Administrator

Administrator

Saturday, 22 November 2014 12:15

ፊታውራሪ እርጅና

ባለ ጋሻ ጀግሬው ሰልፍ የሚያምርለት፣
አጀቡ አስፈሪ ጦር የበዛለት፣
ሠራዊተ ብዙ ፊታውራሪ እርጅና፣
ረጋ ብሎ ይመጣል ሞት ያስከትልና፡፡
    ስሜት ሲደበዝዝ፣
አካል ሲቀዘቅዝ፣
ዕይታ ሲደክም፣
አእምሮ ሲያዘግም፣
አደብ ይገዛሉ ህዋሳት በመላ፣
ሰውነት ይበርዳል ላይሞቅም ላይፈላ፡፡
ሆድ ጠግቦ ላይበላ ጉረሮ እህል ላይውጥ፣
ጉልበት ላይሆንለት ጦርን ሮጣ ማምለጥ፣
ነገርን አስታውሶ ለመናገር ፈጥኖ፣
እንደ ቀድሞ አይሆንም ጠፍቷልና ተንኖ፡፡
ዕቅድና ዓላማ እርግፍ አርጐ ትቶ፣
በትዝታ መኖር ምሃት፣ ተስፋ ጠፍቶ፡፡
እንስት ተባዕትን፣ ተባዕት እንስትን፣
ላይፈቃቀዱ ያሰንፋል ስሜትን፡፡
ጣፋጩ መራር ነው የሞቀው ቀዝቃዛ፣
በስተርጅና ሁሉም ይሆናል ጐምዛዛ፡፡
        ተው እርጅና፣
        ብቻህን ና!
ይህ ሁሉ ሳያንስህ ስኳሩን፣ ግፊቱን፣
ሪሁን፣ ራስ ምታቱን፣ ውጋት፣ ቁርጥማቱን፣
ነጭናጫ መሆኑን መነዝነዝ ዕለቱን፣
በትንሽ ትልቁ ፈጥኖ መከፋቱን፣
አንጋግተህ ያመጣህ ጨካኝ ነህ እርጅና፣
በስንት ጣዕሙ ሞት ይገባው ምስጋና፡፡
ኧረ ተው እርጀና አንተ ጅራታም፣
ምነው ጓዝህ በዛ (ሆንክና/ሆንክብኝ?) ኮተታም!
    ተው እርጅና፣
    ብቻህን ና!
ጥሩ ስም የሰጠህ ንገረን ማነው?
እርጅና እያሉ የጠሩህ ምነው?
እስቲ ከሞት ጋራ ተነጋገሩና፣
ከነ ተከታይህ በአንድ ላይ ሁኑና፣
እናንት? ሁለታችሁ ስብሰባ ግቡና፣
ስምህን ለውጡ ተመካከሩና፡፡
ሌላ ስም ይውጣልህ ከሞት ያላነሰ፣
ሥራህ ቢበዛ እንጂ መች ከእሱ ቀነሰ?
እናም…. ይኸው ወቀስኩህ ላትሰማኝ ነገር፣
 (ከእለታት ቀን ቆጥረህ መከሰትህ ሳይቀር?)
በሥራ በስፖርቱ አካሌን አጥብቄ፣
እጠብቅሃለሁ (አልቀርም) ወድቄ፡፡
ጦሬን ይዤ መጣሁ ደረስሁ ብትለኝም፣
እኔ አለሁ፣ አንተም ና ሥጋት አይገባኝም፡፡
በል እንግዲህ እርጅና - በቸር ያገናኘን
እስከዚያው ድረስ፣
አንተም አርጅተህ ሙት
- ወደ ልጅነቴ እኔም ልመለስ፡፡
*    *    *
ከአምሳሉ ጌታሁን ደርሰህ
ኅዳር 2007 ዓ.ም

Saturday, 22 November 2014 12:12

ፊታውራሪ እርጅና

ባለ ጋሻ ጀግሬው ሰልፍ የሚያምርለት፣
አጀቡ አስፈሪ ጦር የበዛለት፣
ሠራዊተ ብዙ ፊታውራሪ እርጅና፣
ረጋ ብሎ ይመጣል ሞት ያስከትልና፡፡
    ስሜት ሲደበዝዝ፣
አካል ሲቀዘቅዝ፣
ዕይታ ሲደክም፣
አእምሮ ሲያዘግም፣
አደብ ይገዛሉ ህዋሳት በመላ፣
ሰውነት ይበርዳል ላይሞቅም ላይፈላ፡፡
ሆድ ጠግቦ ላይበላ ጉረሮ እህል ላይውጥ፣
ጉልበት ላይሆንለት ጦርን ሮጣ ማምለጥ፣
ነገርን አስታውሶ ለመናገር ፈጥኖ፣
እንደ ቀድሞ አይሆንም ጠፍቷልና ተንኖ፡፡
ዕቅድና ዓላማ እርግፍ አርጐ ትቶ፣
በትዝታ መኖር ምሃት፣ ተስፋ ጠፍቶ፡፡
እንስት ተባዕትን፣ ተባዕት እንስትን፣
ላይፈቃቀዱ ያሰንፋል ስሜትን፡፡
ጣፋጩ መራር ነው የሞቀው ቀዝቃዛ፣
በስተርጅና ሁሉም ይሆናል ጐምዛዛ፡፡
        ተው እርጅና፣
        ብቻህን ና!
ይህ ሁሉ ሳያንስህ ስኳሩን፣ ግፊቱን፣
ሪሁን፣ ራስ ምታቱን፣ ውጋት፣ ቁርጥማቱን፣
ነጭናጫ መሆኑን መነዝነዝ ዕለቱን፣
በትንሽ ትልቁ ፈጥኖ መከፋቱን፣
አንጋግተህ ያመጣህ ጨካኝ ነህ እርጅና፣
በስንት ጣዕሙ ሞት ይገባው ምስጋና፡፡
ኧረ ተው እርጀና አንተ ጅራታም፣
ምነው ጓዝህ በዛ (ሆንክና/ሆንክብኝ?) ኮተታም!
    ተው እርጅና፣
    ብቻህን ና!
ጥሩ ስም የሰጠህ ንገረን ማነው?
እርጅና እያሉ የጠሩህ ምነው?
እስቲ ከሞት ጋራ ተነጋገሩና፣
ከነ ተከታይህ በአንድ ላይ ሁኑና፣
እናንት? ሁለታችሁ ስብሰባ ግቡና፣
ስምህን ለውጡ ተመካከሩና፡፡
ሌላ ስም ይውጣልህ ከሞት ያላነሰ፣
ሥራህ ቢበዛ እንጂ መች ከእሱ ቀነሰ?
እናም…. ይኸው ወቀስኩህ ላትሰማኝ ነገር፣
 (ከእለታት ቀን ቆጥረህ መከሰትህ ሳይቀር?)
በሥራ በስፖርቱ አካሌን አጥብቄ፣
እጠብቅሃለሁ (አልቀርም) ወድቄ፡፡
ጦሬን ይዤ መጣሁ ደረስሁ ብትለኝም፣
እኔ አለሁ፣ አንተም ና ሥጋት አይገባኝም፡፡
በል እንግዲህ እርጅና - በቸር ያገናኘን
እስከዚያው ድረስ፣
አንተም አርጅተህ ሙት
- ወደ ልጅነቴ እኔም ልመለስ፡፡
*    *    *
ከአምሳሉ ጌታሁን ደርሰህ
ኅዳር 2007 ዓ.ም

አሀዱ ኣባይነህ የኪነ-ህንፃ ባለሙያ ነው፡፡ በሙያው ለአስራ ስምንት አመታት ሲሰራ ቆይቷል፡፡ በ90ዎቹ ዓመታት በዝቅተኛ ወጪ የዛፍ ላይ መኖሪያ ቤት ሰርቶ ነበር፡፡ በቅርቡ ደግሞ በአዲስ አበባ ከፈራረሱ ቤቶች ላይ ከተሰበሰቡ የተለያዩ ቁሳቁሶች እየሱስ በመባል በሚታወቀው አካባቢ እጅግ ውብ የሆነ ቤት ሰርቷል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ኤልሳቤት እቁባይ የኪነ-ህንፃ ባለሙያውን በሰራው ቤትና በአጠቃላይ በሙያው ዙሪያ አነጋግራዋለች፡፡


ከቤቶች ፍርስራሽ አዲስ ቤት የመገንባት ሃሳብ እንዴት መጣ?
ቤቱን የሰራሁለት ሰው ዶክተር ኤርሚያስ ሙሉጌታ ይባላል፡፡ ጥንታዊ ቁሶችን በጣም ይወዳል፡፡ እናም በከተማዋ ከሚፈርሱ ቤቶች ላይ መስኮቶች፣ በሮች፣ ሸክላዎች፣ የወለል ጣውላዎችና የደረጃ ድንጋዮችን ከገዛ በኋላ፣ በእነዚህ ቁሳቁሶች ቤት እፈልጋለሁ አለኝ፡፡
የሥራው ሂደት ምን ይመስላል?
የመጀመሪያው ስራ ቁሳቁሶችን መለየት ነበር፡፡ በብዛት ትላልቅ ቢሞች፣ በሮችና መስኮቶች ነበሩ፡፡ መስኮቶቹና በሮቹ ከተለያዩ ቦታዎች የተሰበሰቡ ናቸው፡፡ በመጀመሪያ እነሱን ወደ ንድፍ፣ ከዚያ ወደ ዲዛይን ለወጥኳቸው፡፡ የተሰበሰቡት በሮችና መስኮቶች ዲዛይኑ ላይ መለያ ተሰጥቷቸው ተቀመጡ፡፡ ቤቱን ዲዛይን አድርጌ ስጨርስ ደግሞ መስኮቶቹና በሮቹ በተሰጣቸው ስያሜ መሰረት እንዲገጠሙ ተደረጉ፡፡
የቁሳቁሶቹ አሰባሰብ እንዴት ነበር?
በየቦታው ቤት የሚያፈርሱ ሰዎች የዶክተር አድራሻ አላቸው፡፡ ቤት ሊያፈርሱ ሲሉ ደውለው እዚህ ቦታ ቤት ልናፈርስ ስለሆነ ናና የምትፈልገው ነገር ካለ ተመልከት ይሉታል፡፡ በነገራችን ላይ ይሄን ቤት ከሰራሁ በኋላ፣ በተመሳሳይ መልኩ ከፍራሽ ቤቶች በተሰበሰቡ ቁሳቁሶች ሌሎች ቤቶችንም ሰርቻለሁ፡፡
ከወጪ አንፃር እንዴት ነው?
ወጪው ጥሩ ነው፡፡ አዲስ ቁሳቁሶች ከመግዛት ይረክሳል፡፡ አንዳንዶቹ በሮች የተገዙት ስምንት መቶና ዘጠኝ መቶ ብር ነው፡፡ አዲሱ ይገዛ ቢባል ወደ 20 ሺ ብር የሚጠጋ ወጪ ይጠይቃል፡፡ ነገር ግን መስኮቶቹና በሮቹ ከተለያዩ ቤቶች ፍራሽ ላይ የተወሰዱ በመሆናቸው ቀለማቸው የተዘበራረቀ ነበር፡፡ ማፅዳቱና ወጥ የሆነ መልክ እንዲይዙ ማድረጉ ጊዜ ወስዷል፤ የተወሰነ ወጪም ጠይቋል፡፡ በሮቹና መስኮቶቹን ለማፅዳት በኦክሲጅን ቀለማቸው ተልጦ እንዲሸበሸብ ከተደረገ በኋላ፣ በብርጭቆ ወረቀት ታሽተው ቫርኒሽ ተቀብተው ነው ተመሳሳይ መልክ የያዙት፡፡ ሸክላዎቹም ሲመጡ ከሲሚንቶ ላይ ስለወጡ ነጭ ነበሩ፤ በብርጭቆ ወረቀት ታሽተውና ተቀብተው ነው ጥቅም ላይ የዋሉት፡፡ የተለያዩ አይነት ድንጋዮችንም ተጠቅመናል፡፡ ከአምቦና ከትግራይም አስመጥተናል፡፡
ከተለያዩ ቦታዎች የመጡ ቁሳቁሶች እንዴት ሊጣጣሙ ቻሉ?
 እዚህ ቤት ላይ ሸክላና ድንጋይ እንዲሁም ሸክላና እንጨት ተቀላቅለው ተሰርተዋል፡፡ መጣጣሙ የመጣው ሁሉም የተፈጥሮ ስለሆኑ ነው፡፡ እዚህ ቤት ላይ አልሙኒየም ብንከት አንድነቱ አይጠበቅም፡፡ እንጨትና ድንጋይ አብሮ ይሄዳል፡፡ ተፈጥሮም እንደዚያ ነው የቀላቀለቻቸው፡፡ ዛፍ አፈር ላይ ነው የሚበቅለው፤ ስለዚህ ሸክላና እንጨት ላይጣጣሙ አይችሉም፡፡ ውበት ግኡዝ ነገር አይደለም፡፡ የሃሳቦች ውሁድ ነው፡፡ አንድ የሚያምር የፅጌረዳ አበባ ሳይ ያማረበት ምክንያት ምንድን ነው ብዬ፣ የቀለም ውህደቱንና አወቃቀሩን እማርበታለሁ፡፡ ዛፍ ስናይም በጣም ያምረናል፡፡ ለምን ያምረናል ስንል ምናልባት ከተፈጠርን ጊዜ ጀምሮ ስናየው ስለኖርን ይሆናል፡፡ ዛፍ ውስጥ ግን የምንማራቸው የተፈጥሮ ህግጋት አሉ፡፡ የዛፍ ቅርንጫፍ የት ጋ እንደሚወጣ አናውቅም፤ ግርምት ነው፤ ስለዚህ ከዛፍ የግንድ አበቃቀል አግራሞት የሚፈጥሩ ክስተቶች ተምሬያለሁ፡፡ እዚህ ቤት ውስጥ ልክ እንደ ዛፍ ግንድ ግርምት የሚፈጥሩ ሊያደርጉ የሚችሉ ነገሮችን አስገብቻለሁ፡፡
ኪነ-ህንፃ ሳይንስ ነው አርት በሚል ስለሚደረገው ሙግት ምን ትላለህ?
ይሄ ፀሀይ ብርሀን ነው ሙቀት ብሎ እንደ መሟገት ነው፡፡ በጣም የተያያዙና የማይለያዩ ናቸው፡፡ ስለ አርት ስናወራ፣ አርቱ ያለ ሳይንሱ አይሆንም፡፡ ሳይንሱን ካየን ለአንድ ህንፃ ንፅህና አጠባበቅ የፍሳሽ ማስወገጃው በጣም አስፈላጊ ነው፡፡ ውሀ ሪሳይክል ማድረግ ወይም ማጠራቀም በጣም አስፈላጊ ነው፡፡ ብርሀን በጣም አስፈላጊ ነው፡፡ እዚህ ቤት በማታ መብራቶቹ በርተው ብትመጪ አሁን ከምታይው ጋር በምንም አይገናኝም፣ በጣም የተለየ ነው፡፡ እኛ ሳይንስ የምንለው በአብዛኛው ከቴክኖሎጂ አንፃር ነው፡፡ ብርሀንን በቀለም  እንረዳዋለን፡፡ ይህ ቤት የጠዋት ብርሀን ሲያርፍበትና የማታ ብርሀን ሲያርፍበት ለቤቱ የሚሰጠውና የሚፈጥረው ቀለም በጣም የተለያየ ነው፡፡
አርቱን ካየን ደግሞ አሁን ለምሳሌ እዚህ ቤት ብዙ ቁሳቁሶችን ተጠቅመናል፡፡ እነዚህ ቁሳቁሶች ኮተት እንዳይመስሉ ግን ብዙ ለፍተናል፡፡ በይዘት፣ በመጠን፣ በቀለም ወዘተ… እንዲጣጣሙ በማድረግ ውበቱ እንዲጠበቅ እናደጋለን ይሄ ጥበብ ነው፡፡ እርስ በእርስ ሊስማሙ በሚችሉ ቁሳቁሶች መስራት ለአይን ሻካራ የሆኑ ነገሮች እንዳይኖሩ ያግዛል፡፡ መስኮት የቤት አይን ነው፤ ስለዚህ ነው እያንዳንዱ የዚህ ቤት መስኮት ሲከፈት አይን ጥሩ እይታ ያለው ነገር ላይ እንዲያርፍ የተደረገው፡፡
ከተለመደው የቤት አሰራር ሂደት በተለየ መንገድ ነው ቤቱን የሰራኸው፡፡ ምን ዓይነት ስሜት ፈጠረብህ?
እንደዚህ ቤት ነፃ ሆኜ የሰራሁት ስራ የለም፡፡ ከባለቤቱ ጋር እየተወያየንና እየተስማማን ነው የሰራነው፡፡ በጣም ነፃነት ስለነበረኝ እጅግ ደስ እያለኝ ነው የሰራሁት፡፡ ህንፃ ልክ እንደ ልጅ ነው፡፡ የኪነ-ህንፃ ባለሙያውና የሚያሰራው ሰው እንደ አባትና ልጅ ናቸው፡፡ ሁለቱ የማይስማሙ ከሆነ ልጁ ጥሩ አይሆንም፡፡ ተስማምተው በደንብ መስራት ከቻሉ ውጤቱ ጥሩ ይሆናል፡፡ ባለሙያው ቤቱን አምጦ የሚወልድ ቢሆንም ባለቤትም ቤቱ ምን ያህል ስፋት ይኖረዋል፣ በጀቱ ምን ያህል ነው  ወዘተ… የሚለውን ይወስናል፡፡ ጥሩ ስራ ስትሰሪ መተማመኑ ይመጣል፡፡ ከዚያ ደግሞ ነፃነት ይገኛል፡፡ ይህን ቤት ስሰራ አስቤ ያላደረግሁት፣ ነገር ግን ሌላ ስራ ላይ አደርገዋለሁ ብዬ ያሰብኩት ነገር አለ፡፡ ይኸውም ከዩኒቨርስቲዎች ጋር ተነጋግሬ፣  የኪነ ህንፃ ተማሪዎች ሳይት ላይ መጥተው ከቁፋሮ ጀምሮ ባሉ ስራዎች ላይ እንዲሳተፉ ማድረግ ነው፡፡
ለምንድነው ተማሪዎቹን ማሳተፍ የፈለግኸው?
ለምሳሌ የዚህ ቤት ስራ አራት አመት ነው የፈጀው፡፡ ከቁፋሮ ጀምሮ በዚህ ቤት ስራ ላይ የተሳተፈ ተማሪ፣ ትምህርቱን ጨርሶ ሲወጣ ነገሮችን የሚያይበት አይን የተለየ ይሆናል፡፡ አንድ የተሞላ ኮንክሪት ድሮዊንግ ላይ በቃ አንድ መስመር ነው፡፡ እዚያ አንድ መስመር ላይ ግን ብዙ ነገሮች አሉ፡፡ ብረት፣ ኮንክሪት፣ ኮንዲዩት፣ ፎርም ወርክ፣ የመብራት ኬብል፣ የመብራት መስመር፣ አሸዋ፣ሲሚንቶ፡ ጠጠር እንዲሁም ከዚያ በላይ ደግሞ ወዛደሩና ወዛደሯ አሉ፡፡ ከእነሱ መሀል ምሳ የበላ አለ፤ ያልበላ አለ፣ ከቤት ሰራተኝነት ወጥታ ይሄ ይሻላል ያለች አለች፣ ወደ ቀድሞ ብመለስ ይሻላል በሚል እያመነታች ያለች ትኖራለች፤ሁለቱም ያልተመቻት ደግሞ አለች፡፡ አንድ ተማሪ ይህንን ሁሉ አውቆ ከት/ቤት ሲወጣ ብዙ ነገሮችን ይዞ ይወጣል፡፡
ግቢው እጅግ ባማሩ አበቦችም የተሞላ ነው፡፡ ብዙ ጥረት እንደተደረገበት ያስታውቃል…
አዎ፤ በግቢው ውስጥ 300 የአበባ ዝርያዎች አሉ፡፡ ወደፊት የዕፅዋት አጥኚ (ቦታኒስት) መጥቶ ስለ ዝርያቸው የሚገልፅ ነገር እንዲሰራ ዶክተር እቅድ ይዟል፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን ከብዙ ዓመታት በፊት ሰዎች እንደ ዛሬ ሳይሰለጥኑ በፊት፤ በአንዲት ትንሽ ከተማ አንድ እንደ ተዓምር የሚቆጠር ነገር ተፈጸመ፡፡ አንድ ቀንድ ያለው ጉጉት በአቅራቢያው ከሚገኘው ጫካ መጥቶ ከአንድ ሰው ግቢ ከሚገኝ የእህልና የከብት መኖ፣ እንዲሁም ጥራጥሬ መጋዘን  ውስጥ ይገባል፡፡ ሲነጋ እንዳይወጣ፤ ሌሎች ዶሮዎች ያዩኝና ልዩ ዓይነት ወፍ መሆኔን ሲረዱ ይጮሃሉ፡፡ ስለዚህ ዝም ብዬ ልቀመጥ ብሎ ወሰነ፡፡
ጠዋት የግቢው አሽከር ለከብቶች መኖ ሊወስድ ሲመጣ ጉጉቱን ጣራው አግዳሚ ላይ ሆኖ አየውና ደንግጦ “ጭራቅ! ጭራቅ!” እያለ እየጮኸ ወደ ጌትየው ሄዶ ተናገረ፡፡ የቤቱ ጌታም “አይ አንተ!  አንተንኮ እንደ እጄ መዳፍ ነው የማውቅህ፡፡ በሰፊ ሜዳ ቁራና ጥንብ - አንሣ የማባረር ልብ አለህ! አንዲት ጫጩት አንድ ጠባብ ቦታ ሞታ ብታይ ግን ወደዚያ ለመቅረብ ትልቅ ዱላ ፍለጋ ትሄዳለህ፡፡ ይሄን ጭራቅ ያልከውን እኔ ራሴ ሄጄ አየዋለሁ፡፡  ውሸት ቢሆን ወዮልህ!”
ጌትዬው  ወደ መጋዘን ገብቶ ሲያይ በድንጋጤ ተስፈንጥሮ ወጣ፡፡ ሮጦ ወደ ጎረቤቶቹ ሄዶ “ጎበዝ ማለቃችን ነው፡፡ አንድ አደገኛ ፍጡር ግቢዬ ገብቷል! ወጥቶ ወደ ከተማ ከገባ ህዝብ ማለቁ ነው፡፡ እንረዳዳና እዚሁ እርምጃ እንውሰድበት!” አለ፡፡
ወሬው ወዲያው ከመንደር መንደር በረረ፡፡ ከመንገድ መንገድ ሮጠ፡፡ ሰዉ ከፊሉ  ገጀራ፣ ከፊሉ ቆንጨራ፣  ከፊሉ ጦር፣ አካፋም፣ ማጭድም እያየዘ ወደግቢው ይመጣ ጀመር፡፡ ሰራዊት እንጂ አንድ ቀንዳም - ጉጉት ሊገድል የመጣ አይመስልም፡፡ በመጨረሻ ጭራሽ የከተማው ከንቲባ በሌሎች ሹማምንት ታጅበው መጡ፡፡ በተማው ለጥንቃቄ በየገበያው ምሽግ አሰርተዋል፡፡ አንድ የጎበዝ አለቃ ወደጉጉቱ ሄዶ ነበር፡፡ ድምፁን ሲሰማ በርግጎ ተመለሰ፡፡ ሌሎች ሁለት ሰዎች ሞከሩ፡፡
 ጉጉቱ ዓይኑን እያጉረጠረጠ በፍርሃት የሚያወጣው ድምፅ መብረቅ የመታቸው ያህል አስደግንጧቸው ዘለው ወጡ፡፡ በመጨረሻ አንድ መንዲስ የሚያህል ሰው፣ ያገሩ ጦረኛ ነው የሚባል ጀግና፣ ከጉጉቱ ሊተናነቅ ወስኖ መጣ፡፡ ከዛም በፉከራ ቃና “አንድን ጭራቅ “ጉድ! ጉድ!” በማለትና ዐይን ዐይኑን በማየት ልታባርሩት አትችሉም፡፡ ሁልሺም ቡከን ነሽ፡፡ ይሄን ጭራቅ ቀንዱን ይዤ ከጣራው ማውረድ አለብኝ! አለ፡፡ ሁለቱም የመጋዘኑ በር ብርግድ ብሎ ተከፈተ፡፡ አሁን ጉጉቱ ከጣራው  አግዳሚ እንጨት ላይ ተቀምጦ ቁልጭ ብሎ ይታያል፡፡ ጀግናው መሰላል አምጡልኝ አለ፡፡ መጣለት፡፡ ሰው ከፊሉ “ደፋር!” “አምበሳ!” አለው፡፡ ከፊሉ ይፀልይለት ጀመር፡፡
ጀግናው ወደ ጉጉቱ እየቀረበ ሄደ፡፡ ጉጉቱ ሁኔታውን በመጠራጠር የህዝቡን ጩኸት በመስማትና ምንም መውጫ እንደሌለው በማሰብ፤ ክንፎቹን አርገበገበ፡፡ ኩምቢውን ከፈተ፡፡ መንቆሩን ለጦርነት ያዘጋጀ መሰለ፡፡ ኩ-ፍ-ኩ-ኩ-ህ!” እያለ በፍጥነት መጮህ ጀመረ፡፡ ሰው “በለው!” “ያዘው” “አሳየው!” እያለ ከሥር ይጮህ ጀመር፡፡
“አይ ያገሬ ሰው! እኔ ያለሁበት ቦታ ቆመሽ ቢሆን አዳሜ ትንፍሽ አትይም ነበር!”
ጥቂት እርከን ለመውጣት ሞከረና ጀግናው፤ መርበትበት፣ መራድ ጀመረ፡፡ ቀስ እያለ በደረጃው ወረደ፡፡ ሰውም “አውሬው በትንፋሹ መርዞት ነው እንጂ የእኛ ጀግና እንዲህ ያለ ሰው አልነበረም፡፡ ለመሆኑ እንዲህ ያለ አውሬ ፊት ቆመን ህይወታችንን ማጥፋት አለብን እንዴ?” እያለ መንሾካሾክ ጀመረ፡፡ “ከተማችንን እንዳያጠፋ ምንድንነው የምናደርገው ማለት ቀጠለ?”  በመጨረሻ ከንቲባው መፍትሄ አመጡ፡፡
“ከመዘጋጃ ቤቱ ወጪ ተደርጎ ለመጋዘኑ ባለቤት የገንዘብ ካሳ እንስጥ፡፡ ለእህሉም. ለጭዱም፣ ለነዶውም መግዣ ይካካስለትና መጋዘኑ ከነአደገኛው አውሬ ይቃጠል! አሁን ለኢኮኖሚ የምናስብበት ጊዜ አይደለም!” ብራቮ ተባለ! ተጨበጨበ!
መጋዘኑ በአራቱም አቅጣጫ እሳት ተለቀቀበት፡፡ ምስኪኑ ወፍ በነበልባል ተለብልቦ አሰቃቂ ሞት ሞተ!
*          *           *
ነገሩ “አይ መሬት ያለ ሰው!” ያልነውን ያስታውሰናል፡፡ ነገርን በቅጡ አለማየት አሳቻ ፍፃሜ ላይ ያደርሰናል፡፡ ስለሆነም ወፍ አይተን ጭራቅ አየን እንላለን፡፡ አገሬው መንገኛ ከሆነ እንግዲህ  ይህንኑ ጭራቅ ጭራና ቀንድ ጨምሮለት ያልሆነ  ስዕል ፈጥሮ መዐት ይፈጥራል፡፡ የሰማህ ላልሰማህ የተባለ ይመስል እንደአዋጅ - ቃል ወሬ ይለፍፋል፡፡ ከዚያ ያገሩ ሹማምንት ያገባናል በሚል በተሳሳተው ነገር ላይ መመሪያ ይጨምሩበታል፡፡ መፍትሄ የማይፈጥር፣ ችግር ብቻ የሚያወራ ህዝብ ያልታደለ ነው፡፡ ኑሮ እንጉርጉሮ እንዳይሆን ማሰብ ያሻል! በወሬ የሚኖር ሰው፣ ነገር ያባብሳል እንጂ አንድ የመፍትሔ ጠጠር አይጥልም፡፡ ጎበዙን በለው! በለው! ለማለት የተፈጠሩ ይመስል፤ “በቅሎ ግዙ ግዙ አንድ አምሌ ላያግዙ!” ይሆናል ግርግሩ፡፡ ራሳችን በፈጠርነው የተሳሳተ ምስል “አስፈሪ! አደገኛ! …” እያልን፤ እሱኑም ፈርተን፤ ሌላውንም አስፈርተን፣ እሳት እንለኩሳለን! ይሄው ነው የአገራችን ፖለቲካ ነገረ - ሥራ!
“ጥፋታችንን አናምን፣ ሀጢያታችንን አንቀበል
ሁሌ ዝግጁና ፈጣን፣ በሌላው ላይ ለመቸከል
ደባ ነው መንገዳችን ሰርክ
ለእምዬ የአብዬን እከክ፣ በጥበብ ቅብ ለመላከክ!”
እንዳለው ገጣሚው፣ ራሳችን የሰራነውን ጥፋት በፈረደበት የበታች ወይም ቀን የጣለው ላይ መላከክ ነው ስራችን፡፡ ጥንት በአንድ አገር ዕምነት. ፍየል የዋህ ናት ትባል ነበር፤ አሉ፡፡
በሥርየት ቀን ቄስ ፍየሏ ጭንቅላት ለይ እጁን አድርጎ፣ የህዝቡን ሀጢያት ይናዘዛል፡፡ ጥፋት ሁሉ ወደ የዋህ ፍየል ይሄዳል፡፡ ይተላለፋል፡፡ ከዚያ ፍየሏ ወደ በረሀ ትነዳለች፡፡ እዛው ትቀራለች፡፡ የሰዉን ኃጢያት ሁሉ ይዛለት ጠፋች ማለት ነው፡፡ እንግዲህ Scapegoat የሚለው የፈረንጆች ቃል ከዚህ ነው የመጣው” ሊባል ይችላል፡፡ በሌላ ላይ ማሳበብ፣ በሌሎች ላይ መጫን ነው የአበሻ ኑሮ ዘዴ፡፡ ማዖ የባህል አብዮቱ ከሽፎ ክፉኛ ሲወድቅበት ምንም ይቅርታ አልጠየቀም፡፡ ይልቁንም በከፍተኛው የፓርቲ አመራር አባል ላይ ላከከ፡፡ የግል ፀሐፊውንም እንኳ ከወንጀሉ ነፃ አላደረጋትም፡፡ የእኛን ጨምሮ በየትም አገር በዘመቻም፣ በፕሬስም፣ በማፍረስም፣ በመገንባትም አንዳንድ የዋህ ፍየል አይጠፋም፡፡ ያውም እንደ ሰበብ ተደርጎ ሲቆጠር የማያጉረመርም ፍየል! ሌላ ምሣሌ:- ጥንት ጃንሆይ ለፀሐፊ ትዕዛዙ በቃል መመሪያ ይሰጡ ነበር አሉ፡፡ ያ መመሪያ ወደ ሥራ ተመንዝሮ ውጤቱ ሰናይ ከሆነ ምስጋናው ለጃንሆይ ይሆናል፡፡ ያልተሳካ ከሆነ ግን እርግማኑ ከፀሐፊ ትዕዛዝ ራስ አይወርድም፡፡ ዓለም የሥርዓተ- መላከክ (escapegoatism) ዓለም ነው፡፡
በተግባርና በወሬ መካከል ያለው ገደል - አከል ርቀት ሳይገደብ ለውጥ ማምጣት ከባድ ነው፡፡ ወሬ - ናፈቅ ትውልድ አገር ይሸረሽራል! “ጦር ከፈታው ወሬ የፈታው” የሚለው የአበው አነጋገር ቧልት አይደለም፡፡ “ወሬ ሲበዛ ጥበብ ዋዛ” እንደማለት ነው፡፡ ወሬ ሲበዛ ያልተሰራው ተሰራ፣ ያላሸነፈው አሸነፈ፣ ያልቀናው ቀና ማለትን ይወልዳል፡፡ ከጊዜ ብዛት ሰው ያምናል፡፡ ከዚያ ውሸት ሁሉ ዕውነት ይመስላል፡፡ “ወሬ ሲበዛ ጭቃ ከግድግዳ ተፍረክርኮ ይወድቃል፡፡ ሙቀጫም  ለጭፈራ ይነሳል” የሚለው የወላይታ ተረት የሚነግረን ይሄንኑ ነው!

15 ቢ. ብር የፈጁትን የነፋስ ተርባይኖች፤ በ5 ቢ.ብር የውሃ ግድብ መተካት ይቻላል
ከ10 ቢ. ብር በላይ ሃብት በከንቱ ባከነ፤ እንደ ዘበት በነፋስ ተወሰደ ማለት ነው
በረሃብተኛ ድሃ አገር፣ ይሄ ሁሉ ብክነት እብደት ነው? ወንጀል ነው? ወይስ ምን?
ግን፤ ወይ ነገሬ አላልነውም፤ ወይ አብረን አጨብጭበናል፤ ወይ በዝምታ ፈቅደናል
የግድብ ግንባታን የሚቃወሙ የአካባቢ ጥበቃ ቡድኖች፣ መጫወቻቸው አድርገውናል
ጠ/ሚ መለስ ዜናዊ፤ የአካባቢ ጥበቃ ቡድኖችን፤ “የድህነት ጠበቃ” ብለዋቸው ነበር

አገር    አመት    የነፋስ ተርባይኖች አቅም (ሺሜዋ)    በአመት ያመነጩት ሃይል (ሺ ጊዋሃ)    የተርባይኖቹ ብቃት
ጀርመን    2005    31    50    18%
ፈረንሳይ    2005    7.6    15    22%
ፖላንድ    2005    2.5    5.6    25%
ብሪታኒያ    2005    8.7    19    25%
ስፔን    2005    23    49    24%
ጣሊያን    2005    8    13.6    19%
አሜሪካ    2001    4    6.7    19%

በውሃ ግድብ የኤሌክትሪክ ሃይል የሚያመነጩ ጣቢያዎች ብቃትስ?    ከ40 – 50%
መንግስት ባለፈው ወር የተፈራረመውን ውል ጨምሮ፣ በነፋስ ተርባይን ኤሌክትሪክ የሚያመነጩ ሶስት ጣቢያዎችን ለማቋቋም 770 ሚሊዮን ዶላር ገደማ ሃብት አፍስሷል። ቀላል ገንዘብ አይደለም። ከ15.4 ቢሊዮን ብር በላይ ነው። የሶስቱ ጣቢያዎች ኤሌክትሪክ የማመንጨት አቅም ተደማምሮ ስንት እንደሆነ ደግሞ ተመልከቱ - 325 ሜጋዋት ብቻ ነው። በቃ፡፡ እና …ለዚህ ነው ያ ሁሉ ገንዘብ እየፈሰሰ ያለው? በገንዘብ መጫወት ይሉሃል፣ ይሄ ነው።
ለንፅፅር ያህል የህዳሴ ግድብ፤ ከነፋስ ተርባይኖቹ ጋር የሚመጣጠን የማመንጨት “አቅም” ለመፍጠር ምን ያህል ገንዘብ እንደሚፈጅበት ማስላት እንችላለን። ከግልገል ጊቤ ጣቢያዎች ጋር፣ አልያም ከተከዜ ወይም ከጣና በለስ ግድቦች ጋርም ማነፃፀር ይቻላል። የግድቦቹ አማካይ የግንባታ ወጪ፣ ዝቅተኛ ነው፡፡ ለአንድ ሜጋዋት 1.2 ሚሊዮን ዶላር አይደርስም። በዚህ ሂሳብ፣ ባለ 325 ሜጋዋት ማመንጫ ግድብ ለመገንባት፣ ቢበዛ ቢበዛ በአማካይ 390 ሚሊዮን ዶላር ቢፈጅ ነው (ማለትም፣ ከስምንት ቢሊዮን ብር በታች)። ለነፋስ ተርባይ ሲሆን ግን፣ ከ15 ቢሊዮን ብር በላይ!
ታዲያ፤ በአነስተኛ ወጪ፣ ከውሃ ሃይል ኤሌክትሪክ የሚያመነጩ ግድቦችንና ጣቢያዎችን መገንባት እየተቻለ፣ ያ ሁሉ ገንዘብ ለምን በነፋስ ተርባይን ይባክናል? እንዴ! ከሰባት ቢሊዮን ብር የሚበልጥ ልዩነትኮ፣ በጣም በጣም ብዙ ነው። በየእለቱና በየሰዓቱ መብራት እየተቋረጠ ስራ የሚስተጓጎለው፣ ፋብሪካዎች የሚከስሩት፣ ጨለማ ውስጥ የምናድረው፤ የኤሌክትሪክ ማሰራጫና ማከፋፈያ ተቋማት በማርጀታቸውና በማነሳቸው ነው ተብሎ የለ! በከንቱ የሚባክነውን ገንዘብ፣ ለዚህ ለዚህ ማዋል ይቻል ነበር።
“መቼም፣ የበርካታ ቢሊዮን ብር ሃብት በከንቱ እንዲባክን አይደረግም፤ አንዳች አሳማኝ ምክንያት መኖር አለበት” የሚል ሃሳብ ይመጣላችሁ ይሆናል። ‘ሃሳብ’ ሳይሆን፣ ‘ምኞት’ ብትሉት ይሻላል - ለዚያውም የማይጨበጥ ምኞት። አንዳችም አሳማኝ ምክንያት የሚያቀርብላችሁ አታገኙም። በነፋስ ተርባይን አማካኝት የኤሌክትሪክ ሃይል ማመንጨት፣ በጣም ከፍተኛ ወጪ እንደሚፈጅ...፣ በይፋ የሚታወቅ፣ በቁጥር የተሰላ፣ ማንም ጤናማ ሰው ሊክደው የማይችል ሃቅ ነው።
አስገራሚው ነገር፣ የነፋስ ተርባይኖች ችግር፣ ብዙ ገንዘብ መፍጀታቸው ብቻ አይደለም። ለካ አንዳንዴ የአገራችን ሰዎች “የባሰ አታምጣ” የሚሉት ወደው አይደለም! በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ እንደሚባለው ነው። በብዙ ወጪ የተተከሉት የነፋስ ተርባይኖች፣ የታቀደላቸውን ያህል ውጤታማ አይደሉም። ኤሌክትሪክ የማመንጨት ብቃታቸው አነስተኛ ነው። የአቅማቸውን 30 በመቶ ያህል እንኳ ብቃት የላቸውም። በውሃ ግድብ አማካኝነት ኤሌክትሪክ የሚያመነጩ ጣቢያዎች ግን፣ የአቅማቸውን 48 በመቶ በሚደርስ የላቀ ብቃት ኤሌክትሪክ እንደሚያመነጩ የኢትዮጵያ የበርካታ አመታት መረጃ ያሳያል። ይህን ለማረጋገጥና የአምና መረጃዎችን ለማየት፤ ብሔራዊ ባንክ በየሶስት ወሩ የሚያወጣቸውን ሪፖርቶች ተመልከቱ። አልያም ከአስር አመታት በፊት የነበረውን መረጃ፣ ከኤሌክትሪክ ሃይል ኮርፖሬሽን ሪፖርቶች ታገኛላችሁ።  
በአጭሩ፣ የነፋስ ተርባይን ጣቢያዎችን እና የውሃ ግድብ ጣቢያዎችን ስናነፃፅር፣ የነፋስ ተርባይኖች ኪሳራና ብክነት እጥፍ ድርብ መሆኑን በማያጠራጥር መንገድ መገንዘብ እንችላለን። የውሃ ግድብ ጣቢያዎች፣ የግንባታ ወጪ በግማሽ ያህል ቅናሽ ነው። ኤሌክትሪክ የማመንጨት ብቃታቸው ደግሞ ከነፋስ ተርባይኖች በ70 በመቶ ያህል ይልቃል።
እንዲያውም፣ ወደ ፊት የነፋስ ተርባይኖቹ ብቃት ይባስ እየቀነሰ መሄዱ አይቀርም። ለምን በሉ። አንደኛ ነገር፣ የነፋስ ተርባይኖች እድሜ በጨመረ ቁጥር፣ ብቃታቸው እየወረደ ይሄዳል። ሁለተኛ ነገር፣ ለነፋስ ተርባይኖች እጅግ በጣም ተስማሚ የሆኑ ነፋስ የሚበዛባቸውና የሚዘወትርባቸው ቦታዎች ናቸው አሁን ጥቅም ላይ የዋሉት። ወደ ፊት ተመሳሳይ ቦታ ለማግኘት አስቸጋሪ ነው። እናም የነፋስ ተርባይኖች ብቃት ከ25 በመቶ በታች መውረድ አይቀርለትም።
የነፋስ ተርባይኖች ብቃት 30 በመቶ እንኳ መድረስ ያልቻለው በኢትዮጵያ ብቻ አይደለም። በሁሉም የአውሮፓ አገራትና በአሜሪካ ጭምር፣ ላለፉት በርካታ አመታት በተጨባጭ የተመዘገበ መረጃ ነው። የነፋስ ተርባይን አፍቃሪ ተቋማት ራሳቸው የሚያቀርቡትን መረጃ ብቻ ልጥቀስላችሁ። የነፋስ ተርባይኖችን ለማስፋፋት መንግስታት ተጨማሪ ድጎማ መስጠት ይኖርባቸዋል እያለ ዘመቻ የሚያካሂደው የጀርመን ተቋም HSH NORDBANK፤ ባለፈው መስከረም ወር Sector Study WIND ENERGY በሚል ርዕስ ካቀረበው አመታዊ ሪፖርት የተወሰዱ ጥቂት መረጃዎችን እነሆ።
ከአመት በፊት በ2005 ዓ.ም፤ ጀርመን ውስጥ የሚገኙ ባለ 31ሺ ሜጋዋት የነፋስ ተርባይን ጣቢያዎች፣ 50ሺ ጊዋሃ ሃይል አመንጭተዋል ይላል ሪፖርቱ። ይህም ማለት የተርባይኖቹ ብቃት 18% ገደማ እንደሆነ ያረጋግጣል። የአሜሪካም ተመሳሳይ ነው። በ2001 ወደ አራት ሺህ ሜጋዋት የሚጠጋ አቅም ያላቸው የነፋስ ተርባይኖች በ19% የብቃት ደረጃ 7ሺ ጊዋሃ የኤሌክትሪክ ሃይል እንዳመነጩ፣ የአሜሪካ የኢነርጂ መስሪያ ቤት ገልጿል - እየተገባደደ ባለው የፈረንጆች አመት ባወጣው ሪፖርት።
የብሪታኒያ ትንሽ ይሻላል። የ8.7ሺ ሜጋዋት አቅም ያላቸው የነፋስ ተርባይኖች፣ በአመት ውስጥ ያመነጩት የሃይል መጠን 19 ሺ ጊዋሃ ነው። (ማለትም ተርባይኖቹ የሚሰሩት በ25% ብቃት ነው)። ምን አለፋችሁ? በየትኛውም የአውሮፓ አገር፣ በየትኛውም ጊዜ፣ የነፋስ ተርባይኖች ብቃት 30% ደርሶ እንደማያውቅ፤ HSH NORDBANK ያወጣው ሪፖርት ያስረዳል። ከተርባይኖቹ እድሜ ጋርም፣ ብቃታቸው ወደ ሃያ በመቶ ይወርዳል።
ነፋስ ተርባይኖች ብቃት፣ በአንዳንዶቹ አገራት ከ20 በመቶ ሊበልጥ የቻለው አንዳች ተአምረኛ ዘዴ ስለፈጠሩ አይደለም። በመሬት ላይ ሳይሆን በባህር ላይ የተተከሉ ተርባይኖችን ስለሚጠቀሙ ነው ልዩነት የተፈጠረው። ምድር ላይ ከሚተከሉት ተርባይኖች ይልቅ የባህር ላይ ተርባይኖች፤ በጥቂቱም ቢሆን የላቀ ብቃት አላቸው። እንዲያም ሆኖ፤ ብዙም ለውጥ የለውም። አንደኛ፣ የባህር ላይ ተርባይኖች ያን ያህልም የሚያስመካ ልዩነት አያመጡም። ሁለተኛ ነገር፤ ባህር ለሌላቸው እንደ ኢትዮጵያ ለመሳሰሉ አገራት፤ ትርጉም የለውም። ምን ለማለት ፈልጌ ነው? ነጋ ጠባ የአካባቢ ጥበቃ ቡድኖችና አጨብጫቢዎች ከሚለፍፉት ስብከት በተቃራኒ፤ የነፋስ ተርባይኖች ብቃት ውሎ አድሮ በተጨባጭ 20% ገደማ እንደሚሆን ለመግለፅ ፈልጌ ነው።
በውሃ ግድብ አማካኝነት የኤሌክትሪክ ሃይል የሚያመነጩ ጣቢያዎች ግን፣ ከብዙ አመታት አገልግሎት በኋላም በአማካይ 48 በመቶ ገደማ መሆኑን ደግሞ አትርሱ። ለዚህ ማረጋገጫ፣ ከኤሌክትሪክ ኮርፖሬሽንና ከብሄራዊ ባንክ የ2006 ዓ.ም ሪፖርቶች በተጨማሪ፣ ሌላ መረጃ ትፈልጉ ይሆናል። Study on the Energy Sector in Ethiopia በሚል በጃፓን ኤምባሲ የተዘጋጀውን የጥናት ሰነድ መቃኘት ትችላላችሁ፡፡ እስከ 2000 ዓ.ም ድረስ በነበረው መረጃ መሰረት፣ የኤሌክትሪክ ሃይል የሚያመነጩ ግድቦች በድምር “ባለ 670 ሜጋዋት” እንደነበሩ በማስታወስ፤ በአማካይ በአመት 2.84 ጊዋሃ ሃይል ያመነጩ እንደነበር ጥናቱ ይገልፃል። (የግድቦቹ ብቃት ከ48% በላይ ነበር ማለት ነው።) የአምና መረጃዎችን ብንመለከትም፣ ተመሳሳይ ውጤት እናገኛለን።    
የነፋስ ተርባይን ጣቢያዎችና የውሃ ግድብ ጣቢያዎች፤ ኤሌክትሪክ የማመንጨት ብቃታቸው እንዲያ የሚራራቀው ያለምክንያት አይደለም። የመኪና ሞተርን እንደ ምሳሌ በመውሰድ ልዩነቱን ለማሳየት ልሞክር። ሞተሩ የአቅሙን ያህል ለመስራት ነዳጅ ያስፈልገው የለ? የነፋስ ተርባይኖች፣ መንቀሳቀሻ ነዳጃቸው “ነፋስ” ነው። ለውሃ ግድብ ጣቢያዎች ደግሞ፤ ነዳጃቸው ውሃ ነው። እንዲህ የየራሳቸው “ነዳጅ” ቢኖራቸውም፤ የነዳጅ አጠቃቀማቸው ግን ይለያል። የነፋስ ተርባይኖች ነዳጃቸውን (ነፋስን) መቆጣጠርና ማጠራቀም አይችሉም። የነዳጅ መቆጣጠሪያና ማርሽ እንደ ሌለው መኪና ቁጠሩት - ለአቀበቱም ለቁልቁለቱም፣ ሲቆምም ሲጓዝም ነዳጁን ይጠቀማል። ነዳጅ ሲቋረጥበት፣ ከማጠራቀሚያ አውጥቶ መጠቀም አይችልም። ነዳጅ ሲያልቅበት በጀሪካን እስኪመጣለት ድረስ መኪናውን አቁሞ እንደሚጠባበቅ ሾፌር ማለት ነው። የውሃ ግድቦች ግን፤ የነዳጃቸው (የውሃ) መጠንን እየተቆጣጠሩ መልቀቅ፤ ብዙ የኤሌክትሪክ ሃይል በማያስፈልግበት ወቅትም ውሃውን ይዘው ማቆየትና ማጠራቀም ይችላሉ። የውሃ ግድብ ጣቢያዎች፤ የኤሌክትሪክ ሃይል የማመንጨት ብቃታቸው ከፍተኛ የሚሆነው በዚህ ዋና ምክንያት ነው።እዚህ ላይ፤ አንድ ቀላል ጥያቄ ቢነሳ አይገርምም። የውሃ ግድብ ጣቢያዎች ብቃት በእጥፍ የሚበልጥ ከሆነ፤ ወጪያቸው ደግሞ በግማሽ ያህል ቅናሽ ከሆነ ለምንድነው የነፋስ ተርባይን ጣቢያዎችን ለመገንባት ሃብት የሚባክነው? ወጪያቸው እጥፍ ነው፤ ብቃታቸው ደግሞ በግማሽ የወረደ መሆኑ እየታወቀ!
በነፋስ ተርባይኖች ምትክ 325 ሜጋዋት የሚያመነጭ ግድብ ቢገነባ ኖሮ፣ ወጪው በ7.6 ቢሊዮን ብር ያነሰ ይሆን ነበር። ከዚህም በተጨማሪ፣ የግድብ ሃይል ማመንጫ ብቃት 48% ገደማ ስለሆነ፤ በየአመቱ 1300 ጊዋሃ ሃይል ማመንጨት በቻለ ነበር። የነፋስ ተርባይኖች ግን፤ ወጪያቸው በእጥፍ ቢበልጥም፤ በየአመቱ የሚመነጩት ሃይል 800 ጊዋሃ ገደማ ብቻ ነው።ልዩነቱ እጥፍ ድርብ ነው። የነፋስና የግድብ ማመንጫ ጣቢያዎቹ “ባለ 325 ሜጋዋት” የሚል ስያሜ ቢለጠፍባቸውም፤ ወጪያቸውና ብቃታቸው በጣም ይራራቃል። የነፋስ ተርባይን ጣቢያዎች፤ ወጪያቸው ከፍተኛ፣ ብቃታቸው ደግሞ ዝቅተኛ ነው። የውሃ ግድብ ጣቢያዎች ደግሞ ወጪያቸው ዝቅተኛ፣ ብቃታቸው ግን ከፍተኛ። እንዳያችሁት፣ “ባለ 325 ሜጋዋት” የተሰኙት የነፋስ ተርባይኖች በአመት 800 ሜዋሃ ገደማ ብቻ ነው ማመንጨት የሚችሉት። የዚህን ያህል የኤሌክትሪክ ሃይል ለማመንጨትማ፤ ባለ 190 ሜጋዋት የግድብ ማመንጫ ጣቢያ መገንባት በቂ ነው - ለዚያውም ወጪው 230 ሚሊዮን ዶላር አይሞላም - ከ5 ቢሊዮን ብር በታች መሆኑ ነው። እንግዲህ አስቡት፤ ይህችኑ የሃይል መጠን ለማመንጨት ነው ከ15 ቢሊዮን ዶላር በሚበልጥ ወጪ ለነፋስ ተርባይን ጣቢያዎች  እየፈሰሰ ያለው። በሌላ አነጋገር፤ ከ10 ቢሊዮን ብር በላይ ሀብት በከንቱ እንዲባክን ተደርጓል። እብደት፣ ወንጀል ወይስ ምን? የጊዜ ጉዳይ እንጂ፤ በዚህ ብክነት ላይ የተሳተፉና የተባበሩ ሃላፊዎች ውሎ አድኖ ተጠያቂ መሆናቸው አይቀርም፡፡ እስከዚያው ግን መብራት በየሰዓቱ እየተቋረጠብን እንቀጥላለን፡፡ ለነገሩ፤ አስር ቢሊዮን ብር በከንቱ ለነፋስ ሲበተን እያየን ዝምታን የመረጥን ሰዎችስ፤ መብራት ሲቋረጥብን ቢውል ቢያድር ይገርማል፡፡ የእጃችንን ነው ያገኘነው፡፡  

በ 6 ወራት 8 አዳዲስ አውሮፕላኖችን አስገባለሁ ብሏል

የኢትዮጵያ አየር መንገድ በምዕራብ አፍሪካ አገራት የተቀሰቀሰው የኢቦላ ቫይረስ በፈጠረው ስጋት ምክንያት የመንገደኞች ቁጥር በመቀነሱ፣ በወር ከ8 ሚ. ዶላር በላይ ገቢ እያጣ እንደሆነ ሮይተርስ ትናንት ዘገበ፡፡
የአየር መንገዱን ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ተወልደ ገብረ ማርያምን ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ ኢቦላ ለአየር መንገዱ ከየትኛውም አለማቀፍ የኢኮኖሚ ቀውስ በበለጠ በእንቅስቃሴው ላይ ተጽዕኖ የሚፈጥር ተግዳሮት ሆኖበታል፡፡
ምንም እንኳን በአዲስ አበባ ከተማ የሚገኘው የአየር መንገዱ ዋነኛ ማዕከል፣ በኢቦላ ቫይረስ ከተጠቁት የምዕራብ አፍሪካ አገራት የረጅም ሰዓታት በረራ የሚወስድ ርቀት ላይ ቢገኝም፣ በሽታው በአየር መንገዱ ተጓዦች ቁጥር ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ መፍጠሩ አልቀረም ያሉት አቶ ተወልደ፤ ሁኔታው በመጪዎቹ ጥቂት ወራት ውስጥ እንደሚቀየርና የመንገደኞች ቁጥርም ወደነበረበት እንደሚመለስ ያላቸውን ተስፋ ገልጸዋል፡፡በአገራቱ የተቀሰቀሰው የኢቦላ ወረርሽኝ፣ በመላ አህጉሪቱ ከሚደረጉ በረራዎች በአብዛኞቹ ላይ ተጽዕኖ መፍጠሩንና በሽታው ለአፍሪካ አየር መንገዶች ዋነኛው ስጋት መሆኑንም ተናግረዋል፡፡
ኢቦላ ወደ አፍሪካ አገራት በሚጓዙ መንገደኞች ላይ ስጋት መፍጠሩን የጠቀሰው ዘገባው፤ በተለይም በእስያውያን  መንገደኞች ዘንድ ያለውን ፍላጎት እንዲቀንስ አድርጎታል፡፡ በዘርፉ የሚታዩ የገበያ ችግሮች እንዳሉ ሆነው፣ አየር መንገዱ የቀየሳቸውን የረጅም ጊዜ የዕድገት ዕቅዶች መተግበሩን እንደሚቀጥል ገልጸው፣ እስከ መጪው 2015 የመጀመሪያዎቹ ስድስት ወራት፣ 3 ቦይንግ 787-8 ድሪምላይነር አውሮፕላኖችን ጨምሮ 8 አዳዲስ አውሮፕላኖችን ገዝቶ በስራ ላይ እንደሚያሰማራ አስረድተዋል፡፡
በተያያዘ ዜና የኢትዮጵያ አየር መንገድ ሁለት ቦይንግ 777 የጭነት አውሮፕላኖችን ለመግዛት የሚውል የ41.4 ሚሊዮን ዶላር ብድር አይኤንጂ ካፒታል ከተባለ አሜሪካ የፋይናንስ ተቋም ማግኘቱን ከትናንት በስቲያ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡
የገንዘብ ብድሩ መገኘቱና አውሮፕላኖቹ መገዛታቸው፣ በአፍሪካ ትልቁ የጭነት አየር መንገድ ሆኖ የመዝለቅ ዕቅድ ለያዘው የኢትዮጵያ አየር መንገድ አቅምንና የአገልግሎት ጥራትን በማሳደግ ረገድ ትልቅ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክትም ተገልጿል፡፡

የዋሽንግተን የጤና ዳይሬክተር ጆክሴል ጋርሺያ
የዋሽንግተን ዲሲ ከተማ የጤና ዲፓርትመንት ዳይሬክተር ጆክሴል ጋርሺያ በከተማዋ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ሌሎች አፍሪካውያን በኢቦላ ምክንያት እየተገለሉ እንደሆኑ ዘ ዋሽንግተን ታይምስ ዘገበ፡፡
ስለ ኢቦላ በቂ ግንዛቤ የሌላቸው የከተማዋ ነዋሪዎች፣ በተለይ በታክሲ ሾፌርነት በመስራት ላይ የሚገኙ ኢትዮጵያውያንንና ሌሎች የአፍሪካ አገራት ዜጎችን እያገለሉ እንደሚገኙ የገለጹት ዳይሬክተሩ፤ አሽከርካሪዎቹ አፍሪካውያን እንደሆኑ ሲያረጋግጡ ቫይረሱን ያስተላልፉብናል በሚል ስጋት ከመኪና እንደሚወርዱ ተናግረዋል፡፡
የመገኛኛ ብዙሃን ሰራተኛ የሆነ አንድ ግለሰብ ኢትዮጵያውያንና ኤርትራውያን ወደ አሜሪካ ሲገቡ ለምን የኢቦላ ምርመራ አይደረግላቸውም የሚል ጥያቄ እንዳቀረበላቸው ያስታወሱት ዳይሬክተሩ፤ ከሁለቱ አገራት ዜጎች ጋር የእጅ ሰላምታ የማይለዋወጡ የከተማዋ ነዋሪዎች እንዳሉም ገልጸዋል፡፡
ዩኒቨርሳል ፒስ ፌዴሬሽን የተባለ መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት ባዘጋጀው ስብሰባ ላይ ተገኝተው ንግግር ያደረጉት ዳይሬክተሩ፤ የሌሎች የአፍሪካ አገራት ዜጎችም በዕለት ከዕለት እንቅስቃሴቸው በኢቦላ ሰበብ መገለል እንደሚደርስባቸው አስታውቀዋል፡፡
በዋሽንግተን ከሚኖሩ የሌሎች አገራት ዜጎች፣ ኢትዮጵያውያንና ኤርትራውያን ከፍተኛውን ቁጥር እንደሚይዙም ዘገባው ጨምሮ ገልጿል፡፡

ጋለሪያ ቶሞካ በትላንትናው እለት “ግልፅና ድብቅ ከብርድልብስ ስር” በሚል ርዕስ ለሁለት ወራት የሚቆይ የስዕል አውደ ርዕይ ከፍቷል፡፡ ለአውደ ርዕይ የቀረቡት የሰዓሊ ዘላለም ግዛው የስዕል ስራዎች ሲሆኑ ብዛታቸው 30 ነው፡፡ ሥዕሎቹ በማህበራዊ ህይወት ላይ የሚያተኩሩ እንደሆኑና በብርድልብስ የተሸፈኑ  ግለሰባዊ የውስጥና የውጭ ችግሮችን አጉልተው እንደሚያሳዩ ሰዓሊው ለአዲስ አድማስ ተናግሯል፡፡
ሰዓሊ ዘላለም ግዛው፤ በ1990 ዓ.ም በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ “አለ ፈለገ ሰላም የስነ ጥበብና ዲዛይን ት/ቤት” ዲፕሎማ እንዲሁም በ2003 ዓ.ም የመጀመሪያ ዲግሪ ያገኘ ሲሆን ከ20 ጊዜ በላይ በአገር ውስጥ አንድ ጊዜ ደግሞ በአየርላንድ ከሌሎች ሰዓሊዎች ጋር ስራዎቹን ለእይታ አብቅቷል፡፡ በግሉ  አውደ ርዕይ ሲያቀርብ የአሁኑ የመጀመሪያው እንደሆነም ለማወቅ ተችሏል፡፡

በዶ/ር ወሮታው በዛብህ የተዘጋጀውና ከ70 የሚበልጡ ሥራ ፈጣሪዎችን ታሪክ የሚያስቃኘው “ለራስ ማን እንደራስ” የተሰኘ መጽሀፍ ሰሞኑን ለንባብ የበቃ ሲሆን የፊታችን ረቡዕ ከቀኑ 10 ሰዓት ጀምሮ በአምባ ሆቴል ይመረቃል፡፡ መፅሀፉ በራስ ፈጠራ እንዴት መለወጥ እንደሚቻልና በመፅሀፉ የተካተቱ ከ70 በላይ ሰዎች እንዴት እንደተለወጡ የተርካል ተብሏል፡፡ በምረቃው ዕለት የጂኒየስ ማሰልጠኛ ተቋም ሰልጣኞች ምረቃ፣ የስኬታማ ሰዎች ልምድና ሌሎች ፕሮግራሞች እንደሚካሄዱ ተጠቁሟል፡፡ መፅሀፉ በ60 ብር ለገበያ የቀረበ ሲሆን የመፅሀፉ አዘጋጅ በሥራ ፈጠራና ብልፅግና ዙሪያ በርካታ መፃህፍትን ለንባብ ማብቃታቸው ይታወቃል፡፡

በወጣቱ ገጣሚ አያሌው እውነቴ የተጻፈውና በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች ዙሪያ የሚያጠነጥኑ ከ65 በላይ ግጥሞችን የያዘው “ቁምታም ጾም”  የተሰኘ የግጥም ስብስብ መጽሃፍ፣ ከትናንት ጀምሮ በገበያ ላይ መዋሉን ገጣሚው ለአዲስ አድማስ ገለጸ፡፡
92 ገጾች ያሉት “ቁምታም ጾም” የግጥም ስብስብ መጽሃፍ፣ በአዲስ አበባና በክልል ከተሞች በሚገኙ የመጽሃፍት መደብሮችና በአዟሪዎች በ42.50 ብር እየተሸጠ ሲሆን፣ ለውጭ አገራት የመሸጫ ዋጋው 9 የአሜሪካ ዶላር ነው፡፡
መጽሃፉ በቅርቡ በአዲስ አበባ፣ በባህር ዳር እና በደብረ ማርቆስ በሚካሄዱ የስነ-ጥበብ ዝግጅቶች በይፋ እንደሚመረቅ የገለጸው ገጣሚው፣ በቀጣይም ለህትመት የተዘጋጁ ሌሎች የግጥምና የወግ ስብስብ ስራዎችን ለአንባብያን እንደሚያበቃ ገልጧል፡፡
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የስነ-ጽሁፍ ተማሪ በነበረበት ወቅት፣ በዩኒቨርሲቲው ባህል ማዕከል የተለያዩ የስነ-ጽሁፍ ስራዎችን በማቅረብ የሚታወቀው ገጣሚው፣ ከ17 አመታት በፊትም ለህትመት የመጀመሪያ ስራው የሆነውን “የበረከቱ አስኳል” የተሰኘ የአጫጭር ልቦለዶች ስብስብ መጽሃፍ ለንባብ አብቅቷል፡፡