Administrator

Administrator

በያቢ ፊልም ፕሮዳክሽን የተሰራው “ከቃል በላይ” የተሰኘ አስቂኝ የፍቅር ፊልም፣ የፊታችን ሰኞ በአቤል ሲኒማ ይመረቃል፡፡ በፊልሙ ላይ ወጣትና አንጋፋ ተዋንያን እንደተወኑበት የፊልሙ ፕሮዱዩሰሮች ገልፀዋል፡፡

በኢዮብ ጌታሁን የተፃፈውና በእውነተኛ ታሪክ ላይ የተመሰረተው “ያልተኖረ ልጅነት” መጽሐፍ በአሜሪካዊቷ ሻርሊን ቻምበርስ ቦልድዊን ወደ እንግሊዝኛ ተተረጎመ፡፡
“ኦርፋንስ ሶንግ” የሚል ርዕስ የተሰጠው ይኸው የእንግሊዝኛ ትርጉም፣ ከአማርኛው ጋር እንዳይጣረስ የመፅሐፉ ደራሲ በአርታኢነት ተሳትፎበታል፡፡ መፅሐፉ 270 ገፆች ያሉት ሲሆን በዋናነት ከኢትዮጵያ ውጪ እንዲሸጥ ታስቦ የተዘጋጀ ነው፡፡ የመፅሀፉም ዋጋ 14.95 ዶላር ነው፡፡ መጽሐፉ በኢትዮጵያ ውስጥ በቡክ ወርልድ የመፃህፍት መደብሮች ለሽያጭ ይቀርባል ተብሏል፡፡

በደራሲ መዓዛ ወርቁ “Desperate to Fight” በሚል በእንግሊዘኛ ቋንቋ ተፅፎ በሱንዳንስ ተቋም የምስራቅ አፍሪካ ሀገራት ውድድር ላይ የተመረጠው ተውኔት፤ “ከሰላምታ ጋር” በሚል ርዕስ ወደ አማርኛ ተተርጉሞ በኢትዮጵያ መታየት ሊጀምር ነው፡፡ ቲያትሩ ከዚህ ቀደም በእንግሊዝኛ ቋንቋ በኬንያ፣ በኒውዮርክ፣ በስቶክሆልም ስዊድን ለተመልካች ቀርቦ ተወዳጅነትን እንዳተረፈ ተገልጿል፡፡ በተጨማሪም በጀርመንኛ ቋንቋ ተተርጎሞ በጀርመን እና በአውሮፓ ለሚገኙ ተመልካቾች ለማቅረብ theatralize company ከደራሲዋ ጋር ኮንትራት ተፈራርሟል፡፡ ቲያትሩ የኬኒያ፣ የዩጋንዳ፣ የአሜሪካ እና የስዊድን ዜግነት ባላቸው ተዋንያን የተሰራ ሲሆን ለሀገራችን በሚቀርበው ተውኔት ላይ በቲያትር ሙያ የዳበረ ዕውቀት እና ልምድ ያላቸው አርቲስት ኤልሳቤጥ መላኩ እና ፈለቀ የማርውሃ አበበ እንደሚተውኑበት ታውቋል፡፡
በኪባ መልቲ ሚዲያ ፕሮዳክሽን ፕሮዱዩስ የተደረገው ይኸው ቲያትር፤ ከፊታችን ሰኞ ጀምሮ በጃዝ አምባ ላውንጅ በየሳምንቱ ለተመልካች ይቀርባል ተብሏል፡፡ ወደፊትም በሌሎች መድረኮች እንደሚቀርብ ለማወቅ ተችሏል፡፡   

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቴአትር ለመጀመሪያ ጊዜ የእያንዳንዱን ክልል የጋብቻ ስነ - ስርዓትና ትውፊታዊ ክንውን ሰንዶ ሊያስቀምጥ እንደሆነ አስታወቀ፡፡ በዚህም መሰረት ሰኔ 2 ቀን 2006 ዓ.ም እያንዳንዱ ክልል፣ ክልሉን ይወክላሉ ያላቸውን የጋብቻ ሥርዓቶች ይዞ በመቅረብ ለሌላው ህብረተሰብ ያስተዋውቃል ተብሏል፡፡ የጋብቻ ስነ ስርዓቱና ትውፊታዊ ክንውኑ በመገናኛ ብዙሃን የሚሰራጭ ሲሆን ከዚያም በብሔራዊ ቴአትር ተሰንዶ ይቀመጣል ተብሏል፡፡ በዚህ ዝግጅት ላይ ሁሉም ክልሎች ተወክለው ይገኛሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቴአትር በላከው መግለጫ አስታውቋል።

“የኢትዮጵያ ህያው ሙዚየም” የተሰኘ የሙዚየም ማውጫ ታትሞ ወጣ፡፡ በሀገሬ ሚዲያ ኮሙዩኒኬሽን የተዘጋጀው ይሄው የሙዚየም ማውጫ፤ በሁለት ከተማ አስተዳደሮችና በሌሎችም ክልሎች የሚገኙ ሙዚየሞችን ይዟል፡፡ 80 ገፆች ያሉት ማውጫው፤ በክፍል አንድ ከያዛቸው ሙዚየሞች ውስጥ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ሙዚየም፣ የኢትዮጵያ ፖስታ ሙዚየም የኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ተቋም ሙዚየም፤ በኦሮሚያ የሻሼ ሀውልትና ባህል ሙዚየም፣ በደቡብ ክልል የስልጤ ዞን ሙዚየም፣ የሆሌሎጂ ሙዚየም፣ የኮንሶ ሙዚየምና በተለያዩ ክልሎች ያሉ በርካታ ሙዚየሞችን አካትቷል፡፡ ሀገሬ ሚዲያና ኮሙዩኒኬሽን ከዚህ ቀደም የቱሪዝም ማውጫዎችን ያሳተመ ሲሆን በቱሪዝም ላይ ትኩረት አድርጐ የሚሰራ ድርጅት ነው፡፡

አድናቂዎች ለዕጩዎቹ ድምጽ መስጠት ይችላሉ

ኢትዮጵያውያኑ ድምጻውያን አስቴር አወቀና ጃኪ ጎሲ፣ “አፍሪካን ሚዩዚክ ማጋዚን አዋርድስ” (አፍሪማ) ለተባለው ታላቅ አህጉራዊ የሙዚቃ ሽልማት በተለያዩ ዘርፎች በእጩነት ቀረቡ፡፡
አፍሪማ ሰሞኑን ይፋ ባደረገው የ2014 ሽልማት እጩዎች ዝርዝር ላይ እንደተጠቀሰው፣ ድምጻዊት አስቴር አወቀ በ“ምርጥ የምስራቅ አፍሪካ ሴት ድምጻዊት”፣ ጃኪ ጎሲ ደግሞ በ“ምርጥ የምስራቅ አፍሪካ ወንድ ድምጻዊ” ዘርፍ በእጩነት የቀረቡ ሲሆን፣ የሌሎች የአፍሪካ አገራት ድምጻውያን፣ የሙዚቃ ቡድኖች፣ ማኔጀሮች፣ ዳይሬክተሮች፣ ፕሮዱዩሰሮች፣ ዲጄዎች፣ የዳንስ ቡድኖችና የሙዚቃ ቪዲዮዎችም በተለያዩ 26 ዘርፎች ለሽልማት ታጭተዋል፡፡
አስቴር አወቀ በታጨችበት የ“ምርጥ የምስራቅ አፍሪካ ሴት ድምጻዊት” ዘርፍ፣ ሌሎች ሁለት የኡጋንዳ፣ ሁለት የኬኒያና አንድ የታንዛኒያ ታዋቂ ድምጻውያን በእጩነት የቀረቡ ሲሆን፤ ጃኪ ጎሲ በቀረበበት የ“ምርጥ የምስራቅ አፍሪካ ወንድ ድምጻዊ” ዘርፍ ደግሞ፣ ሌሎች ሁለት የታንዛኒያ፣ ሁለት የኡጋንዳና አንድ የኬኒያ ድምጻውያን በእጩነት ቀርበዋል፡፡
አድናቂዎች http://afrimma.com/afrimma-nominees-2014/ በሚለው የድረ-ገጽ አድራሻ በመጠቀም ለሚፈልጓቸው እጩ ድምጻውያን፣ የሙዚቃ ቡድኖችና ሌሎች እጩዎች ድምጻቸውን በመስጠት፣ አሸናፊ እንዲሆኑ የራሳቸውን ድጋፍ ማድረግ እንደሚችሉ የሽልማቱ አዘጋጆች ተናግረዋል።
በመጪው ሃምሌ ወር አጋማሽ በአሜሪካ ቴክሳስ ግዛት፣ ሪቻርድሰን ውስጥ በሚከናወነው የሽልማት ስነስርዓት ላይ፣ በአለማቀፍ ደረጃ እውቅናን ያተረፉ የተመረጡ አፍሪካውያን ድምጻውያን፣ ማኔጀሮች፣ ፕሮዲዩሰሮች፣ ዲጄዎች፣ ባህላዊ ተጽዕኖ ፈጣሪዎች በክብር ይሸለማሉ ተብሏል፡፡ በሽልማት ስነስርዓቱ ላይ ከተለያዩ የአሜሪካ ግዛቶች የተጋበዙና ከ17 የአፍሪካ አገራት በክብር እንግድነት ተጋብዘው የሚመጡ ታላላቅ ጀግኖች ይታደማሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡
የአፍሪካን ሙዚቃ የማስተዋወቅ አላማ ያለውና በየአመቱ በሚከናወን ደማቅ ስነስርኣት ለአሸናፊዎች የሚበረከተው ይህ ሽልማት፤ በዘርፉ ከሚሰጡ ታላላቅ አህጉራዊ ሽልማቶች አንዱ እንደሆነ ተገልጿል፡፡ በአለም አቀፍ ደረጃ ታዋቂ የሆኑ ድምጻውያንና የሙዚቃ ቡድኖች ስራዎቻቸውን የሚያቀርቡበትና በቀጥታ የቴሌቪዥን ስርጭት ለእይታ የሚበቃውን የዘንድሮውን የአፍሪማ የሙዚቃ ሽልማት ስነስርዓት ስፖንሰር ያደረጉት የኢትዮጵያ አየር መንገድ፣ ፓዎር ሃውስ ኢንተርናሽናል ኤርላይንና አክሴስ የተባለው የአሜሪካ ሶፍትዌር አምራች ኩባንያ መሆናቸውንም የሽልማት ድርጅቱ መስራች አንደርሰን ኦቢያጉ በድረ-ገጻቸው ላይ በሰጡት መግለጫ ተናግረዋል፡፡

ውድ እግዚአብሔር-
ስለአንተ ሥራ አስተማሪያችን  ነግራናለች፡፡ አንተ እረፍት ስትወጣ ግን  ማነው የሚሰራልህ?
ዴቪድ-የ5 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር-
እኔ ኢትዮጵያዊ ነኝ፡፡ አንተስ?
ቤቢ- የ6 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር-
ትምህርት ቤት ስንማር፣ መብራት የፈጠረው ቶማስ ኤዲሰን ነው ተብለን  ነበር፡፡ ሰንበት ት/ቤት ደግሞ አንተ እንደፈጠርከው ነገሩን፡፡ ኤዲሰን ያንተን ሃሳብ ሰርቆብህ ነው አይደል ?
ዮኒ - የ7 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር-
ህፃን ወንድም ስለሰጠኸኝ አመሰግንሃለሁ፡፡ እኔ ግን የጠየኩህ የምታምር ቡችላ እንድትሰጠኝ ነበር፡፡
ቤቲ- የ6 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር-
ስለእኔ እንዳታስብ እሺ፡፡ ሁልጊዜ መንገድ ስሻገር ግራና ቀኙን በደንብ አይቼ ነው፡፡
ዳኒ-የ6 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር-
እሁድ እለት ቤተክርስትያን የምትመጣ ከሆነ አዲሱን ጫማዬን አሳይሃለሁ፡፡
ሚኪ-የ5 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር-
በዓይን የማትታየው ሰማይ ሩቅ ስለሆነ ነው አይደል?
ሳሚ- የ4 ዓመት ህፃን

Saturday, 24 May 2014 15:00

የፀሐፍት ጥግ

አንድ ፅሁፍ ያለልፋት በቀላሉ ከተነበበ፣ ሲፃፍ በእጅጉ ተለፍቶበታል ማለት ነው፡፡
ኤንሪክ ጃርዴይል ፓንሴላ
እውነተኛ ፀሐፍትን ተስፋ ማስቆረጥ አይቻልም፡፡ ምንም ብትሏቸው ደንታ  ሳይሰጣቸው ይፅፋሉ፡፡
ሲንክሌይር ልዊስ
በእጄ ላይ ብዕር ይዤ እንቅልፍ ከጣለኝ ብዕሬን አትንኩብኝ፣ በእንቅልፍ ልቤ ልፅፍ እችላለሁ፡፡
ቴሪ ጉሌሜትስ
የመፃፍ ተሰጥኦ እንደሌለኝ ለማወቅ አሥራ አምስት ዓመት ፈጅቶብኛል፡፡ ፅሁፍን ማቆም ግን አልቻልኩም፡፡
 ምክንያቱም ያኔ  ዝነኛ ፀሃፊ ሆኛለሁ፡፡
ሮበርት ቤንችሌይ
የምንፅፈው አሁናችንን በኋላ ለማስታወስ ነው፡፡
 ቴሪ ጉሌሜትስ
ማንም ሰው  የፃፈውን ነገር ለሴት ሳያነብ መፅሃፍ ማሳተም የለበትም፡፡
ቫን ዊክስ ብሩክ
ሃኪሜ የምትኖረው ለስድስት ደቂቃ ብቻ ነው ቢለኝ በፍርሃት አልርድም፤ ፍጥነቴን
 ጨመር አድርጌ እፅፋለሁ እንጂ፡፡
አይሳክ አሲሞቭ

ዊሊያም ዎርድስዎርዝ (1770-1850)
እንግሊዛዊው ገጣሚ ዎርድስዎርዝ  ገና 15 ዓመት ሳይሞላው ነበር ወላጆቹን በሞት ያጣው፡፡ እንዲያም ሆኖ በእንግሊዝ የተሳካላቸውና ተፅዕኖ ፈጣሪ ከሚባሉት ገጣምያን ተርታ ከመሰለፍ ያገደው ነገር አልነበረም፡፡ ግጥሞችን መፃፍ የጀመረው ገና ተማሪ ሳለ ቢሆንም 23 ዓመት እስኪሞላው ድረስ ግን አንድም የግጥም ሥራው አልታተመለትም ነበር። ዎርድስዎርዝ  የፃፋቸውን ግጥሞች የሚያነበው ለውሻው ሲሆን  ውሻው በተነበበለት ነገር ከጮኸ ወይም ከተበሳጨ፣ ዎርድስዎርዝ ግጥሙን ማሻሻልና እንደገና መፃፍ እንዳለበት ተገንዝቦ ወደ ሥራው ይገባል፡፡
ዲክ ኪንግ-ስሚዝ (1922-2011) በእንስሳት ላይ የተመሰረቱ የህፃናት መፃህፍትን በመፃፍ ይታወቅ የነበረው እንግሊዛዊው ደራሲ ዲክ ኪንግ- ስሚዝ፤በሙያ ዘመኑ ከ100 በላይ መፃህፍትን ፅፏል፡፡ ዝናን ያጎናፀፈው መፅሃፉ The Sheep Pig የተሰኘው ሲሆን ይሄ ሥራው Babe በሚል ርዕስ ወደ ፊልም ተቀይሮለታል፡፡ የመጨረሻ መፅሃፉ በ2007 እ.ኤ.አ የታተመለት ሲሆን The Mouse Family Robinson ይሰኛል፡፡ ደራሲው የፃፋቸው ታሪኮች አሁንም ድረስ በመላው ዓለም በሚገኙ ህፃናት ዘንድ በፍቅር እንደሚነበብለት ይነገራል፡፡


ከ800 ሚሊዮን በላይ መፃሕፍቶችን የቸበቸበችው የረዥም ልብወለድ ፀሐፊዋ ዳንኤላ ስቲል፤ የመጀመርያ ረቂቅ ፅሁፏን እስክታጠናቅቅ ድረስ በጥንት የትየባ ማሽን ላይ በቀን ለ20 ሰዓታት ትፅፋለች፡፡ በአንድ መፅሃፍ ላይ አተኩሮ ከመስራት ይልቅ በአንድ ጊዜ ከ4-5 የሚደርሱ መፃሕፍት ላይ በመስራትም ትታወቃለች፡፡
ጥቂት የማይባሉ የደራሲዋ ልብወለዶች ወደ አማርኛ ተተርጉመው ለአገራችን አንባቢያን መቅረባቸው የሚታወቅ ሲሆን ወደ ፊልም የተቀየሩ ሥራዎቿም በቅዳሜ የታላቅ ፊልም ፕሮግራም ላይ ለተመልካች  ይቀርቡ ነበር፡፡


ስቲፈን ኪንግ
ከ350 ሚሊዮን በላይ ኮፒዎች የተሸጡለት ይሄ አሜሪካዊ ደራሲ፤ ምንም ሳያስተጓጉል በየቀኑ ስድስት ገፆች ገደማ  ይፅፋል፡፡ በቀን ከ4 እስከ 6 ሰዓታት ማንበብና መፃፍ የማይችል ሰው ታላቅ ፀሐፊ የመሆን ህልሙን ይርሳው ሲልም ደራሲው ያስጠነቅቃል፡፡  
የድርሰት ትምህርት አንድን ሰው የመፃፍ ክህሎት ያስታጥቀዋል ብሎ የማያምነው ስቲፈን ኪንግ፤ ደራሲነት ከተፈጥሮ የሚገኝ ፀጋ ነው ባይ ነው፡፡ የመጀመርያ ድርሰቱን በ7 ዓመት እድሜው የፃፈው ኪንግ፤ ይሄን ድርሰት በ18 ዓመቱ ለአንድ መፅሄት እንደሸጠው ተዘግቧል፡፡ Carrie የተሰኘውን የመጀመርያ ልብወለዱን ከፃፈ በኋላ በተወዳጅ አስፈሪ (horror) ልብወለዶቹ እየታወቀ የመጣ ሲሆን የመጀመርያ አስፈሪ መፅሃፉም The Shining ይሰኛል፡፡  

አሜሪካዊው የልብ አንጠልጣይ ረዥም ልብወለዶች ደራሲ ዳን ብራውን፤ በሳምንት ለ7 ቀናት ሳያሰልስ በመፃፍ ይታወቃል - ከሌሊቱ 10 ሰዓት ጀምሮ፡፡  ይሄ የቀድሞ የእንግሊዝኛ መምህር፤ ዳቪንቺ ኮድ በተባለው ከፍተኛ ሽያጭ ያስመዘገበ ልቦለድ መፅሐፉ የሚታወቅ ሲሆን ይሄ ልቦለድ  በዚሁ ጋዜጣ ላይ በተከታታይ እየተተረጎመ ሲወጣ እንደነበር ይታወሳል፡፡  

    ዮናስ አብርሃም - የ“ትንንሽ ፀሀዮች” ደራሲና አዘጋጅ    

  “የትንንሽ ፀሐዮች” ተከታታይ የሬድዮ ድራማ በድንገት መቋረጡን በተመለከተ ባለፈው ሳምንት የአዲስ አድማስ ዕትም“ጥበብ” አምድ ላይ ቃለ-መጠይቅ እንደተደረገልኝና የጣቢያው ተወካይም ምላሽ መስጠታቸው ይታወሳል፡፡
በቅድሚያ ሀሳባችንን ለማስተናገድ ዕድል ስለተሰጠን አዲስ አድማሶችን ላመሰግን እወዳለሁ። በማያያዝም፣ ከጣቢያው የተሰነዘረው ምላሽ ከዕውነታው የራቀ በመሆኑ መልስ ለመስጠት ተገድጃለሁ፡፡
ድራማውን ማቋረጥ ያስፈለገው በሁለት ምክንያቶች መሆኑ ተጠቅሷል፡፡ አንዱ ምክንያት፡- “እንደማንኛውም ድራማ የሆነ ጊዜ ተጀምሮ ማለቅ ስላለበት ነው” ተብሏል፡፡ ይህ ምክንያት በመልስነት መቅረቡ ትዝብት ላይ ይጥላል፡፡ ታስቦበት የተጀመረ ስራ በታሰበበት መንገድ መጠናቀቅ ነበረበት። ‘ማለቅ’ የሚለው ቃል ደስ አይልም፡፡ ለሕዝብ የቀረበ ትልቅ ስራ እንዲያልቅ ስለተፈለገ በጣቢያው ውሳኔ ብቻ ‘ማለቅ’ የለበትም፡፡ እንዲቋረጥ ከተፈለገ ብዙ ቀና መንገዶች አሉ፡፡ ጊዜውንና ፈቃዱን ለሰጠ አድማጭ ስሜት ማሰብ ግድ ነው፡፡ ተቀባይነት ካገኘ በኋላ ሕዝቡ ባለቤት መሆኑ አይካድም፡፡ እኔ በማይመቹ ሁኔታዎች ውስጥ ስሰራ የቆየሁት፣ አድማጩንና የሙያ ስነምግባርን አክብሬ እንጂ የሚያጓጓ ጥቅም ስላገኘሁ፣ ወይም ሌላ ዕድል አጥቼ አልነበረም፡፡
የከፈልኩትን መስዋዕትነት፣ ያደረግሁትን ልዩ ጥረት… በቅርብ ያሉ ሁሉ ይረዱታል፡፡ ሠፊው አድማጭም የሚመሰክረው ሀቅ ነው፡፡ ‘ማለቅ ስላለበት’ ብቻ ‘አልቋል’ ተብሏል፡፡ ለነገሩ “ጉመደው፣ አስወግደው” የሚሉ ቃላት አዲስ አይደሉም፡፡
ሁለተኛው ምክንያት፡- “ድራማውን ከአድማጭ በሚመጣ አስተያየት እንገመግመዋለን፡፡ ከጊዜ ወደ ጊዜ ይዘት አልባ ሆነ የሚሉ አስተያየቶች ተበራከቱ” የሚል ነው፡፡ ‘ይዘት አልባ’ የሚለው ግምገማ ግልፅ አይደለም፡፡ ከጣቢያው ምስረታ ማግስት ጀምሮ በጋዜጠኝነትና በድራማ ፀሐፊነት (Playwright) የሠራ ሰው ‘ይዘት አልባ’ ስራ ይዞ አድማጭ ፊት አይቀርብም፡፡ ድራማዎች ሁሉ አንድ ዓይነት አይደሉም፡፡ አስተያየቱ አንድ ናቸው ከሚል ድምዳሜ የመጣ ይመስላል፡፡ የዚህ ዓይነቱን አፃፃፍ በራሴ ጥረት አንብቤ የጀመርኩት እንጂ ቴክኒኩና ፈጠራው ከጣቢያው አልተሰጠኝም፡፡ ድራማው በእኛ ካላንደር (ቀን መቁጠሪያ) ከእኛ ጋር የሚራመድ ታሪክ ስለሆነ እንጂ ዝግ ብሎ መሄዱ በስንፍና የመጣ አይደለም፡፡
በገፀ-ባህርያት ላይ የተመሠረተ ወቅታዊ ድራማ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ‘ይዘት አልባ’ ፕሮግራም መስራትን ጣቢያው አላስተማረኝም፡፡ ሚዛናዊነት አንዱ የጋዜጠኝነት ማዕዘን ነው፡፡ ሚዛናዊነቱ ለእኔ ካልሰራ ምንም ማድረግ አልችልም፡፡ ከዚህ ይልቅ ሌላ ምክንያት ቢፈለግ ጥሩ ነበር። “በቃ! አልፈለግነውም” ማለት ከባድ አይደለም። በመላ ሀገሪቱ ድራማውን በጉጉትና በአድናቆት የሚከታተሉት አድማጮች ጊዜያቸውን የሠጡት ‘ይዘት አልባ’ ለሆነ ነገር ከሆነ፣ በዕድሜና በዕውቀት የሚበልጠንን ሠፊ አድማጭ አለማክበር ነው፡፡
በመሠረቱ፣ እኔ የአለቆችን ስሜት እያነበብኩ የምሰራ ሰው አይደለሁም፡፡ እንደ ጣቢያው ሁሉ፣ የእኔም መለኪያ ሕዝብ ነው፡፡ ፈራጁ ተደራሲው ስለሆነም ስሜቱን በትኩረት እከታተላለሁ፤ ባለኝ መረጃ መሠረትም በጥሩ አቋም ላይ ነበርኩ፡፡ እነማን ምን እንዳሉ እኔ አላውቅም፡፡ በእኔ በኩል ግን… ሕዝብ ያልወደደውን ነገር በግድ ለመጋት ምን ምክንያት ይኖረኛል? ብዙ የጥቅም ዕድሎችን ሰውቼ ባልተመቸ ሁኔታ ውስጥ የቆየሁት፣ ደመወዝ ከፋዩ ሕዝብ ስለሆነ ውዴታውን አክብሬ፣ ለፍላጎቱ ተገዝቼ ነው፡፡
‘ይዘት የለውም’ ከሚባል ‘ዘይት የለውም’ ቢባል በአክብሮት እቀበል ነበር፡፡ ያለ እረፍት ለአምስት ዓመታት በየቀኑ እየፃፉ፣ በየሣምንቱ እየቀረፁ መዝለቅ ምን ያህል ከባድ እንደሆነ ማሰብ አለመፈለግ ለደራሲው ያለውን ስሜት ያሳያል፡፡ ሕዝብ ግን ያውቀዋል፤ አድናቆትን ብቻ አይደለም ምርቃትም ስቀበል ኖሬአለሁ፡፡
“ተዋንያኑ እየለቀቁ በመሄዳቸው ድራማው ተዳከመ” የሚል አስገራሚ አስተያየት ተሰንዝሯል። ብቸኛው ደራሲና አዘጋጅ ችግር ገጥሞኛል ብሎ ካላመለከተ፣ ችግሩ ከቁጥጥር ውጪ አይደለም ማለት ነው፡፡
ተመስገን መላኩ (ቅቤው) ወደ አሜሪካ እንደሚሄድ የተነገረው ከሦስት ዓመት በፊት ነበር። በተለያየ ምክንያት ዘግይቶ ከስድስት ወራት በፊት ለስራ ሄደ፡፡ ስለዚህ ድራማው እንዳይጎዳ በቂ ጊዜ ነበረኝ ማለት ነው፡፡ እኔ ደራሲ ነኝ፣ ደራሲ ችግሮቹን ለመፍታት ብዙ መንገድ እንዳለው የሚፅፍ ሰው ያውቀዋል፡፡ የሚወደዱ ገፀ-ባህርያት ከስራው ገለል ሲሉ መናፈቃቸው ያለ ቢሆንም ገፀ-ባህርያቱ ግን ከደራሲው ሀሳብ ስር ናቸው፡፡ ከተፈለገ፣ ግድ የሚል ችግር ቢመጣም - ባይመጣም ከድራማው የሚወጡበት አሳማኝነት ያለው ጥበባዊ መብት በደራሲ እጅ እንዳለ ይታወቃል፡፡
በረከት በላይነህ (አመዶ)፣ ‘ድራማው አይመጥነኝም ብሎ መውጣቱን’ የሰማሁት ጣቢያውን ወክለው ከተናገሩት ኃላፊ ነው፡፡ እሱ፤ አላለም - አይልም፤ ለዚህ ደግሞ መላው የድራማው አባላት ምክንያቱን ያውቃሉ፡፡ ድራማው በጥድፊያ ‘አለቀ’ ተብሎ በተነገረ በሣምንቱ በረከት (አመዶ) የሰጠውን አስተያየት ማድመጥ ይቻላል፡፡
ለጥቂት ሣምንታት ድም    ፁ ባይኖርም፣ እኔ ሊፈጠሩ የሚችሉ ችግሮችን አስቀድሜ በማሰብ ጥንቃቄ ስለማደርግ፣ ሲጀመር ከነበረው ታሪክ ጋር ተያይዞ እንዲሄድ ተደርጓል፡፡ “አመዶ የት ሀገር ነው የሄደው… ለምንድነው የሄደው?” ብዬ በመጠየቅ ‘ይዘት አልባ’ ሆነ የሚሉትን ትዝብት ውስጥ ለመክተት አልፈልግም፡፡
ዋናዋ እና ተወዳጇ ገፀ-ባህሪ ሠብለ ተፈራ (እማማ ጨቤ) ለስራ ጉዳይ እንግሊዝ ስትሄድ፣ ድራማው ጣዕሙን እንደጠበቀ አቆይቼዋለሁ፡፡ ይህንን አድማጮች ይመሰክራሉ፡፡ የእማማ ጨቤን ክፍተት ለመሙላት በጥንቃቄ ተቀርፀው የገቡት እህታቸው (እትየ ጩጩባ) በጥቂት ሣምንቶች ውስጥ ተወዳጅ መሆን የቻሉት ስላላሰብኩበት አይደለም፡፡  
እውነቱን ለመናገር ጣቢያው በእኔ ስራዎች ላይ እምነት አጥቶ፣ ጥርጣሬ አድሮበት አያውቅም። እኔ የሚጠላ ባህርይ አለኝ ብዬ ባላስብም አልተወደድኩም ብዬም አላዝንም፡፡ እንዴት መወደድ እንደሚቻል ግን አውቃለሁ፡፡
“ድራማው ካለቀ ዓመት አልፎታል” ተብሏል። ለእኔ ሲባል ከሆነ የቆየው ስህተት ነው፡፡ አንድ ግለሠብ ከመላው አድማጭና ሕዝብ አይበልጥም። ዓመት ሙሉ በሕዝብ ጆሮ ላይ ‘ይዘት አልባ’ የሆነ ድራማ ማስተላለፍ የማይመስል ነገር ነው።    ሌላው፡- “ዓመቱን ሙሉ ደብዳቤ እየፃፍን ቆይተናል” ለተባለው ደብዳቤውን ማን እንደተቀበለልኝ አላውቅም፡፡ ሁለት መልስ መስጠት ያልፈለግሁባቸው ደብዳቤዎች በግዳጅ እንደተሰጡኝ አልካድኩም፡፡
“… በነገራችን ላይ ተከታታይነት ያለው ታሪክ የያዘ ድራማ አይደለም፡፡ በየሣምንቱ አዳዲስና የተለያዩ ታሪኮችን ይዞ የሚመጣ ድራማ ነው። ስለሆነም እርሱ ቅን ቢሆንና ቢያስብበት በሦስት ሣምንት ለማጠቃለል የሚያስቸግር ነው ብዬ አላስብም” ብለዋል - የጣቢያው ተወካይ፡፡ ለዚህ ምን መልስ መስጠት ይቻላል? ብዙ ዓይነት ድራማዎች አሉ፡፡ የእኔ ድራማ ምን ዓይነት ባህሪ እንዳለው አድማጭ በሚገባ ይረዳል፡፡ “አዳዲስ ሃሳቦችን ይዞ የሚመጣ ድራማ ነው” ከተባለ በኋላ ‘ይዘት አልባ’ ነው መባሉን አትዘንጉብኝ፡፡
በሀገራችን አዲስ ባህሪ ያለው ረጅምና ተከታታይ ድራማ መሆኑን ማድነቅ ባይቻል በአግባቡ ማወቅ ግን ተገቢ ነበር፡፡ “ቅን ቢሆንና ቢያስብበት…” ለተባለው ለማቋረጥ ምን ቅንነት ያስፈልጋል፡፡ ማሰብ የነበረብኝስ ምንድን ነው?
በበኩሌ ሀሳቤን ለመሰንዘር የተነሳሁት ባሰብኩት መንገድ አልጨረስኩትም ለማለት ብቻ ነው፡፡ ቅንነትን ልጠየቅ የምገባው እኔ አልነበርኩም። ለእያንዳንዱ ነገር መልስ መስጠት ቢቻልም ቃለ ምልልሶቹን ያነበቡ ሰዎች ራሳቸው ስለሚፈርዱ ማብራሪያ ከመስጠት ተቆጥቤያለሁ፡፡
በጣም ያስገረመኝ ነገር ግን አለ፤ ለእኔ መልስ ለመስጠት የተወከሉት የፕሮግራም ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር መሆኑን አስምሩልኝ፡፡ አንድ ድምፅ ይዘው የመጡ የጣቢያው አፍ መሆናቸውን “እኛ” እያሉ በሰጡት ምላሽ ተገንዝቤያለሁ፡፡ ይሁን እንጂ በወቅቱ ስለ ስራው የሚያውቀው ማን ነበር? በስተኋላ የመጡት የአስተያየት ሰጪው የስራ ድርሻ ከዚህ ጉዳይ ጋር ባይገናኝም፣ “እኛ… የድራማው ደራሲ እሱ መሆኑን አናውቅም ነበር። … ያኛው ሰው ደራሲ ነኝ ብሎ መጥቶ ገንዘብ ይወስዳል… ይህንን ሁሉ ያወቅነው ከጋዜጠኝነት ስራው ከፋና ከለቀቀ በኋላ ነው፡፡” የሚያሳፍር ስህተት ብቻ አይደለም፡፡ ስምን አጉድፎ ስብዕናን ዝቅ ለማድረግና ለመወንጀል የታለመ ንግግር ነው። የባለቤትነትን መብት ለማጣረስ የተፈበረከ ውዥንብርና ውንጀላ ነው፡፡
የዚህ መልስ አጭርና ግልፅ ነው፡፡ “ያ-ሰው” የሚባል ፀሐፊና ገንዘብ ወሳጅ አልነበረም። የለፋሁበትን ፈርሜ የምወስደው እኔው ራሴ ነበርኩ፡፡ ይህንን ድራማ ለማስጀመር ከብቸኛ ስፖንሰር አድራጊው ዲኬቲ ኢትዮጵያ ጋር ድራማውን በተመለከተ ብዙ ስብሰባዎች የተካሄዱበትን ድርድር ከሽያጭ ክፍል ሠራተኞች ጋር በመሆን የተወጣሁት እኔ ነኝ፡፡ ሲኖፕሲስ (አፅመ-ታሪክ) አቅርቤ፣ የድራማውን ባህሪ አስረድቼ፣ ድራማው ተደማጭና ተጠቃሚ እንደሚሆኑ አብራርቼ … አየር ላይ ውሏል፡፡ ድራማው ካለቀና አለመግባባት ከተፈጠረ በኋላ በዚህ ዓይነት ስም ማጥፋት በአደባባይ መቅረብ ተገቢ አይደለም፡፡  
ድራማው እንዴት እንደተጀመረ፣ በምን መንገድ እንደተጀመረ፣ ሲጀመር ለትንሽ ጊዜ በብዕር ስም ለምን እንደፃፍኩ… እዛው ቢጠይቁ ኖሮ መልስ ያገኙ ነበር፡፡ በብዕር ስም ፅፌ ክፍያዬን ስቀበል ይኼ የመጀመሪያዬ ነው እንዴ? እኔስ የመጀመሪያው ሰው ነኝ?! አይደለሁም፡፡
ምንም እንኳን ለውስጥ ሰራተኞች ተጨማሪ ክፍያ የማይታሰብ ቢሆንም በጋዜጠኝነት እየሰራሁ ለድራማው ‘በደቂቃ 20 ብር’ ይከፈለኝ የነበረው ልዩ ተሰጥዖን የሚጠይቅ ስራ ስለሆነ ነው፡፡ የመስሪያ ቤቱ  ባልደረባ የመዝናኛ ክፍል ኃላፊ ሆኜ ድራማውን መፃፍና ማዘጋጀት ስጀምር፣ ከደመወዜ በተጨማሪ 1,800 ብር የሚከፈለኝ በጋዜጠኝነት እንጂ በደራሲነት ስላልተቀጠርኩ ነው፡፡ ከ70ኛው ክፍል በኋላ ድርጅቱን ለቅቄ ስወጣ፣ በደቂቃ 80 ብር እንዲከፈለኝ ተስማምተናል፡፡ የመጨረሻዎቹን አስራ ስድስት ወራት አካባቢ ደግሞ ክፍያዬ በደቂቃ 100 ብር ደርሷል፡፡ በጠቅላላ በወር 10 ሺህ ብር ማለት ነው፡፡
ለተሰጥኦ (Talent) ብዙ እንደሚከፈል መንገር አይገባኝም፡፡ ተወካዩ ከፍተኛ ገንዘብ ያሉት ይህንን ከሆነ፣ ውጪ ያለውን ገበያና ክፍያ አያውቁትም ማለት ነው፡፡  
ሠብለ ተፈራ በእማማ ጨቤ ገፀ-ባህሪ ተዋናይነቷ፣ በኋላ ላይ ጭማሪ ተደርጎላት እንኳ በወር የምትወስደው 2 ሺህ ብር አይሞላም፡፡ ሁላችንም ስለ ገንዘብ ሳይሆን ስለ ሙያው ፍቅር እንደምንሰራ ጣቢያው አልተረዳም፡፡
“ድራማው የኛ ነው” ማለት በጣም ያስገምታል፡፡ ጣቢያው በድራማው ላይ ያለውን ባለቤትነት ማወቅ ካስፈለገ… ወጪ ስላወጣበት እና ገንዘብ ከፍሎ ስላሰራ ብቻ ነው፡፡ ይሄ ማለት ደግሞ እስካሁን በተቀረፁት ላይ ሙሉ ባለቤትነት እንዳለው ግልፅ ነው፡፡ መረዳት የሚያስፈልገው ነገር የአንድ ደራሲ የአዕምሮ ፈጠራ ውጤት እንደመሆኑ፣ ቢያስፈልግ ፅሁፉን በሌላ ስቱድዮ በራስ ወጪ በመቅረፅ መጠቀም ይቻላል፡፡
በቀጥታ ያልተዋዋልንበት የስራ ግንኙነት ተቋርጧል፡፡ ለአመታት የተላለፉትን መደምሰስ ከተፈለገ ችግር የለም፡፡ ገፀ-ባህሪያቱን ግን ማክሰም አይቻልም፡፡ የአዕምሮዬ ውጤት የሆኑት ገፀ-ባህሪያት ባለቤት እኔው ብቻ ነኝ፡፡
ጣቢያው ትልቅ ቢሆንም ከዕውነትና ከሕግ በላይ ሊሆን አይችልም፡፡ አሁንም እላለሁ፡- “በእኔ በኩል ድራማውን ፅፌ አልጨረስኩም!!”