Administrator

Administrator

     በደራሲና ጋዜጠኛ አሸናፊ ደምሴ የተፃፈው “የኢህአዴግ የማሪያም መንገድ” የተሰኘ ትዝብት አዘል መፅሀፍ ከትላንት በስቲያ ገበያ ላይ ዋለ፡፡ የመፅሐፉን መጠሪያ ጨምሮ ከ20 በላይ በሚሆኑ ርዕሶች የተለያዩ ወጐችን ያካተተው መፅሀፉ፤ ከሶስቱ በቀር ሌሎቹ በየሳምንቱ ረቡዕ ለንባብ በሚበቃው “ሰንደቅ” ጋዜጣ ላይ የተስተናገዱ እንደሆኑ ታውቋል፡፡የመፅሃፉ አዘጋጅ በ “ሰንደቅ” ጋዜጣ ላይ በከፍተኛ ሪፖርተርነት እየሰራ ሲሆን በህትመት ደረጃ የአሁኑ መፅሃፍ የመጀመሪያ ስራው እንደሆነ ታውቋል፡፡ መፅሀፉ በ174 ገፆች የተቀነበበ ሲሆን በ40 ብር ይሸጣል፡፡  

በዚህ “አሸናፊ” በተባለው ድርሰት መጨረሻ አካባቢ በተካተተው “የሞኝ አንግስ” ቤቶች ወሬ እኔንና አያሌ የጓደኞቼን ቤተሰቦች  እጅግ አሳዝኗል። ዕውነታን መሠረት ባደረገም ይሁን በልብ ወለድ ትረካ ውስጥ ለሚጠቀስ የግለሰብ ስም አስፈላጊውን ጥንቃቄ ማድረግ የግድ ነበር፣ ምክንያቱም ስሙ የጎደፈበት ግለሰብ ራሱን ይከላከል ዘንድ በሕይወት ስለማይኖር።

     ታህሳስ 4 ቀን 2007 ዓ.ም በወጣው የአዲስ አድማስ ጋዜጣ “ነቄዎቹ የስድስት ኪሎ ልጆች” በሚል ርዕስ የተጻፈውን ድርሰት አነበብኩ። ይህ ድርሰት በድረ ገጽ በተደረገ ውድድር ያሸነፈና የአዳም ረታን “መረቅ” መጽሐፍ መሸለሙን አዲስ አድማስ እንደ መግቢያ ገልጾታል። እንደ ወትሮዬ የአዲስ አድማስ ጋዜጣን ሳገላብጥ ዓይኔን የሳበው ይህ ርዕስ ለማንኛውም ሰው አቅል ጎታች መሆኑ ግልጽ ነው። ከዚህም አንጻር ፍሰቱን ተከት የበአራድኛ ቋንቋ የተጠናቀሩትን አጫጭር ዓረፍተ ነገሮች በፈገግታ ረካሁባቸው። ደራሲው በሚመራኝ ሰፈሮች አብሬ በመጓዝ ላይ እያለሁ  አንድ የቅርብ ጓደኞቼን አባት ታሪክ እጅግ የሚያወርድ ትንታኔ ላይ ስደርስ  ግንባሬን አኮስኩሸ በትዕግስት ተከታተልኩት። በእርግጥ አዲስ አድማስ ይህን ጽሑፍ ላንባቢ ከማድረሱ በፊት መጠነኛ አርትዖት እንዳደረገበት ከጅምሩ ጠቁሞናል። አርትኦት ማለት የሰዋሰው፣ የቃላት አመራረጥ፣ ያገላለጽ ዘይቤ፣ ያጻጻፍ ሥነ-ምግባር፣ የታሪክ ወይም የሌላ ይሁን ግን ለእኔ ግልጽ አይደለም።
በዚህ “አሸናፊ” በተባለው ድርሰት መጨረሻ አካባቢ በተካተተው “የሞኝ አንግስ” ቤቶች ወሬ እኔንና አያሌ የጓደኞቼን ቤተሰቦች  እጅግ አሳዝኗል። ዕውነታን መሠረት ባደረገም ይሁን በልብ ወለድ ትረካ ውስጥ ለሚጠቀስ የግለሰብ ስም አስፈላጊውን ጥንቃቄ ማድረግ የግድ ነበር፣ ምክንያቱም ስሙ የጎደፈበት ግለሰብ ራሱን ይከላከል ዘንድ በሕይወት ስለማይኖር። የዚህ ስሙና ታሪኩ በጎደፈበት ሰው ልጆችና የልጅ ልጆች ላይም ብርቱ የሞራል መፋቅ ማስከተሉ አይቀርምና ድርሰቱ ኃላፊነት በጎደለው መልኩ ቀርቧል እላለሁ። በዚህ “በነቄ የስድስት ኪሎ” “የሞኝ አንግስ” ቤቶች ትረካ ከተካተቱት ወጎች አንዱ የጓደኞቼ አባት የነበሩት የአቶ አየለ ስብሐቱ ስም ነው። በተራኪው አቀራረብ ከተዘገበው የአየለ ስብሐቱ የትውልድ አገርና አስተዳደግ ሁኔታን አንብቤ የዕውቀት ማነስን ታዝቤያለሁ፣ እግረ መንገዴንም  የአቅም አድማሱን በስንዝር ለክቸዋለሁ። ያም ሆነ ይህ የማንኛውም ሰው ማንነት ከቤተሰቡ ይጀምራልና ለመጣጥፉ ባለቤትም ሆነ በዕለቱ የወጣውን የአዲስ አድማስ ጋዜጣ ላነበቡ ሁሉ የአየለ ስብሐትን እውነተኛ ታሪክና ተጋድሎ ማስተዋወቅ እሞክራለሁ።
የአየለ ስብሐት የትውልድ አገር ደራሲው እንደ ከተበው በሸዋ ክፍለሐገር በወይራ አምባ አይደለም። በቀድሞው የትግራይ ጠቅላይ ግዛት በአጋመ አውራጃ፣ በስሩክሶ ወረዳ ዓድ ዒሮብ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ በዳልጌዳ መንደር ነው። (ወጣቱ ደራሲ ተከተለኝ)፦  ለትምህርት ካላቸው ከፍተኛ ፍቅርም በራሳቸው አነሳሽነት አሊቴና በሚገኘው የካቶሊክ ትምሕርት ቤት ነበር የገቡ። በአሊቴና የካቶሊክ ትምሕርት ቤት የሚሰጠውን ትምሕርት ካገባደዱ በኋላም አዲስ አበባ በሚገኘው የአላያንስ ፍራንሲ ትምህርት ቤት ቀጥለዋል።
የፈረንሳይኛ ቋንቋ ዕውቀታቸውን የተገነዘቡት ልጅ እያሱ፤ ትምሕርታቸውን ካጠናቀቁ በኋላ ከእርሳቸው ጋር ይሠሩ ዘንድ ሐሳብ አቅርበውላቸው ነበር። አቶ አየለ ግን ለትምሕርት ካላቸው ብርቱ ፍቅርና የውጭውን ዓለም ዕውቀት ለመቅሰም ከነበራቸው ጉጉት የተነሳ የልጅ እያሱን ሐሳብ አልተቀበሉም። ከዚህም አንጻር በራሳቸው ወጭ በባቡር ወደ ጅቡቲ ተጉዘው፣ በመርከብ ወደ አሌክሳንደሪያ ግብጽ ቀጠሉ። እንደ ገና  ወደ ፈረንሳይ ተሳፍረውም መጀመሪያ ማርሴይ ከዚያም ወደ ፓሪስ ሔደው በታዋቂው የሰርቦን ዩንቨርሲቲ የሕግ ትምሕርት ተከታትለዋል። እኒህ የሕግ ምሑር “ጃን ሜዳን ሽጠዋል” ብሎ የሚያስብ  የእኒህን ሰው የሕግ ዕውቀት ያላገናዘበ ሰው ብቻ ነው።
በዚያን ወቅት አልጋ ወራሽ የነበሩት ተፈሪ መኮንን ፈረንሳይን በጎበኙበት ወቅት በክብር ካስተናገዷቸው ኢትዮጵያዊያን ወጣቶች መካከል አየለ ስብሐት አንዱ ነበሩ። የኢትዮጵያ ኤምባሲ በፈረንሳይ ይቋቋም ዘንድ አንጋፋውን ሚና የተጫወቱ ብቻም ሳይሆን የመጀመሪያውን የኢትዮጵያዊያን ማሕበር “የኢትዮጵያ ልጅ”ን ከመሠረቱት አንዱና በፕሬዚደንትነትም የመሩ ሳተና ምሑርና አገር ወዳድ ሰው ነበሩ። ብዙ ኢትዮጵያዊያን ወጣቶች ትምሕርታቸውን በፈረንሳይ አገር ይከታተሉ ዘንድ ከፍተኛ ጥረትም አድርገዋል ( እነ አክሊሉ ሐብተወልድን የመሳሰሉ)። ትምሕርታቸውን ለመከታተል የገንዘብ እጥረት ለነበራቸው ኢትዮጵያዊያን ተማሪዎችም ለአልጋ ወራሽ ተፈሪ መኮንን በማመልከት በጀት ያስፈቀዱ አርቆ አሳቢ ሰው ነበሩ።
በ1928 ዓ.ም አጼ ኃይለሥላሴ በዙፋን ላይ እንደ ተቀመጡ ለዘመናዊ ሥልጣኔና ለሥርዓት መሻሻል በር ይከፍታሉ የሚል ዕምነት ካሳደሩ ወጣት ምሑራን መካከል አየለ ስብሐት አንዱ ናቸው። ከዚህም አንጻር ከእነ ሎሬንሶ ትዕዛዝና ከሐኪም ወርቅነህ ጋር ወደ አገራቸው ተመለሱ።( ዝክረ ነገር ገጽ 606፣ ተራ ቁጥር 85 ይመለከቱ) ። ከተመለሱ በኋላም በአገር ግዛት ሚንስትር በዳሬክተርነት አገልግለዋል። ብዙ ሳይቆይ ፋሽስቱ ኢጣሊያ ኢትዮጵያን በመውረሩ  ሥርዓተ- አገር ፈረሰ። በዚህ የጭንቅ ዘመን ባሕሉንና ቋንቋውን ወደ ተላመዱት ፈረንሳይ አልሸሹም። ወደ አገራቸው ወደ ዓዲ ዒሮብ በመዝመት አሲምባ በረሓ መሽገው ከነበሩ ኢትዮጵያዊያን አርበኞች ጋር በመሰለፍ አምስቱን የጠላት ወረራ ዓመታት በጽንዓት በመታገል አሳለፉ እንጅ።
ከነፃነት በኋላም አገራቸዉን በቅንነት ሲያገለግሉ ቆይተዋል። ወደ ኋላ ግን ከመሳፍንቱ ጋር በተፈጠረ አለመግባባት በፈቃዳቸው ራሳቸውን ከሥልጣን አግልለዋል። ይህ ውሳኔያቸው ንጉሠ ነገሥት ቀዳማዊ ኃይለሥላሴን በማስከፋቱ፣ በግዞት እንዲቆዩና በግል ሥራም እንዳይተዳደሩ ማዕቀብ ተጥሎባቸው ነበር። አዝማች አየለ ስብሐት (በአርበኝነት ዘመን ያስተባበሩት ያርበኛው ሕብረተሰብ  እንደሚጠሯቸው) ከላይ በተጠቀሰው ቅጣት አኩርፈው አገራቸውን በመጥላት መሰደድን አልመረጡም።“የአሸናፊው” ድርሰት ባለቤት አዲስ ዓለማየሁ እንዳቀረበው፤ አየለ ስብሐት  “አጥንተ ድሕነቱ የከበደውና የለበሰውን ቡትቶ አሽንቀጥሮ የጣለ” ሳይሆኑ በግል ጥረታቸው ወደ ከፍተኛ ደረጃ የደረሱ የኢትዮጵያ የክፉ ቀን ልጅና ምርጥ ምሑር ነበሩ። እንደ ምሳሌ ለመጥቀስ ያህልም፣ “የስድስት ኪሎ ነቄዎች” ድርሰት ጸሐፊን የስም ሞክሸነት የሚጋሩትና በዘመኑ የኢኮኖሚና የልማት ሚንስትር የነበሩ ታዋቂው ደራሲና አርበኛ ሐዲስ ዓለማየሁ ላንድ ወዳጃቸው የጋብቻ ሽምግልና ወደ አቶ አየለ ቤት በሔዱበት ወቅት “ እነ አቶ አየለ ስብሐት ከፈረንሳይ ሲመለሱ እኛ ገና ወጣቶች ነበርን። የአቶ አየለን አለባበስ፣ ቁመናና አንደበተ ርቱዕነት ለመታዘብ እጅግ እንጓጓ ነበር” ማለታቸውን በወቅቱ የነበሩ ሰዎች ያወጉ ነበር። በኒህ ታላቅ ሰው የቀብር ስነ-ሥርዓት ላይ ተገኝተው የሕይወት ታሪካቸዉን ያነበቡት ቢትወደድ አስፍሐ ወልደሚካኤልም  ትዝታቸውን ወደ ኋላ በማጠንጠን “ አቶ አየለ ስብሐት ጎፈሬያቸውን አበጥረው፣ ዝናራቸውን ታጥቀውና ጠበንጃቸውን አንግበው ከአሲምባ በረሓ በወጡበት ወቅት የተቆጣ አንበሳ ይመስሉ ነበር” ሲሉ ገልጸውታል። አቶ አየለ ስብሐት ልጆቻቸውንና አያሌ የቅርብ ቤተሰብ አባላት ልጆችን አስተምረው ለቁም ነገር ያበቁ ታላቅ ሰው ስለነበሩም በብዙ ሰዎች ዘንድ ተወዳጅነትን ያተረፉ በጎ ሰው ነበሩ።
በአርበኝነት ዘመን ያልተለዩአቸው ባለቤታቸው ወይዘሮ ከፈይ ዘውገ ለረጅም ግዜ በፈረንሳይ አገር የኖሩና የአጼ ምንይልክ የመሣሪያ አቅራቢ የነበሩት የአንኮበሬው የነጋድራስ ዘውገ ኃይሉ ልጅ ናቸው። አዲስ ዓለማየሁ “ከሞኝ አንግስ ቤቶች” በወረሰው ትረካ የአቶ ስብሐቱን ትውልድ ከአዲ ኢሮብ  ወደ ወይራ አምባ ያጓጓዘውም ከዚህ ውዥንብር የተነሳ ይመስለኛል። አየለ ስብሐት “አጥነተ ድሕነቱ የከበደው” ሳይሆኑ ወደ አገራቸው ከመመለሳቸው በፊት  በሊግ ኦፍ ኔሽን የምሥረታ ጉባኤ ላይ ኢትዮጵያን ወክለው ልኡክ (ዴሊጌት) ከነበሩት ሶስት ሰዎች መካከል አንዱ ነበሩ። በዚህ የምሥረታ ጉባኤ ላይ ከኢጣሊያዊው ወኪል የቀረበው የተቃውሞ ሙግት ቀላል አልነበረም። ኢጣሊያዊው ደሊጌት “ በኢትዮጵያ ውስጥ ባርያ ይሸጣልና ከዚህ የሰለጠነ ማሕበረሰብ ማሕበር በአባልነት ሊካተቱ አይገባቸውም” የሚል የመከራከሪያ ነጥብ አንስቶ ነበር። አቶ አየለ ይህን የተቃውሞ ሓሳብ ውድቅ ለማድረግ የወሰዱት እርምጃ ነፃ የወጡ ባርያዎች ስም ዝርዝር ይላክላቸው ዘንድ በወቅቱ አልጋ ወራሽ ለነበሩት ለተፈሪ መኮንን አስቸኳይ መልዕክት እንዲደርሳቸው ማድረግ ነበር። ይህ በአልጋ ወራሽ ተፈሪ መኮንን የተላከ ነፃ የወጡ የባርያዎች የሥም ዝርዝር እንደ መረጃ መቅረቡን ታሪክ ይዘግባል። በSept 10- Oct 4 1930 በተካሓደው “The eleventh section of the Assembly “ የተካፈሉ የደሊጌት አባላት  አየለ ስብሐት፣ ነጋድራስ መኮንንና Leone Legard (ሊየን ለጋህድ) እንደ ነበሩ ዶሴዎች ይጠቁማሉ።የዚህ መጣጥፍ ዋና ዓላማ በማንኛውም  ድርሰት ውስጥ በስም በሚጠቀሱ  ግለሰቦች ታሪክ ላይ የሚለጠፉ ባሕሪያት ከሥነ-ጽሑፋዊ ሥነ-ምግባርና ከትዝብት አንጻር ጥንቃቄ ሊደረግባቸው እንደሚገባ ማሳሰብ ነው። በየጠጅ ቤቱና “ሞኝ አንግስ” ቤቶች ከሰዓት በኋላ የሚነሱ ወጎችን እንደ ዋቤ ማቅረብም አግባብ አይመስለኝም። ድርሰትን እንዳሻው ሰነቃቅሮ ምርጥና ተነባቢ ማድረግ ይቻላል፣ የግለሰቦችንና የቤተሰባቸውን ስም በጭቃ ለውሶ የድርሰቱ መዋቢያ ማድረግ ግን ዕውቀትን ማዕከል ያላደረገ ድፍረት ነው። ለዚህም ነው አሜሪካዊያን “Ignorance Is Blessed” የሚሉት።
ዋቢ መረጃዎች፡(*LeagueNationsPhotoArchive.  www.indianaedu~legue/11thordinaryasembely.httm)
*ወመዘክር ገጽ 606 ተራ ቁጥር 85 (ከ1928 ዓ.ም በፊት ተምረው ወደ አገራቸው የተመለሱ ሰዎች ሥም ዝርዝር)
አስማማው ኃይሉ

Monday, 05 January 2015 08:10

ፖለቲካዊ ሃሜቶች

የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ በቅርቡ በዓለም የኢኮኖሚ ሰሚት ላይ ለመሳተፍ ወደ ቻይና መዝለቃቸው ይታወሳል፡፡ በቤጂንግ ቆይታቸው ታዲያ ሲወጡ ሲገቡ ማስቲካ እያኘኩ ያዩዋቸው ቻይናውያን “እኚህ ፕሬዚዳንት ሳይሆን ራፐር ነው የሚመስሉት” በሚል ክፉኛ ነቅፈዋቸዋል፡፡
*           *          *
በዚሁ የቤጂንግ ስብሰባ ላይ የሩሲያው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲንም ተገኝተው ነበር፡፡ እሳቸው ደግሞ የቻይናን ቀዳማዊት እመቤት አሽኮርምመዋል በሚል ነበር የተወነጀሉት፡፡ ውንጀላው ከበድ ቢልም አንዳንድ ወገኖች “የሰው ድንበር መጣስ ለፑቲን ብርቃቸው አይደለም” ሲሉ የባሰ ወንጅለዋቸዋል፡፡
*           *          *
በቻይና፡-
ሳንሱር - አያሳስብም
ግርፋት - አያሳስብም
የህፃናት ጉልበት ብዝበዛ - አያሳስብም
ማስቲካ ማኘክ ግን - ዓይንህን ላፈር ያስብላል!!
*           *          *
የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ሮናልድ ሬገን እ.ኤ.አ በ1981 ዓ.ም የግድያ ሙከራ ተፈፅሞባቸው ነበር፡፡ ሆስፒታል ተወስደው ወደ ቀዶ ህክምና ክፍል ሊገቡ ሲሉ ሃኪሞቹን ትክ ብለው እያዩ፤ “ሁላችሁም ሪፐብሊካን እንደሆናችሁ ተስፋ አደርጋለሁ” ብለው ነበር ይባላል፡፡ (ዲሞክራት ሃኪሞችን አያምኗቸውም!)
“ይሄ ቡና ከሆነ እባካችሁ ጥቂት ሻይ አምጡልኝ፡፡ ይሄ ሻይ ከሆነ አባካችሁ ጥቂት ቡና አምጡልኝ”
አብርሃም ሊንከን

ከዕለታት አንድ ቀን ሁለት ወንድማማች ዝንጀሮዎች በአንዲት ዝንጀሮ ወዳጃቸው ይጣላሉ፡፡
አንደኛው ለሁለተኛው፤
“እንግዲህ እዚች ሚስቴ ዝንጀሮዬ ጋ ድርሽ እንዳትል” ይለዋል፡፡
ሁለተኛው፤
“አይ ወዳጄ እኔ ልልህ ያሰብኩትን ነው አንተ አሁን ያልከው፡፡ የሀሳብ መመሳሰል ያስገርማል፡፡ ዞሮ ዞሮ እዚች ሚስቴ ጋ ድርሽ ካልክ በራስህ ፈረድህ”
አንደኛው
“እንዴት?”
ሁለተኛው፤
“ሚስትነትዋ ያለጥርጥር የእኔ ነው፡፡ አርፈህ ተቀመጥ”
አንደኛው፤
“አርፈህ መቀመጥ ከቻልክ አንተው አርፈህ ተቀመጥ! አለዛ እንግዲህ እንዴት በቡጢ እንደማንገጫግጭህ ስታይ ዋጋህን ታውቃለህ!”
ሁለተኛው፤
“አንተ እኔን?”
አንደኛው፤
“አዎ አንተን ምናባክ እንዳትሆን ነው?”
ተጋጋሉ፡፡ ሁለቱም ለቡጢ ተቀራረቡ! ተሰነዛዘሩ፡፡ ሌሎች ች መጡና ከበቡዋቸው፡፡ ጩኸት በረከተ! የሠፈሩ አለቃ የሆነው የሁለቱ ወንድማማች ዝንጀሮዎች አባት መጣና ገላገላቸው፡፡
ሁሉም ፀጥ እርጭ አሉ፡፡
አባት፤
“እሺ የፀቡ መንሥዔ ምንድን ነው?” ሲል ጠየቀ፡፡
አንደኛው፤
“ሚስቴን እየነካ አስቸገረኝ”
ሁለተኛው፤
“እኔንም ሚስቴን እየነካ አስቸገረኝ”
አባት፤
“ሁለታችሁም ስለአንዲት ዝንጀሮ ሴት ነው የምታወሩት?”
አዎን አሉ ሁለቱም፡፡
“እንግዲያው” አለ አባት “ይቺ ዝንጀሮ ትጠራና ትምጣ” አለ፡፡
ዝንጀሮይቱ ተጠርታ መጣች፡፡
አባት፤   
“ይሄኛውም ልጄ የአንቺ ባል ነኝ ይላል፡፡
ይሄኛውም ልጄ የአንቺ ባል ነኝ ይላል…የትኛው ነው ትክክለኛ ባልሽ?”
ዝንጀሮይቱ ራሷን ደልደል አድርጋ ተቀመጠችና፤
“ጌታዬ፤ ከእነዚህ ልጆችዎ አንዱ እንኳ ዕውነተኛ ባሌ ቢሆን ከእኔው ጋር እቤቴ ተቀምጦ ያገኙት አልነበር? አርፎ የተቀመጠ ልጅ ኖሮዎት ያቃል?” ስትል መልሷን በጥያቄ አጠቃለለች፡፡
አባት፤
“እግዜር ይስጥሽ ያቺንም ያቺንም እየነካኩ ባል ነኝ ማለት አቋም የለሽነት ነው፡፡ አሳዳጊ የበደለው ልጅ ማለት የእኔ ልጆች ናቸው!! አንቺ ሂጂ፡፡ እኔም ልጆቼን ልሰብስብ” አሉ ይባላል፡፡
*   *   *
በማናቸውም የህይወት ዘርፍ ውስጥ ምግባረ - ብልሹ መሆን የአስተዳደግን ጉድለት ያሳያል፡፡ የአስተዳደግ ጉድለት ግብረገብነትን፣ ዕምነትን፣ ትምህርትን የሚመለከት በመሆኑ በአብዛኛው ከባህል ጋር ቁርኝት ያለው ነው፡፡ ምግባረ - ሠናይ መሆንም እንደዚሁ እንደ ባህሉ፣ እንደአስተሳሰቡ፣ እንደ አኗኗሩ የሚዳኝ ነው፡፡ በየሥራ መስኩ የምናየው የሰዎች አኳኋንም እንደየአስተዳደሩ የሚመዘን ነው የምንለው ለዚህ ነው፡፡
የሥራ - ዲሲፕሊን፣ የሥራ ፍቅር፣ ለሥራውም ለህሊናም ታማኝ መሆን፣ የኃላፊነት ስሜት ወዘተ ከመልካም አስተዳደር ጋር የተያያዙ ናቸው፡፡ በሀገራችን የመልካም አስተዳደር ጉድለት ከሥራ ባህሉና ከፖለቲካው ተፅዕኖ ጋር በተሠናሠለ መልኩ እግለሰቦች አስተዳደግ ጉድለት ድረስ የተለጠጠ እየሆነ መጥቷል፡፡ ከተቋማዊ አቅም ይልቅ ግለሰባዊ አቅም አይሎ ይታያል፡፡ አሳዳጊ - የበደለው ሆኗል እንደማለት ነው፡፡ በዚሁ ላይ የሙስና እጀታ ሲሠራለት በደምባራ  በቅሎ ቃጭል ተጨምሮ ሆኗል፡፡ ይህንኑ በውል ለመነጋገርም ሌላ ሙስና ውስጥ መዘፈቅ የሚያስፈልግበት ጊዜ ሆኗል፡፡
ፓቮ ፒልካነን የተባለ ሐያሲ፤
“ከሰው ልጅ በርካታ ችግሮች ውስጥ ጉልህ ቦታ የሚይዘው ስለችግሮቹ ለማውራት አለመቻሉ ነው፡፡ ለዚህ ትልቅ አስተዋፅዖ ይኖረው የነበረው ደግመ ጥበብ ነው” ይለናል፡፡ ጥበብ የኮሙኒኬሽን ቱባ መሣሪያ ነው እንደማለት ነው፡፡ የአንድ ህብረተሰብ መንፈሣዊ ዕሴት መገለጫ ጥበብ ነው፡፡ ይህ ጥበብ ዕፁብ፣ ክቡርና ንፁህ ዋጋ ያለው ሲሆን ዕውነተኛ ማንነትን ቁልጭ ንጥር አድርጐ ያሳያል፡፡ ያልታየውን ይገልጣል፡፡ ዕሙናዊውን ህይወት ያፀኸያል፡፡ የህብረተሰቡ ማህበራዊ ስነልቡና ሲነክትም ቀና ብሎ ጠቋሚው ጥበብ ነው፡፡ ለህብረተሰብ በጐ በሆነ ገፁ ያፀኸያል፡፡ ይህን ንፁህ ጥበብ ሰውንና ህይወቱን ከመግለፅ አልፎ የፖለቲካ ቅብ ለመቀባት ከተሞከረ ግን ይበረዛል፡፡ ኦርጅናሌነቱን ያጣል፡፡ እንደተቀባው ቅብ ያለ ቀለም እየያዘ የእስስት ጠጨባይ ያመጣል፡፡ ህይወት እንድትፈስ በተፈቀደላት ተፈጥሮአዊ ሂደት መሄዷ ቀርቶ በግድ በፒንሣ ተጠምዝዛ የመሄድ ያህል ጫና ይበዛባታል፡፡ የሀገራችን የጥበብና የጥበብ ባለሙያ ሁኔታ በዚህ መልክ ሊጤን ይገባል፡፡ የጥበብ ባለሙያ መናቅ ጥበብን መግደል ነው፡፡ እርግይ እንደጠባይ ዘርፉ ከጥንተ - ፍጥረቱ ፖለቲካዊ ቃና ያለውም ጥበብ አለ፡፡ ይሄ ለፖለቲካዊ ህይወት መገለጫ ብቻ ነውና በፖለቲካ ሥነ-ውበትና ቃለ-ኃይል ላይ የሚንተራስ ይሆናል፡፡ ከመግባቢያነት አልፎም መቀስቀሻ ዓላማን ማራመጃ ሊሆን ይችላል፡፡ የዚህ ጥበብ ችግር ፖለቲካው ትኩሳት ካበቃ ሽባ ሆኖ የመቅረት ዕጣ ፈንታው ነው፡፡ ስለዚህ ቀድመን የገለፅነው ዓይነቱ ንፁህና ኦርጅናሌ ጥበብ የአብዛኛው የጥበብ ማህበረሰብ መናኸሪያና ዘላቂነት ያለው ነው፡፡ የህብረተሰብን ንቁ ተሳትፎ፣ መንፈሳዊ ልሳን የሚከፍትለትም ንፁህ ጥበብ ነው፡፡ ይህን ዓይነቱን ጥበብ መንከባከብና ማሳደግ ያስፈልጋል፡፡ ጥበብን ማሳደግ የፈጠራ ኃይልን፣ አዲስ የመፍጠርን ባህል ማበልፀግ ነው፡፡ ጥበብ እንደፖለቲካ መፈክር ለጊዜያዊ ግብ ብቻ የምናውለው መሪ ቃል አይደለም፡፡ የፖለቲካ ዲኮሬሽንም፣ ቀለምም አይደለም፡፡ እንደዲፕሎማሲ ነገረ - ስራ የሆድን በሆድ ይዞ አፍአዊ ማማለያ አይደለም፡፡ የጥበብ ሰውን መውደድ፣ ማበረታታትና ማሳደግ መሰረቱ መሆን ያለበት ይሄና ይሄ ዕሳቤ ነው፡፡ ባለፈው ስርዓት “ ኪነት ለመደቧ” ስንል ከርመን አሁን ደግሞ “ ኪነት ለወገኗ” እንዳንል መጠንቀቅ ይገባናል
“የጥበብ ሰው ህሊናውን የተነጠቀ ዕለት አለቀለት” ይላሉ የጥበብ ሊቃውንት! አንድን የጥበብ ሰው ከህሊናው ውጪ እንዲጓዝ ካደረግነው ጥበቡን በንቀት ዐይን ማየታችን ነው፡፡ ፈጠራን ማቀጨጫችን ነው፡፡ በሞቀበት ዝፈን ማለታችን ነው፡፡ ጥበብን ስንንቅ የመወያያ ገመዳችንን መበጠሳችን ነው፡፡ በፖለቲካውም ሆነ በጥበቡ መስክ መናናቅ ካለ ተያይዞ እረብ ማለት አይቀሬ ነው፡፡ “በቆሎ ጤፍን አይታ አሁን እዚችም ሆድ ውስጥ እህል አለ?” ብትል፣ ጤፍ “ሁለታችንም ስንፈጭ ዱቄት ነን” አለች አሉ የሚለው ይሄንን ሁሉ ያካትታል፡፡

         በ1.8 ቢሊዮን ዶላር ወጪ በኦሞ ወንዝ ላይ እየተከናወነ የሚገኘው የግልገል ጊቤ 3 የውሃ ሃይል ማመንጫ
ግድብ ግንባታ 88 በመቶ መጠናቀቁንና በመጪው ሰኔ ወር በከፊል ሃይል ማመንጨት እንደሚጀምር ሮይተርስ ዘገበ፡፡የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ሃይል ኮርፖሬሽን ዋና ስራ አስፈጻሚ ወ/ሮ አዜብ አስናቀ ከትናንት በስቲያ ለሮይተርስ እንደገለጹት፣ ግድቡ ከሚኖሩት አስር ሃይል ማመንጫ ክፍሎች ሁለቱ በመጪው ሰኔ ወር ሃይል ማመንጨት የሚጀምሩ ሲሆን፣ በቀጣይም በየወሩ አንዳንድ ማመንጫዎች ወደ ስራ እንደሚገቡ ይጠበቃል፡፡ከአንድ አመት በኋላ ግንባታው ሙሉ ለሙሉ ይጠናቀቃል ተብሎ የሚጠበቀው የግድብ ፕሮጀክቱ 1ሺህ 870 ሜጋ ዋት ሃይል የማመንጨት አቅም እንደሚኖረው የገለጹት ወ/ሮ አዜብ፣ ግንባታው ተጠናቅቆ በሙሉ ሃይሉ ማመንጨት ሲጀምር አገሪቱ በአሁኑ ወቅት በማምረት ላይ የምትገኘውን የኤሌክትሪክ ሃይል በእጥፍ ያህል ያሳድገዋል ተብሎ እንደሚጠበቅም ገልጸዋል፡፡ግንባታው እ.ኤ.አ በ2008 የተጀመረው የግልገል ጊቤ 3 የኤሌክትሪክ ሃይል ማመንጫ ግድብ ፕሮጀክት፣ የአካባቢ ጥበቃ ቡድኖች ግድቡ በአካባቢ ላይ ተጽዕኖ ያሳድራል በሚል ያካሄዱትን አለማቀፍ የተቃውሞ ዘመቻ ተከትሎ፣ የአፍሪካ ልማት ባንክ እና የአውሮፓ የኢንቨስትመንት ባንክ ለፕሮጀክቱ የሚያስፈልገውን የገንዘብ ብድር በመከልከላቸው ግንባታው እንደተጓተተ ይታወቃል፡፡

   የሩሲያ ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን በተከሰተው የኢኮኖሚ ቀውስ ምክንያት ሚኒስትሮቻቸው የአዲስ ዓመት እረፍት እንደማይወስዱ ሰሞኑን አስታወቁ፡፡ በሩሲያ ትልቁ በዓል እንደሆነ በሚነገርለት የፈረንጆች አዲስ ዓመት፤ በመላ አገሪቱ የሚገኙ የሩሲያ ኩባንያ ሰራተኞች ለበዓሉ የ12 ቀናት እረፍት ይወስዳሉ፤ ከጃንዋሪ 1 እስከ 12፡፡
ፑቲን ባለፈው ሐሙስ በቴሌቪዥን በተሰራጨ የመንግስት ኃላፊዎች ስብሰባ ላይ፣ በዚህ ዓመት የካቢኔ ሚኒስትሮቻቸው እረፍት መውሰድ እንደማይገባቸው ተናግረዋል፡፡ “ቢያንስ ለዚህ ዓመት መንግስት ይሄን ረዥም የበዓል ዕረፍት መስጠት አይችልም - መቼም የምለው ይገባችኋል” ብለዋል - ፕሬዚዳንቱ፡፡
የአገሪቱ ጠ/ሚኒስትር ዲሚትሪ ሜድቬዴቭ በበኩላቸው፤ በበዓሉ ወቅትም ጭምር (ከዓመቱ የመጀመሪያ ቀናት አንስቶ) የኢኮኖሚውን ሁኔታ እንዲከታተሉላቸው እንደሚፈልጉ ለሚኒስትሮቹ ነግረዋቸዋል፡፡
በነዳጅ ዋጋ መቀነስና በምዕራብ አገራት ማዕቀብ ክፉኛ የተጎዳው የሩሲያ ኢኮኖሚ፤ ከስድስት ዓመታት ወዲህ ለመጀመሪ ጊዜ በቀጣዩ ዓመት “ድቀት” ውስጥ የሚገባ ሲሆን፣ የአገሪቱ ገንዘብ ሩብልም በአሁኑ ሰዓት ከዋጋው ግማሽ በታች ወርዷል፡፡ ከያዝነው ወር መጀመሪያ አንስቶ አንድ ዶላር በ80 ሩብል ሲመነዘር የቆየ ሲሆን፣ ባለፈው ሐሙስ የ2 በመቶ መጠነኛ መሻሻል አሳይቶ አንድ ዶላር በ52 ሩብል መመንዘሩ ታውቋል፡፡
የሩሲያ ማዕከላዊ ባንክ የአገሪቱ መጠባበቂያ ገንዘብ ከ2009 ዓ.ም ወዲህ ለመጀመሪያ ጊዜ ከ400 ቢሊዮን ዶላር በታች መውረዱን አስታውቋል፡፡ ዋጋው እጅግ ያሽቆለቆለውን የአገሪቱን መገበያያ ሩብል ማረጋጋት፣ የሩሲያ የገንዘብ ኃላፊዎች ተቀዳሚ ስራ ይሆናል ተብሏል፡፡ ከዩክሬን ጋር በተያያዘ በአገሪቱ ላይ የተጣለው ማዕቀብ፣ በርካታ የሩሲያ ኩባንያዎችን ከምዕራብ አገራት የፋይናንስ ገበያ እንዳስወጣቸው ተዘግቧል፡፡

የትንፋሽ ማጠር ገጥሟቸው ባለፈው ማክሰኞ ሂዩስተን ሜቶዲስት ሆስፒታል የገቡት የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት  ጆርጅ  ኤች ደብሊው ቡሽ፤ ከትላንት በስቲያ የተከበረውን የፈረንጆች የገና በዓል በሆስፒታል አሳለፉ፡፡
የፕሬዚዳንቱ ቃል አቀባይ ጂም ማክግራዝ፤ ቡሽ በጥሩ ጤንነት ላይ እንደሚገኙና የገና በዓልን በሆስፒታል ያሳለፉት በሽታው ከፍቶባቸው ሳይሆን ለጥንቃቄ ሲባል እንደሆነ ገልፀዋል፡፡ የዛሬ ሁለት ዓመት በተመሳሳይ ጊዜ ብሮንካይትና በሃይለኛ ሳል ይዟቸው ሆስፒታል ከገቡ በኋላ የገና በዓልን ጨምሮ ለሁለት ወራት እዚያው መቆየታቸውን ያስታወሱት ቃል አቀባዩ፤ የአሁኑ ግን ከቀድሞው በጣም ይለያል ብለዋል - የፕሬዚዳንቱን ጤናማነት ሲገልፁ፡፡
የፕሬዚዳንቱ ሆስፒታል መግባት ላሳሰባቸው በርካታ ወዳጆችና አድናቂዎቻቸው የቡሽ ዋና ኃላፊ በሰጡት መግለጫ፤ “የቡሽ ቤተሰብ፤ ለጭንቀታችሁ፣ ለፍቅራችሁና፣ ለፀሎታችሁ በእጅጉ ያመሰግናል፡፡ ይሄ የዛሬ ሁለት ዓመት እንደሆነው ዓይነት አይደለም፡፡ የትንፋሽ ማጠር ነው፡፡ በጥቂት ቀናት ውስጥ ወደ ቤታቸው ይመለሳሉ” ብለዋል፡፡ ቡሽ ሆስፒታል መግባታቸውን የሰሙት ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ እና ባለቤታቸውም ለቀድሞው ፕሬዚዳንትና ለመላው የቡሽ ቤተሰብ የመልካም ጤንነት ምኞታቸውን ልከዋል፡፡
ሪፐብሊካኑ የ90 ዓመቱ ቡሽ፤ 41ኛው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት በመሆን አገራቸውን ያገለገሉ ሲሆን የ43ኛው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ጆርጅ ደብሊው ቡሽም አባት ናቸው፡፡ የዊልቸር እስረኛ ባደረጋቸው ከፍተኛ የነርቭ ህመም ሲሰቃዩ የቆዩት ቡሽ፤ በቅርቡ ግን ነቃ ነቃ ማለት ጀምረው ነበር ተብሏል፡፡ ባለፈው ሰኔ ለ90ኛ ዓመት የልደት በዓላቸው ከሄሊኮፕተር ላይ በፓራሹት የዘለሉ ሲሆን የዛሬ ወር “41፡ A Portrait of My Father” የተሰኘ አዲስ መፅሃፋቸው የምረቃ ስነስርዓት ላይ ከልጃቸው ጋር ተገኝተው ነበር፡፡
ፕሬዚዳንት ሆነው የተመረጡበትን 25ኛ ዓመት በዓል በቅርቡ ያከበሩት ጆርጅ ቡሽ፤ በፕሬዚዳንት ሮናልድ ሬገን ዘመን ምክትል ፕሬዚዳንት ሆነው አገልግለዋል፡፡
በሁለተኛው የዓለም ጦርነት በባህር ኃይል አብራሪነት የተሳተፉ ሲሆን ወደ ፖለቲካው ዓለም ከመግባታቸው በፊት በቴክሳስ የነዳጅ ኢንዱስትሪ ውስጥ እንደሰሩ የህይወት ታሪካቸው ያወሳል፡፡

መኪና ሲያሽከረክሩ የተያዙ ሁለት የሳኡዲ ሴቶች ለአንድ ወር ገደማ ከታሰሩ በኋላ ባለፈው ሳምንት ጉዳያቸው ሽብርተኝነትን ለሚመለከት ልዩ ፍ/ቤት እንደተላለፈ ተገለፀ፡፡
የ25 ዓመቷ ሎዩጄይን አል ሃትሎል እና የ33 ዓመቷ ማይላ ይሳ አል - አሙዲ ጉዳይ ወደ ልዩ ፍ/ቤት የተላለፈው በማህበራዊ ሚዲያ ላይ በሰጡት አስተያየት ነው ብለዋል - የመብት ተሟጋቾች፡፡ ሳኡዲ በዓለም ላይ ሴቶች መኪና እንዳያሽከረክሩ የምትከለክል ብቸኛ አገር ናት፡፡
ሴቶች መኪና እንዳያሽከረክሩ በፅሁፍ የተቀመጠ ህግ ባይኖርም የመንጃ ፈቃድ የሚሰጠው ግን ለወንዶች ብቻ ነው፡፡ ሴቶች በአደባባይ ሲያሽከረክሩ ከተገኙም በፖሊስ ተይዘው ከመታሰርም ባሻገር ይቀጣሉ፡፡
የሳኡዲ ሴቶች መኪና እንዳያሽከረክሩ የተጣለባቸው እገዳ እንዲነሳላቸው ማህበራዊ ሚዲያን ጨምሮ የተለያዩ ተከታታይ እንቅስቃሴዎች ሲያካሂዱ ቆይተዋል፡፡
አዣንስ ፍራንስ ፕሬስ የዜና ወኪል እንደዘገበው፤ ሚስ ሃትሎል የተያዘችው ከጐረቤት አገር፣ ዩናይትድ አረብ ኢምሬትስ እያሽከረከረች ወደ ሳኡዲ ለመግባት ስትሞክር ነው፡፡
ነዋሪነቷን በዩናይትድ አረብ ኢምሬትስ ያደረገችው የሳኡዲ ጋዜጠኛ ሚስ አላሙዲም የተያዘችው ሚስ ሃትሎልን ለመርዳት ድንበር ላይ ስትደርስ ነው ብሏል - የዜና ወኪሉ፡፡
ሁለቱም ሴቶች በትዊተር እጅግ በርካታ ተከታይ ያሏቸው ሲሆን ሚስት ሃትሎል ወደ አገሪቱ ለመግባት አንድ ቀን ሙሉ ያችውን ውጣ ውረድ በትዊተር ገጿ ላይ እንዳሰፈረች ተዘግቧል፡፡ ባለፈው ሐሙስ በአገሪቱ ምስራቃዊ ክፍል የሚገኘው አል - አህሳ ፍ/ቤት፤ የሁለቱ ሴቶች ጉዳይ በሪያድ የሽብርተኝነት ክሶችን ለመከታተል በተቋቋመው ልዩ ፍ/ቤት እንዲዳኙ በይኗል፡፡ የሴቶቹ ጠበቆች ግን ይግባኝ ለመጠየቅ ማሰባቸውን የመብት ተሟጋቾች ለአዣንስ ፍራንስ ፕሬስ ጠቁመዋል፡፡

     በደራሲ ሐማቱማ “The case of the Socialist witchdoctor” በሚል ርዕስ ተፅፎ በህይወት ታደሰ “የሶሻሊስቱ ጠንቋይ ጉዳይ” በሚል ወደ አማርኛ የተመለሰው መፅሃፍ ለንባብ በቅቷል፡፡ የተለያዩ በርካታ ታሪኮች ስብስብ የሆነው ይሄው መፅሃፍ፤ በአንድ ሶሻሊስት ጠንቋይ ላይ ያተኮረ ታሪክ የያዘ ሲሆን ሌሎችም አስገራሚ ፖለቲካዊ ታሪኮችን አካትቷል፡፡ መፅሃፉ በ307 ገፆች የተቀነበበ ሲሆን በ50 ብር ከ65 ሳንቲም ለገበያ ቀርቧል፡፡

 “የዘንድሮ ትዳሮች” በሚል ርዕስ በመቅደስ በቀለ (ማክዳ) ተፅፎ በእርከን ቢዝነስ ዲቨሎፕመንት አሳታሚ የታተመው መፅሐፍ በገበያ ላይ ውሏል፡፡ በቅርቡም ይመረቃል ተብሏል፡፡
በመፅሀፉ የዘንድሮ ትዳሮችን ጨምሮ ሌሎች እውነተኛ ታሪክ ላይ የተመሰረቱ ከ15 በላይ አጫጭር ልቦለዶች እንደተካተቱበትና በ200 ገፆች ተሰናድቶ በ60 ብር ለገበያ እንደቀረበ ለማወቅ ተችሏል፡፡
የመፅሃፉ ደራሲ መቅደስ በቀለ (ማክዳ) የበርካታ ፊልሞች ደራሲና ዳይሬክተር ስትሆን “የዘንድሮ ትዳሮችና ሌሎች” ሁለተኛ መፅሃፏ መሆኑ ታውቋል፡፡ ደራሲዋ ከዚህ ቀደም “የፍቅር መስዋዕት” የተሰኘ መፅሃፍ አሳትማለች፡፡