Administrator

Administrator

በሽታው እስካሁን ከ10 ሺ በላይ ሰዎችን ገድሏል

    ከአንድ አመት በፊት በምዕራብ አፍሪካ አገራት የተቀሰቀሰውና ከ10ሺህ በላይ ሰዎችን ለህልፈት እንደዳረገ የተነገረለት የኢቦላ ወረርሽኝ እስከ መጪው ነሐሴ ወር ድረስ ሙሉ ለሙሉ በቁጥጥር ስር ይውላል ተብሎ እንደሚጠበቅ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ማስታወቁን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
የተመድ የኢቦላ ምላሽ ግብረ ሃይል ሃላፊ ኢስማኤል ኦውልድ ቼክን ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ ለመጀመሪያ ጊዜ በጊኒ የተከሰተውንና ወደ ሌሎች የምዕራብ አፍሪካ አገራት የተስፋፋውን የኢቦላ ቫይረስ ወረርሽኝ በቁጥጥር ስር በማዋል ረገድ፣ በመጀመሪያዎቹ የወረርሽኙ ወራት በተመድ የተሰሩት ስራዎች ያልተቀናጁና በእውቀት ላይ ያልተመሰረቱ ነበሩ፡፡
ይሄም ሆኖ ግን ለችግሩ መፍትሄ ለመስጠት የሚደረጉት እንቅስቃሴዎች በሂደት እየተሻሻሉ መጥተዋል ያሉት ሃላፊው፤ ባለፈው አንድ አመት ኢቦላን ለመግታት በተደረገው እንቅስቃሴ ልምድ ቀስመናል፤ ወረርሽኙን እስከ መጪው ነሐሴ ወር ሙሉ ለሙሉ መግታት የሚቻልበት ደረጃ ላይ ደርሰናል ብለዋል፡፡
የኢቦላ ቫይረስ ዳግም በወረርሽኝ መልክ እንዳይከሰት ለመከላከልና አፋጣኝ መፍትሄ ለመስጠት ሲባል፣ ራሱን የቻለ አለማቀፍ የኢቦላ ፈጣን ምላሽ ቡድን ለማቋቋም የሚያስችል ዕቅድ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት መውጣቱንም ዘገባው አስታውቋል፡፡
ድንበር የለሹ የሃኪሞች ቡድን በበኩሉ፤እስካለፈው ጥር ወር ድረስ በምዕራብ አፍሪካ አገራት በቫይረሱ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር እየቀነሰ ቢመጣም፣ ከዚያ በኋላ አልቀነሰም፤ ወረርሽኙ ገና ሙሉ ለሙሉ አልተገታም ብሏል፡፡
የዓለም የጤና ድርጅት መረጃ እንደሚጠቁመው፣እስከያዝነው ሳምንት መጨረሻ ድረስ፣4ሺ 296 ላይቤሪያውያን፣ 3ሺ 742 ሴራሊዮናውያን፣ 2ሺ 261 ጊኒያውያን፣ 8 ናይጀሪያውያን፣ ስድስት ማሊያውያንና አንድ አሜሪካዊ በኢቦላ ሳቢያ ህይወታቸው አልፏል፡፡

በዓለማችን በግዙፍነቱ አቻ እንደማይገኝለት የተነገረውና ሃይብሪድ ኤር ቪሄክልስ በተባለው የእንግሊዝ ኩባንያ ዲዛይን የተደረገው “ኤርላንደር 10” የተሰኘ አዲስ አይነት አውሮፕላን ከስድስት ወራት በኋላ ስራው ሙሉ ለሙሉ ተጠናቅቆ በእንግሊዝ ሰማይ ላይ የሙከራ በረራ እንደሚያደርግ ሲኤንኤን ዘገበ፡፡
በአሜሪካ የጦር ሃይል ለወታደራዊ አሰሳ ስራ እንዲውል ታስቦ የተሰራው ይህ አውሮፕላን፤ርዝማኔው ከአንድ የእግር ኳስ ሜዳ እንደሚበልጥ የጠቆመው ዘገባው፣ 302 ጫማ ቁመት እንዳለው፣ዲዛይኑም ከተለመደው ወጣ ያለና የአውሮፕላንና የሄሊኮፕተር ቅልቅል እንደሆነ አመልክቷል፡፡
ኩባንያው የአውሮፕላኑን ፕሮጀክት ከጀመረ ቆየት ቢልም፣ በበጀት እጥረት ምክንያት ሥራው  ሲጓተት መቆየቱን ያስታወሰው ዘገባው፣ በመጨረሻም ከእንግሊዝ መንግስት ባገኘው የ5.1 ሚሊዮን ዶላር ብድር ስራውን ከዳር ማድረሱን አስታውቋል፡፡
አውሮፕላኑ 10 ቶን ክብደት የመጫን አቅም ያለው ሲሆን አጠቃላይ አሰራሩ ዘመናዊና በቴክኖሎጂ የታገዘ ነው ተብሏል፡፡ ነዳጅ ቆጣቢነቱ፣ በአስቸጋሪ የአየር ንብረት ሁኔታዎችን ተቋቁሞ የመብረር ብቃቱና በአካባቢ ብክለት እምብዛም አለመታማቱም ተመስክሮለታል፡፡
ኤርላንደር 10 ለመነሳትና ለማረፍ ሰፊ ማኮብኮቢያና የተመቻቸ የአውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያ የሚፈልግ አለመሆኑና በቀላሉ መንቀሳቀስ በሚችልበት መልኩ መሰራቱ ደግሞ፣ ከወታደራዊ አሰሳ ባለፈ በአደጋ ጊዜ የፈጥኖ ደራሽ ስራን ለማከናወን ተመራጭ አድርጎታል ብሏል ዘገባው፡፡

Saturday, 28 March 2015 09:14

የግጥም ጥግ

የተነሳህ ለት

የዛፍ ባላጋራ
ከምትተናነቅ
ከመቶ ቅርንጫፍ
ከሺህ ቅጠል ጋራ
እንደጡንቻ ሁሉ
ስልት በማፈርጠም
ወርደህ ከግንዱ ጋር
አንድ ለአንድ ግጠም፡፡

ሠም እና ሠም

አበባው አብቦ ንቡ ገብቶልህ
እንግዲህ ጎበሌ ማር ካላበላህ
“እንኳንስ ማርና አላየሁም ሰፈፍ”
እያልህ በመራራ ዜማ ከመንሰፍሰፍ
ያ! የቀፎው አውራ ማሩን የደበቀው
ንብ ሆኖ ሲመጣ ጭስ ሆነህ ጠብቀው፡፡
(“የአመድ ልጅ እሳት” የግጥም መድበል፤
መጋቢት 2007)

Saturday, 28 March 2015 09:02

የፀሐፍት ጥግ

ሳንሱር፤ ህፃን ልጅ ስቴክ (የተጠበሰ ስጋ) ማኘክ አይችልም በሚል አዋቂን ሥጋ እንዳይበላ መከልከል ነው፡፡
ማርክ ትዌይን
ይህች ዓለም የሌላ ፕላኔት ሲኦል ሳትሆን አትቀርም፡፡
አልዶስ ሁክስሌይ
ከመርህዎች በላይ ለጥቅሞቹ ዋጋ የሚሰጥ ህዝብ ሁለቱንም ያጣቸዋል፡፡
ዲዋይት ዲ. አይዘአንአወር
ህይወት አስደሳች ነው፡፡ ሞት ሰላማዊ ነው፡፡ አስቸጋሪው ሽግግሩ ነው፡፡
አይሳክ አሲሞቭ
እንቅልፍ ኦፔራን የማዳመጫ ግሩም መንገድ ነው፡፡
ጄምስ ስቲፈንስ
ሁሉም ነገር በቁጥጥር ሥር የዋለ ከመሰለ በፍጥነት እየተጓዝክ አይደለም፡፡
ማርዮ አንድሬቲ
ኮስታራ መስለህ ለመታየት ትችላለህ፤ ተጫዋች መስለህ መታየት ግን አትችልም፡፡
ሳቻ ጉይትሪ
የተሳሳተ ጥያቄ ስትጠይቅ ካገኙህ፣ ለመልሱ መጨነቅ አይኖርባቸውም፡፡
ቶማስ ፒንቾን
ፈር ቀዳጅን ጀርባው ላይ ባሉት ኢላማ መምቻ ቀስቶቹ ትለየዋለህ፡፡
ቢቨርሊ ሩቢክ
መደምደሚያ፤ ማሰብ የሚደክምህ ቦታ ነው።
ያልታወቀ ሰው
መፃህፍት በሚቃጠሉበት ቦታ፣ የሰው ልጆችም እጣፈንታ መቃጠል ይሆናል፡፡
ሄይንሪክ ኼይን
አደገኛ መሳሪያዎችን ከጅሎች እጅ በማራቅ እስማማለሁ፡፡ ለምን በመተየቢያ ማሽኖች አንጀምረውም፡፡
ፍራንክ ሊሎይድ ራይት

የተሳሳተና ጎጂ አስተሳሰብ መያዛቸው ነው ችግሩ

   ለግንቦቱ ምርጫ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ በተካሄደው ክርክር ላይ የተሳተፉ ሶስት ፓርቲዎች፣ ተመሳሳይ ሃሳቦችን እንዳቀረቡ የሚገልፅ ነበር የዛሬ ሁለት ሳምንት ፅሁፌ። ምን ያህል ተቀራራቢ እንደሆኑ ለማሳየትም፣ ከተከራካሪዎቹ አንደበት በምሳሌነት ጥቂት አባባሎችን ጠቅሻለሁ። ግን ለወቀሳ አልነበረም። እንዲያውም፣ የዋና ዋና ተፎካካሪ ፓርቲዎች  አስተሳሰብ ተቀራራቢ ካልሆነ፣ የምርጫ ፖለቲካ በአጭሩ ከመቀጨት አይድንም።
በእርግጥ፣ ፓርቲዎቹ የተለያየ የአስተሳሰብ አቅጣጫ እንደሚከተሉ ነው የሚናገሩት። ኢህአዴግን በመወከል የተከራከሩት አቶ አባይ ፀሐዬ፣ ፓርቲያቸው ‘አብዮታዊ ዲሞክራሲ’ ወይም ‘ልማታዊ ዲሞክራሲ’ የተሰኘ አስተሳሰብ እንደሚከተል ገልፀዋል - በከፊል የነፃ ገበያ አሰራርን ብንቀበልም መንግስት በኢኮኖሚ ውስጥ በሰፊው ጣልቃ መግባት አለበት በማለት። የመድረክ አመራር አባል ፕ/ር በየነ ጴጥሮስ በበኩላቸው፣ ትክክለኛው አማራጭ የ‘ሶሻል ዲሞክራሲ’ አስተሳሰብ መሆኑን በመጥቀስ፣ ከከፊል የነፃ ገበያ አሰራር ጋር መንግስት በኢኮኖሚ ውስጥ ጉልህ ሚና ሊኖረው ይገባል ብለዋል - መንግስት ከዜጎች ገቢ 50% ያህል ታክስ ሲሰበስብ የሚታይባቸውን አገራት በምሳሌነት በመጥቀስ። ለነፃ ገበያ ስርዓት የተሻለ ትኩረት የሚሰጥ ‘የሊበራል ዲሞክራሲ’ አስተሳሰብን እንከተላለን ያሉት የኢዴፓው ዶ/ር ጫኔ ከበደ በበኩላቸው፣ መንግስት በኢኮኖሚ ውስጥ በተመረጠ አኳሃን ጣልቃ መግባቱ ግን አስፈላጊ እንደሆነ ተናግረዋል።
የፓርቲዎቹን ክርክር የሚከታተል ሰው፣ የፓርቲዎቹን የዝንባሌ ልዩነት መታዘብ እንደሚችል አያጠራጥርም። ነገር ግን፤ ፓርቲዎቹ የካፒታሊዝምና የሶሻሊዝም ሃሳቦችን ያቀላቀለ ተመሳሳሳይ ቅይጥ አስተሳሰብ የያዙ መሆናቸው ሚስጥር አይደለም። በአንድ በኩል ስለ ነፃ ገበያ እየተናገሩ፣ በሌላ በኩል ደግሞ በሰዎች መካከል የሃብት ልዩነትን ለማጥበብ የመንግስት ጣልቃ ገብነት ያስፈልጋል በማለት ፓርቲዎቹ ይስማማሉ። በአንድ በኩል የንብረት ባለቤትነት መብትን እንደሚያከብሩ እየተናገሩ፤ በሌላ በኩል ደግሞ ሃብት ከሚያፈሩ አምራቾች ላይ ሃብት በመውሰድ ለሌሎች የማከፋፈል አሰራርን እንደሚደግፉ ሲገልፁ፣ “ፍትሃዊ የሃብት ክፍፍል” ወይም “ማህበራዊ ፍትህ” እያሉ ያሞግሱታል። የፓርቲዎቹ የአስተሳሰብ ተመሳሳይነት የዚህን ያህል በግልፅ የሚታይ ነው። ለነገሩ፤ እኔ ሳልሆን ፓርቲዎቹ ራሳቸው በአስተሳሰብ ተቀራራቢ መሆናቸውን በገሃድ ይመሰክራሉ። ፕ/ር በየነ ጴጥሮስ በፋና ሬድዮ በተካሄደ ሌላ ክርክር ላይ እንደገለፁት፣ የሶሻሊዝምና የካፒታሊዝም አስተሳሰቦችን ያዳቀለ ቅይጥ አስተሳሰብ ነው የያዙት። የተወሰነ የነፃ ገበያ አሰራርንና የመንግስት የኢኮኖሚ ገናናነትን ያቀላቀለ ቅይጥ ኢኮኖሚን ነው የሚፈልጉት።
የተዋጣላቸው ተከራካሪ የሆኑት የኢዴፓ መስራች አቶ ልደቱ አያሌው፣ ኢህአዴግ ከጊዜ ወደ ጊዜ አስተሳሰቡን እየቀየረ ወደ ኢዴፓ አስተሳሰብ እየተጠጋ መጥቷል፤ ጥሩ ነው ሲሉ ተናግረዋል - በፋና ሬድዮው ክርክር። የኢህአዴግ ተወካይ አቶ ዛዲቅ አብርሃ በበኩላቸው፣ ተቃዋሚዎች ናቸው አስተሳሰባቸው በመቀየር ወደ ኢህአዴግ አስተሳሰብ እየተቀራረቡ የመጡት ብለዋል። “ማን ተጠጋ?” የሚለውን ጉዳይ አከራካሪ ጥያቄ በማድረግ፣ የፓርቲዎቹን የሃሳብ ልዩነት ለማጉላት እንችል ይሆናል። ግን የዚህችው መከራከሪያ ጥያቄ መነሻ ነጥብ መዘንጋት የለብንም። በአስተሳሰብ ተቀራራቢ መሆናቸውን ፓርቲዎቹ ራሳቸው ያምናሉ። ዋናው ነጥብ ይሄው ነው። አቶ ልደቱ እንዳሉት፣ የፓርቲዎቹ አስተሳሰብ መቀራረቡ ጥሩ ነገር ነው። ለምን?
አንደኛ ነገር፣ ፓርቲዎች የሚፎካከሩበት የምርጫ ፓለቲካ በሰላምና በተረጋጋ ሁኔታ ለረዥም ጊዜ ሊዘልቅ የሚችለው፣ የተፎካካሪ ፓርቲዎች መሰረታዊ አስተሳሰብ ተቀራራቢ ከሆነ ብቻ ነው። አለበለዚያ፣ አስተሳሰባቸው በእጅጉ የተራራቀ ከሆነ፣ አንዱ በምርጫ ተሸንፎ ሌላው ስልጣን ላይ በወጣ ቁጥር በ“ስር ነቀል ለውጥ” አገር ይታመሳላ። ስልጣን ላይ በተፈራረቁ ቁጥር አገሪቱ በ‘አብዮት’ አዙሪት የምትመሳቀል ከሆነች፣ የምርጫ ፓለቲካ ከጊዜያዊ ፋሽንነት ያለፈ እድሜ አይኖረውም። በሌላ ምሳሌ ለማስረዳት ያህል፣ የምግብ አሰራር ውድድር፣ በተለያዩ የምግብ ጣዕሞችና አይነቶች መካከል መሆን አለበት እንጂ፣ ውድድሩ በምግብ እና በአይነ ምድር መካከል ከሆነ ከአንድ ሙከራ በላይ አይዘልቅም። በሌላ አነጋገር፣ ውድድሩ የኮካና የፔፕሲ መካከል ሳይሆን፤ በለስላሳ መጠጥና በመርዝ መካከል እንዲሆን የምንጠብቅ ከሆነ፣ የምንፈልገው ወይም የሚበጀን ነገር ያልገባን አላዋቂዎች ሆነናል ማለት ነው። ከዚሁ ነጥብ ሳንወጣ ሁለተኛውን ቁምነገር ማስተዋል እንችላለን።
የተረጋጋ ስልጡን የምርጫ ፓለቲካ ለዘለቄታው እውን እንዲሆን፣ ሰፊ ድጋፍ ያላቸው ተፎካካሪ ፓርቲዎች በመሰረታዊ አስተሳሰብ ተቀራራቢ ሊሆኑ ይገባል። ይሄ የመጀመሪያው ቁምነገር ነው። ግን፣ ተቀራራቢ መሆናቸው ብቻ በቂ አይደለም። ለምሳሌ፣ ከአርባ አመት በፊት በአገራችን የነበሩ ዋና ዋና ፓርቲዎች፣ ተመሳሳይ የአስተሳሰብ ቅኝትን የተከተሉ እንደነበር ይታወቃል - ኢህአፓ፣ መኢሶን ወዘተ..። እጅጉን ተቀራራቢ ከመሆናቸው የተነሳ፣ አንዱን ከሌላው ለመለየት ያስቸግራል - የለየላቸው ሶሻሊስቶች (ኮሙኒስቶች) በመሆናቸው። ግን፣ ስልጡን የፖለቲካ ምርጫ አልተፈጠረም። ለምን? አስቡታ! የአንድ ፓርቲ አምባገነንነት መስፈን አለበት የሚል ተመሳሳይ አስተሳሰብ የያዙ ፓርቲዎች፣ በጭራሽ በጭራሽ ብዙ ፓርቲዎች የሚፎካከሩበት የምርጫ ፓለቲካ ሊፈጥሩ አይችሉም። የሁሉንም ሰው እውቀትና ንግግር እየተቆጣጠረ የሚያፍን፣ የሁሉም ሰው ኑሮና ንብረት ላይ እያዘዘ የሚወርስ፣ የሁሉም ሰው ማንነትና ሰብእና ላይ አድራጊ ፈጣሪ ሆኖ የሚገዛ አምባገነን መፈጠር እንዳለበት ተስማምተው የለ! ‘እኔ አምባገነን ልሁን’፣ ‘እኔ ልሁን’ እያሉ ይጨፋጨፋሉ፣ ይጨፈጭፋሉ እንጂ፣ እንዴት ብለው የተረጋጋ ስልጡን የምርጫ ፖለቲካ ይፈጥራሉ? ሁለተኛው ቁምነገር ይሄው ነው። ፓርቲዎቹ በአስተሳሰብ መቀራረባቸው ብቻ ሳይሆን፣ ቅርርባቸው በስልጡን የነፃነት አስተሳሰብ ዙሪያ መሆን አለበት።
አሳዛኙ ነገር፤ የአገራችን ፓርቲዎች በስልጡን የነፃነት አስተሳሰብ ዙሪያ ሳይሆን በቅይጥ አስተሳሰብ ዙሪያ ነው የተቀራረቡት። ይበልጥ አሳዛኝና አሳሳቢ የሚሆነው፤ በአለም ዙሪያ የሚታየው አዝማሚያም ተመሳሳይ ነው - ደረጃው ቢለያይም ከሞላ ጎደል ሁሉም አገራት በ“ቅይጥ አስተሳሰብ” ውስጥ የሚተራመሱ ሆነዋል። ከኮሙኒስት ኩባ እና ከቻይና ጀምሮ፣ እስከ ደቡብ አፍሪካና ቬኒዝዌላ... ከሰሜን እስከ ደቡብ፣ ከኢትዮጵያ እስከ ራሺያና ህንድ፣ ከናይጄሪያ እስከ ፈረንሳይና ጃፓን፣ ከብራዚል እስከ ግሪክና ስፔን፣ ከግብፅ እስከ እንግሊዝና አሜሪካ... የቀረ አገር የለም ማለት ይቻላል። የኢኮኖሚ መስክን ብቻ ብንመለከት፣ በአንድ በኩል በነፃ ገበያ ስርዓት፣ አስገራሚ የቴክኖሎጂ ፈጠራዎችንና የምርታማነት እመርታዎችን፣ የየብልፅግና ለውጦችንና የኑሮ እድገትን እናያለን። በሌላ በኩል ደግሞ የነፃ ገበያ ስርዓትን በሚሸረሽር የመንግስት ጣልቃ ገብነት ሳቢያ፣ ቅጥያጣ ድጎማንና የታክስ ጫናን፣ የመንግስታት የእዳ ክምርንና የፋይናንስ ቀውስን፣ የሃብት ብክነትንና ሙስናን፣ ስራ አጥነትንና አመፅን እናመለከታለን። በአጭሩ፣ ከብልፅግና እድል ጋር፣ የጥፋት አፋፍ ላይ የደረሰ የኢኮኖሚ ቀውስ የእለት ተእለት ትዕይንት ሆኗል። የሁለት አገራትን ሙከራ ብቻ በጨረፍታ እንመልከት። በቅድሚያ ኩባን።
አብዛኛው የኩባ ሰራተኛ ወደ ሃያ ዶላር ገደማ የወር ደሞዝ እንደሚያገኝ የገለፀው የኒውስዊክ የትናንት እትም፣ የአንጋፋ ሃኪሞች ደሞዝ በቅርቡ ተሻሽሎ ወደ 70 ዶላር (ወደ 1500 ብር) ግድም የደረሰላቸው ቢሆንም የአብዛኞቹ ዶክተሮች ደሞዝ ግን 26 ዶላር (ወደ 600 ብር የሚጠጋ) እንደሆነ ዘግቧል።
የሃኪሞቹ ደሞዝ ከአብዛኛው ሰራተኛ ደሞዝ ያን ያህልም አይለያይም። ለምን? በፅዳት ሰራተኞችና በህክምና ዶክተሮች መካከል የገቢ ልዩነት እንዳይኖር ለማድረግ ነው - “ፍትሃዊ የሃብት ክፍፍል”፣ “ማህበራዊ ፍትህ” ይሉታል ሶሻሊስቶቹ። በአገራችን ፖለቲከኞች ዘንድ የሚዘወተሩ አባባሎች እንደሆኑም ታዝባችሁ ይሆናል። ያው፣ በሰዎች መካከል የቁመት ወይም የብልህነት ልዩነት እንዳይኖር፣ ረዣዥሞቹን መከርከም ወይም ብሩህ አእምሮዎችን ማደብዘዝ እንደማለት ነው። ይህንን ነው ፍትህ የሚሉት። የ50 ዓመቱ ኩባዊ ራፋኤል ግን፣ ለ“ማህበራዊ ፍትህ” የመስዋዕት በግ መሆን አንገሽግሿቸዋል። በወጣትነት እድሜያቸው በህክምና ተመርቀው መስራት የጀመሩ ጊዜ ምንኛ እንደተደሰቱ ባይረሱትም፣ ዛሬ ግን እንደ ሩቅ ዘመን ትዝታ ነው የያኔ ሙያቸውን የሚያስታውሱት። ስራቸውን ለቅቀው ከወጡ አምስት ስድስት አመታት ተቆጥረዋል። በእርግጥ አንዳንዴ፣ የህክምና ሙያቸውን ሲያስታውሱት፣ ከትዝታነትም አልፎ ያንገበግባቸዋል - ከሚወዱት ሙያ በመለየታቸው። ግን ሌላ አማራጭ አልነበራቸውም። በ12 ዶላር (250 ብር ገደማ) ደሞዝ የህክምና ሙያቸውን እንደጀመሩ የሚናገሩት ራፋኤል፣ ከበርካታ አመታት በኋላ ደሞዛቸው ወደ 15 ዶላር “እንዳደገ” ይገልፃሉ።
በእርግጥ ለአርባ አመታት ኩባን አንቀጥቅጠው የገዟት ፊደል ካስትሮ በእርጅናና በህመም ምክንያት ከስልጣናቸው ከተነሱ ወዲህ፤ ባለፉት ጥቂት ዓመታት ውስጥ አንዳንድ የለውጥ ጭላንጭሎች መታየት ጀምረዋል። የጀማሪ ዶክተሮች ደሞዝ እንኳ ወደ 600 ብር የሚጠጋ ሆኖላቸው የለ! ይሄ፣ በምድረ ኩባ “አጀብ” የሚያሰኝ ለውጥ ነው። ራፋኤል ግን፣ አሁንም ፈፅሞ አልተዋጠላቸውም። የለውጥ ጭላንጭል እየተፈጠረ መሆኑን አይክዱም። እንደ ድሮ ቢሆን ኖሮ፣ መንግስት ከመደበላቸው የስራ ቦታ መልቀቅ ባልቻሉ ነበር። ዛሬ ግን ይቻላል። ሁሉም ነገር በመንግስት ተይዞ በቆየበት አገር፣ ትንንሽ ሱቆችን መክፈት ተፈቅዷል። አንዳንድ ሃኪሞች፣ በሱቅ ንግድ መተዳደርን ቢመርጡ ምን ይገርማል?
ራፋኤል ግን፣ የታክሲ ሾፍርናን ነው የመረጡት። የግል ታክሲ ተፈቅዷላ። ቱሪስቶች በብዛት እንዲገቡ መፈቀዱ ደግሞ ጠቀማቸው። ዛሬ አቶ ራፋኤል በታክሲ ሹፍርና በወር ከ200 ዶላር በላይ ገቢ ያገኛሉ። ልጄ በህክምና ተመርቆ ሥራ ጀምሯል የሚሉት ራፋኤል፣ ነገር ግን ልጃቸው በህክምና ሙያው ከሚያገኘው ደሞዝ ይልቅ እሳቸው በታክሲ ሹፍርና የሚያገኙት ገቢ በአስር እጥፍ ገደማ እንደሚበልጥ ጠቁመዋል። ግን እሱም ሞኝ አይደለም። በእረፍት ቀናት አባቱን በመተካት የታክሲ ሹፍርና እንዲሰራ ሲጠይቁት አላቅማማም - ለሁለት ቀን ሰርቷል። “30 ዶላር ከፍየዋለሁ፤ በወር ከሚያገኘው ደሞዝ ይበልጣል” ብለዋል ራፋኤል። የቅይጥ ኢኮኖሚ ነገር እንዲህ ነው።
ያለ ጥርጥር የዛሬው ቅይጥ ኢኮኖሚ፣ ከትናንቱ “ያልተበረዘ የሶሻሊዝም ኢኮኖሚ” ይበልጣል። ግን አስቡት። የህክምና ዶክተር ከመሆን ይልቅ፤ የታክሲ ሾፌር መሆን ይሻላል - ገቢያቸው የትና የት! ነገር ግን የሃኪምና የሾፌር ገቢ መለያየቱና መራራቁ ወይም የታክሲ ሾፌር በወር 200 ዶላር ገቢ ማግኘቱ አይደለም ችግሩ። ከሃኪሞች ተቀንሶ አይደለም የሾፌሮች ገቢ የጨመረው። እንዲያውም፤ የታክሲ ስራን ጨምሮ በጥቂት መስኮች የግል ቢዝነስ በመፈቀዱ ምክንያት የተፈጠረው ለውጥ፣ እንደ ራፋኤል ለመሳሰሉ የታክሲ ሾፌሮች ብቻ ሳይሆን ለሃኪሞችም በተወሰነ ደረጃ ጠቅሟል። እናም፣ ብዙ ነው ባይባልም፣ የሃኪሞች ደሞዝ ትንሽ እንዲሻሻል ግፊት በማሳደር አስተዋፅኦ አበርክቷል። ምናልባት ወደፊት ደግሞ የግል ክሊኒክና ሆስፒታል ሲፈቀድ፣ የሃኪሞች ገቢ ሙያቸውንና ስራቸውን የሚመጥን የሚሆንበት እድል ይፈጠራል። በኩባ አሁን የታየችው የነፃ ገበያ ጠባብና ቁንፅል ጭላንጭል፣ የዚያችኑ ያህል ትንሽዬ የኑሮ ለውጥ እንደፈጠረችው ሁሉ፤ በጭላንጭሏ የገባው ብርሃን እየደመቀ የነፃ ገበያ ስርዓት እየሰፋና እየጨመረ ቢመጣ፤ የዚያኑን ያህል ከሶሻሊዝም የድንዛዜና የድህነት የሚላቀቁበት ሰፊ የእድገትና የብልፅግና እድል ይፈጠራል። አለበለዚያ ግን፤ “መማር ከንቱ” የሚያስብል፣ በጅምር የቅይጥ ኢኮኖሚ ሳቢያ የሚፈጠር ቀውስ ውስጥ ተዘፍቃ፣ የብልፅግና ጭላንጭሏ በአጭሩ ተቀጭቶ የኋሊት ትንሸራተታለች።
በሌላ አነጋገር፣ ቅይጥ ኢኮኖሚ፣ ወደ በለጠ የነፃ ገበያ ስርዓት የሚያመራ ጊዜያዊ የመሸጋገሪያ ክስተት ከመሆን አልፎ፤ ቋሚ ስርዓት እንዲሆን መመኘት ውሎ አድሮ የኢኮኖሚ ቀውስን ከመጋበዝ የተለየ ትርጉም አይኖረውም። በአሜሪካና በምዕራብ አውሮፓ፣ ከዚያም በእነ ታይዋንና ደቡብ ኮሪያ፣ ባለፉት 20 ዓመታት ደግሞ ፖላንድና ቼክ በመሳሰሉ የምስራቅ አውሮፓ አገራት እንደታየው፤ የነፃ ገበያ ስርዓትን ተግባራዊ ባደረጉት መጠን ነው ብልፅግና እውን የሚሆነው።
ቻይናም ከረሃብ ለመላቀቅና ወደ ብልፅግና ጎዳና የመግባት እድል ያገኘችው፤ በሌላ ምክንያት አይደለም። ከጊዜ ወደ ጊዜ የመንግስት ቁጥጥርን እየቀነሰች፣ ከጊዜ ወደ ጊዜ የነፃ ገበያ አሰራርን ስታስፋፋ ስለቆየች ነው፤ ለ30 አመታት ያለማቋረጥ ከአስር በመቶ በላይ የኢኮኖሚ እድገት ስታስመዘግብ የቆየችው። በእርግጥ ባለፉት አራት አመታት የኢኮኖሚ እድገቱ ረገብ ብሏል፤ ወደ 7.5% ገደማ። ዘንድሮና በሚቀጥለው አመት የኢኮኖሚ እድገቱ ወደ 7 በመቶ እንደሚወርድ የገለፀው የቻይና መንግስት፤ የመቀዛቀዝ አዝማሚያው እንዳይባባስ ስጋት ቢያድርበት አይገርምም። የኢኮኖሚ እድገት ካላስመዘገበ፣ ስልጣን ላይ የመቆየት አቅሙ እንደሚሸረሸር አልጠፋውም። እና ምን ተሻለ?
የቻይና መንግስት ለበርካታ አመታት የነፃ ገበያ አሰራርን እያስፋፋ ቢመጣም፤ አሁንም ኢኮኖሚው ውስጥ የመንግስት ቁጥጥርና ድርሻ ግዙፍ ነው። ማለትም፤ ቅይጥ ኢኮኖሚ። ይህንኑ በቋሚነት ለመያዝ፤ “እስከ ዛሬ ድረስ በተወሰነ ደረጃ ተግባራዊ ያደረግሁት የነፃ ገበያ አሰራር በቂ ነው” ብሎ አሁን ባለው የቅይጥ ኢኮኖሚ ስርዓት መቀጠል እንደማይችል የአገሪቱ ባለስልጣናት ገብቷቸዋል። ለዚህም ይመስላል፣ የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ባለፈው ሳምንት በሰጡት ረዥም ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ፣ እስካሁን እንዳደረግነው የነፃ ገበያ አሰራርን በማስፋፋት እንቀጥላለን ያሉት። ለቢዝነስ ድርጅቶች የታክስ ቅነሳ እንደሚደረግ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጠቅሰው፤ የቢዝነስ ድርጅት የሚያቋቁሙ ሰዎች ላይ የተንዛዛ የቁጥጥርና የምዝገባ ቢሮክራሲ በግማሽ ቀንሰነዋል፤ አሁንም እንደገና በግማሽ እንቀንሰዋለን ብለዋል። ይበጃቸዋል! በቅይጥ አስተሳሰብ ተተብትቦ፣ ቅይጥ ኢኮኖሚን እንደ ቋሚ ስርዓት ይዞ ለመቀጠል መሞከር፣ መጨረሻው አያምርማ። የአገራችን ፓርቲዎችም፣ በጊዜ ይህንን እውነታ ቢገነዘቡ ይሻላቸዋል፤ ለሌሎቻችንም ይሻለናል።

ከዕለታት አንድ ቀን አንዲት ቆቅ ሰባት ልጆቿን ይዛ ከቤት ወጥታ መንገድ ትጀምራለች፡፡
1ኛዋ ጫጩት - እማዬ ወዴት ነው የምንሄደው?
እናት - ቆቅ - ወደሩቅ አገር
2ኛዋ ጫጩት - እዚያ አገር ምን አለ?
እናት ቆቅ - የተሻለ ኑሮ
3ኛዋ ጫጩት - የተሻለ ኑሮ ምንድን ነው?
እናት ቆቅ - የተሻለ ምግብ፣ የተሻለ መጠለያ፣ የተሻለ ወጥቶ - መግባት
4ኛዋ ጫጩት - በመሬትም በአየርም እንደልባችን የመብረር መብት አለን?
እናት ቆቅ - አዎ፡፡ እንደልብ መሮጥ፣ እንደ ልብ መናገር፣ እንደልብ ሀሳባችሁን የመግለጥ፣ የምትወዱን መውደድ፣ የምትጠሉትን መጥላት ትችላላችሁ፡፡
5ኛዋ ጫጩት - የፈለግነው ከተማ ሄደን መኖርስ እንችላለን?
እናት ቆቅ - በደንብ ትችላላችሁ፡፡
6ኛዋ ጫጩት - ትንሽ ትልቅ፣ ቆንጆ አስቀያሚ፣ የተማረ፣ ያልተማረ፣ የዚህ ወፍ ዝርያ የዚያ ወፍ ዝርያ ብለው፤ አንዱን ጠቅመው ሌላውን ጎድተው አያዳሉብንም?
እናት ቆቅ - እንደሱ ቀርቷል፡፡ ጅግራም ሆናችሁ ቆቅ፣ ቁራም ሆናችሁ አሞራ፣ ወፍም ሆናችሁ ወማይ፣ ሣቢሳም ሆናችሁ ጥምብ አንሳ እንደየ ዝርያችሁ የመኖር መብት አላችሁ፡፡ በዝርያችሁ የሚነካችሁ ምንም የለም፡፡
7ኛዋ ጫጩት - እነዚህ የዘረዘርሺልን እርስ በርስ ቢጣሉስ ማን ያስታርቃቸዋል?
እናት ቆቅ - የሁሉም የበላይ የሆነ የአዕዋፍ ንጉሥማ ይኖራል፡፡ ያለንጉሥ መኖርማ አይቻልም፡፡
ይህን እየተጨዋወቱ መንገድ እያቆራረጡ ሄደው ዋናው አውራ ጎዳና ጋ ደረሱ፡፡ አውራ ጎዳናውን ከጠርዝ ጠርዝ በወርዱ አንድ ዘንዶ ተጋድሞበታል፡፡ እናት ቆቅ ዘላ ለመሄድ አልደፈረችም፡፡ ስለዚህ የተኛውን ዘንዶ ቀስቅሳ “ለምን ተኛህ?” ልትለው ፈለገች፡፡ አንገቱን በኩምቢዋ ነካ ነካ አደረገችና፤
“አያ ዘንዶ ምነው በደህና ነው የተኛኸው?” አለችው፡፡ ዘንዶው ለምን እንደተኛ አስቦ አስቦ፤
“ርቦኝ ነው የተኛሁት” አላት፡፡
“እንግዲያው ልጆቼን ልስጥህና ጥገብ፡፡ እኔን ተወኝ” አለችው፡፡
ልጆቿን ዋጠ፡፡ እሷ ተሻግራው ሄደች፡፡
ዘንዶው ጫጩቶቿን በልቶ አላበቃም፡፡ ሀሳብ ያዘው፡፡ “ይቺ ቆቅ እንዴት አምና ልጆቿን ብላ አለችኝ፡፡ ነገር ቢኖራት ነው” አለ፡፡ ቢያስበው ቢያስበው ለተንኮል ነው ብሎ ያሰበው ነገር አልመጣ አለው፡፡ በመጨረሻ፤
“እኔ ምን አሳሰበኝ? እራሷን ብበላት እገላገል የለም እንዴ?” አለና ሲምዘገዘግ ወደ ቆቋ ሄደ፡ ያዛትና “ዓላማሽ ምን እንደሆነ ስላልገባኝ መፍትሔው ራስሽን መዋጥ ነው” ብሎ፤ በልቷት ተገላገለ!
*       *      *
ከማይጠግብ ዘንዶ ይሰውረን፡፡ ልጅም ሰውቶ ራስን ከማጣት ያድነን፡፡ በተጓዝን ቁጥር የተኛ ዘንዶ ከማግኘት፣ እሱን ሳይቸግረን ቀስቅሰን ከመዋጥ የሚጠብቀንን ይዘዝልን፡፡ የማይፈራውን ፈርተን፣ የተኛውን ቀስቅሰን፣ ትውልዳችንን ገብረን፣ የተደሰትን መስሎን ዘራፍ ከማለት ግብዝነት ይሰውረን፡፡
ወደድንም ጠላንም ዘንዶው ዘንዶ ነው! መንገዱን የዘጋው በራሱ ተማምኖ ነው፡፡ ዓመታት መቁጠርና ዘንዶውን “ምስህ ምንድን ነው?” ብለን እንደ ቅድመ ታሪክ ዘንዶ መገበር ሳይሆን መብሰል፣ ራስን ማወቅ፣ ራስን መቻል፣ በራሴ መተዳደር እችላለሁ ማለት ያሻል፡፡
የሀገር ጉዳይ፤ “ያለቀበት” የሚባል የጉልበት ገበያና “ሁሉንም በአምሥት …” የሚባል ዓይነት ንግድ መሆን የለበትም፡፡ ትግልም፣ ልማትም፣ ዲሞክራሲም የሂደት ጉዳይ ነው፡፡ ቁርጥም ነገር፣ ቆረጣም ነገር የለበትም፡፡ እየተወራረደ፣ እየተሞራረደ የሚጠራ፣ የሚሻሻል፣ የሚለወጥ ሂደት ነው!! ዘመን መቁጠር “አዲስ ፍሬ ምን ያህል አፈራሁ?” የማለት የጠራ ዕድገት ከሌለበት እንደው “ዕድሜዬ ይሄን ያህል ነው ከማለት አያልፍም!”
የየራሳችንን የውስጥ ችግር ሳንፈታ ዕድሜዬ ይሄን ያህል ነው ብለን መፎከር የባሰ ምስቅልቅል ችግር ውስጥ መዘፈቅ ነው፡፡ ለአቅመ አዳም ከደረሰ በኋላ ቤተሰቦቹ ጋ የሚኖር ልጅ ከተጧሪ አንድ ነው!
“ፍሬ በስሎ የሚበላው
ወይ በራሱ ጊዜ ሲወድቅ፣ ወይ እኛ ስንለቅመው ነው”
እንደሚባል የገባው ዕውነተኛ ብስለት ያለው ነው፡፡ የውስጥ ደም መፍሰስ (Internal Bleeding) ከአዲስ ደም መቀበል (New Blood Injection) ጋር አይገናኝምና መጀመሪያ የአንጎል ውስጥ ደም ፍሰቱን መገላገል ዋና ነገር መሆኑን ማስተዋል ነው!
“እናቴን ያገባ ሁሉም አባቴ ነው!” ዓይነት አስተሳሰብ የትም አያደርሰንም፡፡ ጊዜን ባግባቡ መለካት ነው የፖለቲካ ቁም ነገር!
ቅዱስ አውግስቶስ ኑዛዜ (Confession) በተባለ ግጥሙ፤
ምንም ነገ ባያልፍ፤ ትላንትና የለም
ምንም ድርጊት ባይኖር፣ ነገ አይፈጠርም
ዛሬም ነገር ባይኖር፣ መኖርን አናቅም
ያለፈው፣ የመጪው፣ የአሁን ውዝዋዜ
ጊዜ ማለት ያ ነው፣ ያ ነው ለእኔ ጊዜ!
በዓላትን ስናከብር የሠራነውን ፍሬ - ነገር እናስተውል፡፡ ፈንጠዝያን ከብስለት እንለይ! አለበለዚያ፤ “ሞኝ ሁለቴ ይነደፋል፡፡ አንዴ እባብ ሲነድፈው፣ አንዴ እባቡን ሲያሳይ” የሚባለው ተረት ሰለባ እንሆናለን! የኋሊት ወደ ታሪክ ሳይሆን ወደፊት፣ ታሪክ ወደ መስራት እንጓዝ!!

      በኤርትራ የወርቅ ማምረቻና ወታደራዊ ካምፕ ላይ የኢትዮጵያ አየር ሃይል ጥቃት መፈፀሙን የተለያዩ ድረገፆችና ሚዲያዎች ቢዘግቡም የኤርትራው ፕሬዚዳንት ቃል አቀባይ ጥቃቱ አልተፈፀመም ሲሉ ማስተባበላቸውን “ጊስካ አፍሪካ ኦንላይን” ጠቁሟል፡፡
“ቢሻ የወርቅ ማዕድን ማምረቻም ሆነ ወታደራዊ ካምፑ በኢትዮጵያ አየር ሃይል አልተደበደበም” ብለዋል ቃል አቀባዩ ለድረ ገፁ በሰጡት መረጃ፡፡
የሱዳኑ ጋዜጣ “ሳሀፋ” ሰሞኑን ባሰራጨው ዘገባ፤ የኢትዮጵያ አየር ሃይል ከአስመራ በ150 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የሚገኘውንና የካናዳ ኩባንያ የሆነውን ቢሻ የወርቅ ማእድን ማምረቻ መደብደቡን ሲገልፅ፣ “አሰና” የተሰኘ ድረ ገፅ በበኩሉ፤ ቢሻ የወርቅ ማእድን ማምረቻና ማይ እዳጋ በተባለ ቦታ የሚገኝ ወታደራዊ ካምፕ በኢትዮጵያ አየር ሃይል ወታደራዊ ጥቃት እንደተፈፀመባቸው ዘግቧል፡፡
ኢትዮጵያ በኤርትራ ላይ  ወታደራዊ ጥቃት ፈፅማለች ወይ በሚል ከአዲስ አድማስ የተጠየቁት የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ፅህፈት ቤት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ሽመልስ ከማል በሰጡት ምላሽ፤ “ተጎዳን የሚል ይፋ አቤቱታ ሳይቀርብ እንዳልጎዳችኋቸው ማረጋገጫ ስጡ ማለት አግባብነት የለውም” ብለዋል፡፡”  
የቢሻ ወርቅ ማምረቻ አብላጫ ድርሻውን የያዘው “ኔቭሱን” የተባለው የካናዳ ኩባንያ ሰሞኑን በድረገፁ ባሰፈረው መረጃ፤ የወርቅ ማዕድን ማምረቻው በተፈፀመበት ዝርፊያና በዕድሳት ምክንያት  ለተወሰነ ጊዜ ሥራ አቁሞ እንደነበር ጠቁሞ በቅርቡ ወደ ስራው እንደሚመለስና ዝርፊያውን በተመለከተ የኤርትራ የፀጥታ ሃይሎች ምርመራ እያካሄዱ እንደሆነ አስታውቋል፡፡

የአሜሪካ መንግስት ኢትዮጵያ፣ ግብጽና ሱዳን በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ዙሪያ ያለባቸውን አለመግባባት ለመፍታትና ፍትሃዊ የውሃ ክፍፍል እንዲረጋገጥ ለማድረግ ባለፈው ሰኞ የፈረሙትን የትብብር ስምምነት እንደሚያደንቅ ማስታወቁን ኢጂብት ኢንዲፔንደንት ዘገበ፡፡
የአሜሪካ መንግስት የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ጄን ፓስኪ ባለፈው ረቡዕ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፣ አሜሪካ ሶስቱ አገራት በአባይ ወንዝ የውሃ ድርሻ ላይ የሚያነሱትን ጥያቄ በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት ያስችላል የተባለውን ስምምነት፣ አገራቱ በጉዳዩ ዙሪያ አንድ እርምጃ መራመዳቸውን የሚያሳይ ጠቃሚ ሁነት በመሆኑ ታደንቀዋለች ብለዋል፡፡
መንግስታቸው በአገራቱ መካከል የትብብር መንፈስ እንዲፈጠር ለማድረግና የሁሉንም አገራት ጥቅም ባስጠበቀ መልኩ አባይን በዘላቂነት ለማልማት ከኢትዮጵያ፣ ከግብጽና ከሱዳን ጋር በትብብር እንደሚሰራም አስታውቀዋል፡፡
ሶስቱ አገራት የአባይን ውሃ በፍትሃዊነት መጠቀም የመቻላቸው ጉዳይ፣ በአገራቱ መካከል ዋነኛ የውጥረት መንስኤ ሆኖ መቆየቱን የጠቆመው ዘገባው፣ የተፈረመው ስምምነት በሁሉም አገራት የውሃ ደህንነት ላይ ጉዳት እንዳይከሰት የሚያደርግ መሆኑንና ግብጽና ሱዳን ለታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ይፋዊ እውቅና መስጠታቸው የታየበት ነው መባሉን አመልክቷል፡፡
በሌላ በኩል በአዲስ አባባ ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካል ሳይንስ መምህር የሆኑት አቶ ዳር እስከዳር ታዬም፤ የግብጹ ፕሬዚዳንት ወደ ድርድር መምጣታቸውና የግድቡን መገንባት አለመቃወማቸው ከዚህ በፊት አገራቸው ስታራምደው ከነበረው አቋም የተለየና አንድ እርምጃ ወደፊት የተራመደ ነው ብለዋል፡፡ የትብብር መንፈሱ ጠቃሚነት እንዳለው የጠቆሙት ምሁሩ፣ የትብብሩ መንፈስ እውነት መሆንና አለመሆን ግን በስምምነቱ አፈጻጸም ላይ የሚታይ ይሆናል ብለዋል፡፡
የቀድሞው የኢዴፓ ሊቀመንበር አቶ ልደቱ አያሌው በበኩላቸው፤የግብጹ ፕሬዚዳንት የአባይን ውሃ ከፈጣሪ እንደተበረከተ የግል ስጦታ ከማየት አስተሳሰብ ተላቀው፣ ውሃው የሌሎች አገራትም ሃብት እንደሆነ እውቅና መስጠታቸውን አድንቀው፣ስምምነቱን መፈረማቸው ብስለታቸውን ያሳያል ብለዋል፡፡ “ትብብሩ የሁለቱንም አገራት ህዝቦች በሚጠቅም መልኩ እንዲቀጥል ማድረግ ይገባል፤ የአልሲሲ ጅምር መልካም ቢሆንም ውጤቱ በሂደት የሚታይ ይሆናል” ሲሉ አቶ ልደቱ አስተያየታቸውን ገልጸዋል፡፡

ለአካል ብቃት እንቅስቃሴ የሚያግዙ የጅምናዚየም መሳሪያዎችን እያመረተ በአለማቀፍ ደረጃ በማቅረብ የሚታወቀው ላይፍ ፊትነስ ኩባንያ፣ “ላይፍ ፊትነስ ሮው ጂ ኤክስ” የተባለ ለአጠቃቀም ምቹ የሆነ አዲስ የአካላዊ እንቅስቃሴ መሳሪያ ለገበያ ማቅረቡን በተለይ ለአዲስ አድማስ ገለጸ፡፡
ኩባንያው ለዝግጅት ክፍላችን በላከው መግለጫ እንዳለው፣ ዘመኑ በደረሰበት የአካል ብቃት እንቅስቃሴ መሳሪያዎች ቴክኖሎጂና የጥራት ደረጃ የተመረተው ላይፍ ፊትነስ ሮው ጂ ኤክስ፣ የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ለሚያደርጉ ተጠቃሚዎች ምቹና ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታዎች ያሉት መሳሪያ ነው፡፡
በተለያዩ የአካል ብቃት ደረጃዎች ላይ የሚገኙ ተጠቃሚዎች ከአቅማቸው ጋር በሚመጣጠን መልኩ ተስማሚ አድርገው እንዲገለገሉበት በሚያስችል ሁኔታ እንደተሰራና የተጠቃሚዎችን ሁሉንም የሰውነት ክፍሎች በስፖርታዊ እንቅስቃሴ እንዲዳብሩ የሚያደርግ ነው ተብሏል፡፡
መሳሪያው በግልና በቡድን ለሚደረጉ የአካል ብቃት እንቅስቃሴዎች አገልግሎት መስጠት በሚችልበትና ቦታ በማይፈጅ መልኩ ዲዛይን እንደተደረገም የጂምናዚየም መሳሪያዎችን በአለም ዙሪያ ለሚገኙ ከ120 በላይ አገራት በማቅረብ የሚታወቀው ኩባንያው በላከው መግለጫ አስታውቋል፡፡

  • ረዳት ሊቀ ጳጳሱ የፓትርያርኩን ምደባዎች በደብዳቤ ተቃውመዋል
  •   ቋሚ ሲኖዶሱ፤ጠቅ/ሥራ አስኪያጁ ያቀረቡትን አቤቱታ መመልከት ጀምሯል

    ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ ለአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት አዲስ ዋና ሥራ አስኪያጅ እና ምክትል ሥራ ስኪያጅ መሾማቸውን ተከትሎ ከሀገረ ስብከቱ ረዳት ሊቀ ጳጳስ እና ከጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ተቃውሞ እንደገጠማቸው ተገለጸ፡፡ኹለቱ ሥራ አስኪያጆች ለሀገረ ስብከቱ መመደባቸው የተገለጸው፣ ከትላንት በስቲያ ኀሙስ ከፓትርያርኩ ልዩ ጽ/ቤት ለጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ በደብዳቤ በተሰጠ መመሪያ ነው፡፡የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የፓትርያርኩ ልዩ ሀገረ ስብከት እንደኾነና ከረዳት ሊቀ ጳጳሱ ጀምሮ በሀገረ ስብከቱ የሚመደቡ ሓላፊዎችን የመምረጥና የመመደብ ጉዳይ ከብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ ጋራ መያያዙን፣ በዚኽም መሠረት ሲሠራ እንደቆየ በመመሪያው የተጠቀሰ ሲኾን፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ ለኹለቱ ሥዩማን ሥራ አስኪያጆች ምደባቸውን የሚገልጽ ደብዳቤ እንዲያደርሷቸውና ሥራቸውን እንዲጀምሩ ይደረግ ዘንድ ይጠይቃል፡፡ ለጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ በአድራሻ የተጻፈው ይኸው ደብዳቤ፣ በሀገረ ስብከቱ የፓትርያርኩ ረዳት ሊቀ ጳጳስ ለኾኑት ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ በግልባጭ እንዲያውቁት መደረጉ ተገልጧል፡፡ ረዳት ሊቀ ጳጳሱ የሥራ አስኪያጆቹ ሹመት ከሕገ ቤተ ክርስቲያን፣ ከቃለ ዐዋዲው እና ከሀገሪቱ የሕግ አሠራር ውጭ መኾኑን በመግለጽ ምደባውን በትላንትናው ዕለት ለፓትርያርኩ በጻፉት ደብዳቤ የተቃወሙ ሲኾን፣ ፓትርያርኩ ከሕግ አግባብ ውጭ የሰጡትን መመሪያ እንደገና እንዲያጤኑት መጠየቃቸውም ታውቋል፡፡በሕገ ቤተ ክርስቲያኑ መሠረት፣ የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ እና ምክትል ሥራ አስኪያጅ ተጠሪነታቸው ለረዳት ሊቀ ጳጳሱ እንጂ ለፓትርያርኩ ኾኖ እንደማያውቅና ሊኾንም እንደማይችል የገለጹት አቡነ ቀሌምንጦስ፣ የፓትርያርኩ አካሔድና የሥራ አስኪያጆች ምርጫ ‹‹የሕግ ድጋፍ የሌለው፣ ያልተለመደና የቤተ ክርስቲያኒቱን መዋቅራዊ አሠራር በእጅጉ የሚፃረር ነው፤›› ብለዋል፡፡ አቡነ ማትያስ የሰጡት መመሪያ ተቀባይነት የሚኖረውም ተሿሚዎቹ በሀገረ ስብከቱ ረዳት ሊቀ ጳጳስ ተመርጠው ከቀረቡ በኋላ ምርጫቸው ከጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ ጋር የጋራ ስምምነት ተደርሶበት በፓትርያርኩ ሲሾሙ እንደኾነ በተቃውሟቸው አስረድተዋል፡፡ ፓትርያርኩ ከልዩ ጽ/ቤታቸው በሰጡት መመሪያና በሥራ አስኪያጆች ምርጫዎቻቸው እንደማይስማሙና ምደባውንም ለማስተናገድ እንደሚቸገሩ ያስታወቁት ረዳት ሊቀ ጳጳሱ፣ ‹‹ይህ አሠራር ከትዝብት ላይ የሚጥል መኾኑን ተረድተውልን ለቤተ ክርስቲያን ሰላማዊ አሠራርና ለኹላችንም ሰላም ሲባል ውሳኔዎን እንደገና እንዲያጤኑ በታላቅ አክብሮት አሳስባለኹ›› ብለዋል - በተቃውሞ ደብዳቤአቸው፡፡
የፓትርያርኩን መመሪያ እንዲያስፈጽሙ በአቡነ ማትያስ መመሪያ የተሰጣቸው የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቡነ ማቴዎስ በበኩላቸው፣ ትላንት ከቀትር በፊት በተደረገው የቋሚ ሲኖዶሱ ሳምንታዊ ስብሰባ መመሪያውን በመቃወም አስተያየታቸውን በቃል ማቅረባቸው ተጠቁሟል፡፡ ስብሰባውን በሊቀ መንበርነት የሚመሩት ፓትርያርኩም አጀንዳው ውሳኔአቸውን የሰጡበት በመኾኑ መታየት የለበትም በሚል ቢቃወሙም ቋሚ ሲኖዶሱ ዋና ሥራ አስኪያጁ ተቃውሟቸውን በጽሑፍ እንዲያቀርቡ ማዘዙ ተገልጧል፡፡ ከትላንት በስቲያ በድንገት ይፋ የኾነው የሀገረ ስብከቱ ተተኪ ሥራ አስኪያጆች ምደባ፥ ‹‹የመልካም አስተዳደር ሒደቱን ማቀላጠፍ›› በሚል ከኹሉ አቀፍ የትምህርት ዝግጅት፣ ከሥነ ምግባርና ከብሔር ተዋፅኦ መስፈርቶች አንጻር ፓትርያርኩንና ረዳት ሊቀ ጳጳሳቸውን ላለፉት ሦስት ወራት ሲያወዛግብ መክረሙን የዜናው ምንጮች ተናግረዋል፡፡