
Administrator
“የምግብ እርዳታው ዳግም መጀመር የመኖር ተስፋን ሰጥቶናል”
በአሜሪካው ተራድኮ ድርጅትና በአለም ምግብ ፕሮግራም ይሰጥ የነበረው ተቋርጦ የነበረው የቆየው የምግብ እርዳታ ዳግም መጀመር የመኖር ተስፋን እንዳሳያቸው ተረጂዎች ገለፁ፡፡ እርዳታው በተገቢው መንገድ ለተረጂዎች የሚደረስበትን መንገድ በማመቻቸቱ ረገድ እርዳታ
አቅራቢ ድርጅቶቹ ትኩረት ሰጥተው ሊሰሩ ይገባልም ብለዋል፡፡
የአሜሪካው የተራድኦ ድርጅት (ዩኤስኤይድ) እና የአለም የምግብ ፕሮግራም (WFP) ባለፈው አመት ሰኔ ወር ላይ ሰብአዊ እርዳታው እየተሰረቀ ላልተፈለገ ዓላማ እንዲውል ተደርጓል በሚል ምክንያት ሰብአዊ እርዳታውን መቋረጡን ተከትሎ፣ በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች የነበረው
ሰብአዊ ቀውስ እንዲባባስ ረሃብና ረሃብ ወለድ ሞት እንዲበራከት ምክንያት መሆኑም ተገልጿል፡፡በጦርነቱ ሳቢያ ከመኖሪያ ቀዬአቸው ተፈናቅለው በትግራይ በአማራና በአፋር ክልሎች የተለያዩ አካባቢዎች የሰፈሩ ተፈናቃዮች፣ የሰብአዊ እርዳታው ዳግም መጀመር በእለት ደራሽ እርዳታ እጦት ሳቢያ ለአስከፊ ረሃብና ሞት የሚዳረጉ ወገኖችን የሚታደግ በጎ እርምጃ ነው ብለዋል፡፡ የሰብአዊ እርዳታ አሰጣጥ ላይ ግን ትኩረት ተደርጎ ለእርዳታው ፈላጊዎች
ብቻ እንዲደርስ የሚደረግበት አሰራር ተግባራዊ ሊደረግ እንደሚገባው ተረጂዎቹ ተናግረዋል፡፡
የዓለም የምግብ ፕሮግራም በስርቆት ሳቢያ ኢትዮጵያ ውስጥ አቋርጦት የቆየውን የምግብ እደላ ዳግም ሲጀምር አሰራሩን በመቀየር ግልጽ፣ በማስረጃ በተደገፈና ገለልተኛ በሆነ አሰራር ላይ በማተኮር፣ እርዳታው ከ3.2 ሚሊዮን በላይ ለሚሆኑት ተረጂዎች መድረስ የሚያስችልበትን አሰራር ተግባራዊ እንደሚያደርግ አስታውቋል፡፡
አዲሱ አሰራር በስፋት የተሞከረና ጠንካራ የቁጥጥር አሰራርን ተግባራዊ ያደረገ ይሆናልም ተብሏል፡፡ ሰብአዊ እርዳታው ምግብ ወደ ሚከማችባቸው መጋዘኖችና እደላው ወደሚካሄድባቸው አካባቢዎች በሚጓጓዝበት ወቅት የተጠናከረ ጥበቃና ክትትል እንደሚደረግባበትም የአለም ምግብ
ድርጅት አስታውቋል፡፡ የምግብ እርዳታው ከታለመለት አላማ ውጪ ውሎ በሚገኝበት ወቅት አስቸኳይ ጥቆማና ሪፖርት በማቅረብ አፋጣኝ እምጃ መውሰድ የሚቻልበትን አሰራር እንደሚከተልም የዓለም ምግብ ድርጅት በመግለጫው አስታውቋል፡፡
➡️ የማህፀን ሞኝ ዕጢ ( Uterine fibroids) ምንድን ነው? ምልክቶችና መፍትሄዎችስ?
የማህፀን ሞኝ ዕጢ የምንለው የካንሰርነት ባሕርይ የሌለው የማሕፀን ውስጥ እባጭ ሲሆን ከማሕፀን ግድግዳ ጡንቻዎች የሚነሳ ነው ።
** በቁጥር እና በመጠን ይለያያሉ ።
** በፍጥነት ወይንም በዝግታ የሚያድጉ ሊሆኑ ይችላልሉ፡፡ አንዳንድ ጊዜም በራሱ ሊጠፋም ይችላል፡፡
** አንዲት ሴት በመውለጃ ዘመኗ እንዲሁም ከ 30 እስከ 40 አመት እድሜ ክልል ውስጥ የሚገኙ ሴቶች ላይ አብዝተው ይከሰታሉ።
** በአብዛኛው ግን የሚገኘው በድንገት በሚደረግ ምርመራ ነው ፤ ብዙ ሰዎች በሕይወት ዘመናቸው ውስጥ የማሕፀን ዉስጥ እጢ እንዳለ እንኳ ላያውቁ ይችላሉ ምክንያቱም
ብዙ ጊዜ ምንም አይነት ምልክቶች አያሳይም ።
➡️ የማሕፀን ሞኝ ዕጢ ምልክቶች
የማኅፀን ሞኝ ዕጢ በአብዛኛው ምንም ዓይነት ምልክት የማያሳይ ቢሆንም በአንዳንድ ሰዎች ላይ የሚከሰቱ ምልክቶች እንዚህ ናቸው፡፡
▪️ ከፍተኛ የሆነ የወር አበባ ደም መፍሰስ ወይም የሚያሰቃዩ የወር አበባዎች
▪️ ከሰባት ቀናት በላይ የሚቆይ የወር አበባ ማየት
▪️ ማሕፀን አካባቢ ግፊት መሰማት ወይንም ሕመም
▪️ ቶሎ ቶሎ የውሃ ሽንት መምጣት ወይም ለመሽናት መቸገር
▪️ የሆድ ድርቀትና በሆድ አካባቢ ወይም በታችኛው ጀርባ ላይ ህመም
▪️ በግንኙነት ወቅት ህመም.
➡️ ሐኪምዎን ማማከር የሚገባዎ መቼ ነው?
▪️ ብዙን ጊዜ ምንም አይነት ህመም ከሌላቸው በጊዜ ሂደት አንዲት ሴት ስታርጥ ወይም የወር አበባ ማየት ባቆመች ጊዜ መጠናቸው እየኮመሸሸ እና እያነሰ ስለሚመጣ በመድሀኒትም ሆነ በቀዶ ህክምና መታከም አያስፈልጋቸውም፤ ነገር ግን አንዲት ሴት :-
▪️ በእጢው ምክንያት የመጣ የወር አበባ መዛባት ፣ በብዛት ካለ እና ደም ማነስ ካመጣባት
▪️ ከፍተኛ የሆነ ህመም ካላት (ከእጢው ጋር የተገናኘ)
▪️ እጅግ መጠኑ የበዛ እጢ ከሆነ
▪️ እርግዝና ከከለከላት ወይም ደግሞ እርግዝና ተከስቶ ለውርጃ እንደምክንያት ከሆነ (ሌሎች እርግዝና የሚከለክሉ ወይም ውርጃን የሚያመጡ ነገሮች ሁሉ ከተጣሩ በውሀላ)
➡️ የማሕፀን ሞኝ ዕጢ እና እርግዝና
የማሕፀን ሞኝ ዕጢ በአብዛኛው እርግዝናን የማይቃረን ቢሆንም አንዳንዴ ዕጢው በሚገኝበት ቦታ ምክንያት በጥቂት ሰዎች ላይ እርግዝና እንዳይፈጠር መንስዔ ይሆናል፡፡ ይህ በሚሆንበት ጊዜ ሐኪምን በማማከር ከእርግዝና በፊት
መደረግ ያለባቸውን ቅድመ ሆኔታዎች ማድረግ ተገቢ ነው፡፡
➡️ ኢትዮ ጠቢብ ሆስፒታል
“የአክሊሉ የህይወት ጉዞ በምስል” የፊታችን እሁድ ይመረቃል
ተወዳጅ ሚድያ እና ኮሚኒኬሽን ከዶክተር ጌታቸው ተድላ ጋር በትብብር ያዘጋጁት ጸሀፌ ትእዛዝ አክሊሉ ሀብተወልድን የሚዘክር መርሃ ግብር፣ የፊታችን እሁድ ከጠዋቱ 3 ሰዓት ጀምሮ በሀገር ፍቅር ቴአትር ቤት ይካሄዳል፡፡
የጸሀፌ ትእዛዝ አክሊሉ ሀብተወልድ ቤተሰቦች የመርሃ ግብሩ አጋር ሲሆኑ፤ በዕለቱ ‹‹የአክሊሉ የህይወት ጉዞ በምስል›› የተሰኘ በዶክተር ጌታቸው ተድላ የተሰናዳ መጽሐፍም ይመረቃል ተብሏል፡፡
የተወዳጅ ሚድያና ኮሚኒኬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ እዝራ እጅጉ ለአዲስ አድማስ እንደተናገረው፤ በሚመረቀው መጽሐፍ ውስጥ እጅግ አስደናቂ የሆኑ የአክሊሉ የህይወት ጉዞን የሚያሳዩ 166 ፎቶግራፎች ተካትተዋል፡፡ ዶክተር ጌታቸው መጽሐፉን ለማዘጋጀት ሁለት አመት እንደፈጀባቸው ታውቋል፡፡
በመጽሐፉ የምረቃ ሥነ-ስርአት ላይ ዶ/ር ያእቆብ አርሳኖ፤ ዶ/ር ፍሬህይወት ስንታየሁና ሌሎች ምሁራንም የአክሊሉ ሀብተወልድን አስተዋጽኦ የሚያስረዱ ሲሆን፤ ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የተጋበዙ የመንግስት የሥራ ኃላፊዎችም ይታደማሉ ተብሏል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር አክሊሉ ሀብተወልድ፣ ከወጣትነታቸው አንስቶ ሀገራቸውን በዲፕሎማሲ ያገለገሉ ሲሆን፤ በተለይም በኢትዮጵያ የባህር በር ህጎች እንዲወጡ፤ ኤርትራ በፌዴሬሽን ከኢትዮጵያ ጋር እንድትቀላቀል ትልቅ ስራ የሰሩ ሀገር ወዳድ ኢትዮጵያዊ ነበሩ፡፡ አክሊሉ ሀብተወልድ፣ 60ዎቹ የቀዳማዊ ኃይለስላሴ ባለሥልጣናት በግፍ ሲገደሉ ህይወታቸውን ያጡ ታላቅ ሰው ነበሩ፡፡
ተወዳጅ ሚድያ እና ኮሚኒኬሽን፣ የአክሊሉ ሀብተወልድን አሻራ ለትውልዱ ለማስተላለፍ ባለፉት ዓመታት በርካታ ሥራዎችን ያከናወነ ሲሆን፤ ከእነዚህም ውስጥ ስለ አክሊሉ ሀብተወልድ በኦድዮ ሲዲ እና በዲቪዲ ታሪካቸው በዘጋቢ ፊልም እንዲሰራጭ ማድረጉ ተጠቃሽ ነው፡፡ በተጨማሪም የዋሉት ውለታ በእንግሊዝኛም ተዘግቦ እንዲቀርብ አድርጓል፡፡ ባለፉት 8 አመታት፣ ከ59 ጊዜ በላይ የአክሊሉ ሀብተወልድ አስተዋጽኦ በመገናኛ ብዙኃን እንዲዘገብም ተወዳጅ ሚድያ እና ኮሚኒኬሽን የመሪነት ሚናውን ተወጥቷል፡፡
ይህ ፕሮጀክት አሁን ላለበት ደረጃ እንዲበቃ ደግሞ የጠቅላይ ሚኒስትር አክሊሉ ሀብተወልድ ልጅ አቶ አምዴ አካለወርቅ ትልቁን የአንበሳ ድርሻ የሚወስዱ ሲሆን በመቀጠል ደግሞ ከ10 አመት በፊት የአክሊሉን የእስር ቤት ማስታወሻ ወደ እንግሊዝኛ የመለሱት ዶክተር ጌታቸው ተድላ ለእኚህ ታላቅ ኢትዮጵያዊ መታወቅና መታወስ የበኩላቸውን ተወጥተዋል፡፡
ሳፋሪኮም ኢትዮጵያ ለኩባንያው አዲስ ሥራ አስፈፃሚ መሾሙን አስታወቀ
ሳፋሪኮም ኢትዮጵያ፣ በቅርቡ ለቅቀዋል ሲባል የነበሩትን የቀድሞ ዋና ሥራ አስፈፃሚ በመተካት፣ ለኩባንያው አዲስ ዋና ሥራ አስፈፃሚ እንደተሾመለት አስታወቀ፡፡
ቤልጂየማዊው አዲሱ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ዊልያም ቫንሀለፑተን፣ የቀድሞውን ሥራ አስፈፃሚ አንዋር ሶሳን በመተካት የተሾሙ መሆናቸውን ኩባንያው በዛሬው ዕለት ለመገናኛ ብዙኃን ይፋ አድርጓል፡፡ አዲስ የተሾሙት ሥራ አስፈፃሚ በዘርፉ ትልቅ እውቀትና የ25 ዓመታት ልምድ ያላቸው መሆኑ ተነግሯል፡፡
ሳፋሪኮም በአሁኑ ሰዓት በኢትዮጵያ ከ2 ሺህ በላይ የቴሌኮም አገልግሎት መስጫ ጣቢያዎች እንዳሉት የተናገሩት አዲሱ ዋና ሥራ አስፈጻሚ፤ በቀጣዮቹ ሁለት አመታት ይህንን ወደ 7 ሺህ ለማሳደግ ማቀዱን አስታውቀዋል፡፡
በተጨማሪም በአሁኑ ወቅት 35 በመቶ የኢትዮጵያን ክፍል በኔትወርክ መሸፈን መቻሉን የገለጹ ሲሆን፤ ይህንንም በሁለት ዓመታት ውስጥ ከ80 በመቶ በላይ ለማሳደግ መታቀዱን ጠቁመዋል፡፡
ኩባንያው በአሁኑ ሰዓት ትርፍ አግኝቷል ለማለት ከባድ ነው ያሉት ሥራ አስፈፃሚው፤ በቀጣዮቹ ሁለትና ከዛ በቀረቡ ዓመታት ውስጥ ወደ ትርፍ እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡
ኩባንያው በኢትዮጵያ ከ900 በላይ ሰራተኞች ያሉት መሆኑን የተናገሩት አዲሱ ሥራ አስፈፃሚ፤ በቀጣዮቹ ሁለት አመታት 500 ለሚሆኑ ሰዎች ቀጥተኛ የስራ እድል እንደሚፈጥርም አመልክተዋል፡፡
ዘመናዊ የፕላስቲክ ቧንቧና መገጣጠሚያ ማምረቻ ፋብሪካ ሊመረቅ ነው
ኢትዮቴሌኮም፤ የነዳጅ አቅርቦት ሰንሰለትንና የነዳጅ ኩፖንን ዲጂታል ለማድረግ የሚያስችሉ ሶሉሽኖችን አስተዋወቀ
• የሦስተኛ ወገን ኢንሹራንስን ዲጂታላይዝ የሚያደርጉ መላዎችንም አስጀምሯል
ኢትዮ ቴሌኮም፤ ከንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር፣ ከነዳጅና ኢነርጂ ባለስልጣንና የኢትዮጵያ ነዳጅ አቅራቢ ድርጅት ጋር በመተባበር፣ የነዳጅ አቅርቦት የአሰራር ስርዓትንና የነዳጅ ኩፖንን ዲጂታላይዝ ለማድረግ የሚያስችል እንዲሁም ከትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስቴርና ከመንገድ ደህንነትና ኢንሹራንስ ፈንድ አገልግሎት ጋር የተሽከርካሪ አደጋ የሦስተኛ ወገን መድን አገልግሎትን ዲጂታላይዝ የሚያደርጉ ሶሉሽኖችን በይፋ አስጀምሯል፡፡
ኩባንያው በዛሬው ዕለት የነዳጅ አቅርቦት ሰንሰለትን በተማከለ የዲጂታል ሥርዓት ለማከናወን የሚያስችል የነዳጅ አቅርቦት ትስስር አስተዳደር ሶሉሽን /Fuel Supply Chain Management System/ በማበልጸግ ተግባራዊ ማድረጉን ያስታወቀ ሲሆን፣ ይህም ሶሉሽን በነዳጅ አቅርቦት ሰንሰለቱ ላይ ያሉ ዘልማዳዊ የአሰራር ሂደቶችንና በወረቀት ላይ የተመሰረቱ አሰራሮችን ለማዘመን፣ ግልጽነት ያለው የነዳጅ አቅርቦትና ግብይትን ለማስፈን፣ ትክክለኛ ዳታ በወቅቱ ለማግኘት እንዲሁም በሂደቱ ውስጥ ለሚያስፈልጉ መሳሪያዎች ግዢ የሚውል የውጪ ምንዛሪ እጥረትን ለመቅረፍ ትልቅ ፋይዳ እንደሚኖረው አመለክቷል፡፡
በተጨማሪም፤ የዘርፉ ተዋናዮች ማለትም የነዳጅ ጣቢያዎችና ቀጥተኛ ተጠቃሚ ደንበኞች፣ የነዳጅ አቅራቢ ኩባንያዎች፣ የኢትዮጵያ የፔትሮሊየም አቅራቢ ድርጅት እንዲሁም የነዳጅና ኢነርጂ ባለስልጣን አጠቃላይ የነዳጅ አቅርቦት ሰንሰለት ላይ የሚከናወኑ እንቅስቃሴዎችን ለመከታተል፣ የነዳጅ አቅርቦት ትዕዛዝን በዲጂታል መላ ለመስጠት/ለማቅረብ፣ ትዕዛዝ ለመቀበል እንዲሁም አስፈላጊውን ዳታ በወቅቱ ለማግኘት (real-time data access) ከፍተኛ ጠቀሜታ ይኖረዋል ተብሏል፡፡
በሌላ በኩል፤ ኢትዮ ቴሌኮም፣ የማንዋል የነዳጅ ኩፖን ሽያጭ አገልግሎት አሰራርን ወደ ወረቀት-አልባ የዲጂታል ኩፖን በመቀየር አዲሰ አሰራር ያስተዋወቀ ሲሆን፤ ይህም ዘመናዊ አሰራር የነዳጅ ኩባንያዎች የአገልግሎት አሰጣጥን ለማዘመን፣ የነዳጅ ማደያዎችን የአገልግሎት አማራጭ ለማሳደግ፣ ግብይቶችን ለማሳለጥ፣ የገንዘብ ፍሰትን ለማሻሻል፣ የሥራ ማስኬጃ ወጪዎችን ለመቀነስ፣ የተጠቃሚዎችን መጠን ለመጨመርና ሽያጭ ለማሳደግ፣ የዲጂታል ኩፖን ዳታዎችን ለመቆጣጠር እንዲሁም ደህንነቱ የተጠበቀ ግብይት ለማካሄድ የሚያስችል የዲጂታል ሶሉሽን ማስተዋወቁን በመግለጫው አመልክቷል፡፡
በተመሳሳይ ሁኔታ፤ ኩባንያው የሦስተኛ ወገን የመድን አገልግሎትን በዲጂታል ስርአት አማካኝነት ለመስጠት የሚያስችል ሶሉሽን ከትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስቴርና ከመንገድ ደህንነትና መድን ፈንድ ጋር በመተባበር ይፋ አድርጓል። ይህም የኢንሹራንስ አገልግሎት አሰጣጥ ተግዳሮቶችን በማስቀረት በተለይም የተማከለ መረጃ እንዲኖር ለማስቻል፣ ክፍያን በወቅቱና በዲጂታል መንገድ ለማከናወን፣ የአገልግሎት አሰጣጥ ጥራትን ለማሻሻል፣ የተሟላ ሪፖርት በወቅቱ ለማግኘትና ወረቀት-አልባ አገልግሎት ለመስጠት ትልቅ ፋይዳ ይኖረዋል ተብሏል፡፡
በተጨማሪም ይህ የዲጂታል ሶሉሽን ለኢንሹራንስ ኩባንያዎች የሥራ ማስኬጃ ወጪዎችን ለመቀነስ፣ ተገልጋዮች የሚያደርጉትን ምልልስና ውጣ ውረድ በማስቀረት ባሉበት ሆነው በቀጥታ (online) እንዲስተናገዱ ለማድረግ፣ በኢንሹራንስ ሂደቶች ውስጥ የሚከሰቱትን ተግዳሮቶች ለመቀነስ እንዲሁም የእድሳትና ባለቤትነት ለውጥ አሰራርን ዲጂታላይዝ ለማድረግ ትልቅ ሚና እንደሚኖረው ኢትዮቴሌኮም ጠቁሟል፡፡
12ኛው ዓለማቀፍ የጥራጥሬና ቅባት እህሎች ኮንፈረንስ በህዳር ወር ይካሄዳል
12ኛው ዓለማቀፍ የጥራጥሬና ቅባት እህሎች ኮንፈረንስ በህዳር ወር ይካሄዳል
12ኛው ዓለማቀፍ የጥራጥሬና ቅባት እህሎች ኮንፈረንስ “ኢትዮጵያ ለግብርና ምርት ፍላጎትዎ አስተማማኝ ምንጭ” በሚል መሪ ቃል፣ ህዳር 11 እና 12 ቀን 2016 ዓ.ም በስካይላይት ሆቴል እንደሚካሄድ ተገለፀ።
ኮንፈረንሱን የኢትዮጵያ ጥራጥሬ፣ ቅባት እህሎችና ቅመማቅመም አዘጋጅቶ ላኪዎች ማህበር፣ ከኢፌዲሪ ንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር ጋር በመተባበር እንደሚያዘጋጁት ተጠቁሟል።
የኮንፈረንሱን አጠቃላይ ዝርዝር ሁኔታ አስመልክቶ በዛሬው ዕለት ረፋድ ላይ የኢትዮጵያ ጥራጥሬ፣ ቅባት እህሎችና ቅመማቅመም አዘጋጅቶ ላኪዎች ማህበር፣ ርብቃ ህንፃ 7ኛ ፎቅ ላይ በሚገኘው ፅ/ቤቱ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥቷል።
ለሁለት ቀናት በስካይላይት ሆቴል በሚካሄደው ኮንፈረንስ ላይ 400 የአገር ውስጥ ላኪዎች፣ የእርሻ ግብአትና ማሽነሪ አቅራቢዎች፣ የጉምሩክ አስተላላፊዎች፤ እንዲሁም ከ20 የተለያዩ አገራት የሚመጡ ከ100 በላይ ዓለማቀፍ ምርት ገዢ ኩባንያዎች እንደሚሳተፉ ለማወቅ ተችሏል። ከእነዚህ አገራትም ውስጥ ቤልጂየም፣ ቻይና፣ ግብፅ፣ ህንድ፣ እስራኤል፣ ጃፓን፣ ፓኪስታን፣ ሳውዲ አረቢያ፣ ሲንጋፖር፣ ሱዳን፣ ታንዛኒያ፣ ቱርክ፣ የተባበሩት አረብ ኢምሬትስ፣ ዩክሬን፣ ዩናይትድ ኪንግደም፣ ኡዝቤኪስታን፣ ጣሊያን፣ ናይጀሪያና ቡርኪናፋሶ ይገኙበታል ተብሏል።
የኢትዮጵያ ጥራጥሬ፣ ቅባት እህሎችና ቅመማ ቅመም አዘጋጅቶ ላኪዎች ማህበር አመራሮች በመግለጫው ላይ እንዳመለከቱት፤ ዓለማቀፍ ገዢዎችን፣ የአገራችን የዘርፍ ምርት ላኪዎችን፣ የእርሻ ምርት ግብአት አቅራቢዎችን፣ ከፍተኛ የመንግስት ተቋማትና የተለያዩ አገልግሎት ሰጪዎችን በአንድ መድረክ በማገናኘት የንግድ ትስስር መፍጠር ከኮንፈረንሱ ዓላማዎች አንዱ ሲሆን፤ ተሳታፊዎች በዘርፉ ያለውን ዓለማቀፍ የንግድ አጠቃላይ ሁኔታ (የአቅርቦት ፍላጎትና ዋጋ አዝማሚያዎች) በተመለከተ የተሟላ መረጃ እንዲያገኙ ማስቻልም ሌላው የኮንፈረንሱ ዓላማ ነው ተብሏል።
ኮንፍረንሱን የሀገር ውስጥ ላኪዎች የንግድ ግንኙነታቸውን በላቀ ሁኔታ ለማጠናከር እንዲሁም አዳዲስ የንግድ ግንኙነቶችን ለመመስረት እንደሚጠቀሙበት የተገለፀ ሲሆን ፤ በተጨማሪም ቀጣይ የሽያጭ ውሎችን ለመፈራረም ከፍተኛ ዕድል ይፈጥርላቸዋል ተብሏል፡፡
ሀገሪቱ ዘርፉን እንድታሳድግ በመንግሥት የታቀደውን ዕቅድ ከማሳካት አንፃርም ኮንፈረንሱ ከፍተኛ አስዋፅኦ እንደሚያበረክት የማህበሩ አመራሮች ጠቁመዋል፡፡
በኮንፈረንሱ ላይ 14 ፅሁፍ አቅራቢዎች በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ፅሁፎች እንደሚያቀርቡም ታውቋል፡፡
የማህበሩ መረጃ እንደሚያመለክተው፤ ኢትዮጵያ ወደ ውጭ ከምትልካቸው የግብርና ምርቶች የጥራጥሬና ቅባት እህሎች ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ ከሚያስገኙ ምርቶች መካከል ተጠቃሽ ሲሆኑ፤ አገሪቱ በ2015 በጀት ዓመት 147, 205 ቶን ቅባት እህሎች ወደ ውጭ በመላክ 253,344,754 ዶላር ገቢ አግኝታለች፡፡ በዚሁ በጀት ዓመት 377,261 ቶን የጥራጥሬ ምርቶች ወደ ውጭ ተልከው፣ 310,568,278 ዶላር ገቢ መገኘቱም ታውቋል፡፡
ባለፈው ዓመት በህዳር ወር 11ኛው የጥራጥሬና ቅባት እህሎች ኮንፈረንስ በሸራተን አዲስ ሆቴል መካሄዱን ያስታወሰው የማህበሩ መግለጫ፣ በኮንፈረንሱ ላይ ከ435 በላይ ገዢዎች፣ ላኪዎች፣ አስመጪዎችና አገልግሎት ሰጪዎች መሳተፋቸውን እንዲሁም ከ250 በላይ ጥሪ የተደረገላቸው የመንግስት የሥራ ሃላፊዎችና ተጋባዥ እንግዶች በተገኙበት በስኬት መጠናቀቁን አውስቷል፡፡
የቴሌግራም ቻናልችንን በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…
https://t.me/AdissAdmas
addisadmassnews.com Issue1243
በአልባኒያ ሊግ ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ የነበረው ጋናዊው አጥቂ በጨዋታ መሐል ሕይወቱ አለፈ
ኢትዮጵያን ያመለጣት ዕድል!
ኮሎኔል መንገሻ ወልደ ሚካኤል (8) ከአባቴ ጋር አንድ ኮርስ ሲሆኑ ያገኘኋቸውም አዲስ አበባ ነበር። አባቴ የልዩ ኃይሉ አዛዥ ሆኖ ድሬደዋ የሚሠራበት ወቅት እሳቸው እዚያው ከተማ የመድፈኛ ጦር የትምህርት መኮንን ሆነው ለአንድ ዓመት ቆይተዋል። በወቅቱም ከአባቴ ጋር ብዙ ተቀራርበው እንደነበር ቃለ-ምልልስ ስናደርግ አጫውተውኛል። ከዚያ ወዲያም በደብዳቤ ያስታወሱትን ሁሉ ጽፈው ልከውልኛል። ድሬደዋ በእረፍታቸው ወቅት በአባቴ ላንድሮቨር ሆነው አብረው ይዝናኑ እንደነበር ነግረውኛል።
“በዚያ ወቅት አባትሽ ጂቡቲ ገና ነፃ ሳትሆን ሀረር፣ ጅጅጋና ኦጋዴን በመሯሯጥ እጅግ ይባክን ነበር። አንዳንዴ በጣም በጠዋት ቀድሞ ይነሳና ከተባሉት ሥፍራዎች ሲዞር ውሎ ማታ ይገባል። የተሰጠውን ግዳጅ ለመፈጸም ሁሌ እንደተሯሯጠ ነበር።” ኮሎኔል መንገሻ ወልደሚካኤል።
ኮሎኔል መንገሻ ወልደሚካኤል አባቴን ሲያነሱ “ውድ ወንድሜ ጀግናው ዳግማዊ ቴዎድሮስ” በማለት ነው በደብዳቤአቸውም ሆነ በቃላቸው የሚጠቅሱት። በተለምዶ አብሮ ትምህርት የጨረሰ ሰው ይናናቃል-ይባላል። እሳቸው ግን በጣም የጠራ ቅንነት ቢኖራቸው ነው እንዲህ ማለታቸው። ክፋቱ ግን ከአባቴ ጋር ምንም አብረው አልሠሩምና ስለ አባቴ የሚያቁት ነገር በጣም የተወሰነ መሆኑ ላይ ነበር።
አባቴን ከጂቡቲ ጉዳይ ጋር በማያያዝ ለመጀመሪያ ጊዜ ያነሱልኝ ሰው ግን እሳቸው ነበሩ። አባቴ ጂቡቲን በተመለከተ “በመሯሯጥ እጅግ ይባክን” የነበረው ምን እያደረገ እንደሆነ ግን ፈጽሞ አያውቁም። ምን ዓይነት ተግባር እንደፈጸመ ማወቅ አልቻሉም። በጠዋት ተነስቶ ማታ መግባቱን ግን አስተውለዋል። አብረው እየዞሩ እየጠጡና እየተዝናኑም አላጫወታቸውም። ከባድ ሚስጥር እንደነበር ግልጽ ነው። እናም አልተወው ነገር አክብደው ነው የገለጹት። እናኔም ጂቡቲ ከኢትዮጵያ ጋር ለመቀላቀል እንድትችል ይደረግ ከነበረው የፖለቲካ፣ የፕሮፓጋንዳ እና የውጭ ጉዳይ የዲፕሎማሲ ጥረት ጋር የተያያዘ ሊሆን ይችላል። ጽሁፎችንም በሄሊኮፕተሮች ይበትኑ እንደነበር ሰምቻለሁ። ለዚሁ ተግባር ይሆናል አባቴ ሲሯሯጥ የነበረው ብዬ ገመትኩ።
ይህንን እንደዚህ ደምድሜ ካለፍኩ ወዲያ ብዙ ቆይቶ በሌላ ቃለ-ምልልስ ካልጠበኩትና ከጉዳዬም ጋር ግንኙነት ይኖረዋል ብዬ ካልገመትኩት ሰው ፍንጩን የሚያብራራ አቢይ ነጥብ አገኘሁ። የመደምደሚያ ግምቴም ብዙም ከእውነቱ አለመራቁን አረጋገጥኩ። አንዳንዴ ሰዎች የሚሰጡት ትንሽ ፍንጭ ከሌላ ሰዎች መረጃ ጋር ሲዋሃድና ሲጣመር ይጎላና ይገዝፋል።
አቶ እጅጉ ደሴ (40) በኢትዮጵያ የአየር መንገድ አስተዳደር ውስጥ አንድ ከፍተኛ ባለስልጣን ሆነው ያገለገሉ ናቸው። ስለበረራ ድህንነቱ የአባቴ አገልግሎት- ስናደርግ በአጋጣሚ የጅቡቲውን ነገር አነሱብኝ። አባቴ አየር መንገዱን ከለቀቀ ወዲህ አንዴ እራት ጋብዘውት እቤታቸው ይወስዱታል። በእራቱ ግብዣ ላይ ሲጨዋወቱ በአጋጣሚ የጅቡቲው ነገር ተነሳ። ጅቡቲ ከላይ እንዳሰፈርኩት ተጠቃላ የፈረንሳይ ቅኝ ግዛት የሆነችው እ.ኤ.አ በ1888 ዓ.ም ላይ ነበር። ፈረንሳይ በጀነራል ቻርለስ ደጎል እየተመራች በነበረበት ወቅት፤ እ.ኤ.አ በ1967 ዓ.ም ላይ፤ የጅቡቲ ህዝብ አንድ የብያኔ ህዝብ እድል አገኘ። ቀደም ሲልም ሌላ እድል ተሰጥቶት ከፈረንሳይ ጋር ለመቆየት መርጦ ነበር። ይህን ጊዜ ግን ጄኔራል ደጎል ከጃንሆይ ጋር ጥሩ ቅርበትና መልካም ግንኙነት ነበራቸውና ከብያኔ ህዝቡ ወደ ፈረንሳይ ጅቡቲን በምትለቅበት እለት ኢትዮጵያ በምትኩ ብትገባ ምንም እንደማይቃወሙና እርምጃም እንደማይወስዱ አረጋግጠውላቸው ነበር።
ጂቡቲ የአፋርና የኢሳ ብሔር ህዝቦች ይኖሩባታል። ኢትዮጵያ በአፋሮቹ ከኢትዮጵያ መቀላቀል መፈለግ ስታምን፣ ሱማሊያ ደግሞ በኢሳዎቹ ከሶማሊያ መቀላቀል ታምናለች። ለጅቡቲ ህዝብ ድምጽ አሰጣጥም ኢትዮጵያና ሶማሊያ የራሳቸውን ቅድመ ቅስቀሳና ጥረት አድርገዋል። ሱማሊያ ከቅስቀሳው ባሻገር የእራሷን ሰው ለምርጫ ወደ ጁቡቱ ሱማሌያ ስታግዝ፣ ኢትዮጵያ ከፕሮፓጋንዳ ቅስቀሳ ውጭ አልዘለቀችም ነበር። ውጤቱ ደግሞ ለሁለቱም አልሆነም፤ የጅቡቲ ህዝብ በፈረንሳይ እጅ ሆኖ ወደ ነጻነት ለማምራት በድምጹ ወሰነ።በወቅቱ ጃንሆይ የደጎልን የይግቡ አረንጓዴ መብራት እንዳገኙ የ3ኛ ክፍለ ጦርና የክብር ዘበና ጦርን ከጅቡቲ ድንበር በተጠንቀቅ አሰፈሩ። አባቴ በድንበሩ ተጠንቀቅ ላይም ከ3ኛ ክፍለ ጦር አዛዥ ከጄ/ል አበበ ገመዳ ጋር አብሮ ነበር። ይህንን ነበር አይቶ እጅጉ ደምሴን ያጫወታቸው።
በቦታው ሆነው የጃንሆይን “የወደፊት ቀጥሎ” ትዕዛዝ ሲጠባበቁ ከሌሊቱ 6፡00 ሰዓት ገደማ ላይ እራሳቸው ጃንሆይ በስልክ/ሬዲዮ ጄኔራሉን አስቀርበው፣ “አበበ አትግባ!” አሏቸው። ጄነራሉ ስልኩን ሰምተው ስቅስቅ እንዳሉ ገልጾ፤ “ሁለተኛ ኢትዮጵያ እንደዚህ አይነት እድል አያጋጥምሽም! ደጎል እኮ እኛ ስንወጣ እናንተ ግቡ ብሏል!” ብሎ በምሬትና ቁጭት አባቴ እንዳጫወታቸው አቶ እጅጉ ደምሴ ገለጹልኝ።
ጃንሆይ ለምን አትግባ አሉ? ለሚለው ጥያቄም አቶ እጅጉ ደምሴም መልሱን በደንብ ደርሰውበታል። ቀደም ሲል አልጀሪያና ሞሮኮ ተጋጭተው ሊዋጉ ጦራቸውን በየድንበራቸው በማዘጋጀት ላይ እያሉ በአጋጣሚ ጃንሆይ በወቅቱ በይይቤሪያ በጉብኝት ላይ ሆነው ሁኔታውን አወቁ። ከዚያ አልጀርስና ካዛብላንካ ተመላልሰው መሪዎችን አነጋግረው፣ የሁለቱንም ጦር ከድንበራቸው እንዲያፈገፍጉ በማድረግ ጦርነቱን አስቀሩት። ሱዳንንም ከተቃዋሚ ቡድን ጋር አስታርቀው ነበር።
ስለዚህም ጃንሆይ “የሰላም የኖቤል ሽልማት” ያገኛሉ ተብሎ በተስፋ ላይ ነበሩ። በዚያ ወቅት ጅቡቲን ከወረሩ ያ የኖቤል ሽልማት እድል መቅረቱም ሆነ ለዚህ ነው ጦሩን እንዲመለስ ያደረጉት። ሻምበል ጌታቸው ወ/ማርያም የክብር ዘበኛ ጦር፣ ያኔ ድንበሩ ድረስ መሄዱንና የጃንሆይን የኖቤል ሽልማት ጉዳይ ትክክለኝነት ማወቃቸውን በደንብ አረጋግጠውልኛል። ዶ/ር ሰለሞን አበበ (41) ደግሞ የኖቬል ሽልማትን ጉዳይ እንደ አንድ ምክንያት ተቀብለው በተጨማሪም ጃንሆይን ከጅቡቲ ህዝብ መሃል በፈረንሳይ ደሞዝተኝነት የሚተዳደረው ብዙ ነበርና ያንን ማስተዳደሩና ደመወዝ መክፈሉን ፈርተው የውሃና የመብራት ችግሩን ብቻ እንኳን ምን ያህል ወጪ እንደሚጠይቅ አውቀውና መክረው ያደረጉት ነው ብለው ያምናሉ። ጦሩ ድንበር ላይ በተጠንቀቅ መቆሙን በተመለከተም እሳቸው በወቅቱ ሀረር ክፍለ ሀገር የልማት አስተዳዳሪ ሆነው ይሰሩ ስለነበር በደንብ ማወቃቸውን አረጋግጠውልኛል።
ዶ/ር ሰለሞን የተወለዱትና ያደጉት ሀገር ሲሆን በተለያዩ ክፍለ ሀገራት በአስተዳደርና ልማት ስራ አገልግለው ከዚያም በተመድ የስደተኛ አስተዳዳሪነት በየሀገሩ ተዘዋውረው አሁን ዳላስ ቴክሳስ ውስጥ በጡረታ ይኖራሉ። በዚህ በዳለስ ከተማ ባለው የኢትዮጵያ ህብረተሰብ በአባትነት መካሪ፣ አስተባሪና አስታራቂ በማገልገል ተወዳጅነት አላቸው።
በሌላ ምዕራፍ ላይ የጠቀስኳቸው ኮሎኔል ዘሩ እጅጉ (921) ደግሞ ለሁለተኛ ጊዜ በስራ አባቴን የተገናኙት ድሬዳዋ ሆኖ ነበር። እሳቸው በዚህም ወቅት በመረጃ ሥራው ላይ ነበሩ። ድሬዳዋ አየር ኃይል ማሠልጠኛ ሲቋቋም እሳቸውም በሙያቸው መምጣታቸውን ያስታውሳሉ። የፕሮፓጋንዳ ሥራውን በተመለከተ በጣም የቀረበና የበለጠ ትዝታ አላቸው። በዚህ ወቅት አባቴ የሚመራው ልዩ ኃይል የሱማሌን መንግስት ለማናወጥ ብዙ የፕሮፓጋንዳና ቅስቀሳ ሥራን መስራቱን በደንብ ያስታውሳሉ። ጽሁፎችን በአየር ላይ ሆነው ለመበተን አባቴና አባባሎቹ እስከ በረራ ድረስ ጠልቀው ይገቡ እንደነበር ገልጸው፤ አባቴ ጦሩን ይዞ ሲንቀሳቀስ እሳቸው መረጃ በመስጠት የጠበቀ የስራ ግንኙነት ትብብር እንደነበራቸውና እሳቸው እራሳቸውም በሙያቸው የተካፈሉበት ጉዳይ መሆኑን በመግለጽ አረጋግጠውልኛል።