Administrator

Administrator

    ታዋቂው የመኪና አምራች ኩባንያ ሃዩንዳይ ሞተር፤ የሾፌር እገዛ ሳያስፈልጋቸው ሙሉ ለሙሉ በራሳቸው መንቀሳቀስ የሚችሉበት ቴክኖሎጂ የተገጠመላቸውን ዘመናዊ መኪኖች አምርቶ በመጪዎቹ አምስት አመታት ውስጥ ለአለም ገበያ እንደሚያቀርብ አስታወቀ፡፡
ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተባባሰ በመጣው የዓለማችን የአውቶሞቲቭ ኢንዱስትሪ የቴክኖሎጂ ውድድር ተፎካካሪ ሆኖ በመዝለቅ ላይ ያለው የደቡብ ኮሪያው የመኪና አምራች ኩባንያ ሃዩንዳይ፣ እነዚህን መኪኖች እ.ኤ.አ እስከ 2020 በገበያ ላይ እንደሚያውል ባለፈው ማክሰኞ ማስታወቁን ሮይተርስ ዘግቧል፡፡
ሃዩንዳይ ሞተር፤ ከዚህ በፊትም በተለየ ሁኔታ ባመረታቸው ጄነሲስን የመሳሰሉና እግረኛ ድንገት ወደ መንገድ ሲገባ ያለ ሾፌሩ ትዕዛዝ ፍሬን የሚይዙ ውድ መኪናዎቹ ላይ፣ መሰል ቴክኖሎጂዎችን መግጠሙን ዘገባው አስታውሷል፡፡
የጀርመኑን መርሴድስና የአሜሪካውን ጄኔራል ሞተርስ የመሳሰሉ ታላላቅ የዓለማችን የመኪና አምራች ኩባንያዎች እንዲሁም፤ ጎግልንና አፕልን የመሳሰሉ የቴክኖሎጂው ዘርፍ ፊታውራሪዎች፣ ምንም አይነት የሰው ድጋፍ ሳያስፈልጋቸው ሙሉ ለሙሉ ራሳቸውን ችለው ረጅም ርቀት መሽከርከር የሚችሉ መኪናዎችን ከዚህ ቀደም ማምረታቸውን ዘገባው አስታውሷል፡፡
ይሄም ሆኖ ግን፣ አንዳንድ ተንታኞች ሾፌር አልባ መኪናዎች፣ ከአገራት ጥብቅ የትራንስፖርት ህጎችና አደጋን ለመከላከል ሲባል ከወጡ መመሪያዎች ጋር በተያያዘ በአፋጣኝ ተቀባይነት ያገኛሉ ብለው እንደማያስቡ መናገራቸውን የጠቀሰው ዘገባው፤ እ.ኤ.አ እስከ 2020 አጋማሽ ድረስ ለአለማቀፍ ገበያ ይቀርባሉ የሚል ግምት እንደሌላቸው መግለጻቸውንም አመልክቷል፡፡

- የማስደነስ ፈቃድ የሌላቸው ባሮችና የምሽት ክበቦች ይቀጣሉ
- ፖሊስ ዳንስ ለግርግርና ለብጥብጥ ይዳርጋል ብሏል
- 10 ሺህ ዜጎች የሚሳተፉበት የጎዳና ላይ የዳንስ ተቃውሞ ይደረጋል
   የአገሪቱ ዜጎች ህዝብ በተሰበሰበባቸውና በመዝናኛ ስፍራዎች የሚያደርጉትን እንቅስቃሴ በተመለከተ ገደብ የሚጥል አዋጅ አውጥቶ ሲተገብር የቆየው የስዊድን ፓርላማ፣ የአዋጁ አንድ አካል የሆነውና ህገ-ወጥ ዳንስን የሚከለክለውን አነጋጋሪ ህግ ተግባራዊ መደረጉን እንዲቀጥል መወሰኑን ዴይሊ ሜል ዘገበ፡፡
የአገሪቱ ፖሊስም ህገወጥ ዳንስ፤ለግርግርና ብጥብጥ የሚዳርግ በመሆኑ ህጉን እንደሚደግፈው ያስታወቀ ሲሆን አንዳንድ አስተያየት ሰጪዎች በበኩላቸው፤ አሳፋሪ የቢሮክራሲ መገለጫ በመሆኑ ሊሻር ይገባል ሲሉ ነቅፈውታል፡፡ ፓርላማው ድምጽ የሰጠበትና እንዲቀጥል የወሰነበት ይህ ህግ፣ ሙዚቃ ስለሰሙ ብቻ እግራቸውን ለዳንስ የሚያነሱ ግለሰቦችን በህገወጥነት የሚፈርጅ ሲሆን፣ የማስደነስ ፍቃድ የሌላቸው የባርና የምሽት ክለብ ባለቤቶች ሲያስደንሱ ከተገኙ እንደሚቀጡ ይደነግጋል፡፡
ደንበኞቻቸው በሰሙት ሙዚቃ ሁሉ ሳያቋርጡ ሲደንሱ ወይም ፈቃድ ሳያገኙ ሲውረገረጉ ከተገኙም የባርና የምሽት ክለብ ባለቤቶች እንደሚቀጡ ህጉ ይገልጻል፡፡ ህጉን የተቃወሙት አንድሪያስ ቫርቬስ የተባሉ ስዊድናዊ የምሽት ክለብ ባለቤት፣ ከዚህ በፊት እንደተደረገው ሁሉ በመጪው ነሐሴ ወር ላይ ህጉን የሚቃወም የጎዳና ላይ የዳንስ ተቃውሞ ለማድረግ  ማቀዳቸውን ተናግረዋል፡፡ በጎዳና ላይ ዳንሱ ከ10 ሺ በላይ ሰዎች ይሳተፋሉ ብለው እንደሚገምቱም ገልጸዋል፡፡

  የቻይና የአውቶሞቲቭ ኢንዱስትሪ መስክ መሃንዲሶች ለመጀመሪያ ጊዜ በባለሶስት አውታር ማተሚያ ማሽን (3D printer) አትመው ያወጧትን ቀላል መኪና ሃይናን በተባለችው የአገሪቱ ግዛት ውስጥ ለእይታ ማብቃታቸውን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
3.6 ሜትር ቁመትና 1.63 ሜትር ስፋት ያላትን ይህቺን መኪና፣ በቀላል ወጪ የሚገዙ ቁሳቁሶችን በግብዓትነት በመጠቀም በማተሚያ ማሽኑ አማካይነት ሰርቶ ለማጠናቀቅ፣ አምስት ቀናትን ብቻ እንደፈጀ የጠቆመው ዘገባው፣ ክብደቷም አነስተኛ እንደሆነ ገልጧል፡፡
የመኪናዋ ዋና ዲዛይነር የሆኑት ቼን ሚንጊያኦ እንዳሉት፤ ባለ ሁለት መቀመጫዋ መኪና ክብደቷ አነስተኛ ቢሆንም ጥንካሬን የተላበሰች ናት ብለዋል፡፡ ክብደቷ አነስተኛ መሆኑ ደግሞ ሃይል ለመቆጠብ ያስችላታል ሲሉም ተናግረዋል፡፡ ከኮምፒውተር ጋር በተያያዘ ባለሶስት አውታር ማተሚያ አማካይነት ቁሳቁሶችን ማተም የሚያስችለውን የዘመኑ ቴክኖሎጂ በመጠቀም በቻይና ታሪክ የመጀመሪያዋ የሆነችው ይህቺ መኪና፣ ቻርጅ ከሚደረግ ባትሪ በምታገኘው ሃይል የምትንቀሳቀስ ሲሆን በሰዓት እስከ 40 ኪሎ ሜትር ርቀት የመጓዝ አቅም አላት፡፡

Monday, 06 April 2015 09:06

የየአገሩ አባባል

ለጅል መድሃኒቱ ሞት ብቻ ነው፡፡
በፀሐይ እረስ፣ በዝናብ አንብብ፡፡
ያልተጠየከውን ምክር አትለግስ፡፡
አንዳንዴ መድኀኒቱ ከበሽታው ይከፋል፡፡
የጫማ ሰሪ ልጅ ሁልጊዜ በእግሩ ይሄዳል፡፡
ስጦታ የሚቀበል ነፃነቱን ይሸጣል፡፡
መንሾካሾክ ባለበት ሁሉ ውሸት አለ፡፡
ገንዘብ የሌለው ሰው ገበያ ውስጥ ጥድፍ ጥድፍ ይላል፡፡
አንዴ የሰረቀ ሁልጊዜ ሌባ ነው፡፡
ሆድ ሲሞላ ልብ ደስተኛ ይሆናል፡፡
ቁራ ካረባህ ዓይንህን ይጓጉጡታል፡፡
ማልዶ የተነሳ ያልደፈረሰ ውሃ ይጠጣል፡፡
ጥርጣሬ የዕውቀት ቁልፍ ነው፡፡
ፅጌረዳውን የፈለገ እሾሁን ማክበር አለበት፡፡
ዓይነስውር በራሰ በራ ይስቃል፡፡
እባብ ለመያዝ የጠላትህን እጅ ተጠቀም፡፡
ነፋስ ያመጣውን ነፋስ ይወስደዋል፡፡
ልብ ውስጥ ያለውን ምላስ ያወጣዋል፡፡
በወጣት ትከሻ ላይ አሮጌ ጭንቅላት መትከል አትችልም፡፡
ሰነፍ በግ ፀጉሩ የከበደው ይመስለዋል፡፡

   አሜሪካ ለግብጽ ስትሰጥ የቆየችውንና ለሁለት አመታት ያህል አቋርጣው የነበረውን ወታደራዊ ድጋፍ እንደገና ሙሉ ለሙሉ መስጠት ልትጀምር እንደሆነ ማስታወቋን ዋሽንግተን ፖስት ዘገበ፡፡ የኦባማ አስተዳደር ለግብጽ ሲሰጠው የቆየውንና ከ2013 ጥቅምት ወር ወዲህ አቋርጦት የነበረውን 1.3 ቢሊዮን ዶላር የሚገመት አመታዊ የወታደራዊ መሳሪያዎች ድጋፍ እንደገና ለመጀመር ውሳኔ ላይ መድረሱን ባለፈው ክሰኞ አስታውቋል፡፡የግብጹ ፕሬዚዳንት ሞሃመድ ሙርሲ ከስልጣን መውረዳቸውን ተከትሎ፣ አገሪቱ እስከምትረጋጋና ዲሞክራሲያዊ ማሻሻያዎችን ተግባራዊ ለማድረግ የሚያስችል ተጨባጭ ለውጥ እስኪታይ ድረስ፣ አሜሪካ ለግብጽ የምትሰጠውን ወታደራዊ ድጋፍ አቋርጣ መቆየቷን ዘገባው አስታውሷል፡፡ የአሜሪካ መንግስት ወታደራዊ ድጋፉን እንደገና ለመስጠት መወሰኑ፣ ግብጽን ከፍተኛ ዋጋ የሚያወጡ አሜሪካ ሰራሽ የወታደራዊ መሳሪያዎች ባለቤት ያደርጋታል ያለው ዘገባው፣ ላለፉት ሁለት አመታት በአሜሪካ እጅ የቆዩ 12 ኤፍ-16 ተዋጊ ጀቶችን፣ 20 ቦይንግ ሃርፖን ሚሳየሎችን፣125 አሜሪካ ሰራሽ አብራምስ ኤምዋንኤዋን ታንኮችንና ሌሎች መሳሪያዎችን ማግኘት እንደሚያስችላት የአሜሪካ ብሄራዊ የደህንነት ካውንስል ቃል አቀባይ በርናዴት ሜሃን መናገራቸውን ጠቁሟል፡፡  አሜሪካ ወታደራዊ ድጋፉን እንደገና ለመቀጠል የወሰነችው፣ የራሷን የብሄራዊ ደህንነት ፍላጎት መሰረት በማድረግ ነው ያሉት ቃል አቀባይዋ፣ ለግብጽ የምትሰጠውን ወታደራዊ ድጋፍ በተለይ ሽብርተኝነትን ለመዋጋት፤ የድንበርና የባህር ደህንነቶችን ለማስጠበቅና አይሲሲ የተባለው ታጣቂ ቡድን በሲናይ አካባቢ የሚያደርገውን እንቅስቃሴ ለመግታት በሚደረጉ እንቅስቃሴዎች ላይ እንዲውሉ በሚያስችል መልኩ ማሻሻሏንም አስታውቀዋል፡፡ ኦባማ ክግብጹ ፕሬዚዳንት አል ሲሲ ጋር ባደረጉት የስልክ ውይይት፣ 1.3 ቢሊዮን ዶላር የሚገመተውን ወታደራዊ ድጋፍ በዘላቂነት ለማስቀጠል ለአሜሪካ ምክር ቤት ጥያቄ እንደሚያቀርቡ ቃል ገብተዋል፡፡ ግብጽ ከ2018 ጀምሮ የጦር መሳሪያዎችን በብድር መግዛቷን ማቆም እንደሚገባት አሳስበዋቸዋል፡፡አልጀዚራ በበኩሉ፤ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ተቋማት አሜሪካ ለግብጽ ሙሉ ወታደራዊ ድጋፍ ለመስጠት መወሰኗ እንደሚያሳስባቸው መግለጻቸውን ጠቅሶ፣ ሂውማን ራይትስ ፈርስት የተባለው ተቋም ዳይሬክተር ኔል ሂክስ “አሜሪካ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት ለሚታዩባት ግብጽ ድጋፏን ለመቀጠል መወሰኗ ለሰብዓዊ መብቶች መከበር ቅድሚያ አትሰጥም የሚል አደገኛ መልዕክት ሊያስተላልፍ ይችላል” ማለታቸውን ዘግቧል፡፡አሜሪካ ባለፈው አመት ተመሳሳይ ወር ለግብጽ የምትሰጠውን ድጋፍ በከፊል እንደምትጀምር ማስታወቋን ያስታወሰው ዘገባው፣ ግብጽ ከአሜሪካ ከፍተኛ ወታደራዊ ድጋፍ በማግኘት ከእስራኤል ቀጥላ በሁለተኛ ደረጃ ላይ እንደምትገኝም ጠቁሟል፡፡

Monday, 06 April 2015 08:58

የፍቅር ጥግ

ፍቅር ልዩ ቃል ነው፡፡ የምጠቀምበት ከልቤ ሲሆን ብቻ ነው፡፡ ቃሉን ደጋግማችሁ ስትሉት ይረክሳል፡፡
ሬይ ቻርልስ
ድንገት በጭጋጋማው የለንደን ከተማ ውስጥ አየሁሽ፡፡ ፀሐይዋ ሁሉን ስፍራ አድምቃው ነበር፡፡
ጆርጅ ገርሽዊን
ፍቅር እንደ ቧንቧ መክፈቻ ነው፤ ይዘጋል ይከፈታል፡፡
ቢሊ ሆሊዴይ
ከፍቅረኛህ ጋር ስትለያይ ጠቅላላ ማንነትህ ይፈራርሳል፡፡ ልክ እንደሞት ማለት ነው፡፡
ዴኒስ ቋይድ
ለሥራ ጊዜ አለው፡፡ ለፍቅር ጊዜ አለው፡፡ ከሁለቱ የሚተርፍ ሌላ ጊዜ የለም፡፡
ኮኮ ቻኔል
በዓለም ላይ ምርጡ ጠረን የምትወጂው ወንድ ነው፡፡
ጄኔፈር አኒስተን
ጀግንነት ሰውን ያለቅድመ ሁኔታ፣ ምላሽ ሳይጠብቁ ማፍቀር ነው፡፡
ማዶና
ፍቅር እንደ ጦርነት ሁሉ ለመጀመር ቀላል፤ ለመጨረስ ግን ከባድ ነው፡፡
ያልታወቀ ሰው
ሦስት ነገሮችን መደበቅ አይቻልም፡- ጉንፋን፣ ድህነትና ፍቅር፡፡
የአይሁዳውያን አባባል
ፍቅር ማለቂያ የሌለው ይቅር ባይነት ነው፡፡
ፒተር ኡስቲኖቭ
ፍቅር ነበልባል የመሆኑን ያህል ብርሃንም መሆን አለበት፡፡
ሔነሪ ዴቪድ ቶሪዮ
ፍቅር የሌላው ሰው ደስታ ለራስህ ወሳኝ የሚሆንበት ሁኔታ ነው፡፡
ሮበርት ሔይንሌይን
ፍቅር ሰውን ከራሱ ባርኔጣ ውስጥ ስቦ የሚያወጣ ምትሃተኛ ነው፡፡
ቤን ሄሽት

Monday, 06 April 2015 08:55

የሲኒማ ጥግ

ሥራውን ሰርተህ ሰዎች እንዲያዩልህ ትፈልጋለህ፡፡ ነገር ግን ሥራውን እየሰራሁ ሳለ ስለውጤቱ አላስብም፡፡ ፊልሙ ተወዳጅ ሆኖ ቦክስ ኦፊስ ቢገባ ወይም ከንቱ ቢሆን ግዴለኝም፡፡ ለእኔ ፊልሙ ተሰርቶ ከተጠናቀቀ በራሱ  ስኬት ነው፡፡ ሁሉም በየራሳቸው መንገድ ስኬት ናቸው፡፡
ጆኒ ዲፕ
የአማካዩ የሆሊውድ ኮከብ ተዋናይ ፍላጎት በአሜሪካዊ መደነቅ፣ በጣሊያናዊ መጠበስ፣ ከእንግሊዛዊ ጋር ትዳር መያዝና ፈረንሳዊ ፍቅረኛ መያዝ ነው፡፡
ካትሪን ሄፕበርን
ለወጣት ፊልም ሰሪዎች የምለግሰው ምክር፡- “ያለውን አካሄድ አትከተሉ፤ አዲስ ጀምሩ!” የሚል ነው፡፡
ፍራንክ ካፕራ
ፊልም ከሦስቱ ዓለም አቀፍ ቋንቋዎች አንዱ ነው፡፡ የቀሩት ሁለቱ ሂሳብና ሙዚቃ ናቸው፡፡
ፍራንክ ካፕራ
ለፊልም ፈተና መሄዴ ነው ብዬ ስናገር መላው ቤተሰቤ ከልቡ ነበር የሳቀው፡፡
ቪክቶሪያ አብሪል
ታላቅ የፊልም ተዋናይ እሆናለሁ፡፡ ይሄ የሚሆነው ግን መጠጥና ወሲብ ካልቀደሙኝ ብቻ ነው፡፡
ጄይ ፕሪሰን አለን
ተዋናይ ከሚሰራበት ፊልም የበለጠ ገዝፎ መታየት የለበትም፡፡
ክርስቲያን ቤል
ፊልምን በተመለከተ ሰዎች ብዙ ጊዜ የመጥፎ ማዕከላዊ ገፀ ባህርይ መልዕክትንና የፊልሙን መልዕክት ብዙ ጊዜ አይለዩትም፡፡ ግን ሁለት የተለያዩ ነገሮች ናቸው፡፡
ክርስቲያን ቤል
ሜክሲኮ ያገኘኋት አንዲት ሴት እንድፈውሳት ፈልጋ ነበር፡፡ እኔ ግን ማንንም መፈወስ አልችልም፡፡ እጄን ጭንቅላቷ ላይ አድርጌ፤ “ፊልሙን በማየትሽ አመሰግንሻለሁ” አልኳት፡፡
ጂም ካቪዜል

በኢጋ ሚዲያና ኮሙዩኒኬሽን አዘጋጅነት የሚቀርበው “ሰሙነ ህማማት የስነ ጽሑፍና የበገና ምሽት” የፊታችን ሰኞ ከቀኑ 11፡30 ሰዓት ጀምሮ በዋቢ ሸበሌ ሆቴል እንደሚካሄድ አዘጋጆቹ አስታወቁ፡፡
በዝግጅቱ ላይ አንጋፋና ወጣት ፀሐፍት፤ ግጥሞችንና ወጐችን በባህላዊ የሙዚቃ መሳሪያዎች እየታጀቡ ያቀርባሉ ተብሏል፡፡
በምሽቱ ከ20 በላይ የበገና ደርዳሪዎች በአንድ ላይ ተጣምረው በገና በመደርደር ዝግጅቱን እንደሚያደምቁም ተገልጿል፡፡ የዝግጅቱ አላማ ባህላዊ የሙዚቃ መሳሪያና ስነ - ጽሑፍ ያላቸውን ተዛምዶ ለማህበረሰቡ ማስገንዘብና ትኩረት እንዲሰጣቸው ማድረግ ነው ብለዋል - አዘጋጆቹ፡፡  

   ወጋገን ኮሌጅ በፊልም ሙያ ያሰለጠናቸውን ከ130 በላይ አንጋፋና ጀማሪ አርቲስቶች በዛሬው እለት ከጠዋቱ 3 ሰዓት ጀምሮ በአለም ሲኒማ አዳራሽ ያስመርቃል፡፡ በምረቃ ስነ ሥርዓቱ ላይ የዩኒቨርስቲ መምህራን፣ ታዋቂ አርቲስቶች እና ጥሪ የተደረገላቸው የመንግስት ባለስልጣናት ይገኛሉ ተብሏል፡፡ የምረቃ ፕሮግራሙን ይታደማሉ ተብሎ ከሚጠበቁ አርቲስቶች መካከል መሰረት መብራቴ፣ ይገረም ደጀኔ፣ ሸዊት ከበደ እና ሌሎችም ይገኙበታል፡፡

Monday, 06 April 2015 08:34

የፖለቲካ ጥግ

ወፍራም ደሞዝ ተከፋይ የአፍሪካ ፕሬዚዳንቶች!!

የደቡብ አፍሪካው ፕሬዚዳንት ጃኮብ ዙማ መደበኛ ትምህርት እንዳልተከታተሉ “አፍሪካ ክራድል” የተባለው ድረገፅ ሰሞኑን ይፋ ያደረገ ሲሆን “7 ቀለም ያልዘለቃቸው የአፍሪካ ፕሬዚዳንቶች” በሚል ባወጣው ዝርዝር ውስጥ ዙማን በአንደኝነት ነው ያስቀመጣቸው፡፡  ሰውየው ያልተማሩ መሆናቸው እምብዛም አልጐዳቸው፡፡ እንደውም ሳይጠቅማቸው አልቀረም፡፡  የዙማ ዓመታዊ ገቢ 270ሺ ዶላር (5ሚ.400ሺ ብር ገደማ) ሲሆን በአሁኑ ሰዓት በአፍሪካ ከፍተኛ ተከፋይ  ፕሬዚዳንት ናቸው፡፡ ዙማ ከዓለማችን 10 ከፍተኛ (Top 10) ተከፋይ ፕሬዚዳንቶች ውስጥ አንዱ ናቸው፡፡
አልጄሪያን እ.ኤ.አ ከ1999 ጀምሮ በመምራት የአገሪቱ አምስተኛ ፕሬዚዳንት የሆኑት አብደላዚዝ ቡቴፍሊካ ዓመታዊ ደሞዛቸው 168ሺ ዶላር ነው፡፡ ቡቴፍሊካ ሁለተኛው፤ ከፍተኛ ተከፋይ የአፍሪካ ፕሬዚዳንት ናቸው፡፡
ኡሁሩ ሙይጋይ ኬንያታ አራተኛው የኬንያ ፕሬዚዳንት ሲሆኑ ሥልጣን የተቆናጠጡት እ.ኤ.አ በ2013 ዓ.ም ነበር፡፡ ኬንያታ በዓመት 132ሺ ዶላር ያገኛሉ፡፡ በ2014 ዓ.ም በወር ይከፈላቸው የነበረውን 14ሺ ዶላር ወደ 11ሺ ዶላር እንዲቀነስ በማድረግ አርአያ ለመሆን ሞክረዋል፡፡ እንዲያም ሆኖ ግን ሶስተኛው የአፍሪካ ከፍተኛ ተከፋይ ፕሬዚዳንት ከመሆን ያገዳቸው ነገር የለም፡፡
ኮሞሮስን ከ2011 ዓ.ም ጀምሮ በመምራት ላይ የሚገኙት አይኪሊሎ ዲሆይኒኔ፤ በ115ሺ ዶላር ዓመታዊ ገቢ 4ኛው ከፍተኛ ተከፋይ ፕሬዚዳንት ሆነዋል፡፡ ሰውየው ስልጣን ሲይዙ ሙስናን ከአገሪቱ ለማጥፋት ቃል እንደገቡ ተዘግቧል፡፡ ዲሆይኒኔ ያጠኑት ፋርማሲስትነት ነው፡፡
ዴኒስ ሳሶ ንግዩሶ፤ ከ1997 ዓ.ም ጀምሮ የኮንጎ ሪፐብሊክ ፕሬዚዳንት በመሆን አገሪቱን  እየመሩ ይገኛሉ፡፡ በቅርቡ  “ግሎባል ዊትነስ”  እንደዘገበው፤ የፕሬዚዳንቱ ልጅ ዴኒስ ክሪስትል የአንድ ወር የግል ፍጆታ፣ የ80ሺ የኮንጎ ህፃናትን የኩፍኝ መከላከያ ክትባት ወጪ ይሸፍናል፡፡ የኮንጐው መሪ ዓመታዊ ክፍያ 110ሺ ዶላር ሲሆን 5ኛው ከፍተኛ ተከፋይ የአፍሪካ ፕሬዚዳንት ናቸው፡፡