ ስትገባ
ወይ ስትወጣ
ባታንጎዳጉድ፤ መሬት ትጨነቅ ነበር!
የአንድ ንጉሥ አገር በጣም ሥቃይና ዕንባ በዛበት፡፡ ይኸውም በአንድ ሰብል በሚያጠፋና ሰው በሚገድል አውሬ ምክንያት ነበር፡፡ ንጉሡ መላ ፍለጋ ብዙ አውጥተው አውርደው ሲያበቁ፤ በመጨረሻ “ይህን አውሬ ገድሎ ወይም እስከ ህይወቱ አጥምዶ አገሬን ከሥቃይ ላወጣ ሰው ከፍተኛ ሽልማት እሰጣለሁ” አሉ፡፡ ሆኖም አውሬው እጅግ ግዙፍ በመሆኑ ሰው ሁሉ ወደ ጫካው መሄድ ፈራ፡፡ ንጉሡ የበለጠ ህዝቡን ለማበረታታት ብለው ከሽልማቱ በተጨማሪ ሴት ልጃቸውን እንደሚድሩለት አሳወቀ፡፡
በዚያ አገር የሚኖሩ የአንድ ደሀ ሰው ሁለት ወንዶች ልጆች ነበሩ፡፡ መጥተው ለንጉሡ አውሬውን እንደሚገድሉ ተናገሩ፡፡ ታላቅዬው ብልጥና ጉልበተኛ ሲሆን የሚመራው በምኞት ነበር፡፡ ታናሽዬው ደግሞ ሁሉ ነገሩ የዋህና ገር ነበረና በልበ-ቀናነቱ ብቻ ይመራ ነበር፡፡ ንጉሡ፤
“እንግዲህ አውሬውን ለማግኘታችሁ እርግጠኛ እንድንሆን ወደ ጫካው ከሁለት አቅጣጫ ግቡ” አሉ፡፡ በዚህ መሰረት ታላቅዬው በምዕራብ በኩል ገባ፡፡ ታናሽዬው ደግሞ በምሥራቅ፡፡
ታናሽዬው ትንሽ  መንገድ እንደሄደ አንድ ጥቁር ጦር የያዘ አጭር ሰው ድንገት ከጫካው ብቅ ብሎ፤
“እንካ ይሄንን ጦር ያዝ፡፡ ምክንያቱም ልብህ ንፁህ ነው፡፡ በዚህ ጦር አውሬውን ሳትፈራ ልትወጋው ትችላለህ፡፡ ምንም ጉዳት አያደርስብህም አይዞህ” አለና ሰጠው፡፡
ታናሽ ወንድም የተሰጠውን ጦር አንግቦ አመስግኖ መንገዱን ቀጠለ፡፡ ልበ - ሙሉ ሆነ፡፡ ጥቂትም ሳይጓዝ አውሬው ብቅ አለ፡፡ ገና ጦሩን ወድሮ እንደቆመ አመለኛው አውሬ ከፍርሃት በመነጨ ጭካኔ የዕውር የድንብሩን መጥቶ ጦሩ ላይ ተንደርድሮ ተሰካበት፡፡ ጦሩ ልቡ ላይ ተሰካና ሁለት ላይ ከፈለው፡፡ ታናሽ ወንድም የአውሬውን ሬሣ ተሸክሞ ለንጉሡ ሊያስረክብ መንገዱን ቀጠለ፡፡
በአንፃሩ ታላቅ ወንድሙ በሄደበት በተቃራኒው አቅጣጫ ሰዎች ሁሉ የሚዝናኑበት አንድ መሸታ ቤት አለ፡፡ ታላቅ ወንድም እዚህ መሸታ ቤት ሊገባ አሰበና “አውሬው እንደሆነ ከዚህ ጫካ ወጥቶ አይሄድም፡፡ ለምን ለድፍረት እንዲሆነኝ ጥቂት እህል ውሃ አልልም?” ብሎ ገባና ጥቂት መጠጥ ጠጣ፡፡
ከመሸታ ቤቱ ሲወጣ ታናሽ ወንድሙ አውሬውን ተሸክሞ ሲመጣ አየው፡፡ እቡይና እኩይ ልቡ ሸር አሳሰበውና፤
“ና ወንድም ዓለም አረፍ በልና ወይን ጠጣ” አለው፡፡ ምንም ተንኮል ያልጠረጠረው ታናሽ ወንድም፣ ግብዣውን ተቀብሎ ሲጠጣ ቆየ፡፡ ያ አጭር ሰውዬ ጦር እንደሰጠውና አውሬውን እንደገደለው ነገረው፡፡ ሲመሻሽ አብረው መንገድ ጀመሩ፡፡ ከጅረቱ ላይ ካለው ድልድይ አጠገብ ሲደርሱ ድቅድቅ ጨለማ ሆነ፡፡
ታላቅዬው ታናሽዬው እንዲቀድም ይነግረውና ግማሽ ድልድዩን አብረው ይሄዳሉ፡፡ ጥቂት ካደባ በኋላ ከኋላው ክፉኛ ይመታዋል፡፡ በዚህም የታናሽ ወንድም ህይወት ያልፋል፡፡
ቀጥሎም፤ ታናሽ ወንድሙን ድልድይ ሥር ቀብሮ፣ የአውሬውን ሬሳ ይዞ ወደ ንጉሡ ይሄዳል፡፡ ንጉሡም ተደስተው ልጃቸውን ይድሩለታል፡፡
ታናሽ ወንድሙ እስከመጨረሻው ሳይመጣ ቀረ፡፡ ታላቅ ፈጠን ብሎ፤
“ምናልባት ታናሽ ወንድሜን አውሬው በልቶት ይሆናል፡፡” ሲል ዋሸ፡፡ ሰው ሁሉ ግን አመነው፡፡
ሆኖም በዓለም ላይ ምንም ነገር ተሸሽጎ አይቀርምና፤ ከዓመታት በኋላ አንድ እረኛ ከብቶቹን ከዚያ ድልድይ ላይ እየነዳ ሳለ ታች አሸዋው ላይ አንድ ነጭ፤ የሚያበራ፣ ረዥም - አጥንት አየና ለጥሩምባ መሣሪያ ቢሆነኝ ብሎ ወርዶ ወሰደው፡፡ ከዚያም እየፋቀ በጥሩምባ ቅርጽ ሰራው፡፡ ሊነፋው ገና ወደ አፉ እንዳስጠጋው ግን አንድ ተዓምር ተከሰተ፤
“እረኛ ሆይ እረኛ ሆይ፤ የምትጫወተው
በእኔ አጥንት እኮ ነው፡፡
ተመትቼ ሞቼ በገዛ ወንድሜ
የገደልኩት አውሬ ተወስዷል በስሜ፡፡
ከውሃው አጠገብ አካሌን ቀበረ
ለንጉሡ ሴት ልጅ በተንኮል ተዳረ”
ሲል አጥንቱ ዘመረ፡፡ እረኛው በመገረም “ይሄን ጉድ ለንጉሥ ማሳየት አለብኝ” ብሎ ወደ ንጉሱ ሄደ፡፡ ቀርቦም አጥንቱን አሳየ፡፡ አጥንቷ እሱ ሳይናገር በፊት መዘመር ጀመረች፡፡ ንጉሱ ነገሩ ገባቸው፡፡ ቦታው ድረስ ጋሻ ጃግሬ ልከው አስቆፍረው የታናሽዬውን ሬሳ አወጡ፡፡ በቦታውም ታላቅ ወንድሙ ተገድሎ እንዲቀበር ትዕዛዝ ሰጡ፡፡
***
በብልጥነትና በጉልበተኛነት የሰሩት ተንኮል ውሎ አድሮ ከመጋለጥ አያመልጥም፡፡ በልበ - ቀናነት የተሰራ ሥራ ግን ለብዙዎች ጠቀሜታው ሰፊ ነው፡፡ ግዙፉን አውሬ በንፁህ ልቡ ሊዋጋ የሄደው ልጅ ቀንቶት ያገኘውን ድል፤ በተንኮልና በዕቡይነት የነጠቀው ቀማኛው ታላቅ ወንድም ምንም ሳይቆይ ተጋልጧል፡፡ አውሬው ብዙ ጥፋት ያደረሰ ነበረና ከፍርሃቱ በመነጨ ጭካኔው ያልተወረወረ ጦር ላይ መሰካቱም “ደም ያሰከረው” እንዲሉ መሆኑ ነው፡፡ የታናሽ ውንድሙን ሞት በአውሬው ያሳበበው ታላቅ ወንድሙ የሰራው ግፍ ሳያንስ ውሸት መጨመሩ ሁለተኛ ጥፋት ነው፡፡
ምርጫንም ሆነ ድርድርን በልበ - ቅንነት ማካሄድ አንድ በጎ እርምጃ ነው፡፡ አፈ-ቅቤ ልበ-ጩቤ የሆነ አካሄድ ግን ማንንም ወደፊት አያራምድም፡፡ ዕውነቱን ገልጦ የሚወጣ ተዓምረኛ ጥሩምባ ከምድርም ይፍለቅ ከሰማይም ይዝነብ ብቅ የሚልበት ቀን እንዳለ ልብ ብሎ፤ እጅን ከግፍ አፍን ከቅጥፈት መሰብሰብ ወቅታዊው ብልህነት ነው፡፡ በሰፈሩት ቁና መሰፈር እንደማይቀር አለማስተዋል ከባድ እርግማን ነው፡፡ በድፍረት አሻፈረኝ ብለው ዘራፍ ካሉም “ሥጋ ሲመጣ ዳንኪራ፣ ዕዳ ሲመጣ ኩብለላ” መሆኑን ከወዲህ ለመገመት አያዳግትም፡፡
ለውጥን ቀስ በቀስ እንደሚገነባ ጥብቅ ካብ ማሰብ እንጂ በነቶሎ ቶሎ ቤት አሰራር ልናመጣው እንደማይቻል፣ ከተቻለም እንደማያዛልቅ መረዳት ለሀገራችን እጅግ ጠቃሚ መነሻ ይሆናል፡፡ ይህን መሰረት ያልያዘ ሂደት ውሎ አድሮ “የተማመኑበት ቢላዋ በጉበት ይሰበራል” ዓይነት እንደሚሆን ልብ ማለት ደግ ነገር ነው፡፡
በወርሃ የካቲት በኢትዮጵያ አያሌ እንቅስቃሴዎች እየፈሉ እንደነበሩ ሁሉ ወራቸው ሲገባ የሀሳብ፣ የዕውቀት፣ የለውጥ ንፋስ መንፈሱ ያለ ነው፡፡ ከየካቲት 23 እስከ መሬት ላራሹ፣ ከየካቲት 12 እስከ የካቲት 11 ብዙ አይተናል፡፡
ዛሬም ብዙ እንሰማለን፤ የተጨበጠም ያልተጨበጠም፡፡ ሁሉም ምን እንዳዘለ ጊዜ ያሳየናል፡፡ ለውጥ የጊዜ ልጅ ነው፡፡ “የካቲት ወይ ስትገባ ወይ ስትወጣ - ባታንጎዳጉድ፣ መሬት ትጨነቅ ነበር” የሚለው የሰሜኖች ተረት እንዲሁ አልተተረተም፡፡