Administrator

Administrator

ፈጠራው በአዲስ አበባ የትራፊክ አደጋን ይቀንሳል ተብሏል
“እነዚህ የላቀ የፈጠራ ክህሎት ከታደሉ የአሜሪካ ተማሪዎች ጥቂቶቹ ናቸው” - ባራክ ኦባማ

     የ18 አመት ዕድሜ ያለው ትውልደ ኢትዮጵያዊው ተማሪ ፈለገ ገብሩ፣ የትራፊክ አደጋን ለመቀነስ ያስችላል የተባለውን የቴክኖሎጂ ፈጠራውን ባለፈው ሳምንት በዋይት ሃውስ በተካሄደው የሳይንስ ትርዒት ላይ ማቅረቡን ኤምአይቲ ኒውስ ዘገበ፡፡
በማሳቹሴትስ የሚገኘውን ኒውተን ኖርዝ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ወክሎ በትርዒቱ ላይ የቀረበው ፈለገ፣ የትምህርት ቤት ጓደኛው ከሆነችው ካሬን ፋን የተባለች የ17 አመት ወጣት ጋር በመተባበር የፈጠረው አዲስ ቴክኖሎጂ፣ የማስጠንቀቂያ መልዕክቶችን በማስተላለፍና እንቅስቃሴውን የተሳለጠ በማድረግ በአዲስ አበባ ከተማ የሚታውየን የትራፊክ አደጋ ለመቀነስ የሚያስችል እንደሆነ ተነግሯል፡፡
በሳይንስ ትርዒቱ ላይ ተገኝተው የወጣቶችን የተለያዩ የፈጠራ ስራዎች የተመለከቱት ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ፣ በዝግጅቱ ላይ ስራዎቻቸውን ላቀረቡ ተማሪዎች ያላቸውን አድናቆት በመግለጽ፣ እነዚህ በዝግጅቱ ላይ የተሳተፉ ወጣቶች፣ የላቀ ፈጠራ ክህሎት ከታደሉ በርካታ የአሜሪካ ተማሪዎች ጥቂቶቹ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡
ዴቪድ ሁድሰን በዋይት ሃውስ ድረገጽ ላይ ፈጠራውን በተመለከተ ባሰፈሩት ጽሁፍ፣ “እነዚህ ወጣቶች በአለማችን እንደ ኢትዮጵያ በትራፊክ አደጋ በርካታ ቁጥር ያላቸው እግረኞች የሚሞቱበት አገር እንደሌለ በማጤን ነው፣ በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ተግባራዊ የሚደረግና አደጋውን ለመቀነስ የሚያስችል ፈጠራ በማመንጨት ያቀረቡት ”ብለዋል፡፡
የቴክኖሎጂ ፈጠራው አሽከርካሪዎች እግረኞችን በተመለከተ መረጃ የሚያገኙበት እንዲሁም እግረኞችም የተጨናነቁ መንገዶችን ያለ ችግር ማቋረጥ የሚችሉበትን ምቹ ሁኔታ የሚፈጥር ነው ያሉት ሁድሰን፣ ፈጠራው የጸሃይ ብርሃንን በሃይል ምንጭነት የሚጠቀምና የተሸከርካሪዎችን ፍጥነት በማስላት የተወሰነ ቦታ ላይ የሚደርሱበትን ጊዜ የሚያሰላ፣ ለእግረኞችም መንገድ ማቋረጥ የሚችሉበትን የተመረጠ ጊዜ የሚጠቁም መሆኑን ተናግረዋል፡፡
 በሚማሩበት ትምህርት ቤት የተቋቋመው ኢንቬንቲም የተባለ የፈጠራ ክበብ መሪዎች የሆኑት ፈለገ እና ካረን በፈጠራ ስራ ላይ የመግፋት ዕቅድ ያላቸው ሲሆን፣ ፈለገ በአሁኑ ወቅት በብራውን ዩኒቨርሲቲ የኮምፒውተር ሳይንስና የቪዡዋል አርት የመጀመሪያ ዓመት ትምህርቱን በመከታተል ላይ ይገኛል፡፡“የፈጠራ ስራዎቻቸውን በዋይት ሃውስ የሳይንስ ትርዒት ላይ እንዲያቀርቡ መጋበዛቸው፣ ለእነዚህ ልጆች እጅግ የሚደንቅ ክብር ነው የሚያጎናጽፋቸው፡፡ ፈለገም ሆነ ሌሎቹ ተሳታፊ ተማሪዎች ለሌሎች ወጣቶች መነቃቃትን የሚፈጥር የፈጠራ ተነሳሽነትና የአላማ ጽናት የተላበሱ ናቸው።” ብለዋል ሌሊልሰን-ኤምአይቲ የተባለው የፈጠራ ፕሮግራም መምህርና የፕሮጀክቱ አማካሪ የሆኑት ሌይ ስታብሩክስ፡፡
ኤምአይቲ ኒውስ እንደዘገበው፣ ትውልደ ኢትዮጵያዊው ገብሩ፣ በአገሩ በኢትዮጵያ ከትራፊክ አደጋ ጋር በተያያዘ እግረኞች የሚያጋጥሟቸውን ችግሮች በተመለከተ ለኢንቬንቲቭ ያቀረበውን መረጃ መነሻ በማድረግ ፕሮጀክቱ ሊቀጥል ችሏል፡፡

Saturday, 07 June 2014 14:09

የፍቅር ጥግ

ፍቅር እሳት ነው፡፡ ልብህን ያሙቀው ወይም ቤትህን ያቃጥለው ግን ማወቅ አትችልም፡፡
ጆአን ክራውፎርድ
ብዙ ሰዎች ካንተ ጋር በሊሞዚን ተሳፍረው መሄድ ይሻሉ፡፡ አንተ የምትፈልገው ግን ሊሞዚኑ ሲበላሽ አብረውህ አውቶብስ የሚሳፈሩትን ነው፡፡
ኦፕራ ዊንፍሬይ
ፍቅር እርስ በእርስ መተያየት አይደለም፤ ወደ አንድ አቅጣጫ አብሮ ማየት እንጂ፡፡
አንቶይኔ ዴ ሴይንት ኢኤክዮፔሪ
ፍቅር ከባድ የአዕምሮ በሽታ ነው፡፡
ፍቅር ማብሪያ ማጥፊያው በሌላ ሰው ቁጥጥር ሥር የሆነ የኤሌክትሪክ ብርድልብስ ነው፡፡
ካቲ ካርሊሌ
ፍቅር ፒያኖ እንደመጫወት ነው፡፡ መጀመሪያ በህጎቹ መሰረት መጫወት መማር አለብህ፡፡ ከዚያ ህጎቹን ረስተህ ልብህ እንዳዘዘህ መጫወት ይኖርብሃል፡፡
ያልታወቀ ደራሲ
በመጀመሪያ እይታ የሚይዝ የፍቅር ልክፍት በሁለተኛ እይታ ይድናል፡፡
የአሜሪካዊያን አባባል
ፍቅር ሰዎችን ይፈውሳል - ሰጪውንም ተቀባዩንም፡፡
ዶ/ር ካርል ሚኒንገር
ፍቅር ትጋት የሚጠይቅ ከባድ ሥራ ነው፡፡ ከባድ ሥራ ደግሞ አንዳንዴ መጉዳቱ አይቀርም፡፡
ያልታወቀ ደራሲ

Saturday, 07 June 2014 14:08

የፍቅር አቡጊዳ

አቶ መርሻ በኩራት ጨበጠው፡፡
ዕድላዊት ብሩህ ፈገግታዋን ፈነጠቀችለች፡፡
እሱም በቡናማ ዓይኖቹ አስተዋላት…
ያኔ ለመጀመሪያ ጊዜ ልቧ ተሸበረ፡፡ ያኔ የአተነፋፈስ ስርዓቷ በጥቂቱ ተዛባ፡፡ ከያኔዋ ቅፅበት ጀምሮ ዕድላዊት መልስ ያላገኘችለት ጥያቄ በውስጧ ተጭሯል፡፡
የረሐብ የመሰለ፣ ያን ሰው የማግኘት፣ የራስ የማድረግ፣ በውል ይኼ ነው የማትለው፣ ነገር ግን ጠንካራ ስሜት!
ባለ ቡናማ ዓይኑ ወጣት የሸሚዙን እጅጌ እስከ ክንዱ ጠቅልሎ በውስጠኛው ዓይኗ ለውስጠቷ ይታያታል፡፡ የዳበረ ሰውነቱ፣ ወኔና ቆፍጣናነቱ፣ ማርኳታል፡፡
ሰርክ ቤታቸው እየተገኘ ከእርሷና ከመርሻ ጋር እየተጨዋወተ ያመሻል፡፡ ስለ ስራና ስለ ተለያዩ ወቅታዊ ጉዳዮች ይወያያል፡፡ በነዚህ ጊዜያት በደንብ አስተውላለች ወጣትነቱ፣ ብስለቱ በዚያ ላይ ደልዳላ ሰውነቱ አስጎምጅቷታል፡፡
እርግጥ ነው አቶ መርሻም ወዶታል፡፡ በስነምግባሩ፡፡ በተሰጠው ኃላፊነት ላይ ባለው ትጋትና ብቃት፣ ከሁሉም በላይ በመንፈሰ ጠንካራነቱ ሊያከብረው ተገዷል፡፡
ይሄይስ የዕድላዊት ሁኔታ አላማረውም፡፡ ድርጊቶቿ ሁሉ ሰላም አሳጥቶታል፡፡ አንጀት በሚበላ ሁኔታ እንባ ባቀረሩ አይኖቿ እየተመለከተችው፣ እየተንቆራጠጠችና ጣቶቿን እያፍተለተለች ትቀባጥራለች፡፡
አብዛኛውን ጊዜ ወሬዋ ለመልስ የማይመቹ፣ እዚያው በዚያው የሚገጫጩ ፍሬ አልባ ቃላት ስለሚሆኑባት በዝምታ ሲያዳምጣት ይቆይና፡-
“በቃ ልሂድ አይደለም?” ይላታል፡፡
“እባክህ ይሄይስ ትንሽ ቆይ”
“ለምንድነው ዕድል እንዳልሰራ የምታደርጊኝ?”
“ምን አደረኩህ?”
“ይሄው ስንት ወር ሙሉ በተደጋጋሚ እያስጠራሽኝ የረባ ነገር እንኳ ሳትነግሪኝ በጊዜዬ ትጫወቻለሽ፡፡
ቀድሞውንም እኔን ብቻሽን በምትሆኚ ሰዓት መጥራትሽ አግባብነት የለውም! በጣም ነውርና ልፈቅደው የማላስበው ድርጊት ነው እያደረግሽ ያለሽው!”    ጮክ ብስጭት ብሎ፡፡
“የምታስቢው ሁሉ የማይሞከር ነው፡፡ ባለትዳር መሆንሽን፣ ባለቤትሽ ላንቺ ያለውን ፍቅር አስታውሺ እንጂ! እኔም ብሆን የዛን ጨዋ ሰው ጎጆ የማናጋ ከሐዲ አለመሆኔን ብታውቂ ደስ ይለኛል” ረጋ፣ አንገቱን ወደ ፊቷ ሰገግ እያደረገ፡፡
እሷ ፀጥ! አይኖቿን በእንባ ሞልታ ታቀረቅራለች።
የሳሎኑን በር ከፍቶ ሲወጣ ዓይኖቿ ያቆሩትን መራር ፈሳሽ፣ ከታመቀው የስሜት ትንፋሽዋ ጋር እኩል ትለቃቸዋለች…     
(“ፍቅርና ትግል” ከተሰኘው
  የደራሲ ልዑል ግርማ የአጭር ልብወለድ
  መድበል የተቀነጨበ)

ከአሸባሪዎች ጥቃት ጋር የሚያገናኘው ነገር ባይኖርም የተወለደው ሴፕቴምበር 11 ቀን 1862 ዓ.ም ነው፡፡ ኒውዮርክን ሲወዳት ለጉድ ነው። ብዙዎቹ ታሪኮቹም ኒውዮርክ ላይ የተመሰረቱ ናቸው፡፡ የጽሑፍ ሥራውን የጀመረው ወህኒ ቤት ታስሮ ሳለ ነው፡፡ ታሪኮችን እየፃፈ ኦ ሔነሪ በሚል የብዕር ስም ለጓደኞቹ ይልካል፤ ጓደኞቹ ደግሞ በኒውዮርክ በሚታተሙ መጽሔቶች ላይ ያወጡለት ነበር፡፡ እነዚያ ድንቅ ታሪኮች ከወህኒ ቤት እንደሚፃፉ ግን ማንም የሚያውቅ አልነበረም፡፡ ሚስቱን በሳንባ ነቀርሳ በሽታ ባጣ በአጭር ጊዜ ውስጥ ወህኒ ቢወረወርም የሚጽፋቸው ታሪኮች ግን የሚያሳዝኑና የሚጨፈግጉ አልነበሩም፡፡ የሚያዝናኑ፣ የሚያስቁና የሚያነቃቁ እንጂ፡፡
ወጣቱ ፖርተር ቱባውን (ያላጠረውን) መዝገበ ቃላት ተሸክሞ ነበር የሚዞረው፡፡ እንደመጽሐፍም ያነበውና በቃላት ይማረክም ነበር፡፡ የቃላት ክህሎቱን ከሼክስፒር ጋር የሚያወደድሩም አልጠፉም። እንዲያም ሆኖ ፖርተር ኮሌጅ የመግባት ዕድል አላገኘም፡፡ በ15 ዓመቱ ነው ትምህርቱን አቋርጦ በአጐቱ መድሃኒት ቤት ሥራ የጀመረው፡፡ በቴክሳስ ፈረንሳይኛ፣ ጀርመንኛና ስፓኒሽ ቋንቋዎችን በቅጡ የተማረ ሲሆን አስፈላጊ ሲሆን የውጭ ቋንቋ ቃላትን በታሪኩ ውስጥ ይጠቀማል፡፡
ኦ ሄነሪ አንዳንዴ “የአሜሪካው ሞፓሳ” በሚል ይታወቃል፡፡ በአጫጭር ልብወለዶች ላይ ያልተጠበቀ አስገራሚ ወይም አሳዛኝ አሊያም አስቂኝ አጨራረስን እንዳስተዋወቀ ይነገርለታል፡፡ ታሪኮቹ ግን ስለተራ ተርታ ሰዎች ነው የሚተርኩት፡፡ እንዲያም ሆኖ  ዓለማቀፋዊ ጭብጦችን የሚያንፀባርቁ ናቸው - ፍቅርን፣ መስዋዕትነትን፣ ክብርንና ርህሩህነትን፡፡
ኦ ሄነሪ ዝናን የተቀዳጀው በአንድ ጊዜ አይደለም። የሚጽፋቸውን ታሪኮች በመላ አገሪቱ ለሚታተሙ ጋዜጦችና መጽሔቶች ቢልክም፤ በተደጋጋሚ ውድቅ ተደርጎበታል፡፡ “ነገር ግን ይሄ ጉዳይ አሳስቦኝ አያውቅም፤ አዲስ ቴምብር ለጥፌባቸው ወደ ሌላ ቢሮ እልካቸዋለሁ፡፡ እንዲህ ሲመላለሱ ይቆዩና በአንዱ የህትመት ቢሮ ተቀባይነት ያገኛሉ፡፡ ፈጥኖም ይሁን ዘግይቶ ተቀባይነት ያላገኘ ታሪክ ግን ጽፌ አላውቅም” ብሏል፤ አፕሪል 4 ቀን 1909 ዓ.ም ለኒውዮርክ ታይምስ በሰጠው ብቸኛ ቃለምልልስ፡፡ ለምሳሌ The Emanicipation of Billy የተሰኘው ምርጥ ሥራው ከ10 ጊዜ በላይ ውድቅ እንደተደረገበት ጠቅሶ የማታ ማታ ግን እንደሌሎቹ ሥራዎቹ ሁሉ በአንዱ የህትመት ውጤት ላይ እንደታተመለት ተናግሯል፡፡
የኦ‘ሄነሪ በርካታ አጭር ልብ-ወለዶች ወደ አማርኛ የተተረጐሙ ሲሆን ከእነሱም መካከል The Last Leaf (የመጨረሻዋ ቅጠል) እና The Gift of the magi ይገኙበታል፡፡ ጥቂት የማይባሉ የደራሲው ሥራዎች ተተርጉመው በዚሁ ጋዜጣ ላይም ለንባብ በቅተዋል፡፡  
የኦኼነሪ ዝነኛ ሥራዎች
Witches Loaves
A Retrieved Reformation
The pimienta Panckes
The Green Door
Let me Feel your pulse (የመጨረሻ ሥራው)
The Ransom of Red chief
Shoes
Ships (የshoes ቀጣይ ሥራው ነው)

በወንጀል ምርመራ ታሪኮች ላይ ባተኮሩ የልብወለድ ሥራዎቿ የምትታወቀው እንግሊዛዊቷ ደራሲ አጋታ ክርስቲ፤ ከ2 ቢሊዮን በላይ መፃህፍቶቿ ተቸብችበውላታል፡፡ የመጀመሪያ ሥራዋ The Mysterious Affair at Styles እ.ኤ.አ በ1920 ዓ.ም የታተመላት ሲሆን And Then There Were None የተባለው ሥራዋ 100 ሚሊዮን ቅጂዎች እንደተሸጡላት መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡
ከ60 በላይ በወንጀል ምርመራ ላይ የሚያጠነጥኑ ልብወለዶች የፃፈችው አጋታ ክርስቲ፤ 14 የአጭር ልብወለድ መድበሎች ያሳተመች ሲሆን ከ12 በላይ የመድረክ ትያትሮችንም ጽፋለች፡፡ በብዛት በመታተም ከሼክስፒርና ከመጽሐፍ ቅዱስ ቀጥሎ በ3ኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች፡፡ በዓለም ላይ ለረዥም ጊዜ በመድረክ ላይ በመቆየት የአጋታን ትያትር የሚወዳደር የለም፡፡ The Mousetrap የተሰኘው ትያትሯ እ.ኤ.አ ከ1952-2012 ዓ.ም ከመድረክ ሳይወርድ ታይቶላታል፡፡ ለ60 ዓመት ገደማ ማለት ነው፡፡
በልብወለድ መፃሕፍቷ ላይ ተመስርተው የተሰሩ ከ30 በላይ ፊቸር ፊልሞች ያሉ ሲሆን ወደ ቴሌቪዥን፣ ሬዲዮ፣ ቪዲዮ ጌምና ኮሚክ መፃህፍት የተቀየሩ በርካታ ስራዎችም አሏት፡፡ ስድስት የፍቅር ልብወለድ መፃሕፍትን ሜሪ ዌስትማኮት በሚል የብዕር ስም ያሳተመችው ደራሲዋ፤ ስራዎቿ ከ100 በሆኑ በላይ ቋንቋዎች ተተርጉመውላታል፡፡
በከፍተኛ ሽያጭና ተወዳጅነት የምንጊዜም ምርጥ ደራሲ የሚል ክብርና ሞገስ የተቀዳጀችው አጋታ፤ ከግማሽ ክ/ዘመን በላይ የፃፈች ሲሆን የእሷን ሥራዎች ማንበብ ዓለምአቀፍ የጊዜ ማሳለፊያ ተደርጐ እስከመቆጠር ደርሷል፡፡ ቁጥራቸው ጥቂት የማይባሉ የአጋታ ሥራዎች ወደ አማርኛ ተተርጉመው ለኢትዮጵያውያን ተደራሲያን መቅረባቸው ይታወቃል፡፡

  በዋሽንግተን ዲሲ አሜሪካ በየአመቱ እየታተመ የሚወጣው ‘ኢትዮፕያን የሎው ፔጅስ’ የተባለ የንግድ መረጃ መጽሃፍ መስራችና አሳታሚ ኢትዮጵያዊቷ የንግድ ባለሙያ የሺመቤት በላይ፤ በዋሽንግተን ዲሲ ዙሪያ በሚከናወነው የንግድ እንቅስቃሴ ውስጥ ተጠቃሽ ስራ ላከናወኑ ግለሰቦችና የማህበረሰብ መሪዎች በየአመቱ የሚሰጠው የ”ሾው አዋርድ” ተሸላሚ ሆነች፡፡
‘ሾው ሜን ስትሪትስ’ የተባለውና በዋሽንግተን ዲሲ ዙሪያ የሚከናወነውን የንግድ እንቅስቃሴ ለማበረታታትና ለማስፋፋት የሚሰራው ለትርፍ ያልተቋቋመ ድርጅት፣ ዘንድሮ ለአስረኛ ጊዜ ባዘጋጀው አመታዊ ሽልማቱ ኢትዮጵያዊቷን የንግድ ስራ ባለሙያ የሺመቤት  በላይ ጨምሮ ለሶስት ግለሰቦች ሽልማቱን አበርክቷል፡፡
ድርጅቱ፤ የሺመቤት በዋሽንግተን ዲሲ የሚገኘውን የኢትዮ-አሜሪካ የንግድ ማህበረሰብን በማስተዋወቅና የተሻለ እንቅስቃሴ የሚያደርግበትን ዕድል በመፍጠር ረገድ ላከናወነቻቸው ተግባራት እውቅና ለመስጠት በ”ሾው ስታር አዋርድ” ዘርፍ ሽልማቱን እንዳበረከተላት ገልጿል፡፡
የዋሽንግተን ዲሲ ከንቲባ ቪንሸንት ግሬይ፣ የአካባቢውን የንግድ እንቅስቃሴ ለማፋጠን የሚያስችል የበጀት ድጋፍ በማድረጋቸው፤ የሽልማት ድርጅቱ የቀድሞው የቦርድ ሊቀመንበር ቲም ማክ ደግሞ ድርጅቱን በብቃት በመምራት ባበረከቱት አስተዋጽኦ፣ ሁለቱም በ‘ሾው ሻምፒዮን አዋርድ’ ዘርፍ የዘንድሮ ተሸላሚ ሆነዋል፡፡
በጅግጅጋ ተወልዳ ያደገችው የሺመቤት፤ የመጀመሪያና የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቷን በድሬዳዋ ከተማ ከተከታተለች በኋላ ወደ አሜሪካ በማቅናት፣ በባተን ሮግ ሳውዘርን ዩኒቨርሲቲ በቢዝነስ ማኔጅመንት የመጀመሪያ ዲግሪዋን ተቀብላለች፡፡ በመቀጠልም ኑሮዋን በዋሽንግተን ዲሲ በማድረግ አመታትን የፈጀ ጥናት በመስራት፣ በአካባቢው የሚገኙ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን የንግዱ ማህበረሰብ አባላትን የሚያገናኘውንና የንግድ መረጃ የሚያቀርበውን ‘ኢትዮፕያን የሎው ፔጅስ’ የተሰኘ መጽሃፍ እ.ኤ.አ በ1993 ዓ.ም እያዘጋጀች ማሳተም ጀመረች፡፡
ላለፉት 20 ዓመታት በፕሬዚዳንትነት በምትመራው ‘ዘ ኢትዮፕያን የሎው ፔጅስ ኢስታብሊሽመንት’ (ፍቅር ኩባንያ) አማካይነት የሚታተመውን የንግድ መረጃ መጽሃፍ፤ ከጊዜ ወደጊዜ በከፍተኛ ሁኔታ ማሳደግ የቻለችው የሺመቤት፤ እ.ኤ.አ በ2008 ዓ.ም በአሌክሳንድሪያ ቨርጂኒያ ከሚገኘው ስትራየር ዩኒቨርሲቲ በቢዝነስ አድሚንስትሬሽን ሁለተኛ ዲግሪዋን ያገኘች ሲሆን ከባለቤቷ ከታዋቂው ድምጻዊ ይሁኔ በላይ ጋር በመሆን በተለያዩ የንግድ ስራዎች ላይ ተሰማርታ በዋሽንግተን ዲሲ የንግድ ማህበረሰብ ውስጥ ንቁ ተሳትፎ በማድረግ ላይ ትገኛለች፡፡
በኢትዮጵያውያን ማህበረሰብና በተለያዩ ተቋማት መካከል የጠነከረ ግንኙነት የመፍጠር ዓላማ አንግቦ የሚንቀሳቀሰው “ዘ ኢትዮፕያን ኤክስፖ” የተባለ ለትርፍ ያልተቋቋመ ድርጅት እ.ኤ.አ በ2000 በመመስረትና በፕሬዚደንትነት በመምራት አመታዊ ደማቅ ዝግጅቶችን በማዘጋጀት የምትታወቀው የሺመቤት፤ በንግድ መስክ በተሰማሩ የተለያዩ ድርጅቶች ውስጥ በአመራርነትና በአባልነት ትሳተፋለች፡፡
በንግድ፣ በባህል፣ በኪነጥበብና በተለያዩ ጉዳዮች ዙሪያ በአለማችን የሚታዩ እንቅስቃሴዎችን ለኢትዮጵያውያን ማህበረሰብ የማቅረብ ዓላማ ይዞ፣ በአማርኛና በእንግሊዝኛ ቋንቋዎች እየተዘጋጀ በህትመትና በድረገጽ ለንባብ የሚበቃውን ‘ባውዛ’ የተሰኘ መጽሄት፣ እ.ኤ.አ  በ2008 በመመስረት፣ በአሳታሚነት እየሰራች ትገኛለች፡፡
በዋሽንግተን ዲሲ ሾው ሃዋርድ በተባለ አካባቢ የሚገኘውን ‘ሊትል ኢትዮጵያ’ የተሰኘ ታዋቂ ሬስቶራንት በማኔጂንግ ዳይሬክተርነትና በባለቤትነት ለበርካታ አመታት ያስተዳደረችው የሺመቤት፤ በንግዱ ዘርፍ ለረጅም አመታት ባከናወነቻቸው ተግባራት፣ “የማህበረሰብ ስኬት ሽልማት” (2005)፣ “የአመቱ ምርጥ ሴት የንግድ ባለሙያ ሽልማት” (2004) እና “የዋሽንግተን ዲሲ የሴቶች ማህበር የአመቱ ምርጥ ሴት ሽልማት”ን ጨምሮ በርካታ የተለያዩ ሽልማቶችን ለማግኘት ችላለች፡፡

አቶ ደረጀ ሺበሺ የወረኩማ ባርና ሬስቶራንት ዳይሬክተር

ከአዲስ አበባ በቅርብ ርቀት ላይ የምትገኘው ጣፎ ከተማ እንደከተማ ራሷን ችላ መተዳደር የጀመረችው ከ1999 ዓ.ም ወዲህ ነው፡፡ በዚህች ከተማ ባለሀብቶች በተለያዩ ዘርፎች መዋዕለ - ንዋያቸውን እያፈሰሱ ይገኛሉ፡፡ ከነዚህም መካከል ቀደም ሲል በኮንስትራክሽን ዘርፍ ተሰማርተው የነበረው አበባየሁ ከበደ የህንፃ ስራ ተቋራጭ አንዱ ነው፡፡ ባለሀብቶቹ አካባቢውን በማጥናትና ምቹነቱን በማረጋገጥ በሆቴል ኢንደስትሪው የተሰማሩ ሲሆን ከሁለት ሳምንት በፊት የተመረቀውን “ወረ - ኩማ” ባርና ሬስቶራንት ለአገልግሎት አብቅተዋል፡፡ “ከተማዋ ለኢንቨስትመንት ምቹ እንድትሆን የተደረገው ከፍተኛ ጥረት፣ እንደ ወረ ኩማ - ያሉ ለከተማ ጌጥ የሆኑ ሬስቶራንቶችን ለማየት አስችሎናል” ብለዋል የከተማዋ ኃላፊዎች፡፡ በከተማዋ እንደተግዳሮት የሚነሱት የውሃና የመብራት መቆራረጥ ሲሆን ውሃውን በተመለከተ የጥልቅ ጉድጓድ ቁፋሮ ተደርጐ ከተማዋ በተወሰነ መልኩ ችግሯን እንደቀረፈች የጠቆሙት ኃላፊዎቹ፤ በመብራት በኩል ያለው ችግርም እንዲሁ በቅርቡ እልባት እንደሚያገኝ ተናግረዋል፡፡
የዛሬ ሁለት ሳምንት በወረ - ኩማ ባርና ሬስቶራንት የምረቃ ስነ - ሥርዓት ላይ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ፤ ከባለቤቱና ማኔጂንግ ዳይሬክተሩ ከአቶ ደረጀ ሺበሺ ወ/ማርያም ጋር በአዲሱ የባርና ሬስቶራንት ቢዝነስ ዙሪያ፣ ስለ ኮንስትራክሽን ዘርፉ፣ ስለ ከተማዋና የንግድ እንቅስቃሴው እንዲሁም ስለወደፊት ህልምና ራዕያቸው አነጋግራቸዋለች። እነሆ፡-

እስቲ እንዴት ነው ወደ ቢዝነስ ሙያ የገባኸው?
ቢዝነስ የጀመርነው ከቤተሰብ ጋር ነው፡፡ የቤተሰብ የጋራ ቢዝነስ ነው ያለን፡፡ ኤሌክትሮኒክስ እያስመጣን እናከፋፍላለን፡፡ በኮንስትራክሽን ዘርፍም ተሰማርተናል፡፡ አበባየሁ ከበደ የህንፃ ሥራ ተቋራጭ የተባለ ድርጅት አለን፡፡ ደቡብ ሱዳን ጁባ ውስጥ ሆቴል አለን - “ኦአሲስ” የሚባል ቃሉ እንግሊዝኛ ሲሆን የ “በረሃ ገነት” የሚል ትርጓሜ አለው፡፡
ደቡብ ሱዳን እንደ አገር ራሷን ችላ ከተቋቋመች ገና ሶስተኛ አመቷ ነው፡፡ ሆቴላችሁ መቼ ነው የተከፈተው?
ነፃነታቸውን ከማግኘታቸው ከአንድ አመት በፊት ነው ተከፍቶ ስራ የጀመረው፡፡
ዛሬ እዚህ ጣፎ ከተማ የተገናኘነው “ወረ ኩማ” የተሰኘው ባርና ሬስቶራንታችሁን ምርቃት ምክንያት በማድረግ ነው፡፡ ለመሆኑ ጣፎ ላይ በዚህ ዘርፍ እንድትሰማሩ ያነሳሳችሁ ምንድን ነው?
ቀደም ብዬ እንደነገርኩሽ በኮንስትራክሽን ዘርፍም ተሰማርተናል፤ ደረጃ ሁለት ተቋራጮች ነን። ይህ ቢዝነሳችን ከአምስት ዓመት በላይ ሆኖታል። እናም ጣፎ የመጣነው በዋናነት ለኮንስትራክሽን ስራ ነው፡፡ በመጀመሪያ የቤተሰብ የመኖሪያ ቤቶችን ለመገንባት ተሰማራን፡፡ የእህቶቻችንና የእናታችንን ቤት ስንገባ፣ የስራችንን ጥራትና ቅልጥፍና ያዩ ሰዎች ሌሎች ተጨማሪ ስራዎችን አገኘን በኮንትራት ሰጡን፡፡ ለኮንስትራክሽን ስራው ስንንቀሳቀስ ከተማዋን ተዘዋውረን የማየት እድል ነበረን፡፡ እናም አካባቢው አየሩ፣ የመሬት አቀማመጥና ሁሉ ነገሩ ምቹ ሆኖ ታየን፡፡ የከተማ አስተዳደሩም በማንኛውም ኢንቨስትመንት ከተማዋ ላይ ለሚሰማራ አካል የሚፈጥረው ምቹ ሁኔታ ማራኪ መሆኑን በኮንስትራክሽኑ ዘርፍ ስንሰማራ ለመታዘብ ቻልን፡፡ ከተማዋ አዲስ በመሆኗ ብዙ ኢንቨስት ሊደረግባቸው የሚችሉ ዘርፎች እንዳሉ ተገንዝበናል፡፡ ከዘርፎቹ አንዱም የሆቴልና የሆስፒታሊቲ ኢንዱስትሪው በመሆኑ እኛም ወደዚሁ ገባን፡፡ በዚህ ዘርፍ መሰማራት እንፈልጋለን ስንል ከተማ አስተዳደሩም በደስታ ነው የተቀበለን። ይሄው ለከተማዋ ድምቀት የሆነውን “ወረ ኩማ” ባርና ሬስቶራንትን አስፋፍተን ዛሬ ምረቃው ነው፡፡
አስፋፍተን ስትል?
መጀመሪያ ከፊት ለፊት የምታያት ቤት ብቻ ነበረች፡፡ ትንሽዬ ምግብ ቤት፡፡ እኛ ይህን ቦታ ተከራይተነው ነው፡፡ ከዚያ በኋላ ያለው ጠቅላላ ግንባታ በአንድ ወር ውስጥ ተጠናቆ ነው ስራ የጀመረው፡፡ ፊት ለፊት ካለው ቤት በስተቀር ይህን የምታይውን የመናፈሻ ባር፣ መፀዳጃ እና መሰል ግንባታዎች ከከተማ አስተዳደሩ ባገኘነው ይሁንታ አስፋፍተነው ነው፡፡ አሁን ከባለቤቱ ጋር ለአራት አመት ኪራይ ተፈራርመናል፡፡ የአንድ አመት ክፍያ ቅድሚያ ከፍለናል፡፡ እንደዚህ በማድረግ በዘርፉ አገልግሎት ላይ እሴት ለመጨመር እየተንቀሳቀስን ነው፡፡ ሌላው በአካባቢው በዘርፉ የተሰማሩ ባለሀብቶችን ለማነቃቃት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ይኖረናል፡፡ ወረ ኩማንና መስተንግዶውን ሲመለከቱ፣ ሆቴላቸውንና የአገልግሎት አሰጣጣቸውን ለማሳደግና ተፎካካሪ ለመሆን እንዲተጉ ያደርጋል የሚል ከፍተኛ እምነት አለኝ፡፡
ቦታው አስፋልት ዳር ነው፡፡ ሆኖም ተከራይታችሁት እንጂ የእናንተ አይደለም፡፡ የራሳችሁ ለማድረግ ያደረጋችሁት ጥረት አለ?
ይሄ ትልቁ ሀሳባችን ነው፡፡ በዚህ ላይ ትልቅ እቅድ አለን፡፡ ተጨማሪ ቦታ እንዲኖረን በማድረግ ትልቅ ስራ የመስራት ፍላጐት አለን፡፡ ቀደም ሲል እንደጠቀስሽው ጥሩ ቦታ ላይ ነው ያለው፤ ለዘርፉ ስራ የሚመጥን ነው፡፡ በዚህ ቦታ ላይ ከዚህ የተሻለ ስራ መሰራት እንደሚችል እናምናለን፡፡ እና የራሳችን ለማድረግ እንጥራለን፡፡ የጣፎ ከተማ አስተዳደርም ይህንን ያመቻቻል ብለን እናስባለን፡፡ ምክንያቱም ከተማዋ እንደከተማ ራሷን ችላ መተዳደር የጀመረችው ከ1999 ዓ.ም ወዲህ በመሆኑ፣ ከተማ አስተዳደሩ አማራጭ ኢንቨስትመንቶች ወደከተማዋ እንዲመጡ የሚያሳየው ፍላጐት እንድትሰሪ ያበረታታሻል፡፡ ሌሎች ኢንቨስተሮችም መጥተው ቢሰሩ ሁኔታው ምቹና የሚያሰራ ነው ልላቸው እፈልጋለሁ፡፡
”ወረ ኩማ” ባርና ሬስቶራንት መጀመሪያ ከነበረው ቤት ውጭ ሙሉ በሙሉ የተሰራው አገር በቀል በሆኑ ቁሳቁሶች ነው፡፡ እንደ ቀርከሃ፣ ሸምበቆ እና የመሳሰሉትን ለምን መረጣችሁት? አጠቃላይ የቤቱ አደረጃጀትም ባህላዊ ገፅታው ያመዝናል፡፡ ምክንያቱ ምንድነው?
እንግዲህ ሁሉም ነገር ባህልን መሰረት ያደረገ ሲሆን ደስ ይላል፡፡ ለምሳሌ ሁሉም ቁሳቁሶች ከዚሁ ከጣፎ የወጡ ናቸው፡፡ ቢዝነስ ሲሰራ ጐን ለጐን ባህልንም አብሮ ማስተዋወቅ ተገቢ ነው። ይህ እንግዲህ ሌሎች በዘርፉ የሚሰማሩ ሰዎች እንዲህ አይነት ቢዝነስ ውስጥ ሲገቡ የግድ ውድ ማቴሪያል መጠቀም እንደሌለባቸው ማሳያ ይሆናል። ሸምበቆው እንጨቱ፣ የጐጆዎቹ ክዳን ሳሩ ሁሉ… እዚሁ አካባቢው ላይ በቀላሉ የሚገኙ ናቸው። ዋናው ነገር ለተስተናጋጅ ምቾት በሚሰጥና በሚያዝናና መልኩ መስራቱ ላይ ነው፡፡ ለምሳሌ እኔና አንቺ እዚህ ተቀምጠን ስናወራ፣ ድባቡ ደስ ይልሻል፤ አየሩ ተስማሚ ነው፤ ለአካባቢው ጌጥ የሆነ ባርና ሬስቶራንት ሆኗል፡፡ ማራኪና የሚያዝናና የሆነው በውድ ቁሳቁስ ስለተሰራ አይደለም፡፡ ባህልን መሰረት አድርጐ በአገር በቀል ቁሳቁሶች በማራኪ ሁኔታ ስለተሰራ እንጂ፡፡
በሬስቶራንቱና በካፌው ዙሪያ ያሉ ቦታዎች በጌጣጌጥነት ከተጠቀማችሁባቸው ባህላዊ አልባሳት ውስጥ የዶርዜ ደንጉዛ፣ የኦሮሚያ፣ የአማራ፣ የሃድያና መሰል ብሔሮች አልባሳት ይገኙበታል ለምን ተመረጡ?
ያው የቢዝነስና የመዝናኛ ቦታ የሁሉም ሰው ነው። አሁን ከከተማ ወጣ ብሎ መዝናናት ተለምዷል፡፡ ለምሳሌ ሱሉልታ፣ ዱከም፣ ሰበታ፣ ቡራዩ ብቻ በአዲስ አበባ ዙሪያ ወጣ ብሎ መዝናናት ተለምዷል፡፡ እዚህ ቦታ የትኛውም ብሔር ብሔረሰብ መጥቶ ይዝናናል፡፡ በተመሳሳይ መልኩ ቱሪስቶችም ወደዚህ ሊመጡ ይችላሉ፡፡ አንድም ኢትዮጵያዊነትን ማስተዋወቅ ነው፤ ሁለትም እነዚህ አልባሳት በጌጥ መልክ ሲታዩ አይንን ይማርካሉ፡፡ በአንድ ድንጋይ ሁለት ወፍ ማለት ነው፡፡ ህብረ - ኢትዮጵያን ያቀፈ፣ ባህላችንን የሚያንፀባርቅ፣ በአገር በቀል ቁሳቁሶች የተዋበ መሆኑ ቤቱን ኢትዮጵያ ኢትዮጵያ እንዲሸት ያደርገዋል፡፡
እነዚህ ተጨማሪ የመዝናኛ ቦታዎች ማለትም ጐጆዎቹና ማስፋፊያው በአንድ ወር ተሰርቶ መጠናቀቁ የኮንስትራክሽን ባለሙያ በመሆናችሁ ነው ወይስ ሥራውቀላል ነው?
ብዙ ሰው የተገረመው በዚህ ነው፡፡ “ይሄ የማስፋፊያ ግንባታ አንድ አመት ፈጀ ወይስ ስድስት ወር?” ይሉናል። ነገር ግን በአንድ ወር ነው የተጠናቀቀው፡፡ በአንድ ወር ያለቀው በኮንስትራክሽን ዘርፍ ስለተሰማራን ብቻ አይደለም። የእኛ ጥረትና ትጋት ነው በፍጥነት እንዲጠናቀቅ ያደረግነው፡፡ እርግጥ በዘርፉ ውስጥ መኖራችን አንዱ ግብአት ሊሆን ይችላል፡፡ በኮንስትራክሽን ዘርፍ ባሳየነው የሥራ ጥራትና ፍጥነት ሌሎች ስራዎችንም አግኝተናል። ይሄን ሥራ በአንድ ወር የጨረስነው ግን ትኩረት ሰጥተን በመስራታችን ነው እንጂ በኮንስትራክሽን ዘርፍ ውስጥ በመኖራችን ብቻ አይደለም፡፡ በኮንስትራክሽን ውስጥ ኖረው፣ በጥራትና በፍጥነት ስኬታማ ያልሆኑ ብዙ ድርጅቶች አሉ እኮ፡፡ እኛ አሁን ኮንስትራክሽን ላይ ባለን የስራ ብቃት “ቻይኖች ናቸው የሰሩት” የሚሉን አሉ፡፡ ግን ኢትዮጵያውያንም በደንብ መስራት እንደሚችሉ እያሳየን ነው፡፡ ይህም የማስፋፊያ ግንባታ በአንድ ወር ውስጥ ማለቁ የኢትዮጵዊያንን ብቃት ያስመሰክራል፡፡ የራሳችንን ብቃት ስለማናውቅ ነው እንጂ የሚያክለን የለም፡፡ ግን የአመለካከት ለውጥ ያስፈልጋል፡፡ ኢትዮጵያዊያን በምንም ነገር የላቀ ብቃት አለን፡፡ ነገር ግን በውጭ ባለሙያዎች የማመን ነገር ተጠናውቶናል፡፡
የማስፋፊያ ግንባታው ምን ያህል ወጪ ወጣበት?
ያው እንግዲህ ያላለቁና በመገንባት ላይ ያሉ ነገሮች አሉ፡፡ ነገር ግን እስካሁን 1.8 ሚሊዮን ብር ወጥቶበታል፡፡ የተጀመሩት ሲያልቁ ወደ ሁለት ሚሊዮን ይጠጋል፡፡
በከተማዋ ብዙ የኢንቨስትመንት አማራጭ እንዳለ ነግረኸኛል፡፡ በቀጣይ በምን ዘርፍ ለመሰማራት አስባችኋል?
ተዘዋውረሽ እንደተመለከትሽው ከጀርባው ሰፋ ያለ ቦታ አለው፡፡ ከፊት ለፊት የፓርኪንግ ቦታ ስለሌለው ያንን ቦታ ለፓርኪንግ ልናደርገው አስበናል። እንደነገርኩሽ ቦታውን ለመግዛትና የራሳችን ለማድረግ የጀመርነውና መስመር የያዘ ነገር አለ፡፡ ከዚያ በተረፈ ያሰብነው ትልቁ ነገር፣ በዚሁ አካባቢ ትልቅ የመዝናኛ ማዕከል ለመስራት አቅደናል፡፡ ቀደም ሲል እንደነገርኩሽ፣ በአሁኑ ወቅት ሰው ከከተማ ወጣ ባሉ ትንንሽ ከተሞች የመዝናናት ፍላጐት አለው፡፡ እንደነ ሱሉልታና በመሰል አካባቢዎች ማለቴ ነው፡፡ የህዝቡን ፍላጐት ለማሟላት ጣፎን ብቻ ሳይሆን ኢትዮጵያን የሚያስጠራ ትልቅ የመዝናኛ ቦታ ለመስራት አስበናል፡፡ አሁን የተለያዩ ጥናቶች እያደረግን በጥሩ ሂደት ላይ ነው ያለው፡፡ ዋና ግባችን የአገር ውስጥ ደንበኛን ብቻ ሳይሆን ቦታው የቱሪስት መዳረሻ እንዲሆንም እቅድ አለን፡፡
እንዲህ አይነት ኢንቨትመንቶች ሲካሄዱ ለአካባቢው ነዋሪ የስራ እድሎች ይፈጥራሉ፡፡ ወረ ኩማ ባርና ሬስቶራንት ለስንት ሰዎች የስራ እድል ፈጠረ?
በግንባታው ወቅት መቶ በመቶ ሰራተኛ የወሰድነው ከዚሁ አካባቢ ነው፡፡ በጉልበት ስራም በሙያተኝነትም ማለቴ ነው፡፡ አሁን ሬስቶራንቱ ተከፍቶ ስራ ከጀመረ በኋላም በሰርቪሱና ላይ በተለያየ ስራ ላይ ያሉት 80 በመቶዎቹ የአካባቢው ሰዎች ናቸው፡፡ በአጠቃላይ ለ40 ሰዎች የስራ እድል ተፈጥሯል፡፡ ማስፋፊያው ሲያልቅ ለተጨማሪ ሰዎች የስራ እድል መፈጠሩ የማይቀር ነው፡፡
ባርና ሬስቶራንቱ ስራ ከጀመረ በኋላ ገበያው እንዴት ነው?
በጣም አሪፍ ነው፤ እኛ ደስተኞች ነን፡፡ የከተማ አስተዳደሩ ሰዎች እየመጡ ይጐበኙናል፤ ያበረታቱናል። አሁን ገበያውም ጥሩ ነው፡፡ የአካባቢው ሰዎችም ሆኑ ከአዲስ አበባ የሚመጡት እየተስተናገዱበት ነው፡፡ ይሄ ለአዲስ አበባ ቅርብ ነው፤ መንገዱም ጥሩና ቀጥ ያለ ነው። ጣፎ ለወደፊት ተስፋ ያላት ከተማ ናት፤ እንደነ ሮፓክ እና ሲሲዲ የመሳሰሉ ትልልቅ ሪል እስቴቶች እዚሁ አሉ። ወደፊት ትልቅ የመዝናኛና የንግድ ከተማ የመሆን እድል አላት፡፡ እኛም ለከተማዋ ማደግ በተለያየ ዘርፍ አስተዋጽኦ እያደረግን እንገኛለን። በነገራችን ላይ የደንበኛ ችግር የለም፡፡ ብዙ ባለሀብቶች ሩቅ ሳይሄዱ እዚሁ ብዙ ነገር መፍጠርና መስራት ይችላሉ ባይ ነኝ፡፡
ለአንተ የሥራ ትጋትና ጥንካሬ አርአያ የሆነህ ሰው አለ?
ታላቅ ወንድሜ አበባየሁ ከበደ ነው አርአያዬ። ለምን ብትይ… በጣም በጣም ጠንካራና አስተዋይ ሰው ነው፡፡ ከምንም ተነስቶ ነው እዚህ የደረሰው፡፡ የቤተሰባችን ቢዝነስ ያልኩሽ ኮንስትራክሽኑ “አበባየሁ ከበደ የህንፃ ስራ ተቋራጭ ነው” የሚባለው፡፡ ለዚህ ባርና ሬስቶራንት እዚህ መድረስም የእሱ አስተዋጽኦ ከፍተኛ ነው፡፡ ጠንካራ ሰራተኛና ስራ ወዳድ ስላደረገኝ አመሰግነዋለሁ፡፡ ሌሎችም ለዚህ ባርና ሬስቶራንት እዚህ መድረስ የበኩላቸውን ያደረጉ በርካታ ሰዎች አሉ በጥቅሉ እናመሰግናለን፡፡

Saturday, 07 June 2014 13:54

ስኬትን ማረጋገጥ

እጅግ በጣም ጥሩ ለሆነ የተሽከርካሪ ማኔጅመንት የሚከተሉትን ጠቃሚ ልምዶች ይሞክሩ፡፡
በድርጅትዎ ውስጥ ያለ ማንኛውም ሰው፣ ተሽከርካሪ ፣ የድርጅቱ የደም ስር መሆኑን መረዳቱን እርግጠኛ ይሁኑ፡፡
በዓለም አቀፍ ደረጃ እጅግ ከመጠቁ አገልግሎት ሰጪ ድርጅቶች ጋር ይወዳጁ።
በቲሲኦ ስትራቴጂካዊ ዕቅድ መሰረት አዲስ መኪና መፈብረክን ያራርቁ
ከፍተኛ ጥራትና ብቃት ያለው ተሽከርካሪ መስራት ምንድነው ጥቅሙ? የኢንሹራንስ ወጪ ይቀንሳል? የጥገና ወጪስ? በማለት ይጠይቁ ይላሉ፤ ሚ/ር ኦልደንበርግ፡፡

         በአገራችን ስንት ተሽከርካሪዎች እንዳሉ ያውቃሉ? እሱን ተውት፤ በአዲስ አበባ ከተማ በየቀኑ ስንት ተሽከርካሪዎች በየመንገዱ ይመላለሳሉ? ትክክለኛው አኃዝ ባይታወቅም በሺ የሚቆጠሩ ናቸው፡፡  
እነዚህ ተሽከርካሪዎች የሚጠቀሙት ቤንዚንና ናፍጣ ስለሆነ፣ በየቀኑ ወደ ከባቢ አየር የሚለቁትን ካርቦንዳይ ኦክሳይድ (የተቃጠለ በካይ ጋዝ) አስቡት። ምን ያህል እየተጎዳን እንደሆነ መገመት አያቅትም፡፡
ከአሜሪካ የትራንስፖርት መ/ቤት በተገኘ መረጃ መሰረት፣ በአብዛኛው ቀን በመላ አገሪቱ 12 ሚሊዮን ያህል ተሽከርካሪዎች አስፈላጊ ዕቃዎችን በማመላለስ ሲርመሰመሱ ይውላሉ፡፡
እነዚህ ተሽከርካሪዎች ሁሉንም ዓይነት መኪኖች ያጠቃልላሉ፡፡ ከባድ ዕቃ ጫኝ ካሚዮኖች፣ የሰዎች መጓጓዣ፣ ሽፍን ዕቃ ጫኝ ቫኖች፣… ይጨምራል፡፡ እነዚህ ተሽከርካሪዎች በተወሳሰበ ከባቢ፣ በሺዎች በሚቆጠሩ የተወሳሰቡና የተጠላለፉ መንገዶች፣ ፕሮግራሞች፣ ሕግና የደህንነት ጥንቃቄ፣… የሚጓዙ ቢሆንም የሚጠቀሙት አማራጭ ኃይል ስለሆነ ከባቢ አየር አይጎዳም፡፡ የእነዚህ ተሸከርካሪዎች ግዳጃቸውን በብቃት መወጣት የኩባንያዎቻቸው ሀብት ብቻ ሳይሆን በአጠቃላይ የብሔራዊ ኢኮኖሚው ጭምር ነው፡፡
“የተሽከርካሪ ማናጀሮች ማየት ያለባቸው በርካታ ፈታኝ ሁኔታዎች አሉ” ይላሉ የቶዮታ ናሽናል ፍሌት ማርኬቲንግ፣ ሞቢሊቲና ስትራቴጂክ ፕላኒንግ ማናጀር ሚ/ር ማርክ ኦልደንበርግ፡፡ አያይዘውም “ከወጪና ትርፋማነት ጫና በተጨማሪ በየጊዜው የሚለዋወጡ ሕጎችን፣ ለኢንሹራንስ፣ ለጥገናና ለሾፌሮች አስተዳደር ተገቢውን ምላሽ መስጠት አለባቸው፡፡ ይህ ብቻም አይደለም፤ ለዕለት ተዕለት ቢዝነሳቸው በጣም ተስማሚ የሆነ ተሽከርካሪ መምረጥና ንብረታቸው ማድረግ አለባቸው” ብለዋል ኦልደንበርግ፡፡
ስትራቴጂያዊ የዋጋ ቁጥጥር፡- እጅግ በጣም የተሳካላቸው የተሽከርካሪ ማናጀሮች፣ ከመኪናው መግዣ ዋጋ ይልቅ የመኪናውን አጠቃላይ የባለቤትነት ዋጋ (ቶታል ኮስት ኦፍ ኦውነርሺፕ ቲሲኦ) ይመለከታሉ። ከፍተኛው የቲሲኦ ስሌት “መኪናን አረንጓዴ አድርግ” (green the fleet”) የሚል መሆን አለበት፡፡ ይኼውም የተለመደው የነዳጅ ኃይል በውስጡ በሚያቃጥል ሞተር ወደ ኤሌክትሪክ ወይም ቅይጥ ወይም የታፈነ የተፈጥሮ ጋዝ ወይም ፈሳሽ የፔትሮሊየም ጋዝና በቅርቡ ገበያ ላይ ይውላል ተብሎ የሚጠበቀውን ሃይድሮጂን በመጠቀም ከጊዜው ጋር የሚስማማ የኃይል ፍጆታ ሊኖረን ይገባል፡፡
“በመላው ዓለም ጎዳናዎች የሚርመሰመሱ ከ6 ሚሊዮን በላይ Privs ሞዴል መኪኖች አሉን፡፡ እኛ ግን ሌሎች አምራቾች የሰሯቸውንና ከፍተኛ ብቃት ያላቸውን መኪኖች እየተጠቀምን ነው፡፡ ስለዚህ አረንጓዴ መኪኖች የሚገነባ ማንኛውንም ኩባንያ እየደገፍን ነው ያለነው” ብለዋል ሚ/ር ኦልደንበርግ።
የሃይድሮጂን የነዳጅ ሴል የተገጠመለት የቶዮታ መኪና ከዓመት በኋላ በ2015 ገበያ ላይ ይውላል። የዚህ መኪና ተረፈ ምርት ወይም ዝቃጭ ነገር ውሃ ብቻ ስለሚሆን የግሪን ጋዝ ልቀትን በፍፁም በማስቀረት “አረንጓዴን” ወይም አማራጭ ኃይልን ወደላቀ ደረጃ ያሸጋግረዋል፡፡ ሚ/ር ኦልደንበርግ፣ የዛሬ ዘመን የቴክኖሎጂ ጥበብ ርቅቀት የተሽከርካሪ ማናጀሮችን እየረዳ መሆኑን ሲናገሩ፤ “አረንጓዴ የሀይል አማራጭ ስትጠቀም ጥሩ ስለምትሰራ ገንዘብ ታጠራቅማለህ፡፡ ብዙ የንግድ ተቋማት ሀይብሪድ የሆኑትን ተሽከርካሪዎች ሲለውጡ (ሲገዙ) አይተናል። ከነዳጅ ውጪ የሚያገኙት ትርፍ ብቻ የሚያስገኘው ጥቅም ዝቅተኛ ለነበረው ምርት ከሚያወጡት ወጪ ይበልጣል፡፡ ይህ ለንግድ ተሽከርካሪ ማናጀሮች እጅግ ጠቃሚ ነው” ብለዋል።


ህፃናት አካላዊና አዕምሮአዊ ጤንነታቸው ተጠብቆ የሚያድጉበትን መንገድ የሚያመቻችና በህፃናት አያያዝ፣ አመጋገብ እንዲሁም የህፃናትን ባህርይ በመረዳትና በመንከባከብ ላይ ያተኮረ ዘመናዊ የህፃናት አስተዳደግ ስልጠና የወሰዱ 55 ሞግዚቶችን ማስመረቁን “እሹሩሩ” የሞግዚቶች ማሰልጠኛ ተቋም አስታወቀ፡፡
ድርጅቱ ለመጀመሪያ ጊዜ አሰልጥኖ ያስመረቃቸው እነዚሁ ሞግዚቶች፤ በህፃናት እንክብካቤና አስተዳደግ ላይ በቂ እውቀት ኖሮአቸው፣ ህፃናቱን በአግባቡ ለማሳደግ የሚያስችላቸውን ሥልጠናና እውቀት ያገኙ መሆናቸው ተገልጿል፡፡ በህፃናት አስተዳደግ ላይ ጥናት አካሂደው ወደ ሥራው መግባታቸውን የሚናገሩት የድርጅቱ ኃላፊዎች፤፤ በአገራችን ህፃናትን የሚንከባከቡ ሞግዚቶች በእውቀት የታገዘ ልምድ ስለሌላቸውና ሳይንሳዊ የሆነ ሥልጠና ስለአልወሰዱ በህፃናቱ አስተዳደግና የወደፊት ህይወት ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ ማሳደራቸውን ገልፀዋል፡፡ ይህንን ችግር ለመቅረፍም ሞግዚቶቹን አሰልጥነው ወደ ሥራ ለመሠማራት ማቀዳቸውንና የመጀመሪያ ዙር ሰልጣኞችን ማስመረቃቸውንም ገልፀዋል፡፡