Administrator

Administrator

       የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅ/ሲኖዶስ፣ ‹‹ቤተ ክርስቲያንን አዋርደዋል፤ አባቶችን ዘልፈዋል›› ያላቸው አለቆች ቀኖናዊ ምክርና ተግሣጽ እንዲሰጣቸው ያሳለፈው ውሳኔ በፓትርያርኩ ትእዛዝ መታገዱ ከአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት አድባራትና ገዳማት ሰንበት ት/ቤቶች ተቃውሞ ገጠመው፡፡
የአ/አበባ ሀገረ ስብከት ሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ባለፈው ሳምንት እሑድ በሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት አዳራሽ በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ባካሔደው የግማሽ ቀን ውይይት ተሳታፊዎች በሰጡት አስተያየት፤ ቅዱስ ሲኖዶስ በጥቅምቱ የምልአተ ጉባኤ ስብሰባው ‹‹አማሳኝ አለቆች›› ተግሣጽና ማስጠንቀቂያ እንዲሰጣቸው ያሳለፈው ውሳኔ ባለመፈጸሙ ቤተ ክርስቲያኒቱ በከፋ ኹኔታ እየታወከችና እየተመዘበረች እንደምትገኝ ገልጸዋል፡፡
ፓትርያርኩ ውሳኔ እንዲቆዩ ማዘዛቸውን ተከትሎ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ውሳኔውን ለማስፈጸም ባለመቻሉ፣ ‹‹አማሳኝ አለቆች›› በሚል የተገለጹ የአድባራት ኃላፊዎች እንቅስቃሴያቸውን ለሚቃወሙ አገልጋዮች ስም እያወጡ፣ በገንዘብ ኃይል ከሥራቸው እንዲፈናቀሉና ያለፈቃዳቸው እንዲዘዋወሩ፤ የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች የድርሻቸውን እንዳይወጡ ከመዋቅር ውጭ ባደራጇቸው አካላት እየከፋፈሉና በፖሊቲከኛነት እየወነጀሉ ከአገልግሎት በማገድ ለእስርና እንግልት እየዳረጉ እንደኾነ በውይይቱ ላይ ተጠቅሷል፡፡
“የአማሳኝ አለቆች” ቡድኑ ‹‹ፓትርያርኩ በእጃችን ናቸው፤ የምንፈልገውን እናስፈጽማለን›› በሚል ዕድገትና ሹመት ለማሰጠት ወደኋላ እንደማይልና ድጋፍ በማሰባሰብ ላይ እንደሆነ አስተያየት ሰጪዎቹ ተናግረዋል፡፡ ቡድኑ በዋናነት ‹‹ሊያሠሩን አልቻሉም›› ያላቸውን የወቅቱን የሀገረ ስብከቱን ረዳት ሊቀ ጳጳስ የመወንጀል እንቅስቃሴ እያደረገ መሆኑን የጠቆሙት ተሳታፊዎቹ፤ ከመጪው የግንቦት ቅ/ሲኖዶስ ስብሰባ በፊት ከሓላፊነታቸው የሚነሡበትን ተቃውሞ የማጠናከር ዓላማ እንዳለውም ገልጸዋል፡፡  ቅ/ሲኖዶሱ በ‹‹አማሳኝ አለቆች›› ላይ ያሳለፈው ውሳኔ አለመፈጸሙ፣ ‹‹እነ እገሌ ምን ኾኑ? እኛስ ምን እንኾናለን?›› በሚል እየተዘበተበትና ‹‹በእግሩ የመጣ በመኪና ይሔዳል›› በሚልም ለከፋ ሙስና በር እንደከፈተ ተናግረዋል፡፡
ለሀገረ ስብከቱ የታቀደው የአደረጃጀትና የአሠራር ለውጥ በ‹‹አማሳኝ አለቆችና ቲፎዞዎቻቸው የውኃ ሽታ›› መኾኑን የገለጹት ተሳታፊዎቹ፤ ያለተጠያቂነት የሚፈጽሙት ቤተ ክርስቲያኒቱን የመለያየትና የመመዝበር ድርጊት የሰንበት ት/ቤት ወጣቶችን የአገልግሎት ተነሣሽነት እየጎዳ ከመኾኑም በላይ ‹‹የቅ/ሲኖዶሱ ልዕልና ጠፍቶ ቤተ ክርስቲያኒቱ በግለሰቦቹ እጅ ላይ ያለች አስመስሏታል›› ብለዋል፡፡ ‹‹ወዳልተፈለገ ነገርስ አያመራም ወይ?›› ሲሉም ውይይቱን ለሚመሩት በሀገረ ስብከቱ የፓትርያርኩ ረዳት ሊቀ ጳጳስና የአንድነቱ ሊቀ መንበር ጥያቄአቸውን አቅርበዋል፡፡
‹‹በሃይማኖት ሕጸጽ የሚጠረጠሩ ሰባክያን ተመድበውብናል›› ያሉ የመካነ ሰማዕት ቅዱስ ቂርቆስና የደብረ ናዝሬት ቅዱስ ዮሴፍ አድባራት ሰንበት ት/ቤቶች ተወካዮች በበኩላቸው፤ በቤተ ክርስቲያኒቱ ዐውደ ምሕረት በዝማሬና በስብከተ ወንጌል የመሳተፍ መብታቸው አስተምህሮዋን በሚፃረሩ የስብከተ ወንጌል ሓላፊዎችና ሕገ ወጥ ሰባክያን ስምሪት መታወኩን በምሬት ገልጸዋል፡፡ በሰሚት መድኃኔዓለም በግለሰቦች ፍላጎት የባለጸጋ ልጆች ብቻ ተሰብስበው የሚማሩበት ሁኔታ መፈጠሩን የጠቆሙት ተሳታፊዎቹ፤ ቤተ ክርስቲያኒቱን ‹‹የሀብታምና የድኃ›› ብሎ የመክፈል አዝማሚያ መስተዋሉን አስረድተዋል፡፡ የሰንበት ት/ቤቱ አመራር ይህ ዐይነቱ አካሔድ እንዲታገድ በጠየቀው መሠረት በሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት የተሰጠው መመሪያ በደብሩ አስተዳደር ተቀባይነት ባለማግኘቱ የአመራር አባላቱ እስከመታሰር መድረሳቸው በእንባ ተገልጧል፡፡
በውይይት መርሐ ግብሩ ላይ ተገኝተው ትምህርትና ቃለ ምዕዳን የሰጡት በሀገረ ስብከቱ የፓትርያርኩ ረዳት ሊቀ ጳጳስና የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ የበላይ ሓላፊ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ፣ ጉበኞች ፈጽሞ እንደማይተኙ ጠቁመው እያደረጉ ስላሉት እንቅስቃሴም መረጃው እንዳላቸው ተናግረዋል፡፡ እንቅስቃሴአቸው የተደራጀና በከፍተኛ ገንዘብ የተደገፈ እንደኾነ ሊቀ ጳጳሱ ገልጸው፣ ‹‹ጥቅማቸው እንዳይዘጋ በሰው ሕይወትም ከመምጣት ወደኋላ አይሉም›› ብለዋል፡፡ ይኹንና ቤተ ክርስቲያኒቱ ከፓትርያርኩ አንሥቶ ሙስናን ለመዋጋት ወደ ኋላ እንደማትል አረጋግጠዋል፡፡
‹‹መሾምና መሻር የእናንተ ድርሻ ባይኾንም ስለ ቤተ ክርስቲያን ግን አይመለከታችኹም አይባልም፤ እንዲያውም የሰንበት ት/ቤት ተማሪዎች የአስተዳደሩ ሐሳብ መጋቢዎች ናቸው፤›› ያሉት ሊቀ ጳጳሱ፤ ወጣቱ በትጋትና በብልሃት አጥቢያ ቤተ ክርስቲያኑን አጥር ኾኖ ሊጠብቅ ይገባል ብለዋል፡፡ ከየአጥቢያው በተነሡት ችግሮች ዙሪያም የሚገባውን ያኽል አልሠራም ካሉት ከጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ አንሥቶ ኹሉም ራሱን እንዲፈትሽና የድርሻውን እንዲወጣ አሳስበዋል፡፡ ውይይቱ ቀጣይነት እንደሚኖረው አቡነ ቀሌምንጦስ አስታውቀው፤ ‹‹አማሳኞች›› የወጣቱን ጥያቄ ከመንገድ በማውጣት ከግንቦቱ ምርጫ ጋር በተያያዘ ትንኮሳ ከመፍጠር ስለማይመለሱ እንደ ዜጋም እንደ ሃይማኖተኛም በትዕግሥትና በሰላማዊ መንገድ መዋቅርን ጠብቆ በመንቀሳቀስ ማሳለፍ እንደሚያስፈልግ መክረዋል፡፡
ቁጥራቸው ከ780 በላይ የኾኑ የሰባቱም ክፍላተ ከተማ ቤተ ክህነት ጽ/ቤቶች ሰንበት ት/ቤት ክፍሎች ሓላፊዎችና የ160 አጥቢያ አብያተ ክርስቲያን ሰንበት ት/ቤቶች አመራሮች በተገኙበት በዚኹ የውይይት መርሐ ግብር÷ ሰንበት ተማሪው በሃይማኖት ሕጸጽ በሚጠረጠሩና አፍራሽ ተልእኮ ባላቸው ሰባክያን ዙሪያ ተጨባጭ ማስረጃዎችን በቅዱስ ሲኖዶስ ለተቋቋመው አጣሪ አካል እንዲያቀርብ ጥሪ ቀርቧል፡፡
በተያያዘ ዜና÷ የውይይት መርሐ ግብሩን እንደ ስጋት ከሚመለከቱ አካላት እንደኾነ የተጠረጠረ ዛቻና ማስፈራሪያ በሀገረ ስብከቱ የሰንበት ት/ቤት አንድነት አመራሮች ላይ እየተፈጸመ እንዳለ ተጠቁሟል፡፡ በዕለቱ ውይይቱን ሲመሩ በነበሩት የአዲስ አበባ ሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ሊቀ መንበር ቀሲስ ኄኖክ ዐሥራት ዛቻና ማስፈራሪያው ከደረሰባቸው አመራሮች አንዱ እንደሆኑ የጠቆሙት ምንጮች፤ ‹‹መንግሥት ከኛ ጋር ነው፤ አንተን ለማጥፋት ጥቂት ገንዘብ ይበቃናል›› የሚሉ ግለሰቦች ሳያቋርጡ በስልክ ዛቻና ማስፈራሪያ እንዳደረሱባቸው ገልጸዋል፡፡

በአደረባት ድንገተኛ ሕመም ሕይወቷ ያለፈው  ደራሲና ጋዜጠኛ እቱ ገረመው የቀብር ሥነ ሥርዓት የካቲት 7 ቀን 2007 ዓ.ም በትውልድ ሀገሯ አርባ ምንጭ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን የክልሉ መንግሥት ባለሥልጣናት፣ በርካታ ወዳጅ ዘመዶቿና የከተማው ነዋሪዎች በተገኙበት ተፈጽሟል፡፡
የአንዲት ሴት ልጅ እናት የነበረችው ጋዜጠኛ እቱ ገረመው፥ በአዲስ አድማስ፣ በኔሽንና በኢትዮ- ቻናል ጋዜጦች፣ በእፎይታና በቢዝነስ ታይምስ መጽሔቶች፤ በኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት እና በዛሚ ሬዲዮ ላይ በጋዜጠኝነት ሞያዋ ሠርታለች፡፡
ጋዜጠኛዋ ባለፉት ሦስት ዓመታት “ማሺሪያ” (በወላይትኛ ሴትዮዋ ማለት ነው) የተሰኘና በሴቶች ላይ ትኩረት አድርጐ የሚታተም መጽሔት ስታዘጋጅ የቆየች ሲሆን፤ በዚህ መጽሔት በአርባ ምንጭና በአካባቢው የሚታዩ የሙስናና ብልሹ አሠራሮችን በማጋለጥ፣ የክልሉ ሴቶችን ጭቆና በመታገልና መብታቸው እንዲከበር የበኩሏን ጥረት አበርክታለች፡፡ ጋዜጠኛዋ እቱ  “የጭን መነባንብ” የተሰኘ ልብወለድ መጽሐፍም ለኅትመት አብቅታለች፡፡
የአዲስ አድማስ ጋዜጣ ዝግጅት ክፍል፥ በእቱ ገረመው ድንገተኛ ህልፈት የተሰማንን ጥልቅ ሐዘን እየገለፅን፤ ለልጇ፣ ለቤተሰቦቿና ለወዳጅ ዘመዶችዋ መጽናናትን እንዲሰጣቸው እንመኛለን፡፡

አንድ ስዕል 300 ሚሊዮን ዶላር ተሽጧል
የኳታሩ ሚ/ር ከ1 ቢሊዮን ዶላር በላይ የመንግስት በጀት ለስዕል ግዢ አውጥተዋል

በፈረንሳዊው ሰዓሊ ፖል ጎጊን እ.ኤ.አ በ1892 የተሳለውና “ናፊያ ፋ ልፖኢፖ” የሚል ርዕስ ያለው ስዕል በአለማችን የስዕል ስራዎች ሽያጭ ታሪክ ክብረ ወሰን ባሰመዘገበ መልኩ በ300 ሚሊዮን ዶላር መሸጡን ኒውዮርክ ታይምስ ዘገበ፡፡
የሁለት ልጃገረዶችን ምስል የሚያሳየው ይህ ስዕል፣ ሩዶልፍ ስቴችሊን በተባሉት ስዊዘርላንዳዊ የስነጥበብ ስራዎች ሰብሳቢ ግለሰብ ባለቤትነት ኩንስት በተባለ ሙዚየም ውስጥ ለረጅም አመታት እንደቆየና ሰሞኑን በኳታር ለሚገኝ አንድ ሙዚየም እንደተሸጠ ዘገባው ጠቅሷል፡፡
በስቴችሊንና በኩንስት ሙዚየም መካከል በቅርቡ አለመግባባት መፈጠሩን ተከትሎ፣ ግለሰቡ ስዕሉን ለኳታሩ ሙዚየም ለመሸጥ መወሰናቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ ኳታር ከዚህ ቀደምም በስዕል ሽያጭ ታሪክ ከፍተኛው ገንዘብ የተከፈለበትንና በሰዓሊ ፖል ሴዛኔ የተሳለውን የስዕል ስራ በ158 ሚሊዮን ፓውንድ መግዛቷን አክሎ ገልጧል፡፡
ኳታር ለስነጥበብ ስራዎች ግዢ ከፍተኛ ገንዘብ እንደምታወጣና፣ ባለፈው አመት ከዚህ አለም በሞት የተለዩት የቀድሞው የኳታር የባህል ሚኒስትር ሼክ ሳኡድ ቢን ሞሃመድ አል ጣኒ፣ ከ1 ቢሊዮን ዶላር በላይ ገንዘብ ከመንግስት ካዝና ወጪ በማድረግ ለስነጥበብ ስራዎች ግዢ ማዋላቸውንም አስታውሷል፡፡


“ምርጫውን ያራዘሙት ሽንፈት ስላሰጋቸው ነው” ተቃዋሚዎች
*የአሜሪካና እንግሊዝ መንግስታት ምርጫው መራዘሙን ተቃውመዋል


በዛሬው ዕለት ይከናወናል ተብሎ ቀን የተቆረጠለትን የናይጀሪያ ፕሬዚዳንታዊና የፓርላማ ምርጫ ለስድስት ሳምንታት አራዝመዋል በሚል በአለማቀፍ ደረጃ ትችት እየተሰነዘረባቸው ያሉት የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ጉድላክ ጆናታን፣ ምርጫውን አላራዘምኩም ሲሉ አስተባበሉ፡፡
ቢቢሲ እንደዘገበው፤ ፕሬዚዳንቱ ምርጫውን ለማራዘም በተላለፈው ውሳኔ ውስጥ እጃቸው እንደሌለበትና ውሳኔውን ያስተላለፉት አካላት በጉዳዩ ዙሪያ እንዳላማከሯቸው አስታውቀዋል፡፡
የአገሪቱ የምርጫ አስፈጻሚ ባለስልጣናት፣ ቦኮ ሃራም የተባለው ጽንፈኛ ቡድን ምርጫውን የሚያስተጓጉል ድርጊት ሊፈጽም ይችላል በሚል ከጸጥታ ሃይሎች የተገለጸላቸውን ስጋት መነሻ በማድረግ ምርጫው ለስድስት ሳምንታት እንዲራዘም መወሰናቸውን ፕሬዚዳንቱ ጠቁመዋል።
የናይጀሪያ ምርጫ ኮሚሽን ሃላፊ አታሂሩ ጃጋ፣ ምርጫው ሊራዘም የቻለው መራጮችን ከቦኮ ሃራም ከሚሰነዘሩ የሽብር ጥቃቶ መከላከል የሚችል በቂ የጸጥታ ሃይል ባለመኖሩ ነው ቢሉም፣ በምርጫው ለመወዳደር የተዘጋጁ የአገሪቱ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች በበኩላቸው፤ፕሬዚዳንት ጉድላክ ጆናታን ምርጫውን ያራዘሙት እንዳይሸነፉና ስልጣናቸውን እንዳይነጠቁ በመስጋት ነው ሲሉ ተናግረዋል፡፡
ፕሬዚዳንት ጉድላክ ጆናታን እና ፓርቲያቸው ፒዩፕልስ ዲሞክራቲክ ፓርቲ፣ ከቀድሞው የአገሪቱ የጦር መሪ ሙሃማዱ ቡሃሪ እና ኦል ፕሮግሬሲቭስ ኮንግረስ ከተሰኘው ተፎካካሪ ፓርቲ ከፍተኛ ፉክክር ይጠብቃቸዋል ተብሎ እንደሚጠበቅ የገለጸው ዘገባው፤ቡሃሪ በስልጣን ላይ ያለው የጆናታን መንግስት የቦኮ ሃራምን የጥፋት እንቅስቃሴ ለመግታት አቅምም ሆነ ፈቃደኝነት ይጎድለዋል ሲሉ መተቸታቸውንና እሳቸው ስልጣን ላይ ከወጡ ቦኮ ሃራምን በወራት ጊዜ ውስጥ እንደሚያጠፉ ቃል መግባታቸውን ጠቁሟል፡፡
የናይጀሪያ መንግስት ምርጫው መራዘሙን ማስታወቁን ተከትሎ፣ ውሳኔው በአለማቀፍ ደረጃ እየተተቸ እንደሚገኝ የዘገበው ዘ ኢንዲፔንደንት በበኩሉ፤የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጆን ኬሪ በአገሪቱ ያሉ የጸጥታ ስጋቶች ምርጫን ለማራዘም በቂ ምክንያት ሊሆኑ አይችሉም ማለታቸውን ጠቁሟል፡፡
የእንግሊዝ የውጭ ጉዳይ ጸሃፊ ፊሊፕ ሃሞንድ በበኩላቸው፤ ናይጀሪያ ሽብርተኝነትን ለመዋጋት የምታደርገውን ጥረት የምንደግፍ ቢሆንም፣ በአገሪቱ ያለው የጸጥታ ችግር ናይጀሪያውያን ዲሞክራሲያዊ መብቶቻቸውን እንዳይጠቀሙ ለማገድ ምክንያት ሊሆን አይገባም በማለት ምርጫው መራዘሙን ተችተዋል፡፡

ግብጽ ከሁለት አመታት በፊት በሚናያ ግዛት በሚገኝ የፖሊስ ማዘዣ ጣቢያ ላይ ጥቃት ፈጽመዋል በሚል ባለፈው ሰኔ ወር የሞት ፍርድ ከጣለችባቸው 183 የሙስሊም ብራዘር ሁድ አባላት መካከል፣ የሰላሳ ስድስቱን የሞት ቅጣት ማንሳቷንና የፍርድ ሂደቱ እንደገና እንዲታይ ባለፈው ረዕቡ መወሰኑን ቢቢሲ ዘገበ፡፡ ፍርድ ቤቱ ሞሃመድ ባዲ የተባሉትን መንፈሳዊ መሪ ጨምሮ በ36 ተከሳሾች ላይ ጥሎት የነበረውን የሞት ቅጣት ለማንሳትና ፍርዱ እንደገና እንዲታይ የወሰነበትን ምክንያት በግልጽ አለማስታወቁን ዘገባው አመልክቷል፡፡
የተባበሩት መንግስታት ድርጅትን ጨምሮ በርካታ አለማቀፍ ተቋማት በ183 የሙስሊም ብራዘር ሁድ ደጋፊዎች ላይ ፍርድ ቤቱ የጣለውን የሞት ቅጣት በአጽንኦት ሲተቹት እንደነበርም አስታውሷል፡፡
የሞት ፍርዱ ከተጣለባቸው 183 ግብጻውያን መካከል 147 የሚሆኑት የፍርድ ሂደታቸው በሌሉበት ሲታይ መቆየቱንም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡

የጥናት ጽሁፎችን አደባባይ ለማውጣት ትኩረት ተሰጥቷል

 የኢትዮጵያ ደራስያን ማህበር ከተቋቋመ ከ30 ዓመት በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ በነሐሴ ወር 1982 ዓ.ም ለንባብ የበቃችው “ብሌን” የሥነፅሁፍ መፅሔት ፤ ከ15 ዓመት የህትመት መቋረጥ በኋላ ሰሞኑን ታትማ ዳግም ለአንባብያን ቀረበች፡፡
የደራስያን ማህበር 50ኛ ዓመት ክብረበዓልን ምክንያት በማድረግ በሰኔ 2003 ዓ.ም የ“ብሌን” መፅሔት ልዩ ዕትም (ቁ.7) ለንባብ መብቃቱ ይታወሳል፡፡ ይሁን እንጂ መደበኛው የመፅሄቷ ዕትም ለዓመታት ሳይታተም ቀርቷል፡፡ ከማህበሩ የ30 ዓመት ጉዞ በኋላ መጽሄቷ ብቅ ስትል ለኢትዮጵያ ሥነፅሁፍ ዕድገት እንደ አንድ ብስራት ቆጥረን ነበር ያሉት የአሁኗ የ“ብሌን” ዕትም አርታኢዎች፤ መፅሔቷ “ቅፅ 1፣ ቁጥር 1” መባሏ ቢያንስ ሁለት ወይም ከዚያ በላይ ዕትም በየዓመቱ ይታተማል የሚል ተስፋን የሚያመላክት ቢሆንም በማህበሩ የ24 ዓመት ታሪክ ውስጥ ከ7 የበለጠ የ“ብሌን” እትም ሊታተም አልቻለም ብለዋል፡፡
ለመፅሄቷ መቋረጥ ተጠያቂው ሁላችንም ነን በማለትም አርታኢዎቹ ኋላፊነቱን ለሁሉም አከፋፍለዋል፡፡ “… በመጀመሪያ ደረጃ የኢደማን አመራር ይዘው የነበሩትን ሁሉ የሚመለከት ቢሆንም የችግሩ አድማስ ግን ሁላችንንም የሚያካትትና ሁላችንንም በተለያየ የኃላፊነት ደረጃ የሚያስጠይቅ ነው፡፡” ሲሉም አስረድተዋል፡፡
አዲሱ የደራስያን ማህበር ፕሬዚዳንት ዶ/ር ሙሴ ያዕቆብ መፅሄቷ ላይ ባሰፈሩት መልዕክት፤ የጠንካራ ተሳታፊዎች እጦት፣ የህትመት በጀትና የደጋፊ ወገን እጥረት መፅሄቷ ወቅቷን ጠብቃ እንዳትወጣ ዋነኛ ተግዳሮቶቿ እንደነበሩ ጠቁመዋል፡፡
በአሁኑ የመፅሔቷ ዕትም ትኩረት የተደረገው በምርምር አምባው ተወስነው የነበሩ የጥናት ውጤቶችን ወደ “ብሌን” መድረክ በማምጣት አደባባይ ማውጣት ላይ ሲሆን በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ከተደረጉ ጥናቶች ውስጥ ሶስቱ (የስንቅነሽ አጣለ፣ የቴዎድሮስ ገብሬና የአራጌ ይመር) ተመርጠው እንደቀረቡ ተገልጿል፡፡
“የዚህ ዓይነቱ ሙከራ ወደፊት ተጠናክሮ እንዲቀጥልና ብሌን በምርምርና በፈጠራ፣ በሂስና በንድፈ ሃሳብ መካከል ድልድይ ሆና እንድታገለግል ምኞታችን ነው” ብለዋል፤ አርታኢዎቹ፡፡
በ108 ገፆች የተቀነበበችው “ብሌን” መፅሄት፤ ከጥናትና ምርምር ፅሁፎች በተጨማሪ አጭር ልቦለድና ግጥሞችን ያካተተች ሲሆን በ50 ብር ለገበያ ቀርባለች፡፡ መፅሄቷ በዓመት ሁለት ጊዜ እየታተመች ለአንባቢያን እንደምትደርስም ለማወቅ ተችሏል፡፡

Saturday, 14 February 2015 15:22

ጋሽ ስብሃት - የዛሬ 29 ዓመት

ታዬ፡-     አንዳንዶቹ የበዓሉ ግርማ ገጸ ባሕርያት ጋብቻን በሚመለከት … በተለይ በኪነት ዓለም ውስጥ ስሜት ያላቸውና የሚሳተፉቱ … ጋብቻን በጥርጣሬ ዓይን ነው የሚያዩት።  ለምን? ጋብቻን ከኪነት ስራቸው ጋር እንደሚፎካከር፣ እና እንደልቡ ለመሆን እንደማይችል ደራሲው… ለምን? ላገባት ሴት ጊዜውን መስጠት አለበትና ያ ደግሞ የፈጠራ ጊዜውን እንደሚሻማ አድርገው የሚናገሩ፣ የሚሰማቸው ገጸ ባህሪያት አሉ፡፡ እንዲህ ዓይነት ስሜት አንተ የለህም?
ስብሐት፡- እኔ እንደሱ አይሰማኝም፡፡ ግን ይገባኛል የነሱ ስሜት፤ በደንብ ይገባኛል … ምክንያቱም እውነት ነው፡፡ ሚስት የኪነትን ጊዜ፣ ሀሳብ፣ “ኢነርጂ”፣ ሁሉን ትሻማለች ሳይሆን ትጋራለች ብንል ነው ጥሩ፡፡
ታዬ፡-     ለምን?
ስብሐት፡- ሽምያ መነጣጠቅ ነው፡፡ መጋራት ግን የሷ ተራ ሲሆን ለሷ ጊዜህን ትሰጣለህ፡፡ የኪነት ተራ ሲሆን ለኪነት ጊዜህን ትሰጣለህ፡፡ እሷም ከተዋደድን ይሄ ይገባታል፡፡
ታዬ፡-     ስለዚህ የፈጠራ ስራውን ጋብቻ ሊያስተጓጉልበት አይችልማ?
ስብሐት፡- የፍቅር ጋብቻ ከሆነ አይችልም ነው የምለው፡፡ እንዲያውም ሴትዬዋ ብዙ ልታግዘው ትችላለች፤ ብዙ ልታበረታታው ትችላለች፡፤ ጉልበት ልትሆነው ትችላለች … ድክመት ሳይሆን፡፡
ታዬ፡-     ከበዓሉ ጋር ስለ ሥነ ጽሑፍ በምትወያዩበት ጊዜ ብዙ ልዩነት የታየበት ነጥብ አለ እስካሁን ድረስ? ለምሳሌ በዚህ ነገር ላይ እኔ አልስማማም የተባባላችሁበት አለ… ስለ ሥነ ጽሑፍ ባላችሁ አመላከከት?
ስብሀት፡- አዎ፡፡
ታዬ፡-     ምን ምንን በሚመስል ነገር?
ስብሐት፡- ቅድም ያልኩህ ነው … መነሻው ጥያቄ ሌላ ሆኖ ነው እንጂ፡፡ እሱ መጻፍ ስለምትችል ሳንሱር እንዲያልፍ እያሰብክ መጻፍ አለብህ … እና ማሳተም አለብህ፤ ልትነበብ ካልሆነ ለምን ትለፋለህ ያለኝ፡፡ እኔ ደግሞ ለሳንሱር ብዬ ከጻፍኩማ ምኑን ጻፍኩት? ለራሴ … እና በደንብ የሚሰማኝን ለመጻፍ፣ ለማውጣት ካልሆነ ምኑን ጻፍኩት ነው እንግዲህ ልዩነታችን፡፡
ታዬ፡-     ስለዚህ አንተ በምትደርስበት ጊዜ መጀመሪያ የምታተኩረው አድማጭህ ላይ ሳይሆን ራስህ …?
ስብሐት፡- አድማጩ ላይ ነው! አንባቢዬ ላይ ነው! ግን አንባቢዬ ሳንሱር አይደለም፤ ሰው ነው፡፡ እንጂ እንዲያውም አንባቢዬ ላይ ነው በጣም የማተኩረው፡፡ ተግባባን?
ታዬ፡-     አዎን፤ ገባኝ፡፡ ባንተ አስተያየት ደራሲው በሚጽፍበት ጊዜ ይሄ ሳንሱር ያልፋል፤ ይሄ ሳንሱር አያልፍም የሚለው ነጥብ አጻጻፉን ሊወስነው፣ ወይ ሊለውጠው አይገባም ነው?
ስብሐት፡- ልክ! እኔ ስጽፍ ይሄ ለአንባቢዬ ግልጽ አይሆንም፤ ይሄ ግልጽ ይሆናል … ስለዚህ እንደዚህ እያልኩ ነው፡፡ አንባቢ ነው ሀሳቤ ውስጥ ያለው፤ ሳንሱር የለም፡፡
ታዬ፡-     ስለ አንባቢ ካነሳን አልቀረ ምን ዓይነት አንባቢዎች ናቸው በአእምሮህ ውስጥ የሚጉላሉት… በምትደርስበት ጊዜ አንድን የሆነ ድርሰት፣ ልቦለድ? ለምሳሌ ወይ በመደብ፣ ወይ በትምህርት፣ ወይ በጾታ እንደዚህ ታስባቸዋለህ አድማጮችህን? … በዚህ ዓይነት አታያቸውም?
ስብሐት፡- እኔ የማስበው አንባቢዬ ከኔ እኩል ሊያስብ ይችላል፤ ከኔ እኩል ሊሰማው ይችላል፡፡ ስለዚህ እኔ ቃላቱን፣ አባባሉን አጥቼበት ካልሆነ በስተቀር አንባቢዬ አይስተኝም፡፡ ምክንያቱም እኔ ውስጥ ያለ ሁሉ አንባቢዬ ውስጥም አለ፡፡ ያው የሰው ነገር ስለሆነ የምጽፈው … ስለ ምኞት፣. ስለ ኩም ማለት፣ ስለ መውደድ፣ ስለ መጥላት፣ ስለ ተስፋ፣ እንደዚህ፣ እንደዚህ ስለሆነ ምንም ለአንባቢ የማይገባ ነገር አይኖርም፡፡ በቃ እኩያ ነን እኔና አንባቢዬ ማለት ነው፡፡ ስለዚህም ነው ምናልባት እኔ ላስተምር አይደለም የምጽፈው፤ ተረት ልነግር ነው እንጂ፡፡
ታዬ፡-     በዚህስ ነጥብ ላይ አትለያዩም? ለምሳሌ እሱ የስነ ጽሑፍ ሚና ህብረተሰብን ማስተማር …
ስብሐት፡- ነው ይላል እሱ፡፡
ታዬ፡-     ይላል? በዚህ ነጥብ ላይ ግን አትስማሙም?
ስብሐት፡- አንስማማም፡፡
ታዬ፡-     ለማስታረቅም አልሞከራችሁም? ያው እንደተለያየ ነው ያለው ሀሳባችሁ?
ስብሐት፡ አዎ! እርቅ ምን ያደርጋል? በዚህ በኩል እኮ ሲለያዩ ነው ጥሩ፡፡ እሱም የራሱን መንገድ ይይዛል፤ እኔም የራሴን፡፡ ሁለታችንም በየበኩላችን አስተዋጽዖ እናደርጋለን ማለት ነው፡፡
ታዬ፡- እንደዚያም ሆኖ ግን፣ ይህም የሀሳብ ልዩነት ኖሮ ትግባባላችሁ?
ስብሐት፡- በጣም!
(ከላይ የቀረበው በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በትርፍ ጊዜ የሥነፅሁፍ ተባባሪ ፕሮፌሰርና የኢትዮጵያ ደራስያን ማህበር የሥነፅሁፍ መፅሔት “ብሌን” ዋና አዘጋጅ ታዬ አሰፋ፤ የዛሬ 29 ዓመት የለንደን ዩኒቨርሲቲ ተማሪ ሳሉ ስለአማርኛ ልቦለዶች የትረካ ስልት ለሚያደርጉት ጥናት ከደራሲ ስብሃት ገ/እግዚአብሔር ጋር ያደረጉት ቃለምልልስ ሲሆን ሰሞኑን ከወጣው “ብሌን” መፅሔት የቀነጨበ ነው።)
ቅጽ 8፣ ቁ.፤  (ታህሣሥ 2007)

የህንዱ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ ደጋፊዎቻቸው ገንዘብ አዋጥተው በስማቸው በመሰረቱት ቤተ መቅደስ ውስጥ ባቆሙላቸው ጣኦት አማካይነት እየተመለኩ እንደሆነ የዘገበው ሮይተርስ፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በበኩላቸው የደጋፊዎቻቸው ድርጊት እንዳስደነገጣቸውና አፈንጋጭ እንደሆነ መናገራቸውን አስታወቀ፡፡
በመቶዎች የሚቆጠሩት የጠቅላይ ሚኒስትሩ ደጋፊዎች፣ ራጅኮት በተባለችው የህንድ ምዕራባዊ ከተማ በሰሩት ቤተ መቅደስ ውስጥ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ቁጭ ብለው የሚያሳይ ጣኦት አቁመው እያመለኩ እንደሚገኙ ተዘግቧል፡፡
“ነገሩ በጣም አስደንጋጭ ነው፡፡ ግለሰቦቹ የሰሩት ስራ ለዘመናት ከዘለቀው ታላቁ የህንድ ባህል ጋርም የሚጋጭ ነው፡፡ ባህላችን እንዲህ አይነት ቤተ መቅደሶችን እንድንሰራ አላስተማረንም” በማለት ድርጊቱን አውግዘውታል፤ጠቅላይ ሚኒስትሩ፡፡
በጠቅላይ ሚኒስትሩ ምላሽ የተከፉት የተወሰኑ የቤተ መቅደሱ ፕሮጀክት አስፈጻሚ አባላት በበኩላቸው፣ የጠቅላይ ሚኒስትሩን ጣኦት በአንድ የሂንዱ ፈጣሪ ሃውልት ለመተካት አቅደዋል፡፡
“ጠቅላይ ሚኒስትራችንን እንወዳቸዋለን፤ እናመልካቸዋለን፡፡ ምክንያቱም እሳቸው እስከዛሬ ከነበሩት መሪዎቻችን ሁሉ የተለዩ ትልቅ ሰው ናቸው!” ብለዋል፤ለቤተ መቅደሱ ግንባታ የዋለውን መሬት በነጻ ያበረከቱት ፓሬሽ ራዋል የተባሉ ህንዳዊ ባለጠጋ፡፡

Saturday, 14 February 2015 15:01

የኔ ወፍ

ቀኑ የኔን ሃሳብ
ውስጤን ከገለፀ
አንቺነትሽ በኔ
ገብቶ እንደሰረፀ
ሃሳቤን ልንገርሽ
የልቤን ስጦታ
አበባ ያንስሻል
‹ወይን› አይሰጠኝ ደስታ
ተመልከቺ ፍቅሩን
ያንቺን ልዩ ቦታ
ወስደሽ ከጣቴ ላይ
የደሜን ጠብታ፡፡

ትዝታ
ድምፅሽ ሲቀያየር
ሆነሽ አጠገቤ
ፍስስ የሚልብኝ
ቆራጥ ያልኩት ልቤ
ያልሆንኩትን ሆኖ
እኔነ ጠፍቶ
እያሰብኩኝ አንቺን
መናፈቄ በዝቶ
ሲቀያየርብኝ
መውደድና መጥላት
መከልከል መለገስ
መጨከን መራራት
ሲለዋወጥብኝ
ፈሪነት ደግነት
ታዝቤዋለሁኝ
ሲሰማኝ ውብ ደስታ
ትርጉሙ ፍቅርሽ ነው
ሰናይ ነው ትዝታ፡፡
(ከእስክንድር ለማ ክብረት
“የኔ ወፍ” የግጥም መድበል የተወሰደ፤
የካቲት 2007 ዓ.ም)

የዳንስ ውድድር፣ ኮሜዲ፣ የፍቅር ዜማዎች፣ እራትና ወይን ጠጅ
የሆቴሎቹ የመዝናኛ ክፍያ ከ600 ብር - 5ሺ ብር ይደርሳል

   በዛሬው ዕለት በመላው ዓለም የሚከበረውን የፍቅረኞች ቀን (Valentine’s day) ምክንያት በማድረግ አዲስ አበባን ጨምሮ በሃዋሳ ቢሾፍቱና ላንጋኖ የሚገኙ ትልልቅ ሆቴሎች ለፍቅረኞች ምሽት ሽርጉድ እያሉ ሲሆን ለለያዩ መዝናኛዎች ከ600 ብር እስከ 5ሺ ብር ይጠይቃሉ፡፡ የቀይ አልባሳት ገበያ መድራቱንም ነጋዴዎች ገልፀዋል፡፡
አትሌት ኃይሌ ገ/ሥላሴ ጐዳና ላይ የሚገኘው ንግስተ ሳባ ሆቴል ዛሬ ማታ ልዩ የፍቅረኞች ምሽት ያዘጋጀ ሲሆን የተለያዩ የፍቅር ዜማዎችና ግጥሞች ይቀርቡበታል ተብሏል፡፡ አርቲስት አስቴር በዳኔ የንግስተ ሳባን የፍቅር ታሪክ በአጭር ድራማና መነባንብ መልክ ለታዳሚዎች ታቀርባለች፡፡ ንግስተ ሳባ ሆቴል ከአብርሃም ግዛው ኢንተርቴይንመንትና የፕሬስ ስራዎች ድርጅት ጋር በመተባበር ባዘጋጁት በዚህ ልዩ የፍቅር ምሽት፤ በጥንዶች መካከል የሳልሳ፣ የትዊስትና ዋልዝ ዳንሶች ውድድር የሚካሄድ ሲሆን ለሶስት አሸናፊ ጥንዶች ለእያንዳንዳቸው አምስት ሺ ብር የሚያወጣ የእራት፣ የአልጋና የቁርስ ግብዣ ይደረግላቸዋል፤ ብሏል - ጋዜጠኛና ፕሮሞተር አብርሃም ግዛው በምሽቱ ዝግጅት የኮሜዲ ስራዎች የሚቀርቡ ሲሆን ፕሮግራሙን ታዋቂ አርቲስቶች ይታደሙታል ተብሏል፡፡
በማማስኪችን እንዲሁ የፍቅረኞች ምሽት የተዘጋጀ ሲሆን አንጋፋው ድምፃዊ አለማየሁ እሸቴ በስራዎቹ ታዳሚውን ያዝናናል ተብሏል፡፡ መግቢያ 50 ብር እንደሆነም ታውቋል፡፡ በቫራይቲ ሬስቶራንት የፍቅረኞች ምሽት ዛሬ 11፡30 የሚጀምር ሲሆን ልዩ የእራት ፕሮግራም፣ የዲጄ ሙዚቃ፣ ለጥንዶች የሚበረከት ሰርፕራይዝ ስጦታና ሌሎች ፕሮግራሞች መዘጋጀታቸው ተጠቁሟል፡፡
ኔክሰስ ሆቴል፤ ልዩ የቡፌ እራት ከልዩ ልዩ የወይን ጠጆች ጋር ያሰናዳ ሲሆን የቫዮሊንና የፒያኖ ሙዚቃ ይቀርባል፡፡ ሰርፕራይዝ ስጦታም ይኖራል ተብሏል፡፡ የብራይት ካፌ የፍቅረኞች ምሽት ፕሮግራም የሚጀምረው ዛሬ ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ሲሆን ከ10 በላይ ድምፃዊያን በአኩስቲክ ባንድ ታጅበው ሥራዎቻቸውን ያቀርባሉ፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ሳልሳ ዳንስ፣ ስታንዳፕ ኮሜዲና ሌሎች አዝናኝ ዝግጅቶች እንደሚኖሩ ታውቋል፡፡ ታዋቂው የፊልም ተዋናይ ግሩም ኤርሚያስና እውቁ የሙዚቃ አቀናባሪ ቴዎድሮስ መኮንን (ቴዲ ማክ) በክብር እንግድነት እንደሚገኙም ተጠቁሟል፡፡ በሳሮ ማሪያ ሆቴል ደግሞ ለፍቅረኞች ልዩ የእራት ፕሮግራም፣ ሰርፕራይዝ ስጦታዎችና ሌሎች ዝግጅቶች እንዳሉ ታውቋል፡፡
ሰሜን ማዘጋጃ አካባቢ የሚገኘውና ባለፈው አመት የተከፈተው ሳሬም ኢንተርናሽናል ሆቴል፤  ልዩ የፍቅረኞች ምሽት ያዘጋጀ ሲሆን የጥንዶች መግቢያ 600 ብር ነው፡፡  ሆቴል ሲዮናትም ልዩ የፍቅረኞች ምሽት ማዘጋጀቱን ጠቁሟል፡፡ ልዩ ልዩ የፍቅር ሙዚቃዎች በዲጄ የሚቀርቡ ሲሆን፤ የጥንዶች መግቢያ 900 ብር ነው ተብሏል፡፡ ከነአንካሬ ዛሬ ምሽት ከ12 ሰዓት ጀምሮ ነው በሩን ለፍቅረኞች ክፍት የሚያደርገው፡፡ ልዩ የብፌ እራት እንዲሁም የዲጄ ሙዚቃም አሰናድቷል፡፡
ሃዋሳ የሚገኘው ኬራውድ ሆቴል፤ ፕሮግራሙን ከዋዜማው ምሽት የጀመረ ሲሆን የዲጄ ሙዚቃ፣ ልዩ የወይን ጠጅ እንዲሁም ልዩ እራት በማሰናዳት ፍቅረኞች ዕለቱን መቼም  እንዳይዘነጉት ለማድረግ እየታተረ እንደሚገኝ አስታውቋል፡፡ የአዲስ አበባው ዩጐቪያ ክለብ በበኩሉ የምሽቱን ታዳሚዎች የሚያዝናናው ከተወዳጁ ድምፃዊ አብነት አጐናፍር ጋር እንደሆነ ገልጿል፡፡ ጥንዶች ይሄ የደመቀ የፍቅረኞች ምሽት እንዳያመልጣቸው የግብዣ ጥሪውን አቅርቧል፡፡
የቢሾፍቱው ፒራሚድ ሪዞርት፤ የጥንዶች ውድድርና የፍቅር ፊልሞችን ለታዳሚዎቹ ያዘጋጀ ሲሆን ልዩ እራት ከልዩ የወይን ጠጅ ጋር ማሰናዳቱንም ጠቁሟል፡፡ ሀርመኒ ሆቴልም እንዲሁ ሚካኤል ለማን ከኤክስፕረስ ባንድ ጋር አቀናጅቶ ምሽቱን ለፍቅረኞች ውብና አስደሳች ለማድረግ መዘጋጀቱን ጠቁሟል፡፡ በተጨማሪም ልዩ እራት ከወይን ጋር፣ የኮሜዲ ምሽትና የፍቅረኞች ስጦታ አዘጋጅቻለሁ ብሏል፡፡ በሃርመኒ ሆቴል ምሽቱን ለማሳለፍ ላቀዱ ጥንዶች 1800 ብር፣ ብቻውን ለመጣ 900 ብር ይከፍላሉ፡፡
በደብረዘይት የሚገኘው አሻም አፍሪካ ሪዞርት፤ ለምሽቱ ልዩ ራት ከዋይን ጋርና የዲጄ ሙዚቃ ያዘጋጀ ሲሆን በሪዞርቱ የፍቅረኞች ምሽትን ለመታደም የሚሹ ጥንዶች 219 ዶላር ወይም 4423 ብር ያስፈልጋቸዋል፡፡ ቦሌ የሚገኘው ፍሬንድሺፕ ሆቴልም የፍቅረኞችን ቀን አይረሴ ለማድረግ ዛሬ ከምሽቱ 12 ሰዓት ጀምሮ በሩን ለእንግዶቹ ክፍት እንደሚያደርግ አስታውቋል፡፡ የተለያዩ የፍቅር ዜማዎች፣ ሰርፕራይዝ ስጦታዎችና ሌሎች…ፕሮግራሞችም እንደሚኖሩ ገልጿል፡፡
ሳሚ ካፌና ሬስቶራንትም እንዲሁ ልዩ የፍቅረኞች ምሽት ማዘጋጀቱን ገልጿል፡፡ አኩስቲክ ባንድ ምሽቱን እንደሚያደምቀውና ዳዊት ፍሬውም ክላርኔት እንደሚጫወት ተጠቁሟል፡፡
ውሃ ልማት አካባቢ የሚገኘው ባለ አምስት ኮከቡ ካፒታል ሆቴል፤  ምሽቱን ለየት ለማድረግ የቀይ ምንጣፍ ልዩ የፍቅረኞች ምሽት ያዘጋጀ ሲሆን የሰባት ጥንዶች የዋልዝ ዳንስ ውድድርና ሙዚቃ አሰናድቷል፡፡ የፍቅረኞች ምሽቱን በሆቴሉ ለመታደም የሚሹ ጥንዶች 1800 ብር፣ ለብቸኛ ታዳሚ ደግሞ 1200 ብር እንደሚያስከፍል የገለፀው ሆቴሉ፤ እዚያው ተዝንተው፣ አድረውና ቁርስ አድርገው መውጣት ለሚፈልጉ 4500 ብር ይበቃቸዋል ተብሏል፡፡
ላንጋኖ ሪዞርት የፍቅረኞች ቀን ልዩ ዝግጅቱን የጀመረው ከትላንት በስቲያ ሲሆን ዛሬ  የአዝማሪ ሙዚቃ፣ የጀልባ ሽርሽር እንዲሁም ልዩ ልዩ ምግብና ወይኖችን መዘጋጀታቸውንና ጥንዶች 3600 ብር፣ ብቸኛ 1900 ብር እንደሚከፍል ተጠቁሟል፡፡ አፍሮ ዳይት ሆቴልም ልዩ የፍቅረኞች ምሽት እንዳዘጋጀ ለማወቅ ተችሏል፡፡
የፍቅረኞች ቀንን አምነውበት ለሚያከብሩት ብዙ አማራጮች የተዘጋጁ ይመስላል፡፡ ነገር ግን ቫለንታይን የውጭ ባህል ነው በሚል የሚቃወሙትም አሉ፡፡
በ20ዎቹ መጨረሻ ዕድሜው ላይ የሚገኘው እስክንድር፤ የፍቅረኞች ቀን በአገራችን መከበሩን ከእነአካቴው አይቀበለውም፡፡ “ፍቅር በአደባባይ ልታይ ልታይ የሚባልበት ሳይሆን የልብ ትስስር ጉዳይ ነው” ያለው ወጣቱ፤ ቫለንታይን የአገራችን ባህል ስላልሆነ አልቀበለውም ባይ ነው፡፡ ቀይ መልበስና ሌሎቹም ነገሮች የእኛ አለመሆናቸውን ይናገራል፡፡ እንዲያም ሆኖ ፍቅረኛው ደሞ በቫለንታይንስ ዴይ ቀያይ ልብሶች ገዝቶ በስጦታ እንዲያበረክትላት ትፈልግ ነበር፡፡ ነገሩን ፈጽሞ ባላምንበትም ፍቅረኛዬን በጣም ስለምወዳት የማልፈልገውን አደረግሁ ብሏል፡፡  “ፍቅረኛዬ እንዳይከፋት ብዬ ቢያንስ ከውስጥ የሚውል ቀይ ፓንትና ጡት ማስያዣ ገዝቼ በስጦታ አበርክቼላታለሁ፡፡ ዋጋው ግን በጣም ውድ ነው” ሲል በመገረም ገልጿል፡፡
የ31 ዓመቱ አሳየኸኝ፤ ፍቅረኛው ለቫለንታይን እንዲገዛላት የጠየቀችው ስጦታ ዋጋው ናላውን እንዳዞረው ይናገራል፡፡ ባለፈው ዓመትም በከፍተኛ ዋጋ ምክንያት ከፍቅረኛዬ ጋር ተጋጭተን፣ ለሰባት ቀናት ተዘጋግተን ነበር ያለው አሳየኸኝ፤ “ዘንድሮም መጋጨታችን አይቀሬ ነው” ሲል የፍቅረኞች ቀን ስጋት እንደሆነበት ገልጿል፡፡
እየሰራሁ ገቢ ባገኝም እየከፈልኩ እማራለሁ፣ ወንድሜንም አስተምራለሁ የሚለው ወጣቱ፤ እንዲህ ያሉ ወጪች በእጅጉ ይጎዱኛል ብሏል፡፡ በሌላ በኩል በአሜሪካ የዘንድሮው ቫለንታይን ቀን ለስጦታ የሚወጣው አጠቃላይ 18.9 ቢ.ዶላር ይደርሳል ተብሎ እንደሚጠበቅና ይሄም በከፍተኛነት ወጪ ሪከርድ እንደሚሰብር ተገምቷል፡፡ ከዚህ ውስጥ 4.8 ቢ. ዶላር ያህሉ ለጌጣጌጥ ስጦታዎች እንደሚወጣ ሰሞኑን ይፋ የተደረጉ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ በቫለንታይን ቀን ከረሜላዎች፣ ፖስት ካርዶችና  አበቦች በስጦታነት ይበረከታሉ - የአልማዝ ቀለበትና ሌሎች ጌጣጌጦች ሳይረሱ ማለት ነው፡፡
በአዲስ አበባ ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ስማቸውን መግለፅ ያልፈለጉ አንድ የስራ ኃላፊ ስለ ቫለንታይን ቀን አስተያየታቸውን ሲናገሩ፤ “ጉዳዩ ከፍቅር ጋር የተያያዘ በመሆኑ ቀኑ ቢከበር አይከፋኝም፤ አንዳንድ ነጋዴዎች ግን አጋጣሚውን በመጠቀም ትርፍ ለማግበስበስ የሚያደርጉት ሩጫ አያስደስተኝም” ብለዋል፡፡ ሴቶችም ቢሆኑ በዚህ ቀን ፍቅረኞቻቸውን ለአላስፈላጊ ወጭ በመዳረግ ማማረር የለባቸውም ሲሉ ይመክራሉ፡፡ “ውድ ስጦታ እንዲሰጣቸው ማስገደድ ፍቅርን ከማጠንከር ይልቅ ስለሚያሻክረው ጥንቃቄ ያሻል” ብለዋል፡፡ ሁሉም አምኖበት የሚያደርገው ከሆነ፣ አበባ፣ ቀይ ልብሶች የሚሸጡና የሆቴል አገልግሎት የሚሰጡ አጋጣሚውን በጤናማ መንገድ ገቢ ቢያገኙበት ክፋት እንደሌለው ጠቁመው፤ በዓሉ ወግና ስርዓት በጠበቀ መልኩ ቢከበር መልካም እንደሆነ አክለው ገልፀዋል፡፡