Administrator

Administrator

Saturday, 26 April 2014 13:02

የግጥም ጥግ

ዝም ብንል ብናደባ
ዘመን ስንቱን አሸክሞን፤
የጅልነት እኮ አይደለም
እንድንቻቻል ነው ገብቶን፡፡
 ባለቅኔ ሎሬት ጸጋዬ ገ/መድኅን
ቅልስልሱ ይሁዳ
ይሁዳማ ቅልስልስ ነው
አቅፎና ደግፎ
ክርስቶስን ሰጠ
ለሞት አሳልፎ፤
የኛ ዘመን ሰው ግን
ሰቅሏችሁ ሲያበቃ
በፈገግታ ክቦ፤
አቅፎ ይስማችኋል
አይኑን በጨው አጥቦ፡፡
                                       አማኑኤል  መሀሪ
ስሙነኛ ስንኝ
የህዝቦች ልቦና
በታሪክ አንደበት፤
‹‹ንጉሥ ነህ!!›› ባለ አፉ
የሆሳዕና ለት፤
‹‹ስቀለው!!!›› ይልሀል
ውሎ አድሮ እንደ ዘበት፡፡
                                        ፈለቀ  አበበ                           


        በየመን በረሃ የአልቃይዳ ድብቅ ካምፕ ውስጥ የነበሩ 55 የቡድኑ መሪዎችና ታጣቂዎች ሰሞኑን መገደላቸውን የዘገበው አሶሼትድ ፕሬስ፣ ጥቃቱ የተፈፀመው በአሜሪካ ሰው አልባ አውሮፕላን (ድሮን) እንደሆነ ገልጿል፡፡
የአሜሪካ ሰው አልባ አውሮፕላኖች ከነባር የስለላ ቅኝት በተጨማሪ የሚሳኤል ጥቃት መፈፀም የጀመሩት በቀድሞው ፕሬዚዳንት ጆርጅ ቡሽ ትዕዛዝ ቢሆንም፤ የአውሮፕላኖቹ ስምሪት እጥፍ ድርብ የተበራከተው በፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ዘመን ነው - በአፍጋኒስታን፣ በኢራቅ፣ በፓኪስታን፣ በየመን፣ በሶማሊያ፣ በሊቢያ ወዘተ፡፡
የሰው አልባ አውሮፕላኖች ስምሪት ለማበርከትም ነው፤ አውሮፕላኖቹን የሚቆጣጠሩ አብራሪዎችም በብዛት እየሰለጠኑ ሲመረቁ የቆዩት፡፡ ዛሬ ወደ 10ሺ ከሚጠጉ የአሜሪካ የጦር አውሮፕላን አብራሪዎች መካከል 5ሺ ያህሎቹ ሰው አልባ አውሮፕላኖችን ለመቆጣጠር የሰለጠኑ ፓይለቶች ናቸው፡፡
አሜሪካ የጦር ካምፕ ውስጥ በኮምፒዩተሮች ቁሳቁሶችና ስክሪኖች ያሸበረቀ ቢሮ ውስጥ በስራ የተጠመዱት የድሮን ፓይለቶች፤ ጌም የሚጫወቱ ነው የሚመስሉት፡፡ ግን የምር ጦርነት ውስጥ ናቸው፡፡ በየመን ሰማይ የስለላ ካሜራዎችንና ሚሳዬሎችን የተሸከመ ሰው አልባ አውሮፕላን አልቃይዳ ካምፕ ላይ ጥቃት እንዲሰነዝር ትዕዛዝ እየሰጡት ነው፡፡
ከአስር ሺ ኪሎ ሜትር ርቀት ሆነው ይዋጋሉ፡፡ ምን አለፋችሁ? የአልቃይዳ ዋና መሪዎችና ወታደራዊ መሪዎች በአብዛኛው የተገደሉት በድሮን ሚሳዬል ነው፡፡ ውጤታማነታቸውን በማየትም፤ የአሜሪካ ኮንግረስ፣ ለውጤታማ ድሮን አብራሪዎች የጦር ሜዳ ኒሻን ለመስጠት የሚያስችል ህግ አዘጋጅቷል፡፡ በአካል የጦር ሜዳን ባይረግጡም፤ ለውጊያ አደጋዎች ባይጋለጡም፤ በውጊያ የጦርነት ድል ሲያስመዘግቡ የጀብድ ኒሻን ሊበረከትላቸው እንደሚገባ ይገልፃል - አዲሱ ህግ፡፡ ግን በዚሁ የሚያበቃ አይመስልም፡፡ የዛሬዎቹ ሰው አልባ የጦር አውሮፕላኖች፣ የርቀት ተቆጣጣሪ ፓይለት ያስፈልጋቸዋል፡፡
አሁን እየተሰሩ የሚገኙ አዳዲስ የጦር አውሮፕላኖች ግን የርቀት ተቆጣጣሪ ፓይለት አያስፈልጋቸውም፡፡ ራሳቸው ችለውታል እኮ! ሃላፊነት እየተቀበሉ የመሰማራትና ወታደራዊ እርምጃ የመውሰድ አቅም አላቸው፡፡ ያኔስ የጀብድ ኒሻንና ወታደራዊ ማዕረግ ለማን ይበረከታል? ለአውሮፕላኖቹ፡፡

       ከኢትዮጵያ በእጥፍ የሚበልጥ ሕዝብ የያዘችው ናይጄሪያ በአንድ ምሽት፣ ተዓምረኛ የኢኮኖሚ እድገት አስመዘገበች - 90 በመቶ እድገት። እውነት ነው። ግን፣ “አስመዘገበች” የሚለውን ቃል በቸልታ አትዝለሉት።
ነገሩ ቀላል አይደለም። በፈጣን እድገት እየተንደረደረች መሆኗ የሚነገርላት ኢትዮጵያ፣ አሁን ካለችበት ደረጃ ተነስታ በተዓምረኛ ፍጥነት የ90 በመቶ እድገት እውን ለማድረግ፣ ሰባት አመታት ይፈጅባታል - ከ2500 ቀናት በላይ መሆኑ ነው።
ዎልስትሪት ጆርናል (wsj) እንደዘገበው፤ እስከ መጋቢት 20 ቀን ድረስ፣ በጠቅላላ የኢኮኖሚ ምርት፣ ደቡብ አፍሪካ የአህጉሩ ቀዳሚ ነበረች። የደቡብ አፍሪካ አመታዊ የምርት መጠን 370 ቢሊዮን ዶላር ይገመታል። ከኢትዮጵያ በአስር እጥፍ የሚበልጥ ማለት ነው። በሁለተኛ ደረጃ ላይ ደግሞ ናይጄሪያ ነበረች - በ270 ቢሊዮን ዶላር አመታዊ ምርት።
ይሄ የደረጃ ሰንጠረዥ ከመጋቢት 21 ቀን በኋላ ተቀይሯል። ናይጄሪያ በጠቅላላ አመታዊ ምርት፣ የአፍሪካ ቁንጮ መሆኗን አውጃለች - ለዚያውም በሰፊ ልዩነት። የአገሪቱ አመታዊ ምርት 510 ቢሊዮን ዶላር እንደሆነ ነው የተገለፀው። በሌላ አነጋገር፤ ናይጄሪያ በአንድ ምሽት የ240 ቢሊዮን ዶላር (ወደ ሩብ ትሪሊዮን ዶላር የተጠጋ) እድገት አስመዝግባለች። ኢትዮጵያ በፈጣን እድገት ብትገሰግስ፣ አመታዊ ምርቷ ሩብ ትሪሊዮን ዶላር የሚደርሰው ከ20 ዓመት በኋላ ነው። በናይጄሪያ የአንድ ምሽት ጉዳይ ሆኗል።
ጉደኛውን የናይጄሪያ ዜና የዘገቡ እነ wsj እና ዘ ኢኮኖሚስት የመሳሰሉ የሚዲያ ተቋማት፤ ነገሩ ትንግርት ወይም ምትሃት እንደሚመስል ገልፀዋል። ግን፣ “ሐሰት ነው” ወይም “ስህተት ነው” ብለው አልተቹም። የናይጄሪያ አመታዊ ምርት፣ ከግማሽ ትሪሊዮን በላይ ነው በሚል ተስማምተዋል።
ግን፤ በምንኖርባት ዓለምም ሆነ በሌላ ዓለም፤ “ተዓምር”፣ “ትንግርት”፣ “ምትሃት” የሚባል ነገር የለም። እና ናይጄሪያ በአንድ ምሽት ያስመዘገበችው ወደ ሩብ ትሪሊዮን ዶላር የተጠጋ እድገት፣ “የናይጄሪያ ብሔራዊ ተዓምራት” ውስጥ የማይካተት ከሆነ ምን ተብሎ ሊሰየም ነው? ትክክለኛው ስያሜ፣ “የናይጄሪያ መንግስታዊ ዝርክርክነት” የሚል ነው።
የአንድ አገር አመታዊ ምርት ምን ያህል እንደደረሰ የሚታወቀው፣ ጓዳ ጎድጓዳውን፣ ፋብሪካና ገበያውን፣ የእርሻ ማሳና የከብቶች በረትን ሁሉ እያግበሰበሱ ቆጠራ በማካሄድ አይደለም። በየአመቱ አገር ምድሩን ማሰስ አይቻልም። ታዲያ በመላ አገሪቱ፣ 15 ሚሊዮን የገበሬ ቤተሰቦች ቢኖሩ፤ የሁሉንም አመታዊ ምርት በድምር ለማወቅ ምን መላ አለ? ለምሳሌ፣ ከአንድ ሺ ገበሬዎች መሃል የአንዱ ገበሬ ምርት ላይ በማተኮር ጥናት ማካሄድና በአንድ ሺ ማባዛት ነው መፍትሄው። በዚህ የናሙና ጥናት፣ የ15ሺ ገበሬዎችን የምርት መጠን ላይ መረጃ ይሰባሰባል። ከዚያ፤ ይህ ውጤት በአንድ ሺ ይባዛል - ጠቅላላ የአገሪቱ ገበሬዎች አመታዊ ምርት ለማወቅ። በአንድ ሺ ማባዛት የሚያስፈልገው፤ የአንድ ገበሬ ምርት፣ የአንድ ሺ ገበሬዎችን ምርት ይወክላል ከሚል የጥናት መነሻ ስለተነሳን ነው።
አስር ሺ ትልልቅና ትናንሽ ፋብሪካዎች ቢኖሩ፤ የአንድ ሺ ናሙና ፋብሪካዎችን እንቅስቃሴ በማጥናት በመቶ ማባዛት ይቻላል። የትራንስፖርት፣  የጤና፣ የስልክ፣ የኤሌክትሪክ፣ የባንክ፣ የሸቀጥ አቅርቦት የመሳሰሉ አገልግሎቶችም ላይ ተመሳሳይ የናሙና ጥናት ይካሄድና፤ እንደ ውክልናው ክብደት (weighted mean) በመቶም ይሁን በሺ  እያባዛን ጠቅላላ አመታዊ የአገልግሎት ወይም የምርት መጠን ላይ እንደርሳለን። በሌላ አነጋገር፤ እያንዳንዱ ዘርፍና ንዑስ ዘርፍ፤ እያንዳንዱ አካባቢና መረጃ ... ከላይ እስከ ታች በኢኮኖሚ ውስጥ ምን ያህል ድርሻ እንዳለው በቅጡ ተገንዘበን፣ እንደ የድርሻ ተገቢውን የውክልና ክብደት እስከሰጠነው ድረስ፤ አስተማማኝ ቀመርና ስሌት ይኖረናል ማለት ነው።
በሆነ ምክንያት፣ የውክልናው መጠን ወይም ክብደት ከአመት አመት ቢቀያየርስ? ከጊዜ ወደ ጊዜ ብዙ ነገሮች እንደሚቀየሩ አይካድም። የሕዝብ ብዛትን መጥቀስ ይቻላል። ግን ችግር የለውም። በየአመቱ የሚከሰቱና የተለመዱ ጥቃቅን ለውጦችን ሳንዘነጋ በቀመራችንና በስሌታችን ውስጥ በማስገባት መስመር እናስይዘዋለን። በየአመቱ የገጠር የሕዝብ ብዛት በምን ያህል እንደሚጨምር ይታወቃላ። ግን ባልተለመደ ሁኔታና ፍጥነት፤ ለምሳሌ የአገሪቱ የገበሬዎች ብዛት ወደ አስር ሚሊዮን ቢቀንስ ወይም ወደ ሃያ ሚሊዮን ቢያሻቅብስ? ያኔ ለናሙና ጥናት የምንጠቀምበት ቀመርና ስሌት ላይ ችግር ይፈጠራል። ለምሳሌ፤ ከሃያ አመት በፊት፣ የአበባ እርሻ በአገሪቱ ኢኮኖሚ ውስጥ ከቁጥር የሚገባ ድርሻ አልነበረውም።
የፊልምና የቪዲዮ ዝግጅትም እንዲሁ። የዛሬውን የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ፤ በቀድሞው ቀመርና ስሌት ለመመዘን ስንሞክር፣ የምናገኘው ውጤት የተሳሳተ ይሆናል። የናይጄሪያ መንግስት ሲጠቀምበት የቆየው ቀመርና ስሌትም እንዲሁ፤ ከሃያ አመታት በፊት የነበረውን የኢኮኖሚ መዋቅር ላይ የተመሰረተ ስለሆነ የዛሬውን ሁኔታ በትክክል የማሳየት አቅም አልነበረውም። በናይጄሪያ ባልተለመደ ፍጥነት የተስፋፉት የቴሌኮምና የባንክ አገልግሎት፤ የቴክኖሎጂና የኮንስትራክሽን ቢዝነስ፣ እንዲሁም የፊልምና የቪዲዮ ሥራዎች፤ በኢኮኖሚ ውስጥ ያላቸው ድርሻ እየፈረጠመ መጥቷል። ለሃያ አመታት ያልተለወጠው የመንግስት ቀመርና ስሌት ግን፤ በኢኮኖሚ ውስጥ እየጎሉ ለመጡት ለውጦች ተመጣጣኝ የውክልና ክብደት የሚሰጥ አይደለም። እናም የአገሪቱን አመታዊ ጠቅላላ ምርት በትክክል የማወቅ ወይም የመገመት አቅም አልነበረውም። በየአመቱም የግምቱ ስህተት እየተደራረበ ነው የመጣው። ከሳምንት በፊት የመንግስት ቀመርና ስሌት ተለወጠ። ለሃያ አመታት የተጠራቀመው ስህተትም ተስተካከለ። ይሄ ተዐምር አይደለም። ለበርካታ አመታት የዘለቀ ዝርክርክነት እንጂ።

“ካዛኪስታን” የምትባለውን አገር እስከነመፈጠሯ ባታውቋት ችግር የለውም፡፡ የትም ብትሄዱ፣ የካዛኮችን ምድር የሚያውቅ ብዙ አታገኙም፡፡ እንዲያውም፤ ቱሪስቶች ወደ አገራችን ዝር የማይሉት ለምንድነው በማለት የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ማማረር ከጀመሩ ውለው አድረዋል፡፡ ለነገሩ እንኳን በአካል ይቅርና ካዛኪስታንን በስም የሚያውቁ ሰዎች ጥቂት ናቸው፡፡ እነዚህ ጥቂት ሰዎችስ እንዴት አወቋት? እንግሊዛዊው ኮሜዲያን “ቦራት”፣ በካዛኪስታን ላይ የሚሳለቅ ፊልም ስለሰራ ነው፡፡
ፊልሙ በመላው አለም መታየት የጀመረ ጊዜ፣ የካዛኪስታን መንግስት የእገዳ መመሪያ አውጥቶ ነበር፡፡ ለምን መሰላችሁ? በካዛኮች ምድር፣ ያለመንግስት ፈቃድ፣ ያለ ባለስልጣን ይሁንታ መጽሐፍ ማሳተምም ሆነ ፊልም መሥራት አይቻልም፡፡ በአገራችን በደርግ ዘመን እንደነበረው፤ በሳንሱር ጽ/ቤት ታይቶና ተመርምሮ፣ ተቆራርጦና ተበርዞ ነው ለፊልምና ለመጽሐፍ ዝግጅት ፈቃድ የሚሰጠው፡፡ ያው፣ ካዛኪስታንም እንደኛው አገር፣ በኮሙኒዝም ውስጥ የነበረች እና በራሺያ ቅኝ ግዛት ስር የቆየች አገር ስለሆነች፣ የሳንሱር አሰራር ገና አልለቀቃቸውም፡፡ አሁንም የመንግስት ስልጣን በአንድ ፓርቲና በአንድ መሪ የተያዘ ነው፡፡ አሁንም ኢኮኖሚው በአብዛኛው በመንግስት ቁጥጥር ስር ነው፡፡ ቱሪስት እና ኢንቨስተር ወደ ካዛኪስታን ዝር የማይለው በዚህ ምክንያት አይደለም እንዴ?!
የአገሪቱ ፕሬዚዳንት በዚህ አይስማሙም፡፡ አንደኛው ችግር የአገሪቱ የህዝብ ቁጥር 7 ሚሊዮን ብቻ መሆኑ ነው ይላሉ ፕሬዚዳንቱ፡፡ ነገር ግን ሁለት ሚሊዮን ህዝብ ያላት ሞንጐሊያ፣ በርካታ የውጭ ቱሪስቶችንና ኢንቨስተሮችን ለመሳብ ችላለች፡፡ ሞንጐሊያማ ምን ሃሳብ አላት እድለኛ ነች፡፡ የአገር ገጽታን የሚያበላሽ እዳ የለባትም፡፡ ካዛኪስታን ግን እድሏ አልሰምር ብሎ ገጽታዋን ጥላሸት የሚቀቡ ነገረኞችን ተጐራበተች፡፡ ይህ አልበቃ ብሎ ስሟን አሳደፉት፡፡ እነ ማን? እነ ፓኪስታን፣ አፍጋኒስታን ናቸዋ፡፡ ስማቸው ተመሳሳይ ስለሆነ ብቻ፣ ካዛኪስታን የሽብርና የትርምስ አገር ትመስላለች፡፡ ሞንጐሊያ ከዚህ ጥላሸት ነፃ ነች፡፡ ስለዚህ መፍትሔው እንደሞንጐሊያ መሆን ነው፡፡ አፍጋኒስታን ማለት የአፍጋን ቦታ እንደማለት ነው፡፡ ካዛኪስታን ደግሞ የካዛክ ቦታ፡፡ ሞንጐሊያ ማለት የሞንጐል ምድር ስለሆነ፣ የካዛኪስታንን ስም ወደ ካዛኪያ እንቀይረው ብለዋል - ፕሬዚዳንቱ፡፡

“መሣሣት የሰው ነው፡፡ ይቅር ማለት ግን የመለኮት!”
(to err is human, to forgive is divine)
ሁለት ሰዎች ከሩቅ አንድ የአውሬ ቅርፅ ያያሉ፡፡
አንደኛው፤
    “ያ የምናየው እኮ ጅብ ነው” አለ፡፡
ሁለተኛው
    “ያ የምናየው እኮ አሞራ ነው” አለ፡፡
አንደኛው፤
    “እንወራረድ?”
ሁለተኛው፤
    “በፈለከው እንወራረድ!”
አንደኛው፤
    “እኔ አንድ በቅሎ አገባ!”
ሁለተኛው
    “እኔም በቅሎ ከነመረሻቷ አገባ!”
መልካም፡፡ ቀረብ ብለን እንየው፡፡ እየተጠጉ መጡ፡፡
አንደኛው፤
    “አሁንም በአቋምህ ፀንተሃል? አሞራ ነው የምትል?”
ሁለተኛው፤
    “ከፈራህ አንተ አቋምህን ቀይር እንጂ እኔ አሞራ ነው ብያለሁ አሞራ ነው!”
አንደኛው፤
    “እኔ ፈሪ ብሆን ጅብ መሆኑን እያየሁ ቀርበን እናረጋግጥ እልሃለሁ?!” አለ በቁጣ፡፡
እየቀረቡ መጡ፡፡
የእንስሳው ቅርፅ አሁንም አልተለየም፡፡
ተያይዘው ቀረቡ፡፡
እጅግ እየተጠጉ ሲመጡ፤ ያ ያዩት እንስሳ አሞራ ኖሮ ተነስቶ በረረ፡፡
ሁለተኛው ሰው፤
    “ይኼው በረረ፡፡ አሞራነቱ ተረጋግጧል፤ ተበልተሃል!”
አንደኛው፤
    “በጭራሽ አልተበላሁም!”
ሁለተኛው፤
    “እንዴት? ለምን? አስረዳኛ?!”
ይሄኔ አንደኛው፤
    “ቢበርም ጅብ ነው! መብረር የሚችል ጅብ መኖር አለመኖሩን በምን ታውቃለህ? አለው፡፡”
                                            *     *      *
በህይወታችን ውስጥ የዋሸነው፣ የካድነውና በዕንቢ-ባይ ግትርነት አንቀበለውም ያልነው፤ በርካታ ነገር አለ፡፡ የሁሉ ቁልፍ፤ ስህተትን አምኖ፣ ተቀብሎ ራስን ለማረም ዝግጁ መሆን ነው!!
ይቅርታ መጠየቅና ይቅር ማለት የዘመኑ ምርጥ አጀንዳ ነው - በተለይ በኢትዮጵያ - በተለይ በዳግማይ ትንሣኤ ሰሞን! ሰሞኑን “በአይዶል” ፕሮግራም በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ያየናት ልጅ፤ ከፋሲካ እስከ ዳግማይ ትንሣዔ ብሎም እስካገራችን ዕውነተኛ ትንሣዔ ድረስ፣ ከተማርን ከተመካከርንባት፣ ልዩ ተምሣሌት፣ ልዩ አርአያ ናት፡፡ “መሣሣት የሰው ነው፤ ይቅር ማለት ግን የመለኮት” የሚለው አባባል ትርጓሜው” እዚህ ጋ ይመጣል፡፡ የዋሸነውን፣ ለማታለል ያደረግነውን ለማሳመን መንገዱ ይሄ ነው ብለን ሰው ሁሉ/ ህዝብ ሁሉ እንዲያምነን ላደረግነው ነገር፤ ቆይተን፣ ተፀፅተን፣ ለራሳችን ህሊና ተገዝተን፣ ንሥሐ መግባት መልመድን የመሰለ መንፈሣዊ አብዮት የለም፡፡ ያን መሣይ መንፈሣዊ ለውጥ አይገኝም!! እስከዛሬ፤ በቀደሙትም ሆነ አሁን ባሉት ፓርቲዎች ዘንድ፣ በቀደሙት መንግሥታትም፣ አሁን ባለው መንግሥትም ዘንድ የማይታወቀው፤ እጅግ ቁልፍ ነገር፤ “ተሳስቻለሁ… ይቅርታ” ማለት ነው፡፡ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ያየናት የ“አይዶል” ተወዳዳሪ ድምፃዊት ያሳየችንና ያስተማረችን ጉዳይ ይሄው ነው፡፡ በእኛ ግንዛቤ፤ ተወዳዳሪዋ በድምፃዊ አረጋኸኝ ወራሽ ቤት በልጅነቷ በቤት ሠራተኝነት ተቀጥራ፣ ቀጣሪውን ማለትም አርቲስቱን ስለራሷ ህይወት ዋሽታዋለች፡፡ አርቲስቱ በሰማው አሳዛኝ የህይወት ታሪክ ልቡ ተነክቷል፡፡ ትምህርት እንድትጀምርም ያደርጋል፡፡ ልጅቱ ድንገት ከቤት ትጠፋለች፡፡
ዛሬ ግን አርቲስቱ በዳኝነት በተገኘበት መድረክ፤ የ“አይዶል” ድምፃዊት ተፈታኝ ሆና ስትቀርብ ድምጿን ካሰማች በኋላ፤ “ከመዳኘቱ በፊት አንድ ነገር ለመናገር እፈልጋለሁ አለች፡፡” ዳኞቹ ፀጥ አሉ፡፡
እዚህ መካከል አንድ የማውቀው ሰው አለ፡፡ እሱም ግር ብሎት ካልሆነ ያውቀኛል፡፡ እሱ ቤት በልጅነቴ ተቀጥሬ ነበር፡፡ ሁኔታዬንና የውሸት ታሪኬን ሰምቶ፤ አምኖኝ፣ ት/ቤት አስገብቶኝ፤ እኔ ግን ከቤቱ ጠፍቼ ሄጃለሁ፡፡ ያ ሰው፤ ድምፃዊ አረጋኸኝ ወራሽ ነው… እሱ ቤተሰቦቼን ሊያፈላልግ ሞክሯል ግን አልተሳካለትም፡፡
“እኔም ተመልሼ ሁኔታውን ለመግለጽ ሁኔታውም ድፍረቱም አልነበረኝም፡፡” የምትለው አርቲስት፤ “ዛሬ ግን ዕውነቱን ለማሳወቅ እፈልጋለሁ፡፡ ስለቤተሰቦቼ አለመኖርና ስራ ስለማጣቴ ሁሉ ያወራሁት ውሸት መሆኑን ዛሬ በግልጽ ማስረዳት እፈልጋለሁ፤ ይቅርታ እንዲያደርግልኝም እጠይቃለሁ” ነው የንሥሐዋ መንፈስ! የዳግማይ ትንሣዔ መሪ መልዕክት (1) “ልናጠፋ እንችላለን ግን ይቅርታ ጠይቀን ቀሪውን ህይወት ማስተካከል እንችላለን” ነው፡፡ ልብ እንበል፤ ልጅቱ ለአረጋኸኝ ወራሽ ብቻ ሳይሆን ለኢትዮጵያ ህዝብ ነው ንሥሐዋን የተናገረችው! አቤት ተቃዋሚ ፓርቲዎች ይሄን ቢያውቁ! አቤት ገዢው ፓርቲ ይሄን ቢችልበት አቤት በየደረጃው ይቅርታ መጠየቅ አልባ የሆነ ኃላፊ፣ አለቃ እና የበላይ ይህን ቢረዳ! አቤት አበሻ በጠቅላላ፤ ይሄ ቢገባው!
ሁለተኛው የፋሲካና የዳግማይ ትንሣዔ ግብረገባዊ ትምህርት (The Moral of the Story) የ “ጆሲ ኢን ዘ ሐውስ” ገድል ነው፡፡ የማን ያለብሽ ዲቦን ልጆችና እህት አንድ መጠለያ ለማስገኘት ጆሲ ያረገው ጥረት የወቅቱ መልዕክት ነው፡፡
ትምህርት 1) ከኢትዮጵያ የቤት - ነክ ቢሮክራሲ ጋር፣ ውጣ ውረዱን ችሎ፣ ታግሦ፣ ተቻችሎ ውጤት ማስገኘት
ትምህርት 2) እያንዳንዱን ክስተት በካሜራ ቀርፆ፣ መንግሥትም አምኖበት ለዕይታ መብቃቱ፤
ትምህርት 3) የመንግሥት ፈቃደኝነትና አዎንታዊ እርምጃዎች መረጋገጥ
ትምህርት 4) በየደረጃው ያሉ ስፖንሰሮች ሀ) የደብረዘይት መናፈሻ ቦታው ስፖንሰርሺፕ ለ)የመጓጓዣ መኪናው  ሐ) የአዋሳ ኮሜዲያን መምጣት መ) የጋሽ አበራ ሞላ መምጣት ሠ)የቤት - ዕደሳ ላይ የተሳተፉት ስፖንሰር ድርጅቶች መኖር ረ) የቤት ዕቃዎች ለማሟላት አስተዋጽኦ ያደረጉ ስፖንሰሮች መኖር ሰ) ለልጆቹ ትምህርት መቀጠል የት/ቤቶችና የዩኒቨርሲቲዎች ትብብር፣ ሸ) የኮምፒዩተር እገዛ ለማድረግ የተባበሩ ኮምፒዩተር አስመጪዎች     
ትምህርት 5) የልጆቹ መኖሪያ ጐረቤቶችን ማሰባሰብና ጉዳዩን እንዲረዱ ማድረግ፣ ሰው                   የአካባቢው ውጤት መሆኑን ይነግረናል፡፡
እኒህን ሁሉ ስፖንሰሮችና ነዋሪዎች አስተባብሮ ዓይነተኛና አርአያዊ ተግባር መፈፀሙ ጆሲን ድንቅ የሚያሰኘው ነው፡፡ ማስታወቂያ ሰሪዎች እንማር! አገር አልሚዎች እንማር! የተቀደሰ ተግባር፣ ለተቀደሰ ትንሣኤ እንደሚያበቃን ለማረጋገጥ የጆሲ ዚን ዘ ሐውስን ተምሳሌትነት እንገንዘብ፡፡ አንድ ቤተሰብ መገንባት ሙሉ አገር መገንባት ነው፤ “አምሣ ሎሚ ለአንድ ሰው ሸክሙ ለአምሣ ሰው ጌጡ ነው” ነው መንፈሱ፡፡ በርካታ ስፖንሰሮች ለመዝናኛ ስፖንሰር እንደሆኑ ይታወቃል፡፡ ይመሰገናሉም፡፡ ሆኖም ዛሬ የተሻለ ስፖንሰራዊ ተግባር አይተናል፡፡ በየማስታወቂያዎች ውስጥ መዝናኛ ብቻ ሳይሆን ቁምነገር፣ ለሀገር የሚጠቅም ጉዳይ፣ መካተት እንደሚችል በአጽንኦት ይጠቁመናል፡፡ ለብዙዎቻችን ትምህርት ነው፡፡ ሁሉን አቀፍ የስፖንሰርሺፕ እንቅስቃሴ አገር ያለማል፡፡ እንደ ጆሲ ያለ ልባዊና ልባም ሥራ ምን መምሰል እንዳለበት ታላቅ ደርዝ፣ ታላቅ ፍሬ - ጉዳይ ያስጨብጠናል፡፡ አገር የሚመራ ይህን ይገንዘብ፣ ማስታወቂያ የሚሠራ ይሄን ይገንዘብ፤ አገርን የሚያስብ ይሄን ይገንዘብ፡፡ “መልካም ሥራ ሥራና ሠይጣን ይፈር” የሚለው የሼክስፒር ጥቅስ ትልቅ ትርጉም የሚኖረው ዛሬና እዚህ ላይ ነው!!

 በግድቡ ላይ ለሚከሰት አደጋ፣ ሙሉ ለሙሉ ተጠያቂ የማደርገው ግብጽን ነው ብላለች - ሱዳን
“በኢትዮጵያ መንግስት ላይ ጽኑ እምነት አለን፣ የገንዘብ ጉዳይ አያሰጋንም!” - ሳሊኒ ኮንስትራክሽን

ግብፅ ለታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ አለማቀፍ የገንዘብ ብድሮች፣ ከውጭ መንግስታት እንዳይገኙ በማድረግ ግንባታውን ለማደናቀፍ እያሴረች ነው ስትል ሱዳን አወገዘች፡፡
የሱዳን ምስራቃዊ ብሉ ናይል ግዛት ከፍተኛ ባለስልጣን የሆኑት ሁሴን አህመድ፣ ኢትዮጵያ በማከናወን ላይ ለምትገኘው የታላቁ የህዳሴ ግድብ ግንባታ የሚውሉ አለማቀፍ ብድሮችን እንዳታገኝ ለማድረግ በግብጽ በኩል በድብቅ እየተከናወኑ ያሉት አግባብ ያልሆኑ ተግባራት፣ ግድቡ በገንዘብ እጥረት ሳቢያ ከሚፈለገው የጥራት ደረጃ በታች እንዲሰራና ለአደጋ እንዲጋለጥ ሊያደርጉ ይችላሉ በማለት ድርጊቱን ማውገዛቸውን ሱማሌላንድ ፕሬስ ዘገበ፡፡
ግድቡ ከሚፈለገው የግንባታ ጥራት በታች የሚሰራ ከሆነ፣ በረጅም ጊዜ ሂደት የሚፈርስበት ዕድል እንደሚኖርና ተያይዞ የሚከሰተው የጎርፍ አደጋም ሱዳንን ክፉኛ ሊጎዳ የሚችል በመሆኑ፣ ሱዳን የግብጽን ድርጊት አጥብቃ እንደምትቃወመውና ለሚደርሰው አደጋ ሙሉ በሙሉ ተጠያቂ እንደምታደርጋት ባለስልጣኑ መናገራቸውን ዘገባው ያስረዳል፡፡
የሱዳን ምስራቃዊ ብሉ ናይል ግዛት፣ የታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ከሚከናወንባት የቤኒሻንጉል ጉምዝ ክልሏ ጉባ ጋር በቅርብ ርቀት የሚካለል እንደመሆኑ፣ በግድቡ ላይ የመፍረስ አደጋ ቢከሰት፣ ግዛቱ በጎርፍ አደጋ ሙሉ ለሙሉ ሊወድም እንደሚችል ባለሙያዎች የሰጡትን አስተያየት ያቀረበው ዘገባው፣ ይህም የግዛቱን ባለስልጣናት እንዳሳሰባቸው ጠቁሟል፡፡
ግብጽ በግድቡ ላይ ባለቤትነት እንዲኖራት እንጂ፣ ስለ አካባቢው ደህንነት ደንታ የላትም ያሉት ባለስልጣኑ፣ የግድቡን ግንባታ በራሷ ወጪ ለማከናወንና በበላይነት ለማስተዳደር ከመጀመሪያ አንስቶ ፍላጎት እንደነበራት ተናግረዋል፡፡
“በግንባታ ጥራት መጓደል ሰበብ በግድቡ ላይ ለሚፈጠር የመፍረስ አደጋና ከዚያ ጋር ተያይዞ በግዛታችን ላይ ለሚከሰት የጎርፍ አደጋ፣ ሱዳን ሙሉ ለሙሉ ተጠያቂ የምታደርገው ግብጽን ነው” ያሉት ባለስልጣኑ፣ ግብጽ አስር አገራት በጋራ በሚጠቀሙበት የአባይ ወንዝ ላይ ኢኮኖሚዋን ሙሉ ለሙሉ ጥገኛ ከማድረግ ይልቅ፣ ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዋን በሌሎች መስኮችም ማስፋፋት እንደሚኖርባት ተናግረዋል፡፡
ግብጽ ከረጅም አመታት በፊት የገነባችው አስዋን ግድብ፣ የኑብያ ህዝቦችን ህልውና ክፉኛ መጉዳቱንና ጥንታዊ የዕደ-ጥበብ ስራዎችን ማውደሙን ያስታወሱት ባለስልጣኑ፣ ይሄም ሆኖ ግን የትኛውም አገር የግድቡን ግንባታ እንዳልተቃወመና ስራዋን ለማደናቀፍ እንዳልሞከረ ገልጸዋል፡፡
የሱዳኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አሊ ካርቲም፣ ባለፈው ጥቅምት ወር ግብጽ በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ላይ ያነሳችውን ተቃውሞ እንደተቹት የጠቀሰው ዘገባው፣ ሚኒስትሩ በተለይም የግብጽ መገናኛ ብዙሃን ግድቡን በተመለከተ መሰረተ ቢስ መረጃዎችን እያናፈሱ ነው በማለት መክሰሳቸውንና የግድቡ መገንባት ሊያስከትላቸው ይችላሉ ተብለው ከሚጠቀሱ ማናቸውም አይነት ችግሮች ይልቅ፣ ጠቀሜታው እጅግ የጎላ መሆኑን አጽንኦት ሰጥተው መናገራቸውን አስታውሷል፡፡
ተቀማጭነቱ በአውሮፓ የሆነው ስቶክሆልም ኢንተርናሽናል ዋተር ኢንስቲትዩት የተባለ አለማቀፍ ተቋም፣ የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ መገንባት፣ ግብጽ ለደለል ቁጥጥርና በትነት ሳቢያ የሚጠፋውን ውሃ ለማስቀረት ታወጣው የነበረውን በሚሊዮን ዶላሮች የሚቆጠር ገንዘብ የሚያስቀርላት በመሆኑ፣ ለኢትዮጵያ ገንዘብ መክፈል ይገባታል ማለቱንም ዘገባው ጨምሮ አስታውሷል፡፡
የኢትዮጵያ መንግስት፣ በዜጎቹ የገንዘብ መዋጮ የተጀመረው የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ፣ በተያዘለት ዕቅድ መሰረት ግንባታው እየተከናወነ እንደሚገኝ፣ ከግድቡ ግንባታ ጋር በተያያዘ የገንዘብ ችግር እንደማይገጥመውና በታሰበው የጥራት ደረጃና በተያዘለት የጊዜ ገደብ ተሰርቶ እንደሚጠናቀቅ በተደጋጋሚ መግለጹ ይታወቃል፡፡
የሮይተርስ ዘጋቢ አሮን ማሾ በበኩሉ፣ የታላቁን የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ በማከናወን ላይ የሚገኘው ግንባር ቀደሙ የጣሊያን ኮንስትራክሽን ኩባንያ ሳሊኒ፣ ከግንባታው ጋር የተያያዙ ክፍያዎች በሙሉ በወቅቱ እየተፈጸሙለት እንደሆነ  ከትናንት በስቲያ ዘግቧል፡፡
የኮንስትራክሽን ኩባንያው፣ የኢትዮጵያ መንግስት በቀጣይም የግድቡን ግንባታ ለማጠናቀቅ የሚያስፈልገውን በቢሊዮን ዶላሮች የሚቆጠር ቀሪ ገንዘብ በማሟላት ረገድ፣ ችግር ይገጥመኛል ብሎ እንደማያስብና ከፋይናንስ እጥረት ጋር በተያያዘ ምንም አይነት የሚያሰጋው ነገር እንደሌለ መናገሩን የሮይተርስ ዘገባ ጨምሮ ገልጧል፡፡ “በኢትዮጵያ መንግስት ላይ ጽኑ እምነት አለን፣ የገንዘብ ጉዳይ አያሰጋንም!” ብሏል ሳሊኒ ለሮይተርስ፡፡

“ቦርድ” ለሚወጡ ወታደሮች የ2 በመቶ ክፍያ ተጨመረ

የመከላከያ ሚኒስቴር እንደአስፈላጊነቱ እያየ የጦር መኮንኖችን የአገልግሎት ዘመንና የጡረታ መሰናበቻ እድሜ በሁለት ዓመት ለማራዘም የነበረው ሥልጣን እንደተሻሻለ ምንጮች ገለፁ፡፡ የመከላከያ ኃይል አባላት የሥራ ዘመናቸውን በ3 ወይም በ5 ዓመት ማራዘም በአዲሱ አሰራር ተፈቅዷል፡፡ የጡረታ እድሜ በ5 ዓመት የሚራዘመው ለከፍተኛ መኮንኖች እንደሆነ ምንጮች ጠቅሰው፤ ከከፍተኛ መኮንን በታች ደግሞ ካሁን ቀደም የነበረው የሁለት ዓመት ማራዘሚያ ወደ ሶስት አመት ከፍ እንዲል መደረጉን ገልፀዋል፡፡
ከዚሁ የጡረታ ማራዘምያ አዲስ አሰራር ጋር፤በ“ቦርድ” ለሚሰናበቱ የመከላከያ ኃይል አባላት የሁለት በመቶ ክፍያ ተጨምሯል፡፡ የመከላከያ ሠራዊት አባል በተለያዩ ምክንያቶች “ቦርድ” እንዲወጣ ሲወሰን፣ ወርሃዊ ክፍያው የደሞዙ አርባ አምስት በመቶ የነበረ ሲሆን አሁን አርባ ሰባት በመቶ እንዲሆን ተወስኗል፡፡

የፌደራል ባለስልጣናት ጣልቃ ገብተው ሲያረጋጉ ሰንብተዋል

የድሬደዋ ዩኒቨርስቲ የሶማሌ ክልል መስተዳድር የባለቤትነት ጥያቄ ተነስቶበት ካለፈው ቅዳሜ ጀምሮ በሚሊሻ ተቆጣጥሮት የነበረ ሲሆን የፌደራል ጉዳዮች ሚኒስትር ዶ/ር ሽፈራው ተ/ማርያም፣ የቀድሞ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ አዲሱ ለገሠ፣ የግብርና ሚኒስትሩ አቶ ተፈራ ደርበውን ጨምሮ ሌሎች የፌደራል ባለስልጣናት በጉዳዩ ጣልቃ ገብተው ማረጋጋታቸውን ምንጮች ጠቁመዋል፡፡
የዩኒቨርስቲው ባለቤት እኔ ነኝ የሚል ጥያቄ ያነሣው ሶማሌ ክልል ቦታውን በክልሉ ሚሊሻዎች አስከብቦ የክልሉን ባንዲራ ሰቅሎ የነበረ ሲሆን፣ የፌደራል ባለስልጣናቱ በጉዳዩ ጣልቃ መግባታቸውን ተከትሎ ክልሉ ሐሙስ እለት ሚሊሻዎቹን ከአካባቢው ቢያስወጣም የክልሉ ባንዲራ አሁንም በዩኒቨርስቲው አካባቢ እየተውለበለበ መሆኑ ተጠቁሟል፡፡
የድሬደዋ ዩኒቨርስቲ የሚገኘው በድሬደዋ አስተዳደር በኩል “ቀበሌ 02” ተብሎ የሚጠራ ሲሆን፤ የሶማሌ ክልል መስተዳድር በበኩሉ፤ ዩኒቨርስቲው አጠገብ “በሶማሌ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ቦረን ገጠር አስተዳደር” የሚል ታፔላ እንደተከለ ምንጮች ገልፀዋል፡፡ በአካባቢው የሚገኙ መኖሪያ ቤቶችም ባለሁለት ካርታ መሆናቸውን የገለፁት ነዋሪዎች፣ በሶማሌ ክልል እና በድሬደዋ ከተማ አስተዳደር ካርታ የወጣላቸው እንደሆኑ ጠቁመዋል፡፡ እንዲሁም ዩኒቨርስቲው ጀርባ የሚገኙ ገበሬዎች ባነሱት የመሬት ጥያቄ ምክንያት ያለ አጥር ክፍቱን የተቀመጠ መሆኑንም ምንጮች ገልፀዋል፡፡

ለውጪ ገበያ የሚቀርበውን የጥጥ ክር ምርት በእጥፍ ያሳድጋል
ኢትዮጵያን በአለም ከታወቁት ጥቂት የጥጥ ክር አምራች አገራት አንዷ ለማድረግ ያቀደው ኤስቪፒ ቴክስታይልስ በኮምቦልቻ በ11 ቢሊዮን ብር ወጪ ዘመናዊ የጥጥ ክር ፋብሪካ ሊገነባ መሆኑን አስታወቀ፡፡
በኮምቦልቻ የሚገነባው ፋብሪካው  በቀን እስከ 272.9 ቶን የሚደርስ ምርጥ የጥጥ ክር የማምረት አቅም እንዳለው ለማወቅ ተችሏል፡፡ ፋብሪካው ምርት ሲጀምር፣ አገሪቱ በአሁኑ ጊዜ ለውጭ ገበያ የምታቀርበውን ጥራቱን የጠበቀ የጥጥ ክር ምርት፣ በእጥፍ እንደሚያሳድገው የተገለፀ ሲሆን የአገሪቱን የልማት እቅድ መሰረት አድርጎ የተቀረጸው ፕሮጀክቱ፣ በአሁኑ ጊዜ ከቅድመ ዝግጅት ደረጃ አልፎ ወደ ትግበራ እንቅስቃሴ ለመሸጋገር እያኮበኮበ ነው ተብሏል፡፡
የፋብሪካው መገንባት በውጭ ንግዱ ዘርፍ ከፍተኛ አስተዋጽኦ የሚያበረክት ሲሆን ለበርካታ የአካባቢው ነዋሪዎች የስራ ዕድል እንደሚፈጥርና  የተለያዩ ጥቅሞችን እንደሚያስገኝ ተነግሯል፡፡
እ.ኤ.አ በ1898 ዓ.ም  የተመሰረተውና የፕሮጀክቱ ባለቤት የሆነው የህንዱ ፒቲ ግሩፕ፣ በስሩ በርካታ ኩባንያዎችን የሚያስተዳድር ሲሆን  በጨርቃ ጨርቅ፣ በፋይናንስ፣ በሸቀጣሸቀጥ፣ በሪል እስቴትና በጌጣጌጦች የንግድ  ስራዎች ላይ በመሰማራት ትርፋማ ስራዎችን እያከናወነ ይገኛል ተብሏል፡፡

Saturday, 19 April 2014 12:47

የቀልድ - ጥግ

እንደ አረቄ ጠርሙስ መጠጥን ታግሶ የሚያስቀምጥ የለም።
*   *   *
አንድ ሰካራም አንድ ማስታወቂያ ሰሌዳ ፊት ለፊት ቆሞ፤
“አይቻልም! በጭራሽ አይቻልም!” እያለ ያልጎመጉማል። አንድ ፖሊስ ያዳምጠው ነበረና፤
“ምንድን ነው የማይቻለው” ሲል ይጠይቀዋል።
ሰካራሙም፤
“ተመልከት ምን እንደሚል” እያለ ወደ ሰሌዳው ያሳየዋል - ፅሁፉን ያነበዋል፡-
Drink Canada Dry
ይሄ እንዴት ይቻላል? ካናዳን በደረቁ መጠጣት፤ በጭራሽ አይቻልም። ባይሆን በረዶና ሎሚ ከሰጡ ይቻል ይሆናል …. በደረቁ ግን በጭራሽ አይቻልም!! እያለ እያልጎመጎመ መንገዱን ቀጠለ።    
አንድ የሰከረ ሰው እንደድንገት ትኩስ የተቆፈረ መቃብር አጠገብ ይደርስና ሳያስበው ጉድጓድ ውስጥ ይወድቃል። ለመውጣት ቢሞክር ያቅተዋል።
በአጋጣሚ ሌላ ሰካራም በዚያ መቃብር አጠገብ ሲያልፍ ያየዋል። ሁለተኛው ሰካራም አካፋ አንስቶ በመጀመሪያው ሰካራም ላይ አፈር ይሞላበት ጀመር።
የወደቀው ሰካራም፤ “ጎበዝ በእግዚሃር አውጣኝ በጣም እየቀዘቀዘኝ፣ እየበረደኝኮ ነው”
ሁለተኛው፤ አፈር ማልበሱን እየቀጠለ፤
“እንዴት አይበርድህ ወንድሜ! አፈር ስላለበስክ እኮ ነው!!”
*   *   *
አንድ የብቃት ማረጋገጫ ባለሙያ ወደ ሁለት ተላላኪዎች ይመጣና፤ አንደኛዋን፤
“እዚህ ምንድነው ሥራሽ?” ይላታል።
ተላላኪዋ የቢሮክራሲው ሻጥር/ቀይ ጥብጣብ/፣ የአለቆች ሰውነቷን ማሻሸት፣ ቅፆች ማመላለስ፣ የየቢሮው ፖለቲካ፣ ከሁሉም በላይ ደግሞ የብቃት ማገራገጫ ባለሙያዎች ንትረካ አስመርሯታልና፤ “ምንም ሥራ አልሰራም!” አለችው።
የብቃት ማረጋገጫ ባለሙያውም፤
“መልካም። እዘግበዋለሁ” አለና ፃፍ ፃፍ አደረገ። ቀጥሎም ወደ ሁለተኛዋ ተላላኪ ዞሮ፤
“አንቺስ ምን እየሰራሽ ነው?” አላት።
ይቺኛዋም በሥራዋ የተማረረች ነበረችና፤
“እኔም ምንም አልሰራም!” አለችው።
የሥራ ብቃት ማረጋገጫ ባለሙያውም፤
“አሃ! የሥራ መደራረብ አለ ማለት ነው ሁለታችሁ ጋ” አለ።
    (አይ ቢ.ፒ.አር?)
*   *   *
የአሳንስር አስተናጋጅ ምሬት
የአሳንስር አስተናጋጅ ምሬት የታሪኮችን መጨረሻ አለማወቁ ነው!
*   *   *
ሰባኪ ለአንድ ትንሽ ልጅ፤
“ልጄ በየማታው ፀሎት ታደርሳለህ?”
“አዎን አባባ!”
“ጠዋት ጠዋትስ እንደዚያው ትፀልያለህ?”
“አይ”
“ለምን?”
“ቀን ቀን ስለማልፈራ!”