Administrator

Administrator

Saturday, 02 May 2015 10:32

ጣት መቀሰር እስከመቼ?!

(ቆም ብሎ ማሰቡ ለራስም ለሀገርም ይጠቅማል!)

   “ህዝቡ በኑሮ ውድነት እየተሰቃየ ነው፤ በሀገሪቱ ውስጥ ስራ አጥነት ተንሰራፍቶአል፤ መብራት፣ ውሃና ኔትወርክ የለም፤ የከተማዋ ነዋሪዎች በትራንስፖርት ችግር እየተንገላቱ ነው፤ በሀገሪቱ የመልካም አስተዳደር ችግር አለ፤ የግሉ ፕሬስ በነጻነት መንቀሳቀስ ባለመቻሉ ለመጥፋት ተቃርቦአል፤ ተቃዋሚ ፓርቲዎች በሚፈለገው መልኩ በነጻነት መንቀሳቀስ አልቻሉም፤ በርካታ ዜጎች ህይወታቸውን ለአደጋ በሚዳርግ መልኩ እየተሰደዱ ነው፡፡…” ሌሎችም ለቁጥር የሚታክቱ ምሬቶችና አቤቱታዎች ከየአቅጣጫው በየጊዜው ይሰማሉ፡፡ በዚችው በእኛዋ ሀገር፡፡
ከእነዚህ አቤቱታዎች አንዳንዶቹ መንግስትም ጭምር የሚቀበላቸው (የሚያምናቸው) ቢሆኑም እስካሁንም ድረስ ችግሮቹ መቀረፍ አልቻሉም፡፡ ለምን?! ምክንያቱ የሚመስለኝ የችግሮቹ መንስኤዎች ላይ አትኩሮ ችግሮቹን ለመቅረፍ ከመስራት ይልቅ ሰበብ መስጠት ወይም ጥፋቱን ተሸካሚ ፈልጎ በማሸከም ላይ ስለሚታትር ይመስለኛል፡፡ ሐጢአቱን ለሌሎች አሸክሞ እጅን አጣጥፎ መቀመጥ፡፡
እስቲ ጥቂት ወደ ኋላ መለስ እንበልና ከላይ ለተነሱትና ለሌሎች አንዳንድ ችግሮች መንግስት ተጠያቂ ያደረገው እነማንን እንደሆነ እናስታውስ፡፡… በአጭሩ ለየትኛውም ችግር ራሱን ተጠያቂ አላደረገም ማለት ይቀላል፡፡ በተደጋጋሚ ችግሮቹን ከጉዳዮቹ ጋር እጅግ በጣም ጥቂት ንክኪ ያላቸው አካላት ላይ ጭኖ ራሱን “ነጻ አድርጎአል፡፡” አሁንም እየሆነ ያለው እንደዛ ይመስለኛል፡፡ ጊዜ ያለወጠው አዙሪት!
ዛሬም እንደ ቀድሞው መንግስትና ሚዲያዎቹ በደቡብ አፍሪካ፣ በሊቢያ በረሀና በሜዴትራንያን ባህር ዳርቻ ስደተኛ ወገኖቻችን በግፍ መገደላቸውን ተከትሎ ለችግሩና ለጥፋቱ ብቸኛ ተጠያቂ “ህገ ወጥ ደላሎች” (ቃሉ ራሱ የተጣራ ፍቺን ይሻል) ናቸው እያሉን ነው፡፡ ዘይገርም ነው! መቼ ይሆን ጣታችንን ሌሎች ላይ ብቻ መቀሰር የምናቆው?! መቼስ ነው ማድበስበሱን ትተን ከእውነታው ጋር መጋፈጥ የምንችለው?! ያሰኛል፡፡
ከምንጊዜውም በበለጠ መልኩ በአሁኑ ወቅት በርካታ ወገኖቻችን ህይወታቸውን ለአደጋ በሚዳርግ መንገድ ከሀገራቸው ተሰደዋል፤ እየተሰደዱም ነው፡፡ በመንገዳቸውም ሆነ ተሰደው በሚኖሩባቸው ሀገሮችም ህይታቸውን እስከሚያጡ ድረስ በርካታ እንግልቶች እየደረሱባቸው ነው፡፡ ይሄ ሀቅ ነው፡፡ የአለም አቀፍ የሚዲያ ተቋማት የሠርክ ወሬ የሆነና እኛም የምንስማማበት ሀቅ፡፡ ታዲያ ጉዳዩ አቅጣጫውን መሳት የጀመረውና አለመተማመኑ የጎላው ዜጎቻችን የሚሰደዱበትን ምክንያት መጠየቅ ሲጀመር ነው፡፡ ያኔ ጉዳዩ ከመፍትሔው መነጠል ጀመረ፡፡ የሚመለከተውም ለዜጎቹ ኃላፊነት እንደሚሰማው አካል የችግሩን ምክንያቶች አምኖና ተቀብሎ በመጋፈጥ ችግሩን ከስሩ ለመቅረፍ ከመሞከር ይልቅ ችግሩ የሚሳበብበትን አካል መፈለግ ያዘ፡፡ የዚህ ሁሉ ጥፋት ተጠያቂ እከሌ ነው ለማለት፡፡ ያስገርማል፤ ያሳዝናልም!
እርግጥ ነው፡፡ ለአንድ ክስተት መፈጠር በርካታ ምክንቶች ሰበብ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ሆኖም ግን እያንዳንዱ ምክንያቶች ምን ያህል ድርሻ አላቸው? የምክንያቶቹ መነሻስ (ሰበብ) ምንድን ነው? የሚለው ነው ጥያቄው፡፡ እውነታውን እስከፈለግን ድረስ ይህ ወደ እርግጡ ድምዳሜ የሚያደርሰን ጤናማ መንገድ ይመስለኛል፡፡…
እርግጥ ነው ሰዎች ከሀገራቸው እንዲሰደዱ “ህገ ወጥ ደላሎች” የሚያደርጉት የራሱ አስተዋጽኦ አለ፡፡ ይህ ብቻ አይደለም ሌሎች ጭፍጫፊ ምክንያቶችም ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ መልካም፡፡… ቀጥለን ግን መጠየቅ ያለብን እነዚህ ምክንያቶች ለችግሩ የሚያዋጡት ድርሻ ምን ያህል ነው? የሚለውን ነው፡፡ መልሱ ብዙም ጥናትን የሚፈልግ አይደለም፡፡ ብዙም ሳንደክም ልንመልሰው እንችላለን፡፡ በመንግስት እየተጠቀሱ ያሉት ምክንያቶች በምንም መልኩ ለዜጎች መሰደድ በዋና ምክንያትነት ሊጠቀሱ ቀርቶ ስሌት ውስጥም የሚገቡ አይደሉም፡፡ ድርሻቸው ጥቂት ነውና፡፡
እውነቱን እንናገር ከተባለ፣ ወገኖቻችን እንዲሰደዱ ግፊት የሆኗቸው ሌሎች በዋናነት ሊጠቀሱ የሚገቡ ምክንያቶች አሉ፡፡ እነዚህን ምክንያቶች ለማወቅ የሚፈልግ አካል ካለ ተጓዦቹንና ከስደት ተመላሾቹን ቀረብ ብሎ ይጠይቃቸው፡፡ ሀገራቸውንና ወገኖቻቸውን ተለይተውና ህይወታቸውን ለአደጋ አጋልጠው የሚሰደዱባቸውን ምክንያቶች ይነግሩታል፡፡…  ምክንያታቸው የኢኮኖሚ ችግር ነው፡፡ የእንጀራ ጥያቄ! ደግሞም ይህንን ማወቅ ውስብስብና የበዛ ምርምርን የሚጠይቅ ጉዳይ አይደለም፡፡ ሽሽቱንና ማድበስበሱን ስለፈለግነው እንጂ ለማንም ያልተደበቀ ያፈጠጠ ሀቅ ነው፡፡
አንዳንድ ነጥቦችን እያነሳን ጉዳዩን ለመመርመር እንሞክር፡፡ እስቲ በመንግስትና በሚዲያ ተቋማቱ “ፍረጃ” ተስማምተን፣ ለጥፋቱ ተጠያቂዎች “ህገ ወጥ ደላሎች ናቸው” ብለን እንነሳ፡፡ የምንደርስበት ውጤት (ብዙም ስሌት ውስጥ ሊገቡ የማይገቡ ሌሎች ጭፍጫፊ ሰበቦች መኖራቸው እንዳለ ሆኖ) አሁንም የችግሩ ዋና ምክንያት የኢኮኖሚ ችግር መሆኑን የሚያረጋግጥ ነው፡፡ እንዴት?
ሲጀመር ዜጎች የ“ህገ ወጥ ደላሎቹ”ን ስብከት ሰምተውና አምነው ከሆነ የሚሰደዱት፣ ደላሎቹ ጋር የወሰዳቸውም ሆነ ደላሎቹን እንዲያምኑ ያደረጋቸው ያለባቸው የኢኮኖሚ  ችግር ነው፡፡ የኢኮኖሚ ችግር ከሌለባቸውና የዳቦ ጥያቄያቸውን መመለስ የሚችሉ ከሆነማ ለምን ከደላሎቹ ጋር ይገናኛሉ? ለምንስ ደላሎቹ የሚሏቸውን ያምናሉ? መቼስ “መረጃው ስለሌላቸው ነው” የሚል የዋህ እንደማይኖር እገምታለሁ፡፡
ሀገር አቋርጠው ሲጓዙም ሆነ ደርሰው በሚኖሩባቸው ሀገሮች ህይወትን እስከማጣት የሚደርስ እንግልት ሊያገኛቸው እንደሚችል እኮ “ህገ ወጥ” ደላሎቹ “ታገኛላችሁ” ብለው ከሚሰብኳቸው በበለጠ መንግስትም ሆነ በርካታ መገናኛ ብዙሀን ያለማቋረጥ ነግረዋቸዋል፤ እየነገሩአቸውም ነው፡፡ ግን ከመሄድ አላመነቱም፡፡ ለምን? ማመን ስለማንፈለግ እንጂ መልሱ አሻሚ አይደለም፡፡ ይህንን የሚያጠነክር ሌላም ነጥብ እዚህ ጋ ማንሳት እንችላለን፡፡ በተሰደዱበት ሀገር ሲደርስባቸው ከነበረው እንግልት፣ ከሞት መንጋጋ አምልጠው… የመጡት ወገኖቻችንም ውለው ሳያድሩ አሁንም ተመልሰው ከሞት ወዳመለጡባቸው ሀገሮች እየሄዱ ነው፡፡ መቼም እጅግ የዋህ ካልሆንን በቀር “እነሱም በደላሎቹ ተታለው ነው” አንልም፡፡ አይተውታልና፡፡ ይኸው ነው፤ ማመን ቢገደንም ቅሉ በዚህም አልን በዚያ ዜጎቻችን ህይወታቸውን ለአደጋ አጋልጠው ከሚሰደዱባቸው ምክንያቶች ትልቁን ድርሻ የሚወስደው የኢኮኖሚ ችግር፣ የእንጀራ ጥያቄ… ነው፡፡ ይህንን ማመን ግን ተጠያቂ ስለሚያደርገን ሳይሆን አይቀርም፤ ሐጢአቱን ሁሉ ለደላሎች ሰጥተን ለመንጻት የምንሞክረው፡፡
ደግሞም እኮ (ለአጭር ጊዜ የፖለቲካ ትርፍ ካልሆነ በቀር) በደሉን የሚሸከም አካል ፈልገን እሱ ላይ ጣት መቀሰር በምንም ስሌት መፍትሔ አይደለም፡፡ መፍትሔው ስህተትንና ድክመትን አምኖ መቀበልና ችግሩን ፊት ለፊት መጋፈጥ ነው፡፡ በዚህም የችግሮቹ ምክንያቶች ላይ በማተኮር መስራት ነው ለሀገርም ለራስም የሚጠቅመው፡፡ ችግሩን ሌሎች ላይ ስላንከባለልንና ጣታችንን ስለቀሰርን ወይም ጉዳዩ ሌላ አቅጣጫና ትርጉም እንዲይዝ ስለደከምን “ነጻ” የምንሆን ይመስለናል እንጂ አንሆንም፡፡ ይህንንም በተደጋጋሚ አይተነዋል፡፡ እያየነውም ነው፡፡
የትናንት ቀመር ለትናንት እንጂ ለዛሬ አይሰምርም፡፡ ይህ ዘመን ሌላ ነው፡፡ የህዝቡ አስተሳሰብም ሆነ እውቀት የቀድሞው አይደለም፡፡ ተለውጦአል፤ አድጓልም”፡፡ ያልነውንና የሰጠነውን ብቻ የሚያምንበትና የሚቀበልበት ዘመን አልፎአል፡፡ ስለ ሁሉም ነገር ምናልባትም ከምንነግረው በላይ ያውቃል፡፡ ስለ ሁሉም መረጃ አለው፡፡ ለቴክኖሎጂው ምስጋና ይግባውና ትውልዱ መረጃን በእጁና በኪሱ ይዞ ነው የሚዞረው፡፡ ለዚህም ነው በአዎንታም ይሁን በአሉታ ለየክስተቱ ምላሽ ሲሰጥ የሚስተዋለው፡፡ ይህንን ማወቅና መገንዘብ፣ ተገንዝቦም ራስን ከትውልድና ከሁኔታዎች ጋር ማዘመን ከአንድ መንግስት የሚጠበቅ ብልህነት ነው፡፡ ቆም ብሎ ማሰቡ እንደ ግለሰብ፣ እንደ ፓርቲም ሆነ እንደ መንግስት… ይጠቅማል፡፡
በተለይ አሁን ከምንጊዜውም በላይ ሀገራችንና ዜጎቿ በየአቅጣጫው እየተፈተኑ ያሉበት ወቅት ነው፡፡ በመሆኑም ሀገሩንና ህዝቦቿን እወዳለሁ የሚል ዜጋም ሆነ መንግስት ዛሬ ትናንት እንዳልሆነ ሊያስተውል፣ ቆም ብሎም ሊያስብ ይገባል፡፡ ይህንን ማድረግ ለሁሉም ይጠቅማልና፡፡… በተለይ መንግስት ከተለመደው አዙሪት መውጣት፣ ኃላፊነት መውሰድና ከችግሮች ጋር ፊት ለፊት መጋፈጥ ይኖርበታል፡፡ እስከፈለገ ድረስ ይህንን ማድረግ አያቅትም፡፡ ሥራን መስራት፣ ኃላፊነትን መወጣት ነው፡፡ ከዚያ ባለፈ ግን ሁሌም ሌሎችን ተጠያቂ ማድረግና ጣትን መቀሰር ራስን ለትዝብት ከመዳረግ ባለፈ አንዳች ትርፍ የለውም፡፡ ደጃፍን እንጂ ወንዝ አያሻግርም፡፡  
አንድ ነገር ኮሽ ባለ ቁጥር እውነቱን አምኖና ተጋፍጦ ዘላቂ መፍትሔ ከመሻት ይልቅ ጣት የምንቀስርበትን መፈለግ ለጊዜው የሚበጅ ቢመስለንም የነገ እጥፍ ኪሳራ ነው፡፡ ደግሞም እኮ ድክመትን መቀበል ጀግንነት እንጂ ሽንፈትና ክስረት አይደለም፡፡ አያስከፋምም፡፡ የሚያስከፋውስ ችግሮችን ሌሎች ላይ መጣል፣ ለማድበስበስ መሞከርና ችግሩን ላልተገባ የፖለቲካ ትርፍ ለማዋል መድከም ነው፡፡
ደግሞም እንደ መንግስት በዚህ ሂደት ውስጥ የምናደርጋት እያንዳንዷ ክንውን፣ የዛሬ አንድምታዋንና ነገ የምታፈራውን ፍሬ መገመት ይገባል፡፡ እስከ ዛሬ የዘራነው ምን እንዳፈራልን እያየን ነው፡፡ ዛሬ የምንዘራውም ነገ ልጆቻችንን ሊያጠፋ እንደሚችል እንገንዘብ፡፡ ፊታችን ስለቆመው ዛሬ ብቻ ሳይሆን ስለነገም ቆም ብለን እናስብ፡፡ ደግሞም የምር ከፈለግን አያቅተንም፡፡ በፍጹም!
መልካም ሰንበት!

የሰሞኑ አሳዛኝ ክስተት በመላው ዓለም የሚገኙ ኢትዮጵያውያንን አንድ ሊያደርግ ይችላል፤ ነገር ግን በሃገሪቱ ተመዘገበ በተባለው ተአምራዊ ኢኮኖሚ ላይ ግን ጥርጣሬን ያጭራል?”    ረዳት ፕሮፌሰር ሃሰን ሁሴን

በአንድ ሳምንት ውስጥ ኢትዮጵያውያን ተደራራቢ የሞት መርዶን አስተናግደዋል፡፡ ሚያዚያ 11 ቀን 2007 ዓ.ም በሊቢያ የሚንቀሳቀሰው የእስላማዊ መንግስት አቀንቃኙ አይኤስ፣ ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖችን መግደሉን አስታውቋል፡፡ ኢትዮጵያውያኑ በአይኤስ እጅ የወደቁት ደግሞ የተሻለ ህይወት ፍለጋ በሊቢያ አቋርጠው ወደ አውሮፓ ለመግባት ባደረጉት ጥረት መሃል ነው፡፡
ይህ አስከፊ አጋጣሚ የተፈጠረውም በዚያው ሳምንት በደቡብ አፍሪካ በስደት በሚገኙ ኢትዮጵያውያን ላይ ጥቃት እየተፈጸመ ባለበትና 3 ኢትዮጵያውያን የመገደላቸው መርዶ በተነገረበት ወቅት መሆኑ ጉዳዩን ይበልጥ ለኢትዮጵያውያን መራር ያደርገዋል፡፡
በሌላ በኩል አልጀዚራም ሆነ ሌሎች መገናኛ ብዙሃን እንደዘገቡት፤ በየመን እንዲሁ በተመሳሳይ ስደት ላይ የሚገኙ በሺዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን በጦርነት መሃል ለሰቆቃ ተዳርገዋል፡፡ በዚያው አስከፊ ሳምንት በኦሮሚያ ክልል በሚገኘው ሮቤ ከተማ እና አካባቢው የሚገኙ ወላጆች፣ ሚያዚያ 11 ከሊቢያ ወደ ጣሊያን ከ900 በላይ ስደተኞች ጭና ስትገጓዝ የነበረችው ጀልባ መስጠሟን ሰምተው መሪር ሃዘንን አስተናግደዋል፡፡
በአንድ ሳምንት ውስጥ የተፈጠሩት እነዚህ ሁሉ አሳዛኝ ክስተቶች፣ለጊዜው ኢትዮጵያውያንን አንድ ያደረጉ ቢመስልም በዚያው ልክ ኢትዮጵያውያኑን ከአስፈሪ ሞት ጋር ለመጋፈጥ ለምን ስደትን የመጀመሪያ ምርጫቸው ያደርጋሉ የሚለው በሁሉም ህሊና ውስጥ የሚመላለስ ጥያቄ ሆኗል፡፡
ቀውሱ የተፈጠረው የኤስያ ነብሮች የተባሉ ሃገራት በ1970ዎቹ ያስመዘገቡት አይነት ተአምራዊ ኢኮኖሚ ሃገሪቱ አስመዝግለች በሚባልበትና የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅዱ ማጠናቀቂያ ዓመት ላይ መሆኑ እንዲሁም ዲሞክራሲያዊነትን እየተላበሰች ነው በተባለባት ሀገር መሆኑ ነገሩን ይበልጥ አጠያያቂ ያደርገዋል፡፡ በተደጋጋሚም ሃገሪቱ ከአፍሪካ ሃገሮች ፈጣን ኢኮኖሚ እያስመዘገበች ነው ከተባለ ለምንድነው በሺዎች የሚቆጠሩ ወጣቶቿና ሴት ልጆቿ በአስከፊ ሁኔታ ውስጥ ሃገራቸውን ጥለው የሚሰደዱት? መቼስ ነው ይሄ ፍልሰት የሚያበቃው?
እንደሚታወቀው አስደንጋጩ ዜና ከተሰማ በኋላ የመንግስት ቃል አቀባይ አቶ ሬድዋን ሁሴን፤ “ክስተቱ በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ወደ አውሮፓ ለመጓዝ ላሰቡ ሰዎች ማስጠንቀቂያ ነው” ብለዋል፤ ግን የሃገሪቱ ወጣቶች እንደ ማስጠንቀቂያ አላዩትም፡፡ በአገራቸው የተሻለ ህይወት የመኖር ህልም ያላቸው አይመስልም፡፡ በሃገሪቱ ከፍተኛ ድህነት፣ የኑሮ ውድነት፣ የስራ አጥ ወጣቶች ቁጥር መበራከት፣የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት እድል----ከፖለቲካ ጋር መያያዙና የኢኮኖሚ ተጠቃሚ ለመሆን የፓርቲ አባልነት መስፈርት ማስፈለጉ፣ ከፍልሰቱ ጀርባ እንዳለ በርካታ እማኞች ይገልጻሉ፡፡
መቀመጫውን ለንደን ያደረገው አለማቀፉ የእድገት ማዕከል፤ በ2012 እ.ኤ.አ ይፋ ባደረገው ሪፖርቱ፤ በከተማ የሥራ አጥነቱ በከፍተኛ ደረጃ ላይ እንደሚገኝ፣
ማስማ በገጠርም ወጣቱ መሬት አልባ መሆኑን ጠቃሚ የስራ እድሎ እንደሌሉት ጠቁሟል፡፡ በሪፖርቱ እንደተጠቀሰው፤በሃገሪቱ በሚታይ ደረጃ የትምህርት አቅርቦት ቢጨምርም ተምሮ ለሚወጣው ዜጋ በተማረበት የሙያ መስክ በቂ የስራ እድል አለመኖሩን አስቀምጧል፡፡
በአይኤስ ከተገደሉት መካከልም በዲግሪ የተመረቁ እንዳሉ ተጠቁሟል፡፡ ሳውዲ አረቢያ ከ100ሺህ በላይ ኢትዮጵያውያንን ባስወጣችበት ወቅት ወደ ኢትዮጵያ የተመለሱም የአይኤስ ሰለባ ሆነዋል፡፡ እንዲሁ በሃገሪቱ ካሉ የመንግስት መስሪያ ቤቶች አንዱ በሆነው የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ኮርፖሬሽን በጥሩ ደመወዝ ተቀጥሮ ይሰራ የነበረ ወጣትም አለበት፡፡
ይሄ ሁሉ የሚያመለክተን ብዙ የሚወራለት የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ፣ የሃገሪቱን ወጣትና የህዝብ ቁጥር ምጣኔን ለማስተናገድ አለመብቃቱን ነው፡፡ የሀገሪቱን ወጣቶች ለስደት የሚዳርገው የኢኮኖሚ ችግር ብቻ አይደለም፡፡ ወጣቶች አማራጭ የመረጃ ምንጭ መከልከላቸውና የነፃነት ስሜት እንዳይሰማቸው መደረጉ አንዱ ምክንያት ነው፡፡ በየአገሩ የሚገኝ አብዛኛው ኢትዮጵያዊ ስደተኛ የፖለቲካ ጥገኝነት ጠያቂ ነው፡፡ በየመን 75ሺህ ያህል የተመዘገቡ ስደተኞች መኖራቸውን የተባበሩት መንግስታት ሪፖርት የጠቆመ ሲሆን በኬንያ ከ20 ሺህ በላይ፣ በግብፅና በሶማሊያ ወደ 3ሺህ የሚጠጉ ኢትዮጵያውያን በስደተኝነት ተመዝግበዋል፡፡
አገሪቱ በዚህ ሁኔታ ውስጥ እያለች በግንቦት ወር ምርጫ ይደረጋል፡፡ ለ5ኛ ጊዜ የሚካሄድ ምርጫ ቢሆንም ላለፉት 10 ዓመታት ገዥው ፓርቲ፣ የፀረ ሽብር ህግና የሲቪል ማህበራት ህግ በማውጣት እንዲሁም ተቃዋሚዎችን በተለያዩ መንገዶች በማዳከም፣የምርጫ መወዳደሪያ ሜዳውን መዝጋቱም በገሃድ የሚታይ ሆኗል፡፡
ሃሳብን የመግለፅ ነፃነትን በማፈን ደግሞ አገሪቱ ከአለም በ4ኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች፡፡ ጋዜጠኞችን በማሰርም ከአፍሪካ በሁለተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች፡፡ ገዥው ፓርቲ መገናኛ ብዙሃንን በሙሉ ተቆጣጥሯል፡፡ እንዲያም ሆኖ አሁን ባለው ሁኔታ ጥቂት ተቃዋሚዎች በቀጣዩ ምርጫ ፓርላማ ሊገቡ ይችሉ ይሆናል፤ ወጣቶች ግን አሁንም የፖለቲካ ተሳትፏቸው የተገደበ ነው፡፡
ከእነዚህ ሁሉ ውስብስብ ችግሮች ባሻገር ኢትዮጵያ በአካባቢው ከሚገኙት ሶማሊያ፣ ደቡብ ሱዳን፣ ኤርትራ እና ጅቡቲ አንፃር የተረጋጋች ሃገር ነች ማለት ይቻላል፡፡ የአገሪቱ መንግስት በሽብርተኝነት ላይ ጦርነት አውጃለሁ ማለቱ ደግሞ የአሜሪካን ቀልብ ገዝቷል፡፡ ይሄም አሜሪካን የመሳሰሉ ለጋሽ ሃገራት ኢትዮጵያውያን የፖለቲካ ነፃነታቸውን እንዲያገኙ ግፊት ከማድረግ እንዲቆጠቡ አድርጓቸዋል፡፡ በሃገሪቱ ያለው የጎሳና የሃይማኖት ግጭት፣ የፖለቲካ ነፃነት እጦት በሃያላኑ ሃገራት እምብዛም ትኩረት የተሰጠው አይመስልም፡፡ ዜጎቿን በስደት እያጣች ያለችው ሃገር፣ ይበልጥ በአካባቢው በሽብርተኝነትና ደህንነት ላይ ብቻ አተኩራ የምትቀጥል ከሆነ፣የዜጎች ፍልሰትና የማህበራዊ አለመረጋጋቱም በዚያው መጠን ይቀጥላል፡፡ ከዚያ ይልቅ የቅርብ ጊዜውን አሳዛኝ ክስተት መነሻ በማድረግ መንግስት የመፍትሄ ሃሳቦችን መፈለግ ይጠበቅበታል፡፡ ከዚህ ቀደም የታለፈባቸውን የፖለቲካ እና የኢኮኖሚ ጉዳዮችን ቁጭ ብሎ በመመርመር፣ሁነኛ የመፍትሄ አቅጣጫዎች ካልተቀመጡ አሁንም ስደቱ ይቀጥላል፡፡ ኢትዮጵያውያንም አሳዛኝና አስደንጋጭ መርዶዎችን መስማታቸውን ሊቀጥሉ ይችላሉ፡፡ ረዳት ፕ/ር ሀሰን ሁሴን፤ በአሜሪካ ሚኒሶታ ቅድስት ማርያም ዩኒቨርሲቲ ፕሮፌሰር ናቸው፡፡
 ፅሁፉ ሚያዚያ 20 ቀን 2007 ዓ.ም በአልጀዚራ ድረ-ገፅ ላይ ታትሞ ለዓለም የተሰራጨ ነው፡፡  
*ከላይ በቀረበው ጽሁፍ ውስጥ የተካተቱት ሃሳቦች በሙሉ የጸሃፊው ብቻ ነው፡፡

198 ሜትር ይረዝማል፣ 46 ወለሎች ይኖሩታል

የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከምስራቅ አፍሪካ አገራት በእርዝማኔው ቀዳሚ እንደሚሆን የተነገረለትን ሰማይ ጠቀስ ህንጻ በአዲስ አበባ ከተማ ለማስገንባት ከቻይናው የኮንስትራክሽን ኩባንያ (ሲኤስሲኢሲ) ጋር ስምምነት መፈጸሙን ዥንዋ ዘገበ፡፡
ባለፈው ማክሰኞ በአዲስ አበባ በተከናወነው የፊርማ ስነስርዓት ላይ ንግግር ያደረጉት የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ፕሬዚዳንት አቶ በቃሉ ዘለቀ፣ 198 ሜትር ርዝመትና 46 ወለሎች የሚኖረው የወደፊቱ የባንኩ ዋና ጽ/ቤት፣ በእርዝማኔው ብቻ ሳይሆን በአጠቃላይ ጥራቱም ከአፍሪካ ምርጥ ህንጻዎች አንዱ እንደሚሆን እናምናለን ብለዋል፡፡
ህንጻውን የሚገነባው የቻይናው የኮንስትራክሽን ኩባንያ ሲኤስሲኢሲ የኢትዮጵያ ቅርንቻፍ ጄኔራል ማናጀር ሶንግ ሱዶንግ በበኩላቸው፣ ኩባንያው በቻይና መሰል ግዙፍ የህንጻ ግንባታ ፕሮጀክቶችን በስኬታማ ሁኔታ ሲያከናውን እንደቆየ አስታውሰው፣ ህንጻው ለቻይና እና ለኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ለምስራቅ አፍሪካም አዲስ ገጽታን የሚያላብስ እንደሚሆን ያላቸውን እምነት ገልጸዋል፡፡
ኩባንያውና ባንኩ በቀጣይ በጋራ ተረባርበው ፕሮጀክቱን ስኬታማ በማድረግ የጋራ ተጠቃሚነታቸውን እንደሚያረጋግጡም ገልጸዋል፡፡

   ታዋቂዎቹ ድምፃዊያን ነዋይ ደበበ እና ጎሳዬ ተስፋዬ በሊቢያ አሰቃቂ ግድያ ለተፈፀመባቸው   ኢትዮጵያውያን ሰማዕታት መታሰቢያ የሚሆኑ ዜማዎችን እንደሰሩ ለአዲስ አድማስ ገለፁ፡፡
ኢትዮጵያውያን ለገጠማቸው ብሄራዊ ሃዘን ከማንም በላይ የጥበብ ሰዎች ትልቅ ኃላፊነት አለባቸው ያለው ነዋይ፤ ህዝቡ አንደበታችን ብሎ የጥበብ ሰዎችን ስለሚወክል እኔም  የተሰማኝን ጥልቅ ሀዘን ለመግለፅ ሙዚቃውን ሰርቻለሁ ብሏል፡፡ “በኢትዮጵያዊያን ወገኖቻችን ላይ የተፈፀመው ግፍ መቆም አለበት ብለን ዛሬ ካልወሰንን ነገ የባሰ እንዳይመጣ ያሰጋኛል” ያለው ድምፃዊ፤ ሙዚቃውን ህዝቡን ለማፅናናትና መልዕክት ለማስተላለፍ እንደሰራው ተናግሯል፡፡
“ሁሉም ያልፋል እስኪያልፍ ግን ያለፋል” በሚል ስያሜ የሰራሁት ሙዚቃ እንደ መዝሙር ሊታይ የሚችልና ዜማዊ ማስተማሪያ የሚሆን ነው ያለው ድምፃዊው፤ ግጥምና ዜማውን ራሱ እንደሰራው ገልፆ ሙዚቃውን ያቀናበረለት ወደፊት በሚያወጣው አልበሙ ከአምስት በላይ ዘፈኖችን የሰራለት ታምራት አማረ በቀና እንደሆነ ገልጿል፡፡ ሙዚቃው ከትናንት ጀምሮ በተለያዩ የኤፍኤም ሬዲዮ ጣቢያዎች መሰማት እንደጀመረ ጠቁሞ፤ ለሙዚቃው ክሊፕ ለመስራት በሳምሶን ስቱዲዮ በኩል እየተንቀሳቀስን ነው ብሏል፡፡  
እንዲህ ያለ መሪር ሀዘን ሲያጋጥም ቅስም ይሰብራል ያለው ጐሳዬ በበኩሉ፤ በወገኖቻችን ላይ የተፈፀመው ግፍ ከተወለድኩበት ጊዜ ጀምሮ ተሰምቶኝ የማያውቅ ጥልቅ ሀዘን ፈጥሮብኛል ብሏል፡፡ ሀዘኑን የሰማሁት አዳዲስ ስራዎችን እያዘጋጀሁ ባለሁበት ሰዓት ነው ያለው ጎሳዬ፤ እንደ ድምፃዊነቴ ሀዘኔን የምገልፀው በጉሮሮዬ በመሆኑ “አኬልዳማ” የሚል የመታሰቢያ ሙዚቃ ሰርቻለሁ ብሏል፡፡ አገሪቱን በገጠማት ሀዘን ኢትዮጵያዊያን ብቻ ሳይሆኑ የኢትዮጵያ ደም ያላቸው የዓለም ህዝቦች ሁሉ ክፉኛ ማዘናቸው ልቤን ነክቶታል ያለው ወጣቱ ድምፃዊ፤ በሙያው ያለውን ለማበርከት ማቀንቀኑን ተናግሯል፡፡
የመታሰቢያ ሙዚቃውን ግጥም፣ ዜማና ቅንብር የሰራው መኮንን ለማ (ዶክተሬ) እንደሆነ የገለፀው ጎሳዬ፤ ጌታቸው ኃይለማርያም አብሮት እንደተጫወተ፣ አሌክስ ባሪያው ደግሞ ካጀቡት ድምፃዊያን አንዱ እንደሆነ ተናግሯል፡፡
 የጎሳዬ “አኬልዳማ” ካለፈው ሳምንት ጀምሮ በተለያዩ የሬዲዮ ጣቢያዎች እየተሰማ ነው፡፡ ከዚህ ቀደም በድሬደዋ የጎርፍ አደጋ ባጋጠመበት ወቅት የመታሰቢያ ሙዚቃ ሰርቼ ነበር ሲል ያስታወሰው ጎሳዬ፤ ማህበራዊ ሃላፊነቴን ለመወጣት ምንጊዜም ከኢትዮጵያዊያን ወገኖቼ ጎን እቆማለሁ ብሏል፡፡       

    የኢትዮጵያ ሴቶች ማህበራት ቅንጅት ባለፈው ዓመት ሐምሌ መጨረሻ ላይ ጀምሮ ያቋረጠውን 8400 አጭር የፅሁፍ መልዕክት ሎተሪ (SMS) ከነገ አንስቶ እንደሚቀጥል አስታወቀ፡፡
ሎተሪው በየቀኑ የሚበረከቱ የሳምሰንግ ሞባይሎች፣ በየሳምንቱ የሚበረከቱ ቶሺባ ላፕቶፖችና 21 ፍላት ስክሪን ቲቪዎች ሲኖሩት፣ በየ15 ቀኑ የሚወጡ የልብስ ማጠቢያ ማሽኖች፣ ሞተር ሳይክሎችና ፍሪጆች እንዳሉት ማህበሩ አስታውቋል፡፡ በሎተሪው መሃልና መጨረሻ ላይ የሚወጡ መኪኖችም እንደተዘጋጁ ለማወቅ ተችሏል፡፡
ከሎተሪው ሽያጭ የሚገኘው ገቢ በቀጥታ ማህበሩ ለጀመረው የኢ.ሴ ማዕከል ማሰሪያ የሚውል ሲሆን ማዕከሉ ለስብሰባዎችና ስልጠናዎች የሚያገለግሉ አዳራሾች፣ የቢሮ ክፍሎች፣ የሚከራዩ አዳራሾች ይኖሩታል ተብሏል፡፡ ከኪራይ የሚገኘው ገቢ ለጥቃት ሰለባዎችና በኢኮኖሚ አቅማቸው ዝቅተኛ ለሆኑ ሴቶች ድጋፍ ማድረግያ እንዲሁም ማህበሩ በገንዘብ ራሱን እንዲችል ያግዛል ተብሏል፡፡
ባለፈው ዓመት ሐምሌ መጨረሻ ላይ የተጀመረው የማህበሩ 8400 አጭር የፅሁፍ መልዕክት ሎተሪ ከ15 ቀናት በኋላ የተቋረጠው የ8100 የህዳሴ ግድብ SMS ሎተሪ በመጀመሩና ሁለቱን መልዕክቶች በአንዴ ማስተላለፍ ስለማይቻል ነበር ያለው ማህበሩ፤ ከነገ አንስቶ የሚጀመረው የ8400 አጭር የፅሁፍ መልዕክት ሎተሪ ለ3 ወራት ይቀጥላል ብሏል፡፡

 የግድያ ቪድዮዎቹ አለማቀፍ ስነ-ልቦናዊ ተጽዕኖ እየፈጠሩ ነው
      አይሲስ የተባለው አሸባሪ ቡድን እያሰራጫቸው የሚገኙና በተለያዩ አገራት ዜጎች ላይ የፈጸማቸውን አሰቃቂ ግድያዎች የሚያሳዩ የቪዲዮ ምስሎች፣ ቡድኑ በአለማቀፍ ደረጃ የከፈተው የስነልቦና ጦርነት አካል ናቸው መባሉን አሶሼትድ ፕሬስ ዘገበ፡፡
የጀርመን የአገር ውስጥ የስለላ ተቋም ሃላፊ ሃንስ ጆርጅ ማሰን እንዳሉት፣ አገራት እነዚህ አሰቃቂ የግድያ ቪዲዮዎች በወጣት ዜጎቻቸው ላይ የሚያሳድሩትን የስነልቦና ተጽዕኖ ለመቅረፍ የራሳቸውን እርምጃ መውሰድ ይገባቸዋል፡፡
የቪዲዮ ምስሎቹ የአሸባሪውን ቡድን የጥፋት ፕሮፓጋንዳ በወጣቱ ትውልድ ልቦና ውስጥ የሚያሰርጹ ናቸው ያሉት ጆርጅ ማሰን፤ ምስሎቹ ለእይታ ሲበቁ የቡድኑን የጥፋት ተልዕኮ አሰቃቂነት የሚያሳዩ መልዕክቶችን አብሮ ማቅረብ ይገባል ሲሉ ተናግረዋል፡፡
ቡድኑ በቅርቡ በጀርመን ለሚገኙ ደጋፊዎቹ ባሰራጨው የቪዲዮ መልዕክት፣ ባለፈው ጥር ወር በፈረንሳይ የተፈጸመውን ዓይነት ጥቃት እንዲፈጽሙ ጥሪ አቅርቧል ያለው ዘገባው፣ የጀርመን የደህንነት ባለስልጣናትም መልዕክቱን ያስተላለፈው ትውልደ ጀርመናዊው አለማቀፍ አሸባሪ ዴኒስ ኩስፐርት መሆኑን ማረጋገጣቸውን አስታውሷል፡፡
ሲኤንኤን በበኩሉ፤አይሲስ እያሰራጫቸው ያሉት የግድያ ቪዲዮዎች በአለማቀፍ ደረጃ ፍርሃትን እያነገሰ እንደሚገኝና የቡድኑ ቪዲዮዎች ሌሎችም ለመሰል ጥፋቶች እንዲነሳሱ ተጽዕኖ እንደሚያደርግ ዘግቧል፡፡
በሜሪላንድ ዩኒቨርሲቲ የስነልቦና መምህር ፕሮፌሰር አሪ ክሩግላንስኪ እንዳሉት፤ የአይሲስ የአሰቃቂ ግድያ ቪዲዮዎች፣ ግለሰቦች በግጭት ወቅት  ተመሳሳይ ጥቃቶችን እንዲፈጽሙ የሚያነሳሳ ስነልቦናዊ ጫና የመፍጠር ሃይል አላቸው፡፡
የጀሃዲስቶች አሰቃቂ ግድያዎች በቪዲዮ ምስሎች በስፋት መሰራጨታቸው፣ ግለሰቦች ከዚህ ቀደም የማያስቡትን አንገት ቀልቶ መግደል የሚል የጭካኔ ሃሳብ ትኩረት ሰጥተው ማሰብ እንዲጀምሩ በማድረግ ረገድ በአለማቀፍ ደረጃ አሉታዊ ተጽዕኖ እየፈጠረ ነው ብለዋል ፕሮፌሰሩ፡፡

ላይ ወታደራዊ ዘመቻ ልትፈጽም እየተዘጋጀች ነው
  በዚህ ወር ብቻ ከ1 ሺህ በላይ ስደተኞች በሜዲትራኒያን ባህር ሞተዋል
በእሁዱ የጀልባ አደጋ የተጠረጠሩ ፍርድ ቤት ቀርበዋል
       የሜዲትራኒያን ባህርን አቋርጠው ወደ አውሮፓ አገራት ለመግባት ሲሞክሩ ለህልፈተ ህይወት በሚዳረጉ ስደተኞች ዙሪያ ለመምከር ከትናንት በስቲያ በብራስልስ አስቸኳይ ስብሰባ የጠሩት የአውሮፓ አገራት መሪዎች፣ ሊቢያውያን ህገወጥ የሰዎች አዘዋዋሪዎችን ለማጥቃትና አካባቢውን ለማረጋጋት የሚያስችል ወታደራዊ ዘመቻ ለማካሄድ ዝግጅት እያደረጉ እንደሆነ አልጀዚራ ዘገበ፡፡
በዚህ አመት ብቻ 36 ሺህ ያህል የተለያዩ አገራት ዜጎች ባህር አቋርጠው በስደት ወደ ጣሊያን፣ ማልታ እና ግሪክ እንደገቡ የጠቆመው ዘገባው፣ የአውሮፓ መሪዎች ስደተኞችን በህገወጥ መንገድ የሚያጓጉዙ ጀልባዎችን ተከታትሎ በመለየት በቁጥጥር ስር የሚያውልና በሊቢያውያን ህገወጥ የሰዎች አዘዋዋሪዎች ላይ እርምጃ የሚወስድ የአውሮፓ ጥምር ወታደራዊ ዘመቻ ማድረግ በሚቻልበት ሁኔታ ላይ መክረዋል ብሏል፡፡
ባለፈው እሁድ ከሊቢያ በመነሳት ሜዲትራኒያን ባህርን አቋርጣ ወደ ጣሊያን ስትቃረብ በሰመጠችው ጀልባ ከ800 በላይ የተለያዩ አገራት ዜጎች ለህልፈተ ህይወት መዳረጋቸውን ተከትሎ አስቸኳይ ስብሰባ ያደረጉት መሪዎቹ፣ በሜዲትራኒያን ባህር ስደተኞችን ለማዳን ለሚከናወኑ ተግባራት የሚሰጡትን የገንዘብ ድጋፍ በሶስት እጥፍ ለማሳደግ የተስማሙ ሲሆን በወር በድምሩ 9.7 ሚሊዮን ዶላር ለመስጠት ቃል ገብተዋል፡፡
የእንግሊዙ ጠቅላይ ሚኒስትር ዴቪድ ካሜሩን ስደተኞችን ለመታደግ የሚሰሩ ስራዎችን ለማገዝ የሚውሉ ሶስት ሄሊኮፕተሮችንና ሁለት መርከቦችን ለመስጠት ቃል ሲገቡ፣ ጀርመንና ፈረንሳይም እያንዳንዳቸው ሁለት መርከቦችን ለመስጠት ቃል መግባታቸውን ዘገባው ገልጧል፡፡
የውሮፓ አገራት መሪዎች በህገወጥ ስደት ለህልፈተ ህይወት የሚዳረጉ ዜጎችን ጥፋት ለመቀነስና ዜጎቻቸው ከሚሰደዱባቸው አገራትና የስደተኞች መተላለፊያ ከሆኑ አገራት ጋር በትብብር መስራትን ጨምሮ፣ ለስደት ምክንያት የሆኑ ችግሮችን የመቅረፍ ስራ በስፋት ለመስራት ተስማምተዋል፡፡
የአውሮፓ ህብረት በበኩሉ ባለፈው ሰኞ በሜዲትራንያን ባህር የሚከሰተውን የስደተኞች ሞት ለመቀነስና ቀጣይ ጥፋቶችን ለመቀነስ የሚያስችል ባለ 10 ነጥብ የድርጊት መርሃ ግብር ቢያወጣም፣ መርሃግብሩ ጥፋትን ከመቀነስ ይልቅ የሚያባብስና ተጨማሪ ስደተኞችን ለስደት የሚያበረታታ ነው በሚል እየተተቸ እንደሚገኝ ቢቢሲ ዘግቧል፡፡  
በዘንድሮው አመት ብቻ ሜዲትራኒያን ባህርን አቋርጠው ወደ አውሮፓ አገራት ለመግባት ሲሞክሩ ለህልፈተ ህይወት የተዳረጉ ስደተኞች ቁጥር ከ1 ሺህ 700 በላይ መድረሱን የዘገበው ቴሌግራፍ በበኩሉ፣ ይህ የሞት መጠን ባለፈው አመት ተመሳሳይ ወቅት ከተመዘገበው ጋር ሲነጻጸር በ30 እጥፍ እንደሚበልጥም ገልጧል፡፡
አሶሼትድ ፕሬስ በበኩሉ የተመድ የስደተኞች ድርጅትን ጠቅሶ ከትናንት በስቲያ ባወጣው ዘገባ፣ ባለፈው አመት ብቻ 219 ሺህ ያህል ስደተኞች ሜዲትራኒያን ባህርን አቋርጠው በህገወጥ መንገድ ወደ አውሮፓ አገራት መግባታቸውንና ከ3 ሺህ 500 በላይ የሚሆኑም በጉዞ ላይ ሳሉ ለሞት መዳረጋቸውን አስነብቧል፡፡ ከእነዚህ መካከልም ከ1ሺህ በላይ የሚሆኑት በዚህ ወር ብቻ መሞታቸውንም አስታውቋል፡፡
ጣሊያን ባህር አቋርጠው የሚመጡ ስደተኞችን ከአደጋ ለመታደግ በሊቢያ ድንበር አቅራቢያ ታደርግ የነበረውን እንቅስቃሴ በጥቅምት ወር 2014 ማቋረጧ፣ ለሟቾች ቁጥር ማሻቀብ ምክንያት ሆኗል ብለው የሚተቹ አስተያየት ሰጪዎች መኖራቸውንም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡  
ባለፈው እሁድ ከደረሰውና በአካባቢው ከደረሱ መሰል አደጋዎች ሁሉ የከፋ ጥፋት የደረሰበት ነው በተባለው አደጋ ከ800 በላይ ሰዎች መሞታቸውንና ስደተኞቹ ኤርትራ፣ ሶማሊያና ሶሪያን ጨምሮ የ20 የተለያዩ አገራት ዜጎች እንደሆኑም ሲ ኤን ኤን ዘግቧል፡፡
ከእሁዱ የስደተኞች ጀልባ አደጋ ጋር በተያያዘ ተጠርጥረው ሲሲሊ ውስጥ በፖሊሰ ቁጥጥር ስር የዋሉት የጀልባዋ ካፒቴንና አንድ የህገወጥ የሰዎች ዝውውሩ ተሳታፊ ትናንት ፍርድ ቤት ቀርበው ቃላቸውን ሰጥተዋል፡፡

22 የሙስሊም ብራዘርሁድ ደጋፊዎችም በሞት ተቀጥተዋል
የቀድሞው የግብጽ ፕሬዚዳንት ሞሃመድ ሙርሲ፣ በስልጣን ዘመናቸው ዜጎች ያለአግባብ እንዲገደሉ፣ እንዲታሰሩና እንዲሰቃዩ መመሪያ አስተላልፈዋል በሚል ተከስሰው የ20 አመት እስር እንደተፈረደባቸው ቢቢሲ ዘገበ፡፡
ከሁለት አመታት በፊት በግብጽ የተቀጣጠለውን ህዝባዊ ተቃውሞ ተከትሎ ከስልጣናቸው የወረዱት የሙስሊም ብራዘርሁድ  መሪ ሞሃመድ ሙርሲ፣ በታህሳስ ወር 2012 በቤተመንግስታቸው አቅራቢያ ለተቃውሞ የወጡ ከአስር በላይ ግብጻውያን እንዲገደሉ፣ ብዙዎችም እንዲታሰሩና ለስቃይ እንዲዳረጉ ትዕዛዝ መስጠታቸውን አረጋግጫለሁ በማለት ነው ፍርድ ቤቱ ቅጣቱን የጣለባቸው ተብሏል፡፡
ባለፈው ማክሰኞ በካይሮ የዋለው ችሎት ከሙርሲ በተጨማሪ በሌሎች 12 የሙስሊም ብራዘርሁድ ባለስልጣናት ላይ ተመሳሳይ የእስራት ቅጣት እንደጣለ ዘገባው ጠቁሟል፡፡
ሙርሲ በተቃዋሚዎች ላይ ግድያ መፈጸምን ጨምሮ የሞት ቅጣት ሊያስጥሉባቸው የሚችሉ ሌሎች ክሶች በተለያዩ ፍርድ ቤቶች እንደተመሰረቱባቸው ያስታወሰው ዘገባው፤ ይሄኛው ፍርድ ቤት ግን የቀረቡለትን የግድያ ክሶች ውድቅ ማድረጉንና ለግድያና ለእስራት ትዕዛዝ መስጠት በሚለው ክስ ብቻ ቅጣቱን እንደጣለባቸው አስታውቋል፡፡
የሙስሊም ብራዘርሁድ የቀድሞ ከፍተኛ ባለስልጣን አምር ዳራግ፤ የፍርድ ቤቱን ውሳኔ ፍትህን ያዛባ ነው ሲሉ ተችተውታል፡፡
ባለፈው ሰኞ 22 የሙስሊም ብራዘርሁድ ደጋፊዎች በካይሮ በሚገኝ የፖሊስ ጣቢያ ላይ ጥቃት አድርሳችኋል በሚል ተከሰው የሞት ቅጣት እንደተላለፈባቸው የገለጸው ዘገባው፤ ታዋቂውን የሙስሊም ብራዘር ሁድ የቀድሞ መሪ ሞሃመድ ባዴን ጨምሮ በመቶዎች የሚቆጠሩ የቀድሞው የግብጽ አስተዳደር ባለስልጣናት ከዚህ በፊት የሞት ፍርድ እንደተጣለባቸውም ጨምሮ አስታውሷል፡፡

Saturday, 25 April 2015 11:04

የፍቅር ጥግ

(ስለውበት)
ውበት ሌላ ሳይሆን እውነታ በፍቅር አይን ሲታይ ነው፡፡
ራቢንድራናዝ ታጎር
ውበት፤ ዘላለማዊነት ራሱን በመስተዋት ሲመለከት ነው፡፡
ካሊል ጂብራን
ውበት ከወይን ጠጅ ይብሳል፤ ባለቤቱንም ተመልካቹንም ያሰክራል፡፡
አልዶስ ሁክስሌይ
ውበት፤ ጥሩ የትውውቅ ደብዳቤ ነው፡፡
የጀርመናውያን ምሳሌያዊ አባባል
ውበት በዕለት ሥራ ውስጥም ይገኛል፡፡
ማሚ ሲፐርት በርንስ
ውበት፤ የእግዚአብሔር የእጅ ፅሁፍ ነው፡፡
ቻርልስ ኪንግስሌይ
ሰዎች ውበት ውስጣዊ ነው ይላሉ፡፡ እኔ ግን ከቆንጆ ኩላሊት ይልቅ ቆንጆ ፊትን እመርጣለሁ፡፡
ያልታወቀ ምንጭ
ውበት የአፍቃሪ ስጦታ ነው፡፡
ዊልያም ኮንግሪቭ
ውበት የሚጠወልግ አበባ ነው፡፡
ምሳሌያዊ አባባል
አካላዊ ውበት እንደተመልካቹ ሊሆን ይችላል፤ ውስጣዊ ውበት ግን ከውስጥ የሚያበራ በመሆኑ ማንም ሊክደው አይችልም፡፡
ኒሻን ፓንዋር
የሴት እውነተኛ ውበት ያለው ቆዳዋ፣ ፀጉሯ ወይም ተክለ ሰውነቷ ላይ አይደለም … ልቧ፣ ነፍሷ፣ መንፈሷ ላይ እንጂ፡፡
አሌክሳ ዶልም
ለውስጣዊ ውበታችሁ ስትል የምትወዳችሁ ብቸኛዋ ሴት እናታችሁ ናት፡፡
ያልታወቀ ምንጭ
 በዙሪያችሁ ውበትን በፈጠራችሁ ጊዜ ሁሉ ነፍሳችሁን እያደሳችሁ ነው፡፡
አሊስ ዎከር
ሴቶች ሆይ፤ ውበት የሚተረጎመው በጂንስ ሱሪያችሁ ልክ አይደለም፡፡
ሮበርት እስካሌት


Saturday, 25 April 2015 11:00

የሰዓሊያን ጥግ

 በብሩሼ እሰብካለሁ፡፡
ሔነሪ ኦሳዋ ታነር
ስዕል ሃሳቦቼን የማያይዝበት ምስማር ነው፡፡
ጆርጅስ ብራኪው
እኔ ነገሮችን አልስልም፤ የምስለው በነገሮች መካከል ያለውን ልዩነት ብቻ ነው፡፡
ሔነሪ ማቲሴ
ስዕሎች በጣም መማረክ የለባቸውም፡፡
ራልፍ ዋልዶ ኢመርሰን
ስዕል ማለቂያ የሌለው የሚመስል ጀብዱ ነው፡፡
ጃሶን
ስዕሎች ብዙ ጊዜ ግድግዳን ከማሳመር ይልቅ ያበላሻሉ፡፡
ዊሊያም ዎርድስ ዎርዝ
ሰዓሊ ሃሳቦቹን ከቆሻሻ ጋር እንዳይጥላቸው መጠንቀቅ አለበት፡፡
ቴሪ ጉይሌሜትስ
ለምንድን ነው የሞቱ ዓሳዎች፣ ሽንኩርቶችና የቢራ ብርጭቆዎች የምስለው? ልጃገረዶች እኮ እጅግ ውብ ናቸው፡፡
ሜሪ ሎውሬንሲን
ዓይኖቼ የተፈጠሩት የሚያስጠላውን ሁሉ ለመሰረዝ ነው፡፡
ራኦል ዱፊ
ማስታወቂያዎች የ20ኛው ክ/ዘመን የዋሻ ስዕሎች ናቸው፡፡
ማርሻል ማክሉሃን
ስዕል ቃላት አልባ ግጥም ነው፡፡
ሆራስ
ሰዓሊ፤ ሰዎች እንዲኖራቸው የማይፈልጉትን ነገር የሚፈጥር ነው፡፡
አንዲ ዋርሆል
ፎቶግራፍን ልዩ ፈጠራ የሚያደርገው የመጀመሪያ ጥሬ እቃዎቹ ብርሃንና ጊዜ መሆናቸው ነው፡፡
ጆን በርገር
ስዕል በተፈጥሮ አንፀባራቂ ቋንቋ ነው፡፡
ሮበርት ዴላዩናይ
ፀሐፊ በዓይኖቹ መፃፍ፣ ሰዓሊ በጆሮዎቹ መሳል አለበት፡፡
ጌርትሩድ ስቴይን
የሰው ልጅ ሁሉ ሰዓሊ ነው፡፡ የህይወትህ ህልም ውብ ስዕል መስራት ነው፡፡
ሚጌል ኤንጅል ሩይዝ
ስዕሎች የተንጠለጠሉበት ክፍል ሃሳቦች የተንጠለጠሉበት ክፍል ነው፡፡
ጆሹዋ ሬይኖልድስ