Administrator

Administrator

የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ስነ - ጥበባት ኮሌጅ የማስተርስ ዲግሪ ተማሪዎች ከህንድ ኤምባሲ ጋር በመተባበር፣ በአገራችን የመጀመሪያ የተባለውን የአጫጭር ፊልሞች ፌስቲቫል ያካሂዳሉ፡፡ ፌስቲቫሉ ዛሬና ነገ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ስድስት ኪሎ ካምፓስ በሚገኘው የባህል ማዕከል የሚካሄድ ሲሆን አላማውም የአጫጭር ፊልሞችን ጥበብ ለአገራችን ተመልካቾች ለማስተዋወቅና በአገራችን ለሚገኙ የአጫጭር ፊልም ፀሐፊዎች፣ አዘጋጆች፣ ፕሮዱዩሰሮችና ተዋንያን እውቅናና ክብር ለመስጠት እንዲሁም ሙያቸውን ለማበረታታት እንደሆነ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የቴአትር ጥበባት ትምህርት ክፍል በላከው መግለጫ አስታውቋል፡ 

የኒታ የቀለም ማዕከል ባለቤትና ሥራ አስኪያጅ በሆኑት በኬሚካል መሐንዲስ ጌታሁን ሔራሞ ባለፉት አስር ዓመታት ከወጣት ሠዓሊያን የተሰበሰቡ 80 የሥዕል ስራዎች የተካተቱበት ዐውደ ርዕይ የፊታችን ሐሙስ በአለ የሥነ ጥበብና ዲዛይን ትምህርት ቤት ተመርቆ ይከፈታል፡፡ “የማይሸጡ ሥዕሎች” በሚል ርዕስ የተዘጋጀው አውደርዕይ ላይ የሚቀርቡት የሥዕል ሥራዎች፤ ሙሉ በሙሉ በሀገር ውስጥ በተመረቱ የዘይትና አክሪሊክ የሥዕል ቀለሞች የተሰሩ መሆናቸው አውደርዕዩን ልዩ ያደርገዋል ብለዋል አዘጋጁ፡፡ አውደ ርዕዩ እስከ ሰኔ 13 ቀን 2006 ዓ.ም ድረስ ለተመልካቾች ክፍት ሆኖ ይቆያል ተብሏል፡፡ 

በኢትዮጵያ ብሄራዊ ቴአትር የተዘጋጀው “ቅጥልጥል ኮከቦች” የተሰኘ ቴአትር የፊታችን ሰኞ ይመረቃል፡፡ ቴአትሩ የሙሉ ሰዓት ሲሆን ሰኞ ከቀኑ 10 ሰዓት ጀምሮ ለጥበብ ባለሙያዎችና ጥሪ ለተደረገላቸው እንግዶች በቴአትር ቤቱ አዳራሽ እንደሚቀርብ ታውቋል፡

በካህሳይ አብርሃ በተፃፈው “የአሲንባ ፍቅር” መፅሃፍ ላይ ነገ ከቀኑ 8፡30 ጀምሮ በብሄራዊ ቤተ መፃህፍትና ቤተ-መዛግብት ኤጀንሲ አዳራሽ ውይይት እንደሚደረግ ሚዩዚክ ሜይዴይ ኢትዮጵያ አስታወቀ፡፡
ደራሲ ኃይለመለኮት መዋዕል ለውይይቱ የመነሻ ሀሳብ የሚያቀርቡ ሲሆን ተጨማሪ የውይይት ሀሳቦች በፕ/ር ገብሩ ታረቀ እንደሚቀርብ ታውቋል፡፡

ርዕስ - ውለታ ለነብስ (የግጥም መድበል)
ደራሲ - እዩኤል ደርብ
የመፅሃፉ መጠን - በ89 ገፆች 88 ግጥሞች
ዋጋ - 46 ብር
*          *           *
ርዕስ - የነጎድጓድ ልጆች (ልብወለድ)
ደራሲ - ቃልኪዳን ኃይሉ
የመፅሃፉ መጠን -208 ገፆች
ዋጋ - 46ብር

Saturday, 31 May 2014 14:32

የጸሐፍት ጥግ

የአንዱ ደራሲና የሌላው ደራሲ ቃል አንድ አይደለም፡፡ አንዱ ሃሞቱን ቀዶ ሲያወጣ፣ ሌላው ከካፖርቱ ኪስ መዥርጦ ያወጣል፡፡
ቻርልስ ፔጉይ
በጣም ልታነበው የምትፈልገው መፅሃፍ ካለና ገና ያልተፃፈ ከሆነ፣ ራስህ ልትፅፈው ይገባል፡፡
ቶኒ ሞሪሰን
ከጥሩ ፀሐፊ የምወድለት የሚለውን ሳይሆን የሚያንሾካሹከውን ነው፡፡
ሎጋን ፒርሳል
ወረቀትህን በልብህ እስትንፋሶች ሙላው፡፡
ዊሊያም ዎርድስ ዎርዝ
የጨረቃዋን መፍካት አትንገረኝ፤ የብርሃኑን ፍንጣቂ በተሰበረ መስተዋት ላይ አሳየኝ፡፡
አንቶን ቼኾቭ
አንዳንዴ ቀለምና ወረቀት እፍ ፍያሉ ፍቅረኛሞች ይሆናሉ፡፡ ብዙ ጊዜ ግን ወንድምና እህት ናቸው። አልፎ አልፎ ደግሞ የለየላቸው ጠበኞች፡፡
ቴሪ ጉሌሜትስ
ተለዋጭ ዘይቤዎች (Metaphors) ግዙፉን እውነት በትንሽዬ ቦታ የመያዝ ብልሃት አላቸው።
ኦርሶን ስኮት ካርድ
የምፅፈው ታሪክ አዲስ አይደለም፤ ያለነው፤ በወጉ ተፅፎ የተቀመጠ፤ የሆነ ቦታ፤ አየሩ ላይ። ከእኔ የሚጠበቀው ፈልጐ መገልበጥ ብቻ ነው።
ጁሌስ ሬናርድ  

Saturday, 31 May 2014 14:31

የፍቅር ጥግ

ለእኔ ፍቅር ማለት አንድ ሰው “ቀሪውን ህይወቴን ካንቺ ጋር ለማሳለፍ እሻለሁ፤ከፈለግሽ ላንቺ ስል ከአውሮፕላን ላይ እዘልልሻለሁ” ሲለኝ ነው፡፡
ጄኒፈር ሎፔዝ
ጀግንነት ማለት ያለምንም ቅድመ-ሁኔታ ማፍቀር ነው፡፡ በምላሹ ምንም ሳይጠብቁ ማፍቀር፡፡ በቃ ፍቅር መስጠት፡፡ ይሄ ድፍረት ይጠይቃል፡፡ ራሳችንን ለጉዳት አጋልጠን መስጠት አንፈልግማ፡፡
ማዶና  
ፍቅር ሲይዝህ እንቅልፍ አይወስድህም፡፡ ምክንያቱም ተጨባጩ እውነታ ከህልምህ የተሻለ ነውና፡፡
ዶ/ር ሴዩስ
ከፍቅር የሚገኘው ደስታ ጊዜያዊ  ሲሆን  የፍቅር ስቃይ ግን  ለእድሜ ልክ ይዘልቃል፡፡
ቤቲ ዴቪስ
ልብ የሚፈልገውን ያውቃል፡፡ ለዚህ ምንም አመክኖ የለውም፡፡ አንድ ሰው ታገኛለህ፤ከዚያም ታፈቅራለህ፡፡ በቃ ይኼው ነው፡፡
ዉዲ አለን
ፍቅር ሲይዝህ ሁሉ ነገር እንደ ብርሃን ግልጥልጥ ይልልሃል፡፡
ጆን ሌኖን
በፍቅር ውስጥ ስትሆኚ  አደገኛ ስሜት መፈጠሩ አይቀርም---- የገዛ ልብሽን አሳልፈሽ ለሌላ ሰው እኮ ነው የምትሰጭው፡፡ ያውም በስሜትሽ ላይ የማዘዝ ስልጣን እንዳለው እያወቅሽ። ሁልጊዜም አይበገሬ ለመሆን ለምጥረው ለእኔ፣ ይሄ አደገኛ ነገር እንደሆነ አውቃለሁ፡፡  
ቢዮንሴ ኖውሌስ

ፋርዛና በአደባባይ ለ40 ደቂቃ በቤተሰቦቿ ስትደበደብ ፖሊስ በዝምታ አይቷል
ያለኔ ፈቃድ ባል በማግባት ስላዋረደችኝ ገደልና፤ አይፀፅተኝም - አባት
ፋርዛናን ለማግባት ብዬ ነው የመጀመሪያ ሚስቴን አንቄ የገደልኳት - ባል
የመጀመሪያ ሚስቱን ገድሎ ያልታሰረው ልጆቹ ይቅርታ ስላደረጉለት ነው - ፓሊስ

ባለፈው ማክሰኞ በፓኪስታን ላሆር ከተማ የተፈፀመው ዘግናኝ ግድያ ከቀን ወደ ቀን እየተወሳሰበ ነው፡፡ አጀማመሩ ግን እንዲህ ነው፡፡ “በፍቅር ግንኙነት ከአመት በላይ አሳልፈናል” በማለት የተናገሩት ፋርዛና ፓርቪን እና ኢቅባል መሐመድ፤ ተጋብተው አብረው ለመኖር ከወሰኑ ቆይተዋል፡፡ የፋርዛና ቤተሰብ ግን ፈቃደኛ አልሆነም፡፡
ፓርዛና የ25 ዓመት ወጣት ናት፡፡ ኢቀባል በእድሜ ይበልጣታል፤ ልጆችንም ወልዷል፡፡ ለፋርዛና ቤተሰብ ግን፤ ይሄ አላስጨነቃቸውም፡፡ ኢቅባል 1000 ዶላር ጥሎሽ አልከፍልም በማለቱ የተቆጡ የፋርዛና ቤተሰቦች፤ ለሌላ ባል ሊድሯት ተነጋግረው ጨርሰዋል፡፡ በዚህ መሃል ነው ባለፈው ጥር ወር ፋርዛና ያለ ቤተሰቧ ፈቃድ ከኢቅባል ጋር ተጋብታ የሄደችው፡፡ ቤተሰቦቿ ደግሞ ኢቅባልን ከሰሱት-“ልጃችንን ጠልፎ ወስዷል” በሚል፡፡
ባለፈው ማክሰኞ እለት ፋርዛና ከኢቅባል ጋር ወደ ፍ/ቤት የመጣችው፣ “እኔ አልተጠለፍኩም” የሚል ምስክርነት ለመስጠት ነው፡፡ ኢቅባልን የከሰሱት ቤሰቦቿ… አባቷ፣ ወንድሞቿ፣ የአክስትና የአጐት ልጆች ሁሉ ተሰብስበዋል፡፡ ሃያ ይሆናሉ፡፡ ከፍርድ ቤት ስትወጣ ጠብቀው፤ ጠልፈው ሊወስዷት ቢሞክሩም እሺ አላለችም፡፡ ያኔ ነው ዙሪያዋን በመክበብ የድንጋይ መዓት ያወረዱባት - በአባቷ መሪነት፡፡
ባለቤቷ ኢቅባል እንደሚለው፤ ከፍ/ቤቱ በራፍ ላይ አደባባይ መሃል በጠራራ ፀሐይ በድንጋይ ሲወግሯት አላፊ አግዳሚ ሁሉ ከሩቅ ሆኖ ከመመልከት በስተቀር ለመገላገል የሞከረ ሰው የለም፡፡ ፖሊሶችም ነበሩ፡፡ የሦስት ወር እርጉዝ የነበረችው ፋርዛና ቶሎ አልሞተችም፡፡ ለ40 ደቂቃ በቤተሰቦቿ የድንጋይ ውርጅብኝ እንደተደበደበች የገለፀው ቢቢሲ፤ ይህንን የግድያ ጥቃት ለማስቆም ፖሊስ እንዳልሞከረ ዘግቧል፡፡ ፋርዛና በአሰቃቂ ስቃይ ህይወቷ ካለፈ በኋላ የታሰሩት አባቷ፤ ያለፈቃዳችን በማግባቷ አዋርዳናለች፤ ለክብራችን ስንል ገድለናታል፤ የሚፀፅተኝ ነገር የለም ብለዋል፡፡ በግድያው የተሳተፉ ወንድሞቿና ዘመዶቿ አልታሰሩም፡፡ ግን እነሱም በግድያው አልተፀፀቱም፡፡
እንዲያውም፤ ካሁን ቀደም ተመሳሳይ ግድያ እንደፈፀሙ ከመናገር ወደኋላ አላሉም፡፡ የዛሬ አራት አመት በተመሳሳይ የጋብቻ ውዝግብ ሰበብ ታላቅ እህቷን መግደላቸው በሲኤንኤን ተዘግቧል፡፡ ለነገሩ በፓኪስታን እንዲህ በቤተሰብ የሚፈፀም ግድያ አዲስ ነገር አይደለም፡፡ የፓኪስታን ምድር፤ የሰብአዊ መብት ኮሚሽን ተወካይ ዛህራ ዮሱፍ እንደሚሉት በየአመቱ አንድ ሺ ገደማ ሴቶች ያለ ቤተሰብ ፈቃድ አግብተዋል ተብለው ይገደላሉ፡፡
ዘግናኙ የግድያ ታሪክ በዚህ አልተቋጨም፡፡ የፋርዛና ባለቤት ኢቅባል ንፁሕ ሆኖ አታገኘም፡፡ ለካ፣ የዛሬ ስድስት አመት የመጀመሪያ ሚስቱን ገድሏል፡፡ ከፋርዛና ጋር ለመጋባት በማሰብ ነው የመጀመሪያ ሚስቴን አንቄ የገደልኳት ብሏል - ኢቅባል፡፡ አስገራሚው ነገር ከአንድ አመት በላይ አልታሰረም፡፡ ከመነሻውም በፖሊስ የታሰረው፤ “እናታችንን ገደላት” በማለት ልጆቹ በመመስከራቸው ነው፡፡ ከጥቂት ወራት በኋላ ደግሞ፤ ልጆቹ “ይቅርታ አድርገንለታል” ብለው ስለተናገሩ ከእስር መለቀቁን ሲኤንኤን ዘግቧል፡፡ የሴት ህይወት የረከሰባት ፓኪስታን፤ የቅዠት አገር አትመስልም?

ሃውኪንግ ለቀመሩ ክፍያ ተቀብሏል - ፓዲ ፓወር ከተሰኘው የቁማር ኩባንያ

      ከዩኒቨርስ አፈጣጠር እስከ አቶሞች ባሕርይ፣ በበርካታ የምልዐተ ዓለሙ ሚስጥራት ላይ የሚመራመር ታዋቂው የፊዚክስ ጥበበኛ ስቴፈን ሃውኪንግ፤ ሰሞኑን በእግር ኳስ ዙሪያ የምርምር ግኝቶቹን አቅርቧል።
በዘንድሮው የአለም ዋንጫ የእንግሊዝ ቡድን እንዴት ውጤታማ ሊሀን እንደሚችል ምክር የለገሰ ሲሆን፣ የ50 ዓመታት መረጃዎችን በመተንተን ለአሸናፊነት የሚያበቃ ቀመር (ፎርሙላ) አዘጋጅቷል። የተጫዋቾች አሰላለፍና የማሊያ ቀለም፣ የውድድር ሰዓትና የሙቀት መጠን፣ የፍፁም ቅጣት አመታትና የዳኞች ማንነት እንዲሁም ሌሎች በርካታ ተለዋዋጭ (variable) ነገሮችን ያካትታል - ቀመሩ።
በእርግጥ፤ የሃውኪንግ ቀመር ለሂሳብ ጠበብት እንጂ ለአብዛኛው ሰው ሊገባ የሚችል አይደለም። እንዲያውም፣ ነገሩን ይበልጥ ያወሳስብባቸዋል። ግን ችግር የለም። ስቴፈን ሃውኪንግ፣ ውስብስቡን ቀመር፣ በቀላል ቋንቋ ለማስረዳት ሞክሯል። ለምሳሌ፣ ለእንግሊዞች የሚስማማቸው መካከለኛ የሙቀት መጠን እንደሆነ ሳይንቲስቱ ጠቅሶ፤ የሙቀት መጠን በ5 ዲግሪ ሴንቲግሬድ ሲጨምር የቡድኑ ውጤታማነት በ59% ይቀንሳል ብሏል። በዚያ ላይ፣ እንደ አዲስ አበባ በመሳሰሉ ከፍታ ቦታ ላይ የእንግሊዝ ቡድን ማሸነፍ አይሆንለትም። የቦታው ከፍታ ከ500 ሜትር በታች ከሆነ ግን፤ የማሸነፍ እድሉ በእጥፍ ይጨምራል። ጨዋታው የሚጀመረው ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት ከሆነም፣ ቡድኑ ይቀናዋል።
ምን ዋጋ አለው? የሙቀት መጠን፣ የአካባቢው ከፍታና የውድድር ሰዓት፣ በምርጫ የሚወሰኑ ነገሮች አይደሉም። ነገር ግን የእንግሊዝ ቡድን የተጨዋቾቹን አሰላለፍና የማሊያውን ቀለም በትክክል ከመረጠ፣ የማሸነፍ እድሉን ማሻሻል እንደሚችል የሃውኪንግ ቀመር ያስረዳል። 4-4-2 አሰላለፍ ለእንግሊዝ እንደማይበጅ የገለፀው ሃውኪንግ፣ ቡድኑ ስኬታማ የሚሆነው በ4-3-3 አሰላለፍ እንደሆነና ቀይ ማሊያ መልበስ እንዳለበት ተናግሯል። ቀይ ማሊያ፤ በተቀናቃኝ ቡድን ላይ የስነልቦና ተፅእኖ ያሳድራል፤ እናም የእንግሊዝ ቡድን የአሸናፊነት እድሉን በ20% ያሻሽላል።
ሃውኪንግ እንደሚለው፤ ውድድሩ የሚካሄደው ቅርብ በሆነ አገር ቢሆን መልካም ነበር፤ ብራዚል ድረስ አትላንቲክ ውቅያኖስን ለማቋረጥ የሚደረገው በረራ፣ በተጫዋቾች ላይ ድካምን ይፈጥራል፤ የማሸነፍ እድላቸውንም በ22 በመቶ ይቀንሳል። ዳኞቹ አውሮፓውያን ሲሆኑ የእንግሊዝ ቡድን ይቀናዋል፤ አለበለዚያ ግን የማሸነፍ እድሉ በ25% ይወርዳል።
የቲፎዞና የአጃቢ ሴቶች ጉዳይስ? ይሄ በቡድኑ ውጤታማነት ላይ ምንም ለውጥ ስለማያመጣ በቀመሩ ውስጥ እንዳልተካተተ ሃውኪንግ ገልጿል።
ወደ ፍፁም ቅጣት የሚያመራ ውድድር ሲያጋጥምስ? የሃውኪንግ ምርምር፣ ሶስት ነባር ጉዳዮችን በድጋሚ ያረጋገጠ ሆኗል። አንደኛ፣ ፍጥነት ወሳኝ ነው። ፍፁም ቅጣት የሚመታ ተጫዋች፣ ቢያንስ ቢያንስ አራት እርምጃ መንደርደር አለበት።
ከዚህ ባነሰ እርምጃ ከተንደረደረ፣ ግብ የማስቆጠር እድሉ በግማሽ ይቀንሳል። ሁለተኛ፣ ከግራ ወይም ከቀኝ በኩል ከፍ አድርጎ መምታት ያስፈልጋል። 84 በመቶ ያህል ይሳካለታል። ኳሷን በደንብ ለመቆጣጠር በጎን እግር መምታት ነው። ሦስተኛ፣ ከተከላካይና ከመሃል ተጫዋቾች ይልቅ አጥቂዎች እንዲመቱ ማድረግ ያዋጣል ብሏል ሃውኪንግ።
ሳይንቲስቱ፣ ለእንግሊዞች ምክሩን ቢለግስም፣ ያሸንፋሉ የሚል ተስፋ የለውም። በቀመሩ መሰረት፣ ዋንጫውን የሚወስደው ብራዚል ነው። ግን የሳይንቲስቱ ምርምር ቀልጦ አይቀርም።
ከመነሻው፣ የፊዚክስ ባለሙያው ስቴፈን ሃውኪንግ፣ በእግር ኳስና በአለም ዋንጫ ላይ ጥናትና ምርምር ያካሄደው፣ ለእንግሊዝ ቡድን የማሸነፊያ ቀመር ለመፍጠር አይደለም። የሃውኪንግ ቀመር ለማንኛውም ቡድን ይሰራል። ያንን ቀመር የሚያሟላ ቡድን ያሸንፋል። ቀመሩን በእጅጉ ተፈላጊ የሚሆነው ግን፣ ሜዳ ውስጥ ገብተው በአለም ዋንጫው ለሚሳተፉ ቡድኖች አይደለም። ከዳር ሆነው ቁማር ለሚያጫውቱ ኩባንያዎች እንጂ። ስቴፈን ሃውኪንግም ቀመሩን ያዘጋጀው፣ ፓዲ ፓወር ለተሰኘ የቁማር ኩባንያ ነው - በክፍያ። እውነትም፣ የቁማር ኩባንያ ስኬታማ ሊሆን የሚችለው፣ በአንዳች የቀመር ስሌት የትኞቹ ቡድኖች ምን ያህል የማሸነፍ እድል እንዳላቸው የሚያውቅ ከሆነ ነው። አለበለዚያ ከፍተኛ ኪሳራ ሊደርስበት ይችላል። እናም፤ የሃውኪንግ ቀመር፣ የጊዜ ማሳለፊያ ጨዋታ አይደለም፤ የቢዝነስ መሳሪያ ነው።

እንግሊዝ ከቡድን ማጣሪያ እንደማታልፍ የገለፁት የጎልድማን ሳችስ ታዋቂ የባንክ ኤክስፐርተቶች፣ ብራዚል ብርቱ ተፎካካሪዎች ቢኖሩባትም ዋንጫ የማንሳት እድሏ ከፍተኛ ነው አሉ።
እልፍ አይነት መረጃዎችን በመተንተንና በማጠናቀር፣ ዙሪያ ገባውን አበጥሮና አንጥሮ፣ ፈጭቶና ጋግሮ፣ እጥር ምጥን ያለች ፎርሙላ መፍጠር፣ ለፊዚክስ ጠብተቶች ብቻ የተተወ ስራ አይደለም። በአለም ኢኮኖሚ ውስጥ ትልቅ ስፍራ የያዙ እንደ ጎልድማን ሳችስ የመሳሰሉ ባንኮች፤ የእለት ተእለት ስራቸው፣ መረጃዎችን ማበጠርና መፍጨት ነው። በቅርቡ፣ የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ጤንነትን በሚመለከት፣ “ቢ” የተሰኘ ማርክ ሰጥተዋት መንግስት ምን ያህል እንደተደሰተ አላያችሁም? በመቶ የሚቆጠሩ አገራትን፣ በአስር ሺ የሚቆጠሩ ኩባንያዎችን እየፈተሹና እየመረመሩ፣ ማርክ ይሰጣሉ። በዚሁም መሰረት በቢሊዮን ዶላሮች ያበድራሉ፣ ኢንቨስት ያደርጋሉ፤ አክሲዮን ይገዛሉ፣ ይሸጣሉ። እንጀራቸው ነው። አሁን ደግሞ ለአለም ዋንጫ ተሳታፊ ቡድኖች ማርክ ሰጥተዋል።
ምን ይሳናቸዋል? ጨዋታዎችንና ጎሎችን፣ ድሎችንና ሽንፈቶችን፣ እንዲሁም ወቅታዊ ብቃትና ውጤቶችን በሚመለከት የ55 ዓመታት መረጃዎችን በመፈተሽ ነው የባንኩ ኤክስፐርቶች የራሳቸውን ቀመር ያዘጋጁት።
በባንኩ ቀመር መሰረትም፣ የዋንጫው ባለቤት ብራዚል ይሆናል። ለምሳሌ ከእንግሊዝ ቡድን ጋር ሲነፃፀር፣ የብራዚል የማሸነፍ እድል፣ ከ35 እጥፍ በላይ ይበልጣል። ምን ማለት መሰላችሁ? በውርርድ አንድ ብር ታስይዛላችሁ እንበል። ሁለት አማራጭ ይቀርብላችኋል። እንግሊዝ ያሸንፋል ብሎ የሚወራረድ፣ በአንዷ ብር 35 ብር ያገኛል። ብራዚል ያሸንፋል የሚል ካለ ደግሞ፣ በአንዷ ብር 2 ብር ያገኛል። ከእነዚህ ሁለት አማራጮች የትኛውን ትመርጣላችሁ? ከታዋቂው አለማቀፍ ባንክ ምክር የምትቀበሉ ከሆነ፣ “ብራዚል ያሸንፋል” ብላችሁ ለውርርድ ብታስይዙ ይሻላል።
ብራዚል በአለም ዋንጫው ወደ ሁለተኛ ዙር የማለፍ እድሏ ከ99 በመቶ በላይ ሲሆን፣ የእንግሊዝ እድል 54 በመቶ ያህል ነው። ለፍፃሜ የመድረስ እድላቸውስ? የብራዚል 60 በመቶ ሲሆን፣ የእንግሊዝ ግን ከ5 በመቶ ብዙም አይበልጥም።
ከብራዚል በመቀጠል ከፍተኛ ግምት የተሰጣት አርጀንቲና ነች። ከዚያ ደግሞ ጀርመንና ስፔን።