Administrator

Administrator

ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ልጅ ገመድ ዝላይ ከሚዘሉ ልጆች ጋር ሊጫወት ከቤቱ ይወጣል፡፡ አባቱ ከፎቅ ሆኖ የስተውለዋል፡፡
አባትየው የሚያየውን ለማመን አልቻለም፡፡
ልጁ ገመዱን የሚያዞሩትን ልጆች፤
“እኔንም ገመድ ዝላይ አጫውቱኝ?” ሲል ጠየቃቸው፡፡
“እሺ ዝለል” አሉት፡፡
ልጁ መዝለል ጀመረ፡፡
ልጆቹም ገመዱን ማዞር ቀጠሉ፡፡
አስገራሚው ነገር ግን ልጁ የሚዘለው ሌላ ቦታ ነው፤ ልጆቹ ገመዱን የሚያዞሩት ሌላ ቦታ ነው፡፡ ልጁ መዝለውን ቀጠለ፡፡
ልጆቹ ይቀልዱበታል፡፡ ይስቁበታል፡፡ እሱ መዝለሉን ቀጥሏል፡፡ አይፎርሽም፡፡ ደስ ብሎታል፡፡
አባትዬው በሁኔታው አዝኖ ከፎቅ ወርዶ መጥቶ ልጁን መዝለሉን አስቆመውና ወደቤት አስገባው፡፡ ልብሱን አስቀይሮ ወደ ሐኪም ቤት ወሰደው፡፡ ሐኪሙም፤
“ምን ችግር ገጠማችሁ፤ ምን ልርዳችሁ?” አለ
አባት ልጁ ሲጫወት ምን ያደርግ እንደነበረ ገለጠለትና “ምናልባት ልጄ አንድ ዓይነት የአዕምሮ ወይም አካላዊ ችግር እንዳይኖርበት ብዬ ነው” ሲል አስረዳ፡፡
ሐኪሙ ለልጁ ብዙ ምርመራ ካደረገለት በኋላ የዓይን ችግር እንዳለበት አረጋገጠና መነፅር አዘዘለት፡፡
ልጁ መነፅር ተገዛለት፡፡ መነፅሩን አድርጐ ወደ ገመድ ዝላይ ጨዋታው ሄደ፡፡
አሁን በትክክል ገመዱ ማህል ገባ፡፡ አዞሩለት፡፡ በትክክል መዝለል ጀመረ፡፡ አንዳንዴ ነው እንጂ አልፎረሸም፡፡ ቀጠለ ዝላዩን!!
*    *    *
ገመዱ በሌለበት የምንዘል አያሌ ነን፡፡ ሐኪም ያላየ ዐይን ያለን በርካታ ነን፡፡ በትክክል እንዳልዘለልን እያዩ፣ እየታዘቡ፤ እየሳቁ፣ እየተሳለቁ የሚያዩንም ብዙ ናቸው፡፡ ገመድ ማዞሩን እንደስራ ቆጥረው ዕድሜ - ልካቸውን ቢሮክራሲው ውስጥ የሚኖሩም የትየለሌ ናቸው፡፡ እንደ መልካም አባት ያለ መልካም መሪ፣ መልካም ኃላፊ፣ መልካም አለቃ የልጁን ችግር ተረድቶ ወደሀኪም ዘንድ ይወስዳል፡፡ ለችግሩ መፍትሔ ይፈጥራል፡፡
የሚስቁ፣ የሚሳለቁትን ሁሉ ኩም ያደርጋቸዋል፡፡ “የሚሠሩትን አያውቁትምና ይቅር በላቸው” ይላቸዋል፡፡
በገመድ ዝላይ መፎረሽ እንግዳ ነገር አይደለም፡፡ ግን የፉረሻውን ቁጥር መቀነስ ይቻላል። ከገመዱ ውጪ መዝለል ከጨዋታው ውጪ ነው ቢባልም፣ ልምዱ ግን ቀላል አደለም ብሎ መከራከርም ይቻላል፡፡ የልጁ የዕይታ ችግር (Sight problem) የሁላችንም ችግር ቢሆንስ ብለን ማሰብ አለብን (myopic or farsighted እንዲል ፈረንጅ - የአፍንጫ ሥር ማየትና አርቆ - ማስተዋል እንደማለት)፡፡ ማመን ነው እንጂ አለማመን ምን ያቅታል፤ ይላል አንድ ፀሐፊ
ዕውነትን መሠረት ካደረግን ውሸትን መናቅ ቀላል ነው፡፡
“ሐሰተኞች ሰዎች ቢምሉ ቢገዘቱ ነገራቸውን በአየር ላይ በሚበሩና ፍለጋቸው በማይገኝ ዎፎች መስለው፡፡ ለመብረራቸው ፍለጋ እንደሌለው፤ ሐሰተኞች ሰዎች ለሚናገሩትም ነገር ሥር መሠረት የለውምና” ይላሉ የአገራችን ፈላስፎች፡፡
በነባራዊነትና በህሊናዊነት አንፃር ከተመለከትን የማይዋሹ ነገሮችን መዋሸት ጅልነት ነው። አንድ አዛውንት “እንዴት ፖለቲከኛ ለመሆን ቻሉ?” ተብለው ቢጠየቁ፤ “የዕውቀት ማነስ ነው ፖለቲከኛ ያደረገኝ!” አሉ፤ አሉ፡፡ “አንተስ የአገራችን ምሁር ያደረገህ ምንድነው?” ብለው አዛውንቱ ቢጠይቁት “ያው መማሬ ይመስለኛል ሌላ ሰበብ አይሰማኝም” አለ ምሁሩ፡፡ አዛውንቱም “አንተን ምሁር ያረገህ ደሞ ምን መሰለህ?...የዕውነት ማነስ!” አገራችን ከእኒህ አዛውንት ዕሳቤ ውጪ አይደለችም፡፡ የዕውነትና የዕውቀት ማነስ ፖለቲከኛም፣ ምሁርም አድርጐናል፡፡ ያወቀ ያውቀዋል። ያለቦታው ገመድ መዝለልም ክህሎት ይሆናል፡፡ በዛሬ ግንቦት ሃያ ማግስት ሆነን፣ “አንጋረ - ፈላስፋ” የሚለው መፅሐፍ የሚለንን ብናስብ ፀጋ ነውና እነሆ:-
“ዕውነትን መናገር፣ በሐሰት ከመማል መራቅ፣ ሰውን ፊትን አብሮቶ መቀበል፣ እንግዶችን አክብሮ መቀበል፣ በጐ ሥራ መሥራት፣ ጐረቤትን ተጠንቅቆ መያዝ፣ Uዕቢትን አለማድረግ፣ ሁልጊዜ ሰውን ማክበር፣ ትህትናን ማዘውተር፣ አንደበትን ክፉ ከመናገር መግታት፣ ቀናውን ነገር መናገር፣ ለሁሉም በቅንነት መመለስ፣ የወንድምን ኃጢያት መሠወር፣ ሽንገላን (ምሎ - መክዳትን) መተው፣ ጉባዔ ፊት ጮክ ብሎ አለመናገር” እነዚህን ቃላቶች ሁሉ ገንዘብ ያደረገ ሰው በዕውነት አዋቂ ነው፣ ዐዋቂ ይባላል”
ትርጓሜውም፤ ባጭሩ፤
“ዕምነትህን አትካድ፡፡ ከጐረቤት ጠንቅ መጠበቅ፡፡ የፖለቲካ አቀባበልና አያያዝን ማወቅ። በፓርላማ ፊት አለመፎከር፡፡ መሬት ላይ ምን እንደሚጠብቀን አናውቅምና፡፡” ይሄ የወቅቱ መልዕክት ይሁነን፡፡
ነብሳቸውን ይማረውና አባ ጳውሎስ ረዥም ፍትሐተ - ፀሎት ያደረጉለት፤ ነብሱን ይማረውና የአድዋው ደራሲ ስብሃት ገ/እግዚአብሔር፤
“ግንቦት ሃያን እንዴት ታየዋለህ?” ሲባል፤
“እንደሰኔ ሃያ” ያለው አይረሳንም፡፡
ድሎቻችንን አንረሳም፡፡ ሌላ ድል ለማስመዝገብ የቀደሙት ድሎች ከትውስታነት ባሻገር አገልግሎት የላቸውም፤ እንደ አድዋ ድል ሁሉ፡፡ ወሳኙ የዛሬ ዝግጁነታችን ነው፡፡ የዛሬ ማንነታችን ነው፡፡ የሚከፈለን ካሣም በወቅቱ ፍሬ ነበረ፡፡ ወደ ሰላማዊ ትግል ስንዘዋወር ምርቱ ለሌላ ዕድገት መስፈንጠሪያ - ድልድይ (Spring Board) ሆኗል፡፡ ስለዚህም ጊዜው ብዙ መናገሪያ ሳይሆን ማድረጊያ ሆኗል ማለት ነው፡፡ መስከረም ሁለትን ከግንቦት ሃያ የሚለየው ይሄ ነው፡፡ ድፋትና ቅናት ነው በያሬድኛ፡፡ ትንሽ ምላስ እና ብዙ እጅ እንደማለት ነው፡፡ ይሄ ለተቃዋሚም፣ ለአልተቃዋሚም፣ ለአዘቦት - ሰውም ዕውነት ነው፡፡
ለዚህ ነው ከምዕተ - አመታት በፊት የነበሩ ፈላስፎቻችን፤ “ድምፅን ከፍ አድርጐ በመጮህ ቤት የሚሠራ ቢሆን፤ አህያ በቀን በቀኑ ሁለት ቤት በሠራ ነበር!” ያሉት፡፡   

አባል ለመሆን፤ በቴሌኮም፣ በባንክና በኤሌክትሪክ ሃይል ኢንዱስትሪው የመንግስትን ድርሻና ቁጥጥር መቀነስ ግዴታ ነው

የኢትዮጵያ መንግስት በቴሌኮምና በባንክ ዘርፎች ላይ ያለውን ከፍተኛ ድርሻና ቁጥጥር በማቆም ዘርፎቹን ለአገር ውስጥና ለውጭ ኢንቨስትመንት እንዲከፍት የሚገደድ ከሆነ በመጪው አመት የአለም የንግድ ድርጅት አባል የመሆን እቅዱን እንደሚያራዝም የንግድ ሚኒስትር አቶ ከበደ ጫኔ ተናገሩ፡፡
ሚኒስትሩ ባለፈው ማክሰኞ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት እንደተናገሩት፣ የአለም የንግድ ድርጅት አባል አገራት የኢትዮጵያ መንግስት የቴሌኮምና የባንክ አገልግሎት  ለአለማቀፍ ውድድር ክፍት የሚያደርግበትን ጊዜ በተመለከተ ተደጋጋሚ ጥያቄዎች እያቀረቡ ነው፡፡
“የአገልግሎት ዘርፉን በተመለከተ በርካታ ጥያቄዎች እየተነሱ ይገኛሉ፡፡ የቴሌኮም፣ የባንክ እና የኤሌክትሪክ ሃይል ኢንዱስትሪዎችን ለግል ባለሃብቶች ክፍት የምናደርግበትን ጊዜ በግልጽ እንድናሳውቅ በተደጋጋሚ እንጠየቃለን” ያሉት ሚኒስትሩ፤ “የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድን ከማጠናቀቃች በፊት፣ የህግ ማሻሻያዎችን በማድረግ የአገልግሎት ዘርፉን ለአገር ውስጥና ለውጭ ኢንቨስትመንት ክፍት እንድናደርግ ጫና እየተደረገብን ይገኛል” ብለዋል፡፡
መንግስት ጉዳዩን በጥንቃቄ እንደሚይዘው ሚኒስትሩ ጠቅሰው፣ ከአለም የንግድ ድርጅት አባልነት ጋር በተያያዘ አስገዳጅ ቅድመ ሁኔታዎች የሚቀርቡ ከሆነ፣ አገሪቱ በ2015 አባል ለመሆን የያዘችውን ዕቅድ ልታራዝም ትችላለች ብለዋል፡፡
ከሁለት አመታት በፊት የጸደቀው የአለም የንግድ ድርጅት አዲስ ህግ፣ የእድገት ደረጃቸው እጅግ አነስተኛ የሆኑ የአለም አገራት የድርጅቱ አባል ለመሆን የሚችሉበትን መስፈርት በመጠኑ ቀለል እንዳደረገ የዘገበው ሮይተርስ፤ ድሃ አገራት የተለያዩ ዘርፎችን ቀስ በቀስ ወደ ግል ኢንቨስትመንት እንዲያዘዋውሩና ደረጃ በደረጃ ለአለማቀፍ ውድድር ክፍት እንዲያደርጉ የሚፈቅድ መሆኑን አስታውሷል፡፡
“የትኞቹ የአገሪቱ ህጎች ከአለም የንግድ ድርጅት ጋር እንደሚጣጣሙና፣ የትኞቹ እንደሚጣረሱ እየገመገምን ነው” ያሉት አቶ ከበደ፤ “እ.ኤ.አ በ2015 የንግድ ድርጅቱ አባል ለመሆን የያዝነው ዕቅድ ሊራዘም ይችላል” ብለዋል፡፡
አሁን ባለበት ሁኔታ አገሪቱን የአለም የንግድ ድርጅት አባል ለማድረግ ኢኮኖሚው አነስተኛ እንደሆነና የበለጠ ማደግ እንደሚገባው የገለጹት ሚኒስትሩ፤ ከፍተኛ የኢኮኖሚ ደረጃ ላይ የምትገኘው ቻይና፣ የአለም የንግድ ድርጅትን አባል  ለመሆን በርካታ አመታት ወስዶባታል ብለዋል፡፡
በፍጥነት በማደግ ላይ የሚገኘው የአገሪቱ ገበያ በተለይ በአምራች ኢንዱስትሪው ዘርፍ የውጭ አገራት ባለሃብቶችን መሳብ በመቻሉ፣ በርካታ የስዊድን፣ የቻይና እና የቱርክ ባለሃብቶች በዘርፉ ሰፊ ስራ እያከናወኑ እንደሚገኙ የጠቆመው የሮይተርስ ዘገባ፤ የአገሪቱ ህጎች የቴሌኮም እና የባንክ አገልግሎት በመሳሰሉ ፖለቲካዊ ችግር ሊያስከትሉ ይችላሉ ተብለው በሚታሰቡ ዘርፎች የውጭ ኢንቨስትመንትን ያግዳሉ ብሏል፡፡

ካቻምናም ታፍኛለሁ፣ ዘንድሮ ግን በህግ እጠይቃለሁ ብሏል

ተቀማጭነቱን በሳዑዲ አረቢያ ያደረገውና በርካታ የቴሌቪዥን ጣቢያዎችን በተለያዩ የዓለም ክፍሎች የሚያሰራጨው የአረብ ሳተላይት ኮሙኒኬሽን ተቋም (አረብሳት) ካለፈው ሳምንት ጀምሮ እየተፈጸመበት ያለው ዓለማቀፍ የሳተላይት ሞገድ አፈና (Jamming) ምንጩ ከኢትዮጵያ መሆኑን እንዳረጋገጠ ገለጸ፡፡
ሳትኒውስ የተባለው የአገሪቱ የዜና ምንጭ ከትናንት በስቲያ እንደዘገበው፣ አረብሳት በሚያስተላልፋቸው በርካታ የቴሌቪዝን ጣቢያዎቹ ላይ መታየት የጀመረውን የስርጭት መስተጓጎል መነሻ ለማወቅ ባደረገው በረቂቅ ቴክኖሎጂ የታገዘ ጥናት፣ ከኢትዮጵያ ግዛት ውስጥ የሚነሳና ሆን ተብሎ የሚፈጸም የሳተላይት ሞገድ አፈና (Jamming) እየተደረገበት መሆኑን ማረጋገጡን አስታውቋል፡፡ ይህን መሰሉ ህገወጥ ድርጊት መፈፀሙ መሆኑ እጅግ እንዳሳዘነው ያስታወቀው አረብሳት፤ ከኢትዮጵያም ሆነ ከኤርትራ የሚተላለፍ ምንም አይነት ስርጭት ሳይኖረው፣ የሳተላይት ሞገድ አፈና መደረጉ እንቆቅልሽ እንደሆነበት ገልጿል፡፡
የሳተላይት ሞገድ አፈናው፣ ምናልባትም ከሁለቱ አገራት የአንዱ ተቀናቃኝ የሆኑና ከአረብሳት ሳተላይቶች አቅራቢያ በሚገኙ ሳተላይቶች አማካይነት የሚሰራጩ የቴሌቪዝን ጣቢያዎችን ለማፈን የታለመ ሊሆን እንደሚችል ያለውን ግምትም ሰጥቷል፡፡
እየተፈጸመበት ያለውን ህገወጥ ተግባር ለመመከት በብሄራዊና በአለማቀፍ ደረጃ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን የገለጸው አረብሳት፣ ጉዳዩን ለዓለማቀፉ የቴሌኮምኒኬሽን ህብረት እና ለአረብ ሊግ ማሳወቁንም ጠቅሷል፡፡አረብሳት ጉዳዩን በቀጣይ ከመረመረ በኋላ፣ ከአለማቀፍ የህግ  ተቋማትና የአገሪቱ የህግ አካላት ጋር በመቀናጀት ወደ ህግ እንደሚያመራና እየተቃጣበት ባለው የሳተላይት ሞገድ አፈና ለደረሰበትም ሆነ ለሚደርስበት ጉዳት ካሳ እንደሚጠይቅ  ማቀዱን ተናግሯል፡፡ከሁለት አመታት በፊት ከኢትዮጵያ ተመሳሳይ የሳተላይት ሞገድ አፈና እንደተፈጸመበትም አስታውሷል።

በአዲስ አበባ ገርጂ አካባቢ በሚገኘው የኢትዮ ፓረንትስ ት/ቤት የ11ኛ ክፍል ተማሪ የሆነችው ታዳጊ፤ የት/ቤቱን ዩኒት ሊደር አቶ ወንደሰን ተሾመን ሦስት ቦታ በጩቤ በመውጋት ተጠርጥራ በፖሊስ ቁጥጥር ስር ስትውል፣ ተጐጂው በኮርያ ሆስፒታል በህክምና ላይ እንደሚገኙ ምንጮች ጠቆሙ፡፡ ለት/ቤቱ አዲስ ነች የተባለችው ተማሪ ትናንት ከጠዋቱ 5፡30 ላይ ወደ ዩኒት ሊደሩ ቢሮ ለቤተሰብ ስልክ ደውልልኝ በማለት ከገባች በኋላ አደጋውን እንዳደረሰች ታውቋል፡፡ ተማሪዋ አስተማሪውን ለምን በጩቤ እንደወጋች እስካሁን አልታወቀም።
አደጋው የደረሰባቸው የት/ቤቱ ዩኒት ሊደር አቶ ወንድወሰን ተሾመ፤ ከመምህርነታቸው በተጨማሪ፣ የኢትዮጵያ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢዴፓ) የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ እንደሆኑ ታውቋል።

የተከሳሾች መቃወሚያ ውድቅ ሆኗል

የፌደራሉ ከፍተኛ ፍ/ቤት 15ኛ ወ/ችሎት የሙስና ክስ የቀረበባቸውን የቀድሞ ገቢዎችና ጉምሩክ ዋና ዳይሬክተር አቶ መላኩ ፈንታንና በሶስት መዝገቦች የተከሰሱ ሌሎች ተከሳሾችን የክስ መቃወሚያና የአቃቤ ህግን ምላሽ መርምሮ በትናንትናው እለት ብይን ሰጠ፡፡ ፍ/ቤቱ አብዛኛውን የተከሳሾችን መቃወሚያ ውድቅ አድርጓል፡፡
ፍ/ቤቱ ብይኑን ከመስጠቱ በፊት ተከሳሾቹ ያመለከቱትን የክስ መቃወሚያና የአቃቤ ህግን ምላሽ አስታውሷል፡፡
በመዝገቡ 1ኛ ተጠሪ የሆኑት አቶ መላኩ በዚህ መዝገብ በቀረቡባቸው ክሶች፤ የቀረቡብኝ ክሶች በስነ ስርአት ህጉ አንቀፆች መሰረት የተሟሉ አይደሉም፣ ከባለስልጣናት ጋር በመመሳጠር ክስ አንስተሃል ለተባልኩት ኃላፊነት የለብኝም” የሚሉና ሌሎች መቃወሚያዎችን ያስታወሰው ችሎቱ፤ አቶ ገ/ዋህድ በበኩላቸው፤ “በተነሱና በተቋረጡ ክሶች ልጠየቅ አይገባም፤ ክሶችን እንዳነሣ አዋጁም ይፈቅድልኛል፤ ከተፈቀደልኝ ወሰን በላይ ህግ አልጣስኩም” ማለታቸውን ጠቁሟል፡፡
ሌሎች በመዝገቡ የተካተቱ ተከሳሾች “የቀረበው ክስና ማስረጃ ግልፅ አይደለም፣ በተሻረ የህግ አንቀፅ ተከሰናል፣ ኮሚሽኑ በማይመለከተው ስልጣንና በሌለው ውክልና ነው የከሰሰን፣ ክሱ የገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ነው” የሚሉና ሌሎች በርካታ መቃወሚያዎች እንዳቀረቡም ችሎቱ አስታውሷል፡፡
ለተከሳሾቹ መቃወሚያ ከአቃቤ ህግ ከተሰጡ ምላሾች መካከልም፤ ከማስረጃና ከክስ ጭብጥ ጋር ተያይዞ የቀረቡት መቃወሚያዎች በብይን ሳይሆን በክርክር ሂደት ነው መታየት ያለባቸው የሚለው ይገኝበታል፡፡
እነ አቶ መላኩ በእርግጥም ክስ የማንሳት ስልጣን በአዋጅ እንደተሰጣቸው የጠቀሰው አቃቤ ህግ፤ ነገር ግን ተከሳሾቹ ከተፈቀደላቸው የህግ ወሰን በላይ የተሰጣቸውን መብት ተጠቅመዋል ሲል ምላሽ ሰጥቷል፡፡ ሁሉም ተከሳሾች ያቀረቡት የክስ መቃወሚያም ሙሉ ለሙሉ ውድቅ እንዲደረግለት አቃቤ ህግ የጠየቁ ሲሆን፡፡
የግራ ቀኙን መከራከሪያ ሲመረምር መቆየቱን ያስታወሰው ፍ/ቤቱም፤ በዚህ መዝገብ ላይ ክሱ መስፈርቱን አሟልቶ መቅረቡን እንዲሁም ገቢዎችና ጉምሩክ ለፀረ-ሙስና ኮሚሽን ውክልና መስጠት እንደሚችል በመግለፅ በመዝገቡ ከተጠቀሱት 93 ክሶች 90ዎቹ ባሉበት እንዲቀጥሉ ሶስቱ ተሻሽለው እንዲቀርቡ በይኗል፡፡
ፍ/ቤቱ ቀጣይ ሂደቱን ለማየት ሁሉንም መዝገቦች ለሰኔ 3 ቀን 2006 ዓ.ም ቀጥሯል፡፡

ህብረት ባንክ ለሚያስገነባው ባለ 32 ፎቅ ህንፃ፣ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ንግድ ስራ ኮሌጅ ፊት ለፊት በሚገኝ ቦታ ላይ የመሰረት ድንጋይ ተጣለ፡፡
የባንኩን ዘመናዊ ህንፃ ዲዛይን ለማድረግ ከ40 በላይ የኪነ-ህንፃ ባለሙያዎች የተወዳደሩ ሲሆን ህንፃው ባለ 4 ደርዝ የምድር ውስጥ የመኪና ማቆሚያ እንደሚኖረው ተገልጿል፡፡
ከትናንት በስቲያ የመሰረት ድንጋይ የመጣል ስነ-ስርአት ላይ ንግግር ያደረጉት የባንኩ ፕሬዚዳንት አቶ ታዬ ዲበኩሉ፤ ባንኩ ከእለት ወደ እለት በሁሉም ረገድ እያደገ መምጣቱን ጠቅሰው፤ የራሱን ዋና መስሪያ ቤት ህንፃ ማስገንባቱ በህብረተሰቡ ዘንድ የገነባውን መልካም ስምና ዝና ወደ ላቀ ደረጃ እንዲያሸጋግር ያግዘዋል ብለዋል፡፡
በስነ-ስርአቱ ላይ በክብር እንግድነት የተገኘው አትሌት ኃይሌ ገብረሥላሴ በበኩሉ፤ ባንኩ በግሉ ሴክተር የተሰማሩ ባለሀብቶችን በመደገፍ ከሚያደርገው ዘርፈ ብዙ ጥረት ጎን ለጎን አቅሙን በከፍተኛ ሁኔታ እያሳደገ መሆኑን ጠቁሞ፣ ህንፃው መገንባቱ የሚጠበቅና አስፈላጊም ጭምር ነው ብሏል፡፡  

ከኦስትሪያ የሚመጡት አሰልጣኝ በቀን 28 ሺ ብር ይከፈላቸዋል

ለዳቦና ኬክ ምርቶች ጥሬ እቃዎችን በማቅረብ የሚታወቀው ዴልታ የማምረቻና የንግድ ኩባንያ፤ የኢትዮጵያ የዳቦና የኬክ ሼፎችን በውጭ ባለሙያ ሊያሰለጥን እንደሆነ ተገለፀ፡፡ ከኦስትሪያ ቪየና የሚመጡት የዳቦና የኬክ ሥራ አሰልጣኝ ሚስተር ገንተር ኮክሲደር፤ በቀን 28 ሺህ ብር እንደሚከፈላቸው ታውቋል፡፡
ስልጠናው የሚሰጠው በክልልና በአዲስ አበባ የሚገኙ ሆቴሎች ለሚልኳቸው የዳቦና የኬክ ሼፎች ሲሆን በሀርመኒ ሆቴል በሚሰጠው ስልጠና ላይ በቀን 30 ሼፎችን በነፃ ለማሰልጠን መዘጋጀታቸውን የዴልታ ኩባንያ ባለቤትና ስራ አስኪያጅ አቶ አደም ሙዲ ገልፀዋል፡፡ ከ10 አይነት በላይ በሆኑ የኬኮችና የዳቦ አይነቶች አሰራር ላይ የሚሰጠው ስልጠና፤ በአገራችን የሚመረተውን የኬክና የዳቦ የጥራት ደረጃ በማሳደግ፣ ከየትኛውም አለም ለሚመጡ ሰዎች የሚመጥን እንዲሆን ያስችላል ተብሏል፡፡
ዴልታ ኩባንያ፤ የኬክና የዳቦ ምርቶችን ጥራት ባለው ደረጃ ለማምረት የሚስችል ፋብሪካ እየገነባ እንደሆነ የጠቆሙት አቶ አደም፤ ፋብሪካው የስልጠና ማዕከል እንደሚያካትትም ገልፀዋል፡፡ ከፍተኛ ገንዘብ አውጥተው ሥልጠና ለመስጠት ምን እንዳሳሰባቸው የተጠየቁት የዴልታ ኩባንያ ባለቤትና ሥራ አስኪጅ አቶ አደም ሲመልሱ፤ “ከውጭ የምናስገባቸው ለኬክና ለዳቦ ምርት የሚውሉ ጥሬ እቃዎች ጥሩ ሙያተኞች ጋ ካልደረሱ እኛ ዋጋ እናጣለን፤ ለዚህ ነው ባለሙያዎችን ለማሰልጠን የወሰንነው” ብለዋል፡፡ ስልጠናው የተዘጋጀው ጥሬ እቃ ከውጭ ከሚልኩላቸው ድርጅቶች ጋር በመተባበር እንደሆነም ጨምረው ገልፀዋል፡፡

ለበርካታ አመታት በኢትዮጵያ የተለያዩ አካባቢዎች ሰፋፊ የምግባረ ሰናይ ስራዎችን በመስራት የሚታወቀው ‘ሰዎች ለሰዎች’ (Menschen für Menschen) የበጎ አድራጎት ድርጅት መስራች ኦስትሪያዊው በጎ አድራጊና ታዋቂ የፊልም ተዋናይ ካርልሀይንስ በም፣ ከትናንት በስቲያ በ86 አመታቸው አረፉ።
ባለፈው አመት የአልዛይመር በሽታ ተጠቂ መሆናቸው በይፋ የተነገረ ሲሆን ህክምናቸውን ሲከታተሉ ቆይተው፣ ከትናንት በስቲያ ምሽት በኦስትሪያ ከሳልዝቡር አቅራቢያ በምትገኘው ግሮዲግ ከተማ፣ በመኖሪያ ቤታቸው ህይወታቸው ማለፉን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘግቧል፡፡
እ.ኤ.አ በ1928 ጀርመን ዳርምስታድ ውስጥ የተወለዱት ካርልሀይንስ በም፣ በስነጥበብ ታሪክና በትወና ትምህርታቸውን የተከታተሉ ሲሆን ለረጅም አመታት በፊልም ትወና ሙያ ተሰማርተው በርካታ ስራዎችን አከናውነዋል፡፡
እ.ኤ.አ በ1981 ወደ ኢትዮጵያ በመምጣት ‘ሰዎች ለሰዎች’ (Menschen für Menschen) የተባለውን የበጎ አድራጎት ድርጅት በመመስረትና በመምራት፣ በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች ብዙዎችን ተጠቃሚ ያደረጉ ከትምህርት፣ ከጤናና ከሌሎች ዘርፈ ብዙ ጉዳዮች ጋር የተያያዙ ስራዎችን በማከናወን ይታወቃሉ፡፡
‘ሰዎች ለሰዎች’ን ለረጅም ጊዜያት ሲመሩ የቆዩት ባለቤታቸው ወ/ሮ አልማዝ፣ ካለፈው ታህሳስ ወር ጀምሮ ድርጅቱን የማስተዳደሩን ሃላፊነት ለሌሎች አስረክበው ወደ ኦስትሪያ በመሄድ ባለቤታቸውን ሲያስታምሙ እንደነበር  እንደነበር መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡  
በበጎ አድራጎት ስራቸው ላከናወኑት የላቀ አስተዋጽኦ የኢትዮጵያ መንግስት በ1995 ዓ.ም የክብር ዜግነት የሰጣቸውና ሳር ቤት ተብሎ በሚጠራው አካባቢ በስማቸው አደባባይ  ተሰይሞ ሃውልት የቆመላቸው ካርልሀይንስ፣ ታዋቂዎቹን የ‘ባላንዛ የሰብዓዊነት፣ የሰላምና የወንድማማችነት ሽልማት’ እና ‘ኢሴል የማህበራዊ አስተዋጽኦ ሽልማት’ ጨምሮ፤ ከተለያዩ አገራት በርካታ የስኬትና የአገልግሎት ሽልማቶችን አግኝተዋል፡፡
ካርልሀይንስ ‘ሲሲ’፣ ‘ፎክስ ኤንድ ሂዝ ፍሬንድስ’፣ ‘ላ ፓሎማ’፣ ‘ዘ ስቶው አዌይ’ እና ‘ካም ፍላይ ዊዝ ሚ’ን ጨምሮ፤ በአሜሪካ፣ በጀርመን፣ በኦስትሪያና በሌሎች አገሮች በተሰሩ 45 ያህል ፊልሞች ላይ በመተወን ችሎታቸውን ያስመሰከሩ ተዋናይ መሆናቸውን ዘ ሆሊውድ ሪፖርተር ዘግቧል፡፡
በ1983 ዓ.ም ከኢትዮጵያዊቷ ባለቤታቸው አልማዝ ተሾመ ጋር በመሰረቱት ትዳር ሁለት ልጆችን ያፈሩት ካርልሀይንስ በም፤ ከቀድሞ ትዳሮቻቸው ያፈሯቸው አምስት ልጆች አሏቸው፡፡

ጳጳሳት የፓትርያርኩን የማኅበረ ቅዱሳን ደንብ ማሻሻያ ቅድመ ኹኔታ አልተቀበሉትም
‹‹ቅድመ ኹኔታው የማኅበሩን አገልግሎት የሚያቀጭጭና በሒደትም የሚያስቆም ነው›› /ታዛቢዎች/

የማኅበረ ቅዱሳን መተዳደሪያ ደንብ ማሻሻያ ረቂቅን እንደ አንድ አጀንዳ የያዘው የዘንድሮው የሲኖዶሱ የርክበ ካህናት ጉባኤ ከረቂቁ ጋር በተያያዘ በፓትርያርኩና በሊቃነ ጳጳሳቱ መካከል በተፈጠረ ፍጥጫ መጠናቀቁ ተገለጸ፡፡
የፍጥጫው መንሥኤ፣ በቅዱስ ሲኖዶሱ የተሠየመው የማኅበረ ቅዱሳን መተዳደርያ ደንብ አጥኚ ኮሚቴ ያዘጋጀው የማሻሻያ ረቂቅ በዝርዝር ከመታየቱ አስቀድሞ ፓትርያርኩ ለውይይቱ እንደ ቅድመ ኹኔታ ያቀረቧቸው ነጥቦች በአብዛኛው የጉባኤው አባላት የገጠመው ተቃውሞ እንደኾነ ምንጮች ጠቁመዋል፡፡
የቅ/ሲኖዶሱን ስብሰባ በርእሰ ጉባኤነት የሚመሩት ፓትርያርኩ፤ በአጀንዳው ላይ የሚካሔደውን ውይይት ቀጣይነት ይወስናል በሚል ካቀረቧቸው ቅድመ ኹኔታዎች ውስጥ÷ ለአጥኚ ኮሚቴው መመሪያ የሰጡባቸው ‹‹ልዩ ልዩ ድንጋጌዎችና ግዴታዎች›› አንድም ሳይቀነሱ በደንቡ እንዲካተቱና ረቂቁ ሕገ ቤተ ክርስቲያኑ ከጸደቀ በኋላ እንዲታይ የሚሉ እንደሚገኙበት ተመልክቷል፡፡
ፓትርያርኩ በቅድመ ኹኔታ አስቀምጠዋቸዋል በተባሉት ነጥቦች ስምምነት ላይ ከተደረሰ ስብሰባው ሊቀጥል እንደሚችል በመጥቀስ፣ ኃይለ ቃልም ተማኅፅኖም በተቀላቀለበት አኳኋን መጠየቃቸው ተዘግቧል፡፡
ይኹንና የሚበዙት ሊቃነ ጳጳሳት በቀጥታ እንደተቃወሟቸው፣ የተቀሩትም ድጋፍ ከመስጠት እንደተቆጠቡ ታውቋል፡፡ ፍጥጫው ቀጥሎ አቡነ ማትያስ ‹‹አቋሜ ይኽው ነው፤›› በሚል አጀንዳውን መዝጋታቸውን ሲያስታውቁም፣ ‹‹የማኅበረ ቅዱሳን ጉዳይ እንዲህ ተብሎ የሚተው አይደለም፤›› በሚል ከኹሉም ሊቃነ ጳጳሳት ጠንካራ ተቃውሞ እንደገጠማቸው ምንጮች ይገልፃሉ፡፡
የቅ/ሲኖዶሱ መደበኛ ስብሰባ የሚካሔደው ምልዓተ ጉባኤው ከጅምሩ ተስማምቶ ባጸደቃቸው የመነጋገርያ አጀንዳዎች መሠረት እንደኾነ በሊቃነ ጳጳሳቱ ተቃውሞ ተጠቅሷል፡፡
የማኅበሩ የመተዳደርያ ደንብ ማሻሻያ ረቂቅ እንዲቀርብ ከታዘዘበት ከጥቅምት 2005 ዓ.ም. ጀምሮ እየተንከባለለ ለኹለት ዓመታት መዘግየቱን ሊቃነ ጳጳሳቱ አስታውሰው፣ የተጓተተው አጀንዳ ‹‹የማኅበሩን አገልግሎት ያቀጭጫሉ፣ በሒደትም ያስቆማሉ›› በሚል በተተቹት የፓትርያርኩ ቅድመ ኹኔታዎች ሊዘጋ እንደማይችልና ተጨማሪ ጊዜ ሳይወስድ ቅ/ሲኖዶሱ ሊወያይበት እንደሚገባ በአጽንዖት በመናገራቸው፣ ጉዳዩ ሳይቋጭ ለቀጣዩ ቀን በይደር ተላልፏል፡፡
አጀንዳው ሰኞ፣ ግንቦት 18 ቀን 2006 ዓ.ም. ጥዋት መታየት ሲጀምር፣ አጥኚ ኮሚቴው በ37 አንቀጾችና በ34 ገጾች አሻሽሎ ያዘጋጀው የማኅበሩ መተዳደርያ ደንብና የኮሚቴው ቃለ ጉባኤ በንባብ መሰማቱም ታውቋል፡፡ ፓትርያርኩ ‹‹ልዩ ልዩ ድንጋጌዎችና ግዴታዎች›› በሚል ራሱን በቻለ ርእስ በደንቡ እንዲካተት ለአጥኚ ኮሚቴው ጥብቅ መመሪያ የሰጡበት ባለ24 አንቀጽ ሰነድም አብሮ እንዲነበብላቸው መጠየቃቸው የመጀመሪያው ቀን የፍጥጫ መነሻ እንደነበር ታውቋል፡፡
በ24 አንቀጾችና በአምስት ገጾች የተዘረዘሩት የፓትርያርኩ ልዩ ልዩ ድንጋጌዎችና ግዴታዎች÷ በአባላቱ በጎ ፈቃድ ተቋቁሞ ከፍተኛ አስተዋፅኦ በማበርከት ላይ የሚገኘውን ማኅበር፤ ከሕገ ተፈጥሮው ውጭ የሚያደርግ፣ በቅ/ሲኖዶሱ ፈቃድ ከሚመራበት ደንብ በተፃራሪ ተቋማዊ ህልውናውን፣ የአመራር ምርጫውን፣ የአባላት አያያዙንና የሥራ ቦታውን ለውጭ ተጽዕኖ አሳልፎ የሚሰጥና አጣብቂኝ ውስጥ የሚያስገባ፣ በአርኣያነት የሚጠቀሰውን የፋይናንስ አሠራሩን ወደ ኋላ የሚጎትት መኾኑን እንደተረዱ ያብራሩ አንድ የቅ/ሲኖዶሱ አባል፣ ‹‹ቀጣዩ ቀንም የከበደ ነገር ይዞ እንደሚመጣ ግልጽ ነበር፤›› ይላሉ፡፡
በይደር የተያዘው አጀንዳ በቀጣዩ ቀን ማክሰኞ ጥዋት ተጀምሮ ለግማሽ ቀን የቀጠለ ቢኾንም ፓትርያርኩና ሊቃነ ጳጳሳቱ የመተዳደርያ ደንብ ማሻሻያውን በዝርዝር ለመመልከት የሚያስችል ስምምነት ላይ ለመድረስ እንዳልቻሉ ታውቋል፡፡
‹‹ፓትርያርኩ በቅድመ ኹኔታ ያስቀመጧቸውን ነጥቦችና በአጀንዳው ቀጣይነት ላይ የያዙትን አቋም አልቀየሩም፤ ሊቃነ ጳጳሳቱም ባጸደቅነው አጀንዳ መሠረት ቅድሚያ ሰጥተን መነጋገር ያለብን የሠየምነው አጥኚ ኮሚቴ አዘጋጅቶ ባቀረበው ረቂቅ ላይ ነው፤ መካተት ያለበት ነገር ካለም ማኅበሩን በሚያሠራ መልኩ እያገናዘብን በሒደት እናየዋለን እንጂ አጀንዳው በቅድመ ኹኔታ መታሰር የለበትም በሚል ለማስረዳት ጣሩ፤ በመጨረሻም ፓትርያርኩ “እንግዲያውስ ስብሰባውን ለመምራት አልችልም” በማለታቸው የስብሰባው መቋጫ ኾኗል፤›› ይላሉ- ሒደቱን ለአዲስ አድማስ የገለጹ የስብሰባው ምንጮች፡፡
የማኅበሩ ደንብ በመጀመሪያ ረድፍ ከሰፈሩት የቅ/ሲኖዶሱ መነጋገርያ ነጥቦች አንዱ እንደነበር ያስተዋሉ ሌሎች የስብሰባው ተከታታዮች በበኩላቸው፤ አጀንዳው ከቅደም ተከተሉ ወጥቶ እየተገፋ በመጨረሻ መነሣቱ በፓትርያርኩና በሊቃነ ጳጳሳቱ መካከል ይህ ዓይነቱ አለመግባባት ሊነሣ እንደሚችል ጠቋሚ ነበር ብለዋል፡፡  
ተከታታዮቹ አክለውም፣ ፓትርያርኩ ስብሰባውን ለመምራት ፈቃደኛ ባይኾኑም በሕገ ቤተ ክርስቲያኑ በተደነገገው የቅ/ሲኖዶስ ስብሰባ ሥነ ሥርዓት መሠረት፣ ምልዓተ ጉባኤው በማኅበሩ መተዳደርያ ደንብ ማሻሻያዎች ላይ የጀመረውን ውይይት ቀጥሎ ውሳኔ ለማሳለፍ የሚችልባቸው አግባቦች እንደነበሩ ገልጸው፣ ቅ/ሲኖዶሱ በግለጫው የመጨረሻው አጀንዳው ባደረገው የማኅበሩ ደንብ ላይ “ውይይት ተደርጎበታል” ከማለት በስተቀር ስብሰባውን የቋጨበት አኳኋን ያልተለመደና አደናጋሪ ነው ብለዋል፡፡
ማኅበረ ቅዱሳን የዘመኑን ኦርቶዶክሳዊ ትውልድ አደራጅቶ ማንነቱን የሚያውቅበትንና በግብረ ገብ የሚታነፅበትን ትምህርተ ሃይማኖት ከማስተማር ባሻገር፣ የቤተ ክርስቲያኒቱ ተቋማት አገልግሎታቸውን በብቃት የሚወጡበትን ኹለገብ ሞያዊ ድጋፍ የመስጠት ሓላፊነት እንዳለበት በደንብ አጥኚ ኮሚቴው ማሻሻያ ረቂቅ ላይ መስፈሩ ታውቋል፡፡
ይኹንና ‹‹ጥበቃና ጥንቃቄ›› በሚል ፓትርያርኩ እንደ መመሪያ ያቀረቧቸው ድንጋጌዎችና ግዴታዎች እንዲሁም ከልዩ ጽ/ቤታቸው ማኅበሩን አስመልክቶ በየጊዜው የሚወጡ መመሪያዎች የማኅበሩን አገልግሎት የማቀጨጭ፣ በሒደትም አዳክሞ የማስቆም ውጤት ሊኖራቸው እንደሚችል ታዛቢዎች ያስረዳሉ፡፡
የማኅበሩ መተዳደርያ ደንብ ማሻሻያ ረቂቅ፣ ቅ/ሲኖዶሱ የማኅበሩ ደንብ እንዲሻሻል ግንቦት 14 ቀን 2004 ዓ.ም. ባካሔደው ስብሰባ÷ ማኅበሩ ከጊዜው ጋር የሚሔድ፣ አገልግሎቱና አደረጃጀቱ የደረሰበትን ስፋትና ዕድገት የሚመጥን፣ ለቤተ ክርስቲያን ኹለንተናዊ ልማት የሚጠቅም ድርጅታዊ መዋቅር እንደሚያስፈልገው ባሳለፈው ውሳኔ መሠረት አምስት ሊቃነ ጳጳሳት፣ ገለልተኛ የሕግ ባለሞያዎችና የማኅበሩ አባላት በታከሉበት አጥኚ ኮሚቴ የጋራ ጥናት የተዘጋጀ መኾኑ ተመልክቷል፡፡
በግንቦት ወር 1984 ዓ.ም. በበጎ ፈቃድ በተሰበሰቡ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች የተመሠረተው ማኅበሩ፤ እየተመራ ያለው ቅ/ሲኖዶስ በ1994 ዓ.ም. ለሦስተኛ ጊዜ አሻሽሎ በሰጠው መተዳደርያ ደንብ ሲኾን አሁን የተሻሻለው ረቂቅ ተመርምሮ ባለመጽደቁ በነባሩ ደንብ እየተመራ ለመቀጠል እንደሚገደድ ተመልክቷል፡፡

በ800 ሜትር ሳይሸነፍ 15 ወራት አልፈዋል
ዘንድሮ ለዳይመንድ ሊግ ድል ለሃትሪክ ተጠብቋል
አዲስ የዓለም ሪከርድ እንደሚያስመዘግብ ግምት ተሰጥቶታል

አትሌት መሃመድ አማን ባለፉት 15 ወራት በሮጠባቸው የ800 ውድድሮች አልተሸነፈም፡፡ ኢትዮጵያ በዓለም የአትሌቲክስ ስፖርት ላለፉት 30 ዓመታት በረጅም ርቀት ከፍተኛ ስኬት ያስመዘገቡ አትሌቶችን በማፍራት ትታወቅ ነበር፡፡ ባለፉት 5 ዓመታት ግን በ20 ዓመቱ የዓለማችን የመካከለኛ ርቀት ምርጥ ሯጭ  ኮርታለች፡፡ አትሌት መሃመድ የኢትዮጵያን የአትሌቲክስ ዝና በአዲስ ምዕራፍ ቀይሶታል፡፡
ዘንድሮ በዳይመንድ ሊግ ውድድሮች ላይ ምርጥ ብቃት ያሳያሉ ተብለው ከተጠበቁ ምርጥ አትሌቶች አንዱ የሆነው መሃመድ በዚህ የውድድር ዘመን የ800 ሜትር የዓለም ሪከርድን ሊሰብር እንደሚችል በመገመትም ላይ ነው፡፡  በእርግጥም በርቀት አይነቱ  የዓለም ንጉስ ለመባል የሚቀረው ሪከርዱን መስበር ብቻ ነው፡፡ አንዳንድ የአትሌቲክስ ባለሙያዎች አትሌቱ አሁን በያዘው ብቃት ከቀጠለ ዘንድሮ ባይሳካለት እንኳን በሚቀጥሉት ሁለት ዓመታት በዓለም አቀፍ ውድድሮች የሚኖሩት ልምዶች የዓለም ሪከርድን የሚያሻሽልበት ብቃት ላይ እንደሚያደርሱት እየመሰከሩ ናቸው፡፡ ከሁለት ሳምንት በፊት የ2014  የዳይመንድ ሊግ ውድድር በኳታር ዶሃ ሲጀመር አንፀባራቂ ከነበሩ አትሌቶች ዋናው የነበረው አትሌት መሃመድ አማን፤ በወቅቱ በ800 ሜትር ውድድር ሲያሸንፍ ያሳየው አስደናቂ የአጨራረስ ብቃት ከፍተኛ አድናቆት አጉርፎለታል፡፡ እንደውም አንዳንድ ዘገባዎች ‹‹ሱፕር አትሌት›› ብለው አግንነውታል፡፡ ይሁንና አትሌቱ ከ2013 አጋማሽ ጀምሮ በተሳተፈባቸው የ800 ሜትር ውድድሮች ሳይሸነፍ ለመቆየቱ በቂ ምክንያት በማቅረብ የሚከራከሩ አልጠፉም፡፡ በእነዚህ ተከራካሪዎች መሃመድ አማን የሚቀናቀነው የጠፋው በተለይ የርቀቱ ሁለት ምርጥ አትሌቶች ጋር ባለመገናኘቱ ነው የሚል ማስረጃ ይቀርባል፡፡ በ2012 እኤአ ላይ ለንደን ኦሎምፒክ ላይ የዓለምን ሪከርድ ያስመዘገበው የ25 ዓመቱ ኬንያዊው ዴቪድ ሩዲሻ በጉዳት ከውድድር ከራቀ ሁለት ዓመት አልፎታል፡፡ ሌላው ምርጥ አትሌት እና በእድሜው እኩያው የሆነው ደግሞ የቦትስዋናው ኒጄል አሞስ ሲሆን እሱም በጉዳት ከውድድር እንደራቀ ነው፡፡
በዓለም አትሌቲክስ ዘንድሮ በከፍተኛ ጉጉት ከሚጠበቁ ትንቅንቆች ዋንኛው መሃመድ አማን ፤ ኒጄል አሞስ እና ዴቪድ ሩዲሻ የሚገናኙበት የ800 ሜትር  ፍጥጫ እንደሆነ ይገለፃል፡፡ ሶስቱ አትሌቶች በዳይመንድ ሊግ መገናኘታቸው እየተጠበቀ ሲሆን በተለይ ከሳምንት በኋላ በአሜሪካዋ ከተማ ዩጂን፤ የሚደረገው የፕሮፎንታይኔ ክላሲክስ ላይ ከተገናኙ አስገራሚ ፉክክር እንደሚኖራቸው   ተገምቷል፡፡ የ800 ሜትር የዓለም ሪከርድ በዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌደሬሽኖች ማህበር በኦፊሴላዊ ደረጃ መመዝገብ የተጀመረው በ1952 እኤአ ነው፡፡ የመጀመርያው ሪከርድ በአሜሪካዊው አትሌት ቴድ ሜሪንዴዝ በ1.51 ደቂቃዎች የተመዘገበ ሲሆን ከዚሁ ሪኮርድ በኋላ 24 ጊዜ ሰዓቱ ሲሻሻል በርካታ እንግሊዛዊያንና አሜካዊያን አስተዋኝኦ ነበራቸው፡፡ ከ2008 ጀምሮ የተመዘገቡ ሦስት ሪኮርዶችን ማስመዝገብ የቻለው ኬንያዊው ዴቪድ ሩዲሻ ሲሆን የወቅቱ ሪከርድ ከ2 ዓመት በፊት በለንደን ኦሎምፒክ  በ1 ደቂቃ ከ41.54 ሰኮንዶች ያስመዘገበው ነው፡፡ አትሌት መሃመድ አማን ዘንድሮ በርቀቱ ሪከርድ ለመስበር  ፍላጐት እንዳለው በይፋ የተናገረው ነገር ባይኖርም የራሱን ምርጥ ሰዓት ወይንም የኢትዮጵያን ሪከርድ ለ7ኛ ጊዜ ለማሻሻል ያስባል፡፡ 800 ሜትርን ከ1.40 ደቂቃ በታች እንደሚገባም ያምናል፡፡

ምርጥ ሰዓቶቹ- በ800 ሜትር 1፡42.37 ቤልጅዬም ብራሰልስ  በ2013 እኤአ የተመዘገበ ሰዓት ሲሆን የኢትዮጵያ ሪከርድ ነው፡፡ በ800 ሜትር የኢትዮጵያ ሪከርድን ለስድስት ጊዜያት አሻሽሏል፡፡ በ1500 ሜትር 3፡43.52 ምርጥ ሰዓት ያስመዘገበ ሲሆን በ1 ማይል ያለው ምርጥ ሰዓት ደግሞ 3፡57.14 ነው፡፡
ወቅታዊ ደረጃው- በኦልአትሌቲትክስ ድረገፅ ዘንድሮ በ800 ሜትር በ1405 ነጥብ የዓለም አንደኛ አትሌት ሲሆን በሁሉም የአትሌቲክስ የውድድር መደቦች በተመሳሳይ ነጥብ ከዓለም 8ኛ ነው፡፡ በዓለም የ800 ሜትር የምንግዜም ፈጣን ሰዓቶች ደረጃ 9ኛ ነው፡፡
ማኔጅመንት እና ስፖንሰር -የትጥቅ ስፖንሰሩ ናይኪ ሲሆን፤ ከ2009 እኤአ ጀምሮ ኤሊት ስፖርትስ ማኔጅመንት ኢንተርናሽናል ESMI በመታቀፍ እየሰራ ነው፡፡
አስደናቂ ድሎቹ- አሁን በጉዳት ላይ የሚገኘው የኬንያው አትሌት ዴቪድ ሩዲሻ የ800 ሜትር የዓለም ሪከርድን ለስድስት ጊዜያት አሻሽሏል፡፡ ግዙፉ አትሌት በሩጫ ዘመኑ ካደረጋቸው 47 ውድድሮች 45ቱን አሸንፏል፡፡ የተሸነፈባቸው ሁለት ውድድሮች የመሃመድ አማን ሁለት አስደናቂ ድሎች ናቸው፡፡ የመጀመርያው በ2011 እኤአ ላይ በጣሊያኗ ከተማ ሬቲ ያሸነፈበት ሲሆን በወቅቱ ዴቪድ ሩዲሻ ለመጀመርያ ጊዜ የተሸነፈው ከ34 ተከታታይ ድሎች በኋላ ነበር፡፡ ሁለተኛው ደግሞ በ2012 እኤአ ላይ በዙሪክ የተካሄደ የዳይመንድ ሊግ ውድድር ሲሆን በዚህ ወሳኝ ትንቅንቅ ለመጀመርያ ጊዜ የዳይመንድ ሊግ ዋንጫን ያሸነፈበት ነበር፡፡