Administrator

Administrator

“ ሲአይኤና ሞሳድ አይሲስ እና ቦኮ ሃራምን ይደግፋሉ” አልበሽር
“ አይሲስን ለመዋጋት የጦር መሳሪያ ማዕቀብ ይነሳልኝ” ሊቢያ

ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ፤ አይሲስ የተባለውን እስላማዊ ቡድን ጨምሮ ሌሎች ጽንፈኛ ቡድኖች በተለያዩ አገራት የሚፈጽሙትን የሽብር ተግባር ለመግታት የአለም አገራት ተባብረው እንዲሰሩ ጥሪ አቀረቡ፡፡
ኒውዮርክ ታይምስ እንደዘገበው፤ የ60 አገራት ተወካዮች በተገኙበትና በዋሽንግተን በተካሄደው በጽንፈኝነት ላይ ያተኮረ ስብሰባ ላይ ባለፈው ረቡዕ ንግግር ያደረጉት ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ፣ የአለም አገራት መንግስታት የእስላማዊ መንግስት መርህን አንግበው የሚንቀሳቀሱ ጽንፈኛ ቡድኖችን በተባበረ ክንድ መመከት ይገባቸዋል ብለዋል፡፡
የሱኒ ታጣቂ ቡድኖችን አስተሳሰብ ማዳከምና እንቅስቃሴያቸውን መግታት የትውልድ ፈተና ሆኖ ቆይቷል ያሉት ኦባማ፤ ቡድኖቹን በስኬታማ መንገድ ከእንቅስቃሴያቸው መግታት የሚቻለው በእስልምና እምነት ተከታዮች፣ በመንግስታት፣ በሃይማኖት መሪዎች፣ በማህበረሰቦችና በመሳሰሉት የተቀናጀ ርብርብ ብቻ ነው ብለዋል፡፡
ኦባማ አሜሪካ ጦርነት ውስጥ የገባችው ከእስልምና ጋር ሳይሆን የእስልምናን አስተምህሮት ከሚያዛቡ የጥፋት ሃይሎች ጋር ነው ማለታቸውን የዘገበው ሮይተርስ፤ እስላማዊ ታጣቂ ቡድኖች ምዕራባውያን በእስልምና ላይ ጦርነት አውጀዋል በማለት የሚያቀርቡትን ውንጀላ መሰረተ ቢስ ነው ሲሉ ማጣጣላቸውን ጠቁሟል፡፡ አሜሪካም እና ሌሎች ምዕራባውያን አገራት እስልምናን ለመጨቆንና በእምነቱ ላይ ጥላቻ እንዲስፋፋ ለማድረግ ይሰራሉ በሚል ከአንዳንድ አክራሪ ቡድኖች የሚሰነዘረውን ውንጀላ መሰረተ ቢስነት ለማረጋገጥ የእስልምና መሪዎች ጠንክረው መስራት ይገባቸዋል ብለዋል ኦባማ፡፡
አለማችን ከእስልምና አስተምህሮት ጋር ጸብ የላትም፣ አይሲስ እና አልቃይዳን የመሳሰሉ ቡድኖች ግን የሃይማኖት መሪዎች ሳይሆኑ በሃይማኖት ሽፋን ጥፋት የሚፈጽሙ  ሽብርተኞች ስለሆኑ እንታገላቸዋለን ማለታቸውንም ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በጠራው አስቸኳይ ስብሰባ ላይ የተሳተፈችው ሊቢያ በበኩሏ፤ አይሲስን እና ሌሎች ጽንፈኛ ታጣቂ ቡድኖችን በአግባቡ ለመመከት እንድትችል፣ የተመድ የጸጥታ ምክር ቤት የጣለባትን የጦር መሳሪያ ግዢ ማዕቀብ እንዲያነሳላት ጠይቃለች፡፡ ማዕቀቡ ከአራት አመታት በፊት እንደተጣለባት ያስታወሱት የሊቢያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሞሃመድ አል ዳሪ፤ በአገሪቱ ያለው የጸጥታ ሁኔታ አሳሳቢ ደረጃ ላይ መድረሱን ጠቅሰው  የአገሪቱ ታጣቂ ቡድኖች ከአይሲስ ጋር ተባብረው የባሰ ጥፋት ሊፈጽሙ እንደሚችሉ ስጋታቸውን ገልጸዋል፡፡ ለዚህም በቂ የጦር መሳሪያ መያዟ ወሳኝ እንደሆነ ጠቁመዋል፡፡
በቅርቡ  21 ዜጎቿ በአይሲስ ታጣቂዎች ተቀልተው የተገደሉባትና በቡድኑ ላይ የአየር  ላይ የአጸፋ ምላሽ የሰነዘረችው ግብጽ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሳሜህ ሽኩርም፣ በሊቢያ ያለው የጽንፈኛ ቡድኖች እንቅስቃሴ ከፍተኛ ችግር የሚፈጥር በመሆኑ፣ በአገሪቱ ላይ የተጣለው የጦር መሳሪያ ግዢ ማዕቀብ መነሳቱ ጠቃሚ እንደሆነ ጠቁመው  ሃሳቡን እንደሚደግፉት ገልጸዋል፡፡
የሱዳኑ ፕሬዚዳንት ኦማር ሃሰን አልበሽር በበኩላቸው፤ የአሜሪካና የእስራኤል የስለላ ተቋማት ሲአይኤና ሞሳድ ለአሸባሪዎቹ እስላማዊ ቡድኖች አይሲስ እና ቦኮ ሃራም በስውር ድጋፍ ይሰጣሉ ሲሉ መወንጀላቸውን  ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
አይሲስ ከቀናት በፊት በሊቢያ የኮፕቲክ ክርስቲያን አማኝ የሆኑ 21 ግብጻያውንን በመቅላት መግደሉን ተከትሎ ፕሬዚዳንቱ ከዩሮኒውስ ጋር ባደረጉት ቃለመጠይቅ እንዳሉት፣ ይህን መሰሉን የጭካኔ ተግባር የሚፈጽም የእስልምና እምነት ተከታይ የለም፣ ይልቁንም ለዚህ ቡድን የጭካኔ ተግባር ድጋፍ የሚያደርጉት  ሁለቱ የስለላ ተቋማት ናቸው ብለዋል፡፡
መሰል የአሸባሪ ቡድኖችን ለመደምሰስ ሲባል የሚፈጸም ሃይል የተሞላበት እርምጃም ቡድኖቹ የከፋ የአጸፋ ምላሽ እንዲሰጡ የሚገፋፋ ሊሆን ይችላል ሲሉም አልበሽር አስጠንቅቀዋል፡፡ የሊባኖሱ ሂዝቦላህ መሪም ሲአይኤ እና ሞሳድ ከጽንፈኞቹ ቡድኖች በስተጀርባ ድጋፍ ያደርጋሉ ሲሉ መወንጀላቸውን አሶሼትድ ፕሬስ መዘገቡ ተጠቁሟል፡፡
የቱርኳ አንካራ ከተማ ከንቲባ ሜሊህ ጎኬክ በበኩላቸው፤ ሞሳድ በፓሪሱ የቻርሌ ሄቢዶ ጥቃት ውስጥ ተሳትፎ ነበረው ሲሉ መናገራቸውን ባለፈው ጥር ወር ለንባብ የበቃው ፋይናንሽያል ታይምስ ማስነበቡንም ዘገባው አስታውሷል፡፡ ከንቲባው በወቅቱ እንዳሉት፤ እስራኤል በእስልምና ሃይማኖት ላይ ጥላቻ እንዲነግስ በማሰብ ጥቃቱን በማቀነባበር ተሳትፎ አድርጋለች፡፡ በተደጋጋሚ አሰቃቂ ግድያዎችን መፈጸሙን አጠናክሮ የቀጠለው አይሲስ በያዝነው ሳምንትም፣ በ21 ግብጻውያን ላይ ከፈጸመው አንገት የመቅላት ግድያ በተጨማሪ በኢራቋ ከተማ አል ባግዳዲ 45 ሰዎችን በእሳት አቃጥሎ መግደሉ ተዘግቧል፡፡


በታሪክ ከፍተኛው ዝርፊያ ነው ተብሏል

የሩስያ፣ ዩክሬን፣ቻይና እና የአውሮፓ አገራት ዜግነት ያላቸው የኢንተርኔት አጭበርባሪዎች በተለያዩ የአለም አገራት በሚገኙ ከ100 በላይ ባንኮች ላይ በፈጸሙት ስርቆት በድምሩ 1 ቢሊዮን ዶላር መዝረፋቸውን ቢቢሲ ዘገበ፡፡ በኢንተርኔት ከተፈጸሙ መሰል የባንክ ዝርፊያዎች ከፍተኛው ገንዘብ የተሰረቀበት ነው የተባለው ይህ ዘረፋ፣ አጭበርባሪዎቹ በባንኮቹ ኮምፒውተሮች ላይ በጫኗቸው መረጃን የሚሰርቁ ሶፍትዌሮች አማካይነት የተከናወነ ሲሆን፣ በባንኮቹ ውስጥ የነበረው ገንዘብ አጭበርባሪዎቹ ወደከፈቱት የሃሰት አካውንት እንዲዘዋወር ተደርጓል፡፡
ካስፔርስኪ የተባለውን አለማቀፍ የኢንተርኔት ደህንነት ተቋም ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ አጭበርባሪዎቹ ከእያንዳንዱ ባንክ ከ2.5 ሚሊዮን እስከ 10 ሚሊዮን ዶላር ዘርፈዋል፡፡ እስከዛሬ ከተከናወኑት የባንክ ዘረፋዎች ሁሉ ፍጹም ውጤታማ እንደሆነ በተነገረለት በዚህ የኢንተርኔት ማጭበርበር ተግባር ሰለባ  የሆኑት ባንኮች ስም በይፋ ባይገለጽም፣ ባንኮቹ አሜሪካን ጨምሮ በተለያዩ 25 የአለማችን አገራት ውስጥ እንደሚገኙ ታውቋል፡፡
ዝርፊያው አሁንም እንደቀጠለ የጠቆመው ኩባንያው፣ ባንኮች የኮምፒውተር ሲስተሞቻቸው በዚህ የአጭበርባሪዎች ሶፍትዌር እንዳልተጠቁ ማረጋገጥና አስፈላጊውን ፍተሻና ጥንቃቄ ማድረግ ይገባቸዋል ብሏል፡፡

*200ሺ ሰዎች አመልክተው 100 ለመጨረሻው ዙር አልፈዋል
*4 ሴቶችና 1 ወንድ በማርስ የሪያሊቲ ሾው ፕሮግራም ይሳተፋሉ

ኤድሞል በተባለው ኩባንያ የሚዘጋጀውና አምስት ተፎካካሪዎችን የሚያካትተው የ2024  የቢግ ብራዘር የቴሌቪዥን ሪያሊቲ ሾው ፕሮግራም በማርስ ፕላኔት ላይ ሊዘጋጅ ነው፡፡
ኩባንያው በድረገጹ ላይ ባወጣው  መረጃ እንደጠቆመው ፣ ማርስ ዋን በተሰኘው ፕሮጀክት አማካይነት ከ9 አመታት በኋላ ወደ ማርስ  ሊደረግ የታቀደው ጉዞ አካል በሆነው የቢግ ብራዘር ላይ ለመሳተፍ 200 ሺህ ሰዎች ያመለከቱ ሲሆን  ለመጨረሻው ዙር ያለፉት 100 ሰዎች ተለይተዋል፡፡
ከ100ዎቹ እጩ ተፎካካሪዎች መካከል 39 አሜሪካውያን፣ 31 አውሮፓውያን፣ 16 እስያውያን፣ 7 አፍሪካውያን እና 7 አውስትራሊያውያን እንደሆኑ ታውቋል፡፡ በማርስ ላይ በሚከናወነው የ2024 የቢግ ብራዘር ሾው ላይ የሚሳተፉት አራት ሴት እና አንድ ወንድ ተፎካካሪዎች እንደሚሆኑ የተገለጸ ሲሆን  ጉዞው 3.6 ቢሊዮን ፓውንድ እንደሚፈጅ  ታውቋል፡፡ በማርስ ላይ የሚከናወነው ቢግ ብራዘር  በየሁለት አመቱ እንደሚዘጋጅ የጠቆመው መረጃው፣ ወደ ማርስ የሚደረገው ጉዞ 200 ቀናትን ያህል እንደሚፈጅም አስታውቋል፡፡

Saturday, 21 February 2015 13:58

“ሽርሽር” ገበያ ላይ ዋሉ

 በጀሚል አክበር የተፃፈው “ሽርሽር” የተሰኘ የአጭር ልብወለዶች ስብስብ ሰሞኑን ለንባብ በቅቷል፡፡ በመጽሃፉ ውስጥ 18 ያህል ታሪኮች የተካተቱ ሲሆን በ28 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡  ፀሀፊው ከዚህ ቀደም “ካገር ፍቅር እስከ አዲሳባ” የተሰኘ በእስረኞች ታሪክ ላይ የተመሰረተ መፅሀፍ ለንባብ ማብቃቱ የሚታወስ ሲሆን ታሪኩም በሸገር ሬዲዮ እንደተተረከ ደራሲው አውስቷል፡፡

Saturday, 21 February 2015 13:39

የ100ሺ ብር ግጥም

ዳሽን ቢራ አክሲዮን ማኅበር የመጀመሪያውን ዓመት “ዳሽን የኪነ ጥበባት ሽልማት” ጥር 24 ቀን 2007 ዓ.ም በሚሊኒየም አዳራሽ ማካሄዱ ይታወቃል፡፡ በዚሁ ወቅት በስነ - ግጥም ዘርፍ ለውድድር ከቀረቡ 157 ግጥሞች መካከል 1ኛ በመውጣት 100.000 ብር ሽልማት አሸናፊ የሆነው የሰለሞን ሞገስ ግጥም ከዚህ በታች የቀረበው ነው፡፡

ሕልሞቻችሁን ፈልጉ

በንስር ጉልበቶቻችሁ በጉንዳን ጽኑ ሥርዓት፣
በቆሰለ ጅብ ተጋድሎ በሴቴ ሸረሪት ብልሃት፣
በረቂቅ የጣዝማ ጥበብ በአናብስት የወኔ ሙላት፣
ሕልሞቻችሁን ፈልጉ እስከ ከፍታችሁ አናት፡፡
    በየብስና በባህሩ፣
    በበረሃና በዱሩ፣
    በህዋው ላይ በጠፈሩ፣
    መቼም ይሁን የትም ሥፍራ፣
    በመሬት እንደ አደን ውሻ፤ በሰማይ እንደጆቢራ፣
የሰው ልጆች ሆይ ተነሱ!  
ያንቀላፋውን ማንነት ፍጥረታችሁን ቀስቅሱ፣
መክሊታችሁን ፈልጉ ሕልሞቻችሁን አስሱ፡፡
    የየመንገዱ ትብታብ ድር ክንፎቻችሁን ያሰረ፣
    እምቅ ወኔን የፈተተ የእልህ ጉልበት የጨመረ፣
    መገፋት፣ መውደቅ፣ መታሸት፣ መወቀጥን ያስተማረ፣
    እንኳንስ ኖረ ጨለማ እንኳን እሾህ ተፈጠረ፡፡
    አውራ ዶሮ እንኳ በአቅሙ አምፆ ባይሆን በቁጣ፣
    መች ያየው ነበር ዓለሙን ቅርፊቱን ሰብሮ ባይወጣ?
    ወትሮስ ጨለማ ከምንጩ፣ ፅልመት ፊቱን ባይፈጠር፣
    ብራው ቀን ጨለማ አልነበር?
    ወርቅም ዘመን እስኪያነሳው፣
    አፈር ላይ ነው የሚተኛው፡፡
    እና…
የውስጣችሁን ዝማሬ የነፍሶቻችሁን ቅኝት፣
የልባችሁን ተመስጦ የሕልሞቻችሁን ምሪት፣
የተፈጥሯችሁን ጥሪ የመሻታችሁን ትዕይንት፣
    የናፍቆት በገናችሁን የተስፋችሁን ነጋሪት፤
    የልባችሁን ውብ ቋንቋ፣
    የውስጣችሁን ሙዚቃ፤
    ከአጽናፍ እስከ አጽናፍ አልሙ፣
    በእውቀት፣ በጥበብ ማማ ላይ  በኩራት፣ በክብር ቁሙ፡፡
        እንደ ሰንደቅ ዓላማ ክብር በከፍታ እንድታርጉ፣
        መደንዘዝ የሰወረውን መክሊታችሁን ፈልጉ፡፡
        በራስ ለራስ ዋጋ ማነስ ቅስማችሁን አታድቅቁ፣
        በተስፋ ማጣት ስብራት ስፍራችሁን አትልቀቁ፣
        ከአፈር፣ ከጭቃ መሃል ነው የሚገኘው እፁብ ወርቁ፡፡
        ጋንም እንደጥራጊ የትም መበተን ምን ይሆን?
        ዋርካ ሲቻል ሰንሰል መሆን፡፡
        በሉ እንጂ ጃል!            
በልባችሁ ላይ ያለውን ጭሱን፣ ጭጋጉን ጥረጉ፣
የነፍሳችሁን ብርሃን ሕልሞቻችሁን ፈልጉ፡፡
          ለአደን፣ ለግዳይ ተነሱ!
        እምቅ ብቃትን አስሱ!!
    የኑሮ ውጣ ውረዱ ቁልቁለትና ዳገቱ፣
    የብቸኝነት በረሃው ራብ፣ ጥምና እንግልቱ፣
    አሻጋሪ የለሽ ባህር የቀን ጨለማው ብርታቱ፣
    የአማሳኙ፣ የአዋሻኪው፣ የሸንጋዩ፣ የጽልመቱ፤
    ሕልም ካለ ይታለፋል!
ጉም፣ ጭጋጉ ይገፈፋል፡፡
ምሬት ገ’ተህ፤ እንባ አቁመህ፤ ሰበብ ጥለህ እልህ ጨምር፣
ብሶት ትተህ ማርሽ ቀይር፣
የነግ ፀሐይ ጎህ ሲወለድ፤ መጪው ዘመን አቤት ሲያምር!!
ስንት ንቀት ቢለጥፉ ስንት አሉታ ቢከምሩ፣
አበበ ነው ድል ያ’ረገው ይህን ዓለም በሌጣ እግሩ፡፡
አትሰወር!  አትደበቅ!  አንተም ንገስ በከፍታ፣
ተራራ  ሁን ወይ ኮረብታ፡፡
    ንሳ ጎበዝ!
    በጎ ተስፋ ካላለሙ ዕድሜ ከሆነ ሕልም የለሽ፣
    እንደ ደረቀ ቅጠል ነው የሰው ሕይወት ረብ የለሽ፡፡
    ራዕይ የሌለው አገር ሕልም የሌለው ትውልድማ፣
    ነፍስ የሌለው አሻንጉሊት መብራት የጠፋው ከተማ፡፡
    አዎን ጎበዝ!....
ዘመናችሁ እንዲከብር ዱካችሁ “ እከሌ” እንዲሰኝ፣
ሕይወታችሁ እንዲጣፍጥ ኑሯችሁ ትርጉም እንዲያገኝ፤
ስማችሁ በምርጦች ተራ በቀለመ - ወርቅ እንዲፃፍ፣
ፍሬያችሁ ከዘመን ዘመን እርሿችሁ ለትውልድ እንዲያልፍ፤
ተነሱ በአጭር ታጠቁ! ወገባችሁን ሸብ አ’ርጉ፣
መክሊታችሁን አስሱ ሕልሞቻችሁን ፈልጉ!!
የእናት አባት ብቻ አ’ደለም አምጦ የመፍጠር ግዱ፣
ሕልማችሁን ፀንሳችሁ እራሳችሁን ውለዱ፡፡
    የድል፣ የአርበኝነት ውሎን ለየራሳችሁ ንገሩ፣
    እንደ ያሬድ ሰባቴ ነው ወድቆ መነሳት ምስጢሩ፡፡
    መንገዳችሁ ላይ ከበራው አምፖል ከያዘው ሰማዩ፣
    ሕልም ይበልጣል ከፀሐዩ፡፡
    የሰው ልጆች ሆይ ተነሱ!
    ያንቀላፋውን ተፈጥሮ እምቅታችሁን ቀስቅሱ፣
    ጉልበታችሁን አበርቱ፤ ክንፎቻችሁን አድሱ፣
መክሊታችሁን ፈልጉ ሕልሞቻችሁን አስሱ፡፡

Saturday, 21 February 2015 13:31

የቀለም ቆጠራ ጉዳይ

የአማርኛ ሥነ ድምፀልሳን (ፎኖሎጂ) በአጠቃላይ፣ በተለይ ደግሞ የቀለም ቆጠራ በሙላት እና በቅጡ ያልተጠና በመሆኑ በዚህ መስክ እስካሁን ያለን ዕውቀት ያልተሟላ፣ ያልተደራጀና “ግልብ” ዓይነት ነው ማለት ሳይቻል አይቀርም። በአማርኛ ሥነግጥም የቀለም ቆጠራ መርህ በብዙ መልኩ የተዛባና አሳሳች ሆኖ በመቆየቱ፣ የግጥም ዓይነቶች ምደባችንም እንደዚሁ ቅጣንባር የሌለው ወደመሆኑ ተቃርቧል።
ይህንን መወናበድ ዮሐንስ ሰ. የተባሉ ጸሃፊ በጋዜጣችሁ ባቀረቧቸው መጣጥፎች ማለፊያ አድርገው አቅርበውታል። ጸሐፊው ነቅሰው ያወጡዋቸው ስህተቶችና መደናገሮች ትክክለኛ እና ተገቢ ሆነው አግኝቼአቸዋለሁ።
ዕውቀት እምነት አይደለም፤ ይመረመራል፤ ይፈተሻል፤ በየጊዜውም ይሻሻላል። ዕውቀትን በጭፍን ተቀብሎ አምልኮ ማድረግ ከጠማማና ከጽልመት ጎዳና አያወጣም። በቅጡ የተረዱትን ምርመራ በትሁት ድፍረት ማቅረብም ተገቢና የሕልውናም ጉዳይ ነው።
ስለ አማርኛ ሥነግጥም እስካሁን ከቀረቡት ሐተታዎች የመንግስቱ ለማ በብዙ መልኩ የተሻለው ነው፤ ጥቂት ማጠናከሪያ ግን ያስፈልገዋል። የብርሃኑ ገበየሁ፣ “የአማርኛ ሥነግጥም” በብዙ መልኩ የተሟላና  የተደከመበት ነው። ነገር ግን፣ በተለይ ቀለም ቆጠራንና፣ የግጥም ምደባዎችን በተመለከተ ብዙ እንከኖች አሉበት። መጽሐፉ ማስተካከያና እርማቶች ተደርገውበት፣ በሁለተኛ ኤዲሽን፣ ሊታተም ይገባ ነበረ። ነገር ግን ይሔን እንዳንጠብቅ የሚያደርገን አሳዛኝ ነገር አለ፤ አሁን ደራሲው በሕይወት የለም።
በየትኛውም መንገድ ቢሆን በአንድ የዕውቀት ዘርፍ ላይ አማራጭ መጻሕፍት የመኖራቸው ፋይዳ አሌ የሚባል አይደለም። በዚህ አጋጣሚ፣ በቅርቡ ለሕትመት የሚበቃ የአማርኛ ሥነግጥም መጽሐፍ በዝግጅት ላይ እንደሆነ ብገልጽም መልካም ነው።
በማጠቃለያውም፣ ዮሀንስ ሰ. የተባሉት ጸሐፊ፣ ላቀረቡት ማለፊያ ትንተና፣ ከልቤ ያደንቅኋቸው መሆኑን መግለጽ እወዳለሁ።
አብነት ስሜ፤ (የቋንቋና የሥነጽሑፍ መምህር፣ የ“ኢትዮጵያ ኮከብ” እና የ“ፍካሬ ኢትዮጵያ” ደራሲ)

Saturday, 21 February 2015 13:29

የፍቅር ጥግ

ማን እንደሚያደንቅህና እንደሚወድህ ንገረኝና ማንነትህን እነግርሃለሁ፡፡
ኢሪክ ፍሮም
የማያፈቅር ልብ ከሚኖረኝ ይልቅ የማያዩ ዓይኖች፣ የማይሰሙ ጆሮዎች፣ የማይናገሩ ከናፍሮች ቢኖሩኝ እመርጣለሁ፡፡
ሮበርት ቲዞን
ፍቅር፤ ለሁሉም እጅ ቅርብና በማንኛውም ወቅት የሚበቅል ፍሬ ነው፡፡
ማዘር ቴሬዛ
ሰዎች ኢ-ተጠያቂያዊ፣ በምክን የማይመሩና ራስ ወዳድ ናቸው፡፡ ሆኖም ውደዷቸው፡፡
ኬንት ኤም.ኪዝ
በህልምና በፍቅር ውስጥ የማይቻሉ ነገሮች የሉም፡፡
ዣኖስ አራኒ
አፍቅሮ ማግኘት ምርጥ ነው፡፡ አፍቅሮ ማጣት ሁለተኛው ምርጥ ነገር ነው፡፡
ዊሊያም ሜክፒስ ቻክሬ
ብዙ ጊዜ ፍቅር ይዞኛል … ሁሌም ካንቺ ጋር ነው፡፡
ማንነቱ ያልታወቀ ፀሓፊ  
ፍቅር ዓመታትን የመቁጠር ጉዳይ አይደለም … ዓመታቱን ትርጉም ያላቸው ማድረግ እንጂ፡፡
ሚሼል አማንድ
ገነት ሁሌም ፍቅር በከተመበት ስፍራ ይገኛል፡፡
ጆሃን ፖል ፍሬድሪክ ሪሽተር
እውነተኛ የፍቅር ታሪኮች ጨርሶ ማለቂያ የላቸውም፡፡
ሪቻርድ ባች
ለመፋቀር በተመሳሳይ መንገድ ማሰብ የለብንም፡፡
ፍራንሲስ ዴቪድ
ጨቅላ ፍቅር፤ “ስለምፈልግሽ እወድሻለሁ” ሲል፣
የበሰለ ፍቅር፤ “ስለምወድሽ እፈልግሻለሁ” ይላል፡፡
ኤሪክ ፍሮም

Saturday, 21 February 2015 13:03

ወንጀል-ነክ እንቆቅልሾች?

ሰውየው የሆቴል ክፍል ውስጥ ጋደም ብሎ በር ይቆረቆራል፡፡ ከአልጋው ውስጥ ይወጣና በሩን ይከፍታል፡፡ በሩ ላይ የቆመው የማያውቀው እንግዳ ሰው ነበር፡፡ እንግዳውም እየተጣደፈ፤ “ይቅርታ አድርግልኝ፤ ሳልሳሳት አልቀረሁም፤ የእኔ ክፍል መስሎኝ ነው” ይልና ከመቅፅበት የፎቁን ደረጃ ወርዶ ይሄዳል። ሰውየው የክፍሉን በር ዘግቶ ሲያበቃ የሆቴሉ የፀጥታ ሰራተኞች ጋ ይደውልና በሩን የቆረቆረውን ሰውዬ በፍጥነት እንዲይዙት ይጠቁማቸዋል፡፡
ለምንድነው በሩን የቆረቆረው ሰውዬው
እንዲያዝ የጠቆመው?
ሰውየውን ለመጠርጠርስ ምንድነው
ያበቃው?
አንድ ሽማግሌ በተንጣለለ ሰፊ መኖሪያ ቤታቸው ውስጥ ለብቻቸው ይኖራሉ። በዕድሜያቸው መግፋት የተነሳ እንደልባቸው መንቀሳቀስ ስለማይችሉ የሚያስፈልጓቸው ነገሮች ሁሉ እቤታቸው ድረስ ይመጡላቸዋል።
አርብ ዕለት ፖስተኛው ፖስታ ሊያደርስ
ሲመጣ አካባቢው ጭር ይልበትና አንድ
ነገር ጠርጥሮ፣ በበሩ ቁልፍ ቀዳዳ አጮልቆ
ይመለከታል፡፡ ባየው ነገርም ይደነግጣል
ሽማግሌው ወለሉ ላይ በደም ተለውሰው
ይታያሉ፡፡
የወንጀል መርማሪ ከመቅጽበት ከስፍራው
ይደርሳል፡፡
መርማሪው፤ ከመኖሪያ ቤቱ ውጭ ሁለት
ጠርሙስ ወተት፣ የማክሰኞ ጋዜጣ፣ ጥቂት
ያልተከፈቱ ፖስታዎችና ስጦታዎችን
ያገኛል። መርማሪው ነፍሰ ገዳዩን ለማወቅ
ጊዜ አላጠፋም፡፡
ነፍሰ ገዳዩ ማነው?

መልስ
በሩን የቆረቆረው እንግዳ ሰውዬ “የእኔ ክፍል መስሎኝ ነው” ብሎ ነበር፡፡ እንዲያ ቢሆን ኖሮ ግን የክፍሉን ቁልፍ መያዝ ነበረበት፤ በሩንም መቆርቆር አልነበረበትም፡፡
ነፍሰ ገዳዩ፤ ጋዜጣ አዳዩ ሰውዬ ነው፤ ምክንያቱም የረቡዕና ሐሙስ ጋዜጦችን አላመጣም፡፡  ይሄንንም ያደረገው ጋዜጦቹን የሚያነብ እንደሌለ ስላወቀ ነው፡፡


ሰማያዊ ፓርቲ የገባ የአንድነት አመራር የለም
ለኢህአዴጎች ትክክለኛውን የህዝብ ስሜት ነግሬአቸዋለሁ
ለ“አንድነት” ችግር የመጀመሪያው ተጠያቂ መንግስት ነው

በ2002 ምርጫ አሸንፈው ፓርላማ የገቡት ብቸኛው የተቃዋሚ ፓርቲ ተወካይ የተከበሩ አቶ ግርማ ሰይፉ፤ ምርጫ ቦርድ አንድነት ፓርቲን ለእነ አቶ ትዕግስቱ አወሉ ማፅደቁን ተከትሎ በዘንድሮ ምርጫ እንደማይወዳደሩ ገለፁ፡፡
ቦርዱ አንድነትን በተመለከተ የሰጠውን ውሳኔ ክፉኛ የሚተቹት አቶ ግርማ፤ በግንቦቱ ምርጫ ዙሪያና የፓርላማ ቆይታቸውን እንዲሁም ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮችን በተመለከተ ከአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ ጋር ተከታዩን ቃለምልልስ አድርገዋል፡፡



በርካታ የአንድነት አመራር አባላት ወደ ሰማያዊ ፓርቲ ገብተዋል ተብሏል፤ እርስዎ ለምን ፓርቲውን አልተቀላቀሉም? ከዚህ በኋላ የእርስዎ የፖለቲካ ትግል አቅጣጫ ምንድን ነው የሚሆነው?
በርካታ የአንድነት አመራር አባላት ወደ “ሰማያዊ” ገብተዋል የሚለው ስህተት ነው፡፡ አንድም የካቢኔ አባል የነበር ሰው ወደ ፓርቲው አልገባም፡፡ የፈለገ ሰው ግን ያሻውን  ፓርቲ መቀላቀል እንደሚችል አቅጣጫ አስቀምጠናል። መንግስት አንድነት ላይ እንዲህ ያለ “ነውረኛ” እርምጃ ከመውሰዱም በፊት ቢሆን ሰዎች ወደ ፈለጉት ፓርቲ መሄድ ይችሉ ነበር፡፡ አሁን መንግስት በያዘው አካሄድ የመድብለ ፓርቲ ስርአት መሸከም የሚችል መንግስታዊ መዋቅርም ሆነ ፍላጎት የለም፡፡ ስለዚህ የሰላማዊ ትግሉ በምን አይነት መንገድ ሲመራ የተሻለ ለውጥ ያመጣል የሚለውን አስበንበት አቅጣጫ ማስቀመጥ እንዳለብን ወስነናል፡፡
ፓርቲውን ያልተቀላቀላችሁበት ምክንያት ምንድንነው?
ሰማያዊ ፓርቲ ገብተን ብናጠናክረው፣ ሲጠናከር እግሩን የሚቆርጡት ከሆነ ትርፉ አጉል ድካም ነው የሚሆነው፡፡ አንድነት ፓርቲ የሊበራል አስተሳሰብ  የሚከተል እንደመሆኑ የግለሰቦችን መብት ያከብራል፡፡ የፈለገ ሰው ወደ ፈለገው ፓርቲ የመግባት መብት አለው፡፡ ነገር ግን ብዙዎች ወደ ሰማያዊ ገብተዋል የሚለው ፖለቲካ ለምን እንዳስፈለገ አልገባኝም፡፡ ከኛ አመራር ውስጥ ግን ማንም የስራ አስፈፃሚ  አባል ወደ ሰማያዊ አለመግባቱን አረጋግጣለሁ። ይሄ ለሰማያዊ ከጠቀመውና የኢትዮጵያን  የፖለቲካ ሁኔታ ማሻሻል የሚችል ከሆነ በኛ በኩል ቅሬታ የለንም፡፡
አንድነትን ያለአግባብ “ተነጥቀናል” የምትሉ አመራሮች ምንድን ነው ያሰባችሁት?
አስር ጊዜ እየተፈተነ የሚወድቅ የፍትህ ስርአት ቢኖረንም የፍትህ ስርአቱን ለመፈተሽ ፍ/ቤት ሄደናል፡፡ ፍ/ቤቱ ፖለቲካዊ ውሳኔ ነው የሚሰጠው ወይንስ ማስረጃን ተንተርሶ ነው የሚወስነው የሚለውን ወደፊት የምናየው ይሆናል፡፡ ጉዳያችንን ግን ፍ/ቤት አቅርበናል፡፡ ፍ/ቤቱ ትክክለኛ ውሳኔ የሚወስን ከሆነ፣ እኛ ከ2007 ምርጫ ጋር ምንም የተለየ ፍቅር የለንም። ፓርቲያችንን በተሻለ ሁኔታ በመምራት፣ እንደነ ትዕግስቱ አይነት “ሰንኮፎችን” የነቀልንበት ሂደት አድርገን ልንወስደው እንችላለን፡፡
በሌላ በኩል ከእንደነዚህ አይነት ሰዎች ጋር ሌላ ተጨማሪ ጊዜ እንዳናጠፋ የተፈጠረ እድልም ሊሆን ይችላል፡፡ ለወደፊት የሰላማዊ ትግሉን ለማጥራት የሚረዳ አጋጣሚ ነው ብዬም እቀበለዋለሁ፤ ግን በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ በመንግስት ደረጃ እንዲህ ዓይነት “አስነዋሪ” ድርጊት ሲፈፀም ማየትና የዚያ አካል መሆን በጣም ያሳፍራል፡፡ ሁሉም የሚያፍሩ ይመስለኛል፣ ካላፈሩ ደግሞ ህሊና አላቸው ብዬ አላስብም፡፡ በኛ በኩል ግን ባደረግነው ሁሉ ምንም የሚቆጨን ነገር የለም፡፡ በነገራችን ላይ ሲጀመር አንስቶ “ውጤቱን በኋላ ታዩታላችሁ” እያለ ትዕግስቱ ሲያስፈራራን ነበር፤ ስለዚህ እሱ ጨዋታ ውስጥ የገባው ውጤቱን አውቆት ነው፤ እኛ ግን ጊዜና ገንዘባችንን እያባከንን ነበር፡፡
አንድነት ውስጥ በየጊዜው “ደንብና መርህ ይከበር” የሚሉ ውዝግቦች መከሰታቸው ምክንያቱ ምንድን ነው?
በ2002 ምርጫና አሁን የተደረገው ተመሳሳይ ነገር ነው፤ ምንም ልዩነት የላቸውም፡፡ በ2002 በተፈጠረው ሁኔታ መንግስት አንድነትን ለእነ ፕሮፌሰር መስፍን ወይስ ለእነ ኢንጅነር ግዛቸው ብሰጥ ይሻላል የሚል ምርጫ ውስጥ ነው የገባው፡፡ ለኢ/ር ግዛቸው ብሰጠው ይሻላል ብሎ ወሰነ፡፡ አሁን ደግሞ ከእነ በላይ እና ከእነ ትዕግስቱ የቱ ይሻላል ብሎ መረጠ፡፡ ለትዕግስቱ ተሰጠው፡፡
በ2002 ውሳኔ አሰጣጣቸው ላይ  በጣም ጠንቃቃ ነበሩ፤ አሁን ደግሞ ምንም ቀዳዳ ሊያገኙ ስላልቻሉ በጣም አሳፋሪ የሆነ ውሳኔ ወሰኑ፡፡ ለምንድን ነው አንድነት ላይ እንዲህ የሚደረገው? ምንም ጥርጥር የለውም፤ አንድነት አስቦ የሚሰራ ፓርቲ በመሆኑ ነው፡፡ በሳምንት ሁለት ጋዜጣ ያሳትማል፡፡ ኢህአዴግ ራሱ ሁለት ጋዜጣ በሳምንት አያትምም፡፡ ሁለት ጋዜጣ የሚያሳትም ፓርቲን ኢህአዴግ እንዴት አድርጎ መቋቋም ይችላል? እኛ የሚዲያ ቅስቀሳና ክርክር ሲጀምር እንደምንበልጣቸው እርግጠኞች ነበሩ፤ ስለዚህ ይሄን ቡድን ማፍረስ ነበረባቸው፡፡ 13 ያህል የብሮድካስትና ፕሪንት ባለሙያዎችን አዘጋጅተን  ስንጠብቃቸው ነበር፤ ይሄ ያስደነግጣቸዋል፡፡
ሌላው እስከ 500 እጩዎች አቀርባለሁ ብሎ የተዘጋጀ ፓርቲ የለም፡፡ አብዛኞቹ ይሄን የማድረግ አቅም አልነበራቸውም፡፡ ህዝቡ ጋ ተደራሽ ሆኖ፣ ፓርቲው ባለው ጥንካሬ ብቻ ሳይሆን ኢህአዴግ ባለው ደካማ አስተዳደር የሚፈጠረውን የተቃውሞ ድምፅ ሊሰበስብ የሚችለው አንድነት ብቻ እንደሆነ ኢህአዴግ ጠንቅቆ ያውቃል፡፡ በእርግጥም ይሄን ማድረግ የሚችለው አንድነት ብቻ ነበር፡፡ ታዲያ ይሄን ኃይል ፈርተው ካላፈረሱ ምን ሊያፈርሱ ይችላሉ? በ2002 ዓ.ም ተመሳሳይ ነገር ነው ያደረጉት፡፡ የመድረክ ጥንካሬ የነበረውን አንድነት ማተራመስ፣ መድረክን ለማተራመስ ይጠቅማቸው ስለነበር ያንን አድርገዋል፡፡ አሁን መድረክን ለምን አይነኩትም? በኛ ሰበብ ነበር መድረክን ሲጨፈጭፉ የነበሩት፤ ስለዚህ አንድነትን ለማዳከም በቂ ምክንያት ነበራቸው፡፡
እርስዎ በአንድነት ውስጥ ለተፈጠረው ምስቅልቅል የመጀመሪያ ተጠያቂ የሚያደርጉት ማንን ነው?
ምንም ጥርጥር የለውም መንግስትን ነው። የደህንነት አካሉ ነው ይሄን ያደረገው።  ኃላፊነቱን በመውሰድ ያስፈፀሙት ደግሞ ምርጫ ቦርድና ሚዲያዎች ናቸው፡፡ የመጀመሪያ ተኩስ የተጀመረው በአንድ የግል ጋዜጣ ላይ ነው - ከኮሙኒኬሽን የሚታዘዝ ግለሰብ አንድም ነገር ሳይኖር “አንድነት እየተከፋፈለ ነው” ብሎ ፃፈ፡፡ ከዚያ ሬዲዮ ፋና፣ ኢትዮጵያ ቴሌቪዥንና ሌሎች ሚዲያዎች ተግተውበታል፡፡ እኛ መልስ እንስጥ ብንል ተቆርጦ ተቀጥሎ ነው የሚቀርበው፡፡ ለሬዲዮ ፋና ለምንድን ነው መልስ እማትሰጡት ተብለን መልስ ስንሰጥ፣ በቪዲዮ በተደራጀ መልኩ ቀርፆ ከኢቢሲ ጋር ግንባር በመፍጠር በአካል ያልተገናኘን ሰዎችን ስንከራከርና ስንሰዳደብ እንደነበር አድርጎ አቅርቧል፡፡ ከዚያ ውጪ ግን የአባላት ምልመላችን “ሆዳሞችን” እንዳያፈራ መጠንቀቅ እንዳለብን  ተረድተናል፡፡ ከብዙ ሺህ አባላት ሦስትና እና አራት “ሆዳሞች” ቢኖሩ የሚገርም ባይሆንም ጥንቃቄ ማድረግ እንዳለብን ተገንዝበናል፡፡
መድረክን ወክለው ነው ፓርላማ የገቡት። ከእዚህ አንፃር ለምርጫው በፓርላማ መቀመጫ የሚሰጠውን የገንዘብ ድጋፍ መድረክ ይጠቀምበታል?
 መድረክን ወክዬ ነው የገባሁት፤ ስለዚህ ይችላል፡፡ በእርግጥ መድረክን ወክዬ ከተወዳደርኩ በኋላ የህዝብ ወኪል ነው የሆንኩት፡፡ ካልሆነ “አንድነት” ከመድረክ ሲወጣ “ግርማ የመድረክ ተወካዩ አይደለም” ወይም የወረዳ 6 ሰዎች “ግርማ የመድረክ ተወካይ ካልሆነ አንፈልገውም” ብለው ፊርማ ማስገባት ቢፈለጉ ማስተባበር የሚችለው መድረክ ነው፡፡ አሁን ባለው ሁኔታ በፓርቲ ጥቅማ ጥቅም ደረጃ መድረክ የሚጠቀም ይመስለኛል፡፡
ላለፉት አምስት ዓመታት በፓርላማ ብቸኛ የተቃዋሚ በፓርላማ ቆይታዎ የሚጠበቅብኝን  ተወጥቻለሁ ብለው ያስባሉ?
 እኔ በህይወቴ ከወሰንኳቸው ውሳኔዎች ሁሉ የማይቆጨኝ ፓርላማ ለመግባት የወሰንኩት ውሳኔ ነው፡፡ ያደረግሁት አስተዋፅኦ አደርገዋለሁ ብዬ ከገመትኩት በላይ ነው፡፡ ብዙ ነገሮችን አነብ ነበር፤ የማነበው የሚጠበቅብኝን ኃላፊነት ለመወጣት ነው፡፡ መደገፍ ያለብኝን ለመደገፍ፣ የህዝብ ጥያቄ ነው ያልኩትን ለመጠየቅ፡፡ እናም በኔ በኩል ብዙ ደክሜያለሁ ብዬ አምናለሁ፡፡ ሁሉም የም/ቤቱ አባላት ይሄን ያደርጋሉ ወይ ካልከኝ አያደርጉም፡፡ ምክንያቱም ምንም የሚጠየቁበት ነገር ስለሌላቸው ኃላፊነት የለባቸውም፡፡
አንድ ሰው ብቻውን ፓርላማ ውስጥ መቆየት በጣም ከባድ ነው፡፡ እንደ አንድ ሰው ሳይሆን እንደ ሺህ ሆኜ ሰርቻለሁ ብዬ አስባለሁ። ስገባም አዋጅ ላፀድቅ ወይም ለመረጠኝ ህዝብ መሰረተ ልማት ላሟላ አልነበረም - አማራጮችን ለማቅረብና የህዝቡን ስሜት ለማስተጋባት ነው። እስካሁን ካገኘሁት አስተያየት የአብዛኛው ህዝብ ድምፅ ሆኜ አገልግያለሁ ብዬ አምናለሁ። ለኢህአዴጎች ትክክለኛውን የህዝብ ስሜት ነግሬያቸዋለሁ፡፡ ተጠቅመውበታል ወይ ከተባለ አልተጠቀሙበትም ምክንያቱም እነሱ የሚሰሙ ሰዎች አይደሉም፡፡
የቀድሞውን ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስንም ሆነ አቶ ኃይለማርያምን በጥያቄ የመሞገት ዕድል ነበርዎት፡፡ ከሁለቱ የትኛው የተሻለ አሳማኝ ምላሽ ይሰጥዎት  ነበር? በአጠቃላይ ሃገር በመምራት ረገድስ…
ሁለቱም ለህዝብ ምላሽ የሚሰጡ አይደሉም፡፡ ለጥያቄም ምላሽ አይሰጡም፡፡ ግን ቢያንስ መለስ ጥያቄ ሲመልስ ብልጥ ነበር ብዬ አምናለሁ፡፡ ለምሳሌ አቶ ኃይለማርያም ባለፈው ጥያቄ ሲመልሱ “ባለኝ መረጃ መሰረት” እያሉ ነነር፤ እርግጠኛ ባልሆኑበት መረጃ ሃገር እያስተዳደሩ ነው፡፡ በኔ እምነት መለስ በከፍተኛ ስልጣን ነበር የሚመራው፡፡ ኃይለማርያም ያ ስልጣን አላቸው ብዬ አላስብም፡፡
አንድነትን የመሳሰሉ ትላልቅ ፓርቲዎች “ፅንፍ በመያዝ ገዥው ፓርቲ ጥላቻ እንዲያድርበት ይገፋፉታል” የሚሉ አስተያየቶች ይሰነዘራሉ፡፡ እርስዎ ምን ይላሉ?
በመጀመሪያ ደረጃ አንድነት ከጥላቻ ፈፅሞ ነፃ የሆነ ፓርቲ እንደሆነ ነው የሚታወቀው፡፡ እኔ እንደውም የምታማው ለኢህአዴግ ቅርብ ሆኗል እየተባልኩ ነው፡፡ አንድነት ውስጥ ቂም በቀልና ስድብ የለም፡፡ በተለይ የአሁኑ አሰራራችን የሰለጠነ ነበር፡፡ አንድ ጓደኛዬ፤ “ኢህአዴግ ከሚዲያዎች ‹አዲስ ነገር› ጋዜጣን ከፓርቲዎች ‹አንድነትን› መሸከም ካቃተው የፖለቲካ ጨዋታ አይችልም ማለት ነው” ብሎ ነበር፡፡ ኢህአዴግ ነፃ ሚዲያና የመድብለ ፓርቲ ስርአት መሸከም የማይችል እንደሆነ የሚያረጋግጠው ይሄ ነው። ለምርጫው ስትራቴጂና ፕላን አውጥተን ኢህአዴጐችን በግልፅ በዚህ መንገድ ነው የምናሸንፋችሁ ያልነው እኛ ብቻ ነን፡፡ የጥላቻ ፖለቲካን እናስወግዳለን ብለን ነበር ስንሰራ የቆየነው፡፡
ከዘንድሮ ምርጫ  ምን ይጠብቃሉ?
በመጀመሪያ ደረጃ ምርጫ  የሚባል አለ? እኔ ምርጫው አልቋል ብዬ ነው የማስበው፡፡ አሁን እየተደረገ ያለው የሃብት ብክነት ነው፡፡ አንድም መንግስት ለመሆን የሚያስችላቸውን እጩዎች ያላቀረቡ ፓርቲዎች የሚወዳደሩበት ምርጫ‘ኮ ነው፡፡ ለሁለት ወንበር የሚወዳደሩ ፓርቲዎች አሉ፤ እነዚህ በቃ አላማቸው ፓርላማ መግባት ብቻ ነው፡፡ እንደ ፓርቲ የሚወዳደሩትም እንኳ ቢሆኑ ሙሉ ለሙሉ አያሸንፉም እንጂ ቢያሸንፉ መንግስት አይሆኑም፡፡ መንግስት ለመሆን ሳያስቡ መወዳደር ምን ማለት ነው? ስለዚህ ኢህአዴግ መንግስት እንደሚሆን አረጋግጧል፡፡
በእርስዎ አመለካከት፣ አሁን ባለው የሃገሪቱ ተጨባጭ ሁኔታ በምርጫ ተወዳድሮ ስልጣን መያዝ ይቻላል?
እኛ በምርጫ እምነት ነበረን፡፡ ህዝቡ “ስልጣን ለእገሌ ሰጥቻለሁ፤ እሱ ይምራኝ” የሚለው በምርጫ ብቻ ነው፡፡ ይሄ ስልጡን መንገድ ግን እየተጭበረበረ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን እኮ ከማይችሉት ቡድኖች ጋር እየተጋጠመ በማሸነፍ የዋንጫ ጥማቱን ማርካት ይችላል። ጥንካሬና ጉብዝና የሚለካው ከሚመጥኑት ቡድን ጋር ሲወዳደሩ ነው፡፡ ያለዚያ አነስተኛ ኪሎ ያለውን ቡድን መርጠህ በዝረራ እያሸነፍክ  ሁሌም ሜዳሊያ መውሰድ ትችላለህ፡፡
ምርጫ ስልጡን መንገድ ቢሆንም ገዥው ፓርቲ ይሄንን ሊጠቀምበት አልቻለም፡፡ እነዚህ ሰዎች በምርጫ አልጫወትም ካሉ፣ ህዝቡ በሌላ መንገድ  እሞክራቸዋለሁ ሊል ይችላል፡፡ አብዮት ግን በእቅድ የሚመራ አይደለም፤ ሁሉን እንዳልነበረ የሚያደርግ ነው፡፡ አብዮት በዕቅድ የሚመራ ቢሆን እኔ እመራ ነበር፡፡
ጥያቄዬን አልመለሱልኝም፡፡ እምነት አሁን ባለው ሁኔታ  በምርጫ ስልጣን መያዝ ይቻላል አይቻልም?
የ2007 ምርጫ እኮ አበቃ!
ለወደፊትስ?
እርሱን እንግዲህ እኔ ጠንቋይ አይደለሁ፤ በምን አውቃለሁ፡፡ ሆኖም ግን አንዱ ተስፋህ እየጨለመብህ ሲሄድ ሌሎች የሚለመልሙ ተስፋዎች ይኖራሉ፡፡ እኔ በበኩሌ፤ ስልጡኑ መንገድ ምርጫ ብቻ ነው የሚል ጠንካራ እምነት አለኝ፤ ግን ሰይጣናዊ መንገድም አለ። በሰይጣናዊ መንገድ ሲሆን መሳሪያ ያድነኛል ማለት አያስኬድም፤ ሙባረክና ጋዳፊንም አላዳናቸውም፡፡    

      ከዕለታት አንድ ቀን ጦርነት አለ ተብሎ ጐበዝ ሁሉ ክተት ሠራዊት ተባለና ዝግጅት ተጀመረ፡፡
ከአንድ መንደር ወደጦርነቱ የሚሄድ ጐበዝ ሚስቱ ነብሰጡር ነበረችና፤
“ድንገት ጦርነቱ ረዥም ጊዜ ከፈጀ፣ አሊያም አንዳች አደጋ ከገጠመኝ የልጄን ነገር አደራ” ብሏት ተሰናብቶ ወጣ፡፡
ጦርነቱ ከሁለት ዓመት በላይ ፈጀ፡፡ ያ ጀግናም በሰላም ወደ ቤቱ ተመለሰ፡፡
እንደደረሰ “ደህና ከረማችሁ?” አለ፡፡
“ደህና ነህ? እንኳን ደህና መጣህ የኔ ጌታ!” አለች ባለቤቱ፡፡
“ብዙ ሰው ተጐዳባችሁ?”
“ብዙም አይደል፡፡ እኛ ደህና ቦታ ላይ መሽገን ስለነበር ለጠላት አልተመቸንም ነበር፡፡”
ባለቤቱ ወደ ጓዳ ጉድ ጉድ ማለቷን ቀጠለች፡፡
ባልየው አንድ ነገር ግር ብሎታል፡፡ ምንም ዓይነት የህፃን ልጅ ድምፅ አይሰማውም፡፡
“ልጄ የት አለ?” “፣ “ምን ሆነ?” “ወደ እናቴ ልካው ሊሆን ይችላል?” ብዙ ጥያቄዎች ተመላለሱበት፡፡
ሚስቲቱ ምግብ ሠርታ በሉ፡፡ የሚጠጣም ተጠጣና ባል ወደማይቀረው ጥያቄ ሄደ፡፡
“የልጄ ነገር ምን ሆነ?” አለ፡፡
“ልጃችን መወለዱን ደህና ተወልዶ ነበር፡፡ ነገር ግን አንድ ዓመት ተኩል ያህል እንደሆነው በድንገት የብርድ በሽታ አጣደፈው፡፡  በዚያው ህይወቱ አለፈ፡፡”
ባል አዘነ፡፡ ጥቂት ጊዜ ካለፈም በኋላ፤
“ለመሆኑ ስሙን ማን አላችሁት?” አለና ጠየቀ፡፡
“በታወቀው የአካባቢያችን ጀግና ስም ነበር የሰየምነው” አለችው፡፡
“አይ በቃ፤ ልጄ በምን እንደሞተ አወቅሁት” አለ፡፡
“እንዴት? በምንድነው የሞተው?”
“ስሙ ከብዶት ነው!!” አለ፡፡
*   *   *
ስማቸው የከበዳቸው አያሌ ናቸው፡፡ ግማሾቹ ድርጅት ናቸው፡፡ ግማሾቹ ፓርቲ ናቸው፡፡ ግማሾቹ ግንባር ናቸው፡፡ በቅጡ ሳይወለዱ የሞቱ አሉ፡፡ የጨነገፉ እንደማለት፡፡ ተወልደው ብዙም ሳይቆዩ የሞቱ አሉ፡፡ ገና እሚኖሩና ገና እሚሞቱ አሉ፡፡
በተለይ በፖለቲካ ትግል ጉዞ ውስጥ የሆነውን ለምን ሆነ ብሎ ወደኋላ መጨናነቅ እርባና የለውም፡፡ ለትምህርቱና ለተመክሮነቱ ካልሆነ ያዙኝ ልቀቁኝ ቢባል ፍሬ የለውም፡፡ ይልቁንም የተሻለ መንገድን ማቀድና መቀየስ ነው የሚያዋጣው፡፡
“አንዴ ቮልካኖው [አሳተ - ገሞራው] ከፈነዳ በኋላ ላቫውን (ብታኙን) እንደገና መልሶ ወደ እሳቱ ሆድቃ መክተት አይቻልም፡፡ ስለዚህ ማድረግ ያለብን አትክልት መትከል፣ ሣሩን ማጨድና በጐቹን ለግጦሽ ማሰማራት ነው” ይሉናል ፀሐፍት፡፡ የሀገራችንን ነባራዊ ሁኔታ ላስተዋለ የረዥም ጊዜ ሙሾ - አውራጅነት ይበዛዋል፡፡ ውሃ ወቀጣ ነው፡፡ ልብ አላልን ይሆናል እንጂ ከቶም ውሃ - ቅዳ ውሃ መልሱና ድግግሞሹ የትም አላደረሰንም፡፡ ታሪኩና ወቅታዊ ድርጊቱ ተሰምሮ አይለይም፡፡ ሲወድቁ ተስፋ አለመቁረጥና በአጭር ጊዜ የድል ባለቤት ለመሆን መጣደፍ ረብ ያለው ውጤት አያመጡም፡፡ ጥፋትና ጥቃት ደረሰብኝ ብሎ ባንዴ መበታተንም የማለዳ ኢላማን መዘንጋት ነው፡፡
“እያንዳንዱ ወንጀል ፍርሃት መቀፍቀፉ አይቀርም”፡፡ ይሄ ደግሞ ፍርሃትን ለማስወገድ በሚወሰድ የኃይል እርምጃ ይተካና ዲሞክራሲያዊ እንቅስቃሴን ያጨልማል፡፡ አለመዘንጋት ያለብን ዲሞክራሲ አዳጊ ሂደት እንደሆነ ሁሉ አምባገነናዊ ሥርዓትም አዳጊ ሂደት እንጂ ያንድ ጀንበር ጉዳይ አለመሆኑን ነው፡፡ ድንገት የበቀለ አገር እንደሌለ ሁሉ ድንገት ዱብ - ዕዳ የሚሆን ሥርዓት አይኖርም፡፡ የብራ - መብረቅ የሆነ (a Bolt from the blue) ዲሞክራሲ የለም፡፡ በልክ የተሰፋ ዲሞክራሲም ባንድ አፍታ ተፈጥሮ አያውቅም፡፡ ሁሉ ነገር በተዛማጅነት ነው ወደ ዕድገት የሚያመራው፡፡ ያ ማለት ግን ሲያመች በእጅ ሲያቃጥል በማንኪያ በማድረግ ለራስ እንደሚጣፍጥ አርጐ መዋጥ አይደለም፡፡ ሁሌም ማዕከሉ የሀገርና የህዝብ ጥቅም መሆን አለበት!
በኢትዮጵያ ምድር ፖለቲካ ከውሸት ጋር መያያዙ የጥንት የጠዋት ጉዳይ ነው፡፡ “መቦልተክ”፣ መዋሸት የሚል ትርጉም ይዞ ነው የኖረው፡፡ “እገሌ ቦለቲከኛ ነው” ከተባለ ይዋሻል ነው፡፡ ሁሉም ወደወንበር ያመራ ሁሉ ጠዋት ስለህዝብ፤ ማታ ስለራሱ ማውራቱ ነው አስቸጋሪው፡፡ በሀቅ ስለሀቅ በመጓዝ አለመዝለቁ ነው አበሳው፡፡ የየሥርዓቱ ጣጣ መፈክሩ፤ መሸጫው ይሁን መሳቢያው፣ አለመለየቱ ነው፡፡ የሚባለው ሁሉ በሥራ መተርጐም አለመተርጐሙን ለማረጋገጥ ሙስናዊ ግብዓቶቹ እንቅፋት መሆናቸው ነው፡፡ ሙስናው በሙስና መሸፈኑ የባሰ ውስብስብ ሁኔታ ውስጥ እየከተተን መምጣቱ ነው፡፡ ህግ ሽፋን የሚሰጠው ለማን ነው? በሙስና ውስጥ አንበሳው ድርሻ የማነው? የሚለው ጥያቄ እንጂ ሙስናው ራሱን መፈተሽ የቀረ ይመስላል፡፡ ራሳቸው በወንጀል ተጠያቂ የሆኑት በወንጀል ጠያቂ ከሆኑ ወንጀሉ እንዴት መፍትሔ ያገኛል? “የሚያባርረኝ ጣሊያን እንቅፋት መቶት በሞተ ጀግና ነህ ብለው አሠሩኝ እንጂ እኔስ ዓርበኛ አይደለሁም” የሚለው የዓርበኛው ደምበል ንግግር የየዘመኑ ፖለቲካና ፖለቲከኛ መልክ ነው የሚባለው ለዚህ ነው፡፡