Administrator

Administrator

በኢትዮጵያውያን የዲሞክራሲ እና የነፃነት ትግል ላይ ተንተርሶ የተፃፈው “የአሲምባ ፍቅር” መጽሐፍ ዛሬ እንደሚመረቅ ሜሮኢ መልቲሚዲያ አስታወቀ፡፡ 448 ገፅ ያለውን መጽሐፍ የደረሱት ካህሳይ አብርሃ ብስራት ናቸው፡፡ በኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ፓርቲ እና ግንባር (ኢህአፓ/ኢህአሠ) ሁለንተናዊ እንቅስቃሴ ላይ ተመስርቶ የተፃፈው መጽሐፍ የሚመረቀው መስቀል አደባባይ በሚገኘው የቀይ ሽብር ሰማዕታት ብሔራዊ ሙዚየም ነው፡፡ “የአሲምባ ፍቅር” በ100 ብር እየተሸጠ ነው፡፡ በሌላ በኩል “ውጥንቅጥ” የተሰኘው የግጥም መጽሐፍ ነገ እንደሚመረቅ ገጣሚው አስታወቀ፡፡ ባምቢስ አካባቢ በሚገኘው ትልቁ ዮርዳኖስ ሆቴል የሚመረቀውን የግጥም መጽሐፍ የፃፈው ዮርዳኖስ ፍቃዱ ተክለማርያም ነው፡፡

በአስራት አብርሃም የተሰናዳውና “ፍኖተ ቃየል” በሚል ርእስ “የኢትዮጵያን ፖለቲካ ሽርፍራፊ ገፆች” የሚያሳየው መጽሐፍ ለንባብ በቃ፡፡ 199 ገፅ ያለው መጽሐፍ የተቃዋሚ ኃይሎችን አሰላለፍ፣ የርእዮተዓለማዊ ትግልን፣ ሕወሓትንና ሌሎችን የተመለከቱ ርእሰ ጉዳዮች አካቷል፡፡ የመጽሐፉ መሸጫ ዋጋ 45 ብር ነው፡፡ አዘጋጁ አቶ አስራት ካሁን ቀደም “መለስ እና ግብፅ”፣ “ከአገር በስተጀርባ” እና “ጎበዝ ተማሪ የመሆን ምስጢር” በተሰኙ መጻሕፍቶቻቸው ይታወቃሉ፡፡

“ኬሮ” የተሰኘው የድምፃዊት ቢጢቅ እምላዕሉ የሙዚቃ አልበም ለገበያ ቀረበ፡፡ አስራ አራት ዘፈኖች የተካተቱበት አልበም መጠርያ ወላይትኛ ሲሆን አስሩ ዘፈኖች የአማርኛ፣ አራቱ ዘፈኖች ደግሞ የእንግሊዝኛ ናቸው፡፡ ሉሽስ መልቲ ፕሮዳክሽን አሳትሞ አምባሰል ሙዚቃ ቤት እያከፋፈለ የሚገኘውን አልበም ግጥሞች ማትያስ ይልማ፣ ዲጄ ዊሽ፣ ቤቲ ሮክ፣ ዳዊት ወርቁና ሌሎችም የፃፉት ሲሆን ዜማው በማትያስ ይልማ ተዘጋጅቷል፡፡ ሙዚቃውን ያቀናበሩት ደግሞ አቤል ጳውሎስ እና ኬኒ አለን ናቸው፡፡

በአዲስ አበባ የሚገኙ ወጣቶች የሙዚቃ ምትን በመጠቀም መልእክት ማስተላለፍ በሚቻልበት መንገድ ሥልጠና ተሰጣቸው፡፡ ለሃያ ወጣቶች ለአስር ቀናት የተሰጠው ስልጠና በኢትዮጵያ ሲካሄድ የመጀመርያው መሆኑን ሥልጠናውን ያስተባበረው ኢንትራሄልዝ ኢንተርናሽናል - ኢትዮጵያ አስታውቋል፡፡ “ቢት ሜኪንግ ላብ” በተሰኘ በጀርባ ቦርሳ ሊያዝ የሚችል የሙዚቃ ስቱዲዮ በመጠቀም ስልጠናውን የሰጡት በአሜሪካ የሰሜን ካሮላይና ዩኒቨርሲቲ የሙዚቃ ፕሮፌሰሮች እና የተንቀሳቃሽ ስቱዲዮው መስራቾች ናቸው፡፡ በጤና ላይ የሚሠራው ኢንትራሄልዝ እና የዩኒቨርሲቲው የሙዚቃ ፕሮፌሰሮች ቀጣይነት ያለው ሥልጠና የወጣቶችን የሙዚቃ ክህሎት በማዳበር ወጣቱን በተዋልዶ ጤና፣ ኤችአይቪ/ኤድስ፣ በእናቶችና ሕፃናት ጤና እና በሌሎችም ማህበራዊ ዘርፎች የምት ሙዚቃ በመጠቀም ማስተማር እንደሚቻል ያሳየንበት ነው ብለዋል፡፡ ተማሪዎቹ ከትናንት ወዲያ ኮከበ ጽባሕ አካባቢ በሚገኘው የኢንትራሄልዝ ግቢ ሲመረቁ ለማስተማርያ የመጡት ተንቀሳቃሽ ስቱዲዮዎች ከወጣቶች ጋር ለሚሰሩት ለሚዩዚክ ሜይደይ ኢትዮጵያና “ሴቭ አወር ጀነሬሽን” ለተባለ ድርጅት ተለግሰዋል፡፡

  • የኢትዮጵያ ህዝብ ለእግር ኳስ ያለው ፍቅር የሚደንቅ ነው---
  • ዘፈኑ ለሚቀጥለው የእግር ኳስ ድል እንደሚደመጥ ተስፋ አለኝ--
  • ለህዝብ መንደርደሪያ እና ቀብድ ሰጥቼ ከአስር ቀን በኋላ እሄዳለሁ---

ኑሮውን በአሜሪካ ቨርጂኒያ ያደረገው ድምፃዊ ይሁኔ በላይ፣ ለዜማ ደራሲው አበበ መለሰ የመታከሚያ ገንዘብ ማሰባሰቢያ ኮንሰርት ላይ ለመሳተፍ ባለፈው ሰሞን ነው ወደ ኢትዮጵያ የመጣው፡፡ የመጣበትን ጉዳይ ከፈፀመ በኋላ ያገኘችው የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አበባየሁ ገበያው፣ ከድምፃዊው ጋር በሙያው በትምህርቱ፣ በአሜሪካ ኑሮውና በኢንቨስትመንቱ ዙሪያ ሰፊ ቃለምልልስ አድርጋለች፡፡
እንድታነቡት ተጋብዛችኋል;

 በህመም ላይ ለሚገኘው የዜማ ደራሲ አበበ መለሰ የመታከምያ ገንዘብ ለማሰባሰብ ባለፈው ቅዳሜ በላፍቶ ሞል በተዘጋጀው “ውለታ ኮንሰርት” ላይ ተሳትፈሃል፡፡ ቀደም ሲልም በአሜሪካ ከሌሎች ሙዚቀኞች ጋር ኮንሰርት እንደሰራችሁለት ሰምቻለሁ፡፡ እስቲ ጨዋታችንን በዚህ እንጀምር--- 

እስራኤል አገር ለኮንሰርት ሄጄ ነው ‹‹አቤ ታሟል›› የሚል ወሬ የሰማሁት፡፡ እኔ ካየሁት በኋላ የአቤን ጉዳይ ሌሎች አድናቂዎቹና የኢትዮጵያ አርቲስቶች እንዲሰሙና የአቅማቸውን እንዲያደርጉ ሚል እንደ ጓደኛም፣ እንደ ጋዜጠኛም አድርጎኝ --- በምን ሁኔታ ላይ እንደሚገኝ በቪዲዮ ቃለመጠይቅ አደረግንለትና በዩቲዩብ ለቀቅነው፡፡ ያኔ ነው እነ ሃይልዬ ለአቤ የገንዘብ ማሰባሰቢያ ኮንሰርት ለማዘጋጀት ማሰባቸውን የነገሩኝ፡፡ የገንዘብ ድጋፍ ማድረግ ለሚሹ ወገኖች የባንክ አካውንት ከፍተው ስለነበረም የአካውንቱን ቁጥር ከቃለምልልሱ ጋር አካተትኩት፡፡ ሌሎች ሚዲያዎችም መረጃውን እየወሰዱ ማስተላለፍ ጀመሩ፡፡
ከዛ በኋላ አሜሪካ ያሉትን አርቲስቶች አቀናጅተን ትንሽ ገንዘብ ማሰባሰብ ነበረብን፡፡ እዛ ያለው የስራ ጫናና ኑሮ ደግሞ በጣም አስቸጋሪ ነው፡፡ በአሜሪካ ከራስ አልፎ ጊዜን ለሰው መስጠት ትንሽ ይከብዳል፡፡ ሆኖም እንደምንም ብዬ አርቲስቶች በማሰባሰብ ኮሚቴ አቋቋምንና ተወያይተን ‹‹መዓዛ ሬስቶራንት›› ውስጥ የሙዚቃ ዝግጅት ለማቅረብ ተስማማን፡፡ አንዳንድ ጉዳዮች ሲኖሩን እዚያ ሬስቶራንት ውስጥ ነው የምንሰራው፡የሬስቶራንቱ ባለቤት እንደዚህ አይነት ጉዳዮች ሲኖሩ ትተባበራለች፡፡
በእዚህ ኮንሰርት ላይ የተሳተፉት እነማን ነበሩ? ምን ያህል ገቢስ ተገኘ?
የመግቢያ ዋጋው 25 ዶላር ነበር፡፡ እሱን ለመርዳት ብለው ትኬት ቆርጠው የገቡም በጥሪው ገንዘብ የሰጡም አሉ፡፡ አበበን ለመርዳት የተቻለውን ያህል ተረባርበናል፡፡ በዝግጅቱ አርቲስት መሃሙድ አህመድ ነበረበት፡፡ ሌሎችም በርካታ ሙዚቀኞች ተሳትፈዋል፡፡ ከኮሚቴው አባላት መካከል ገጣሚ አለምጸሃይ ወዳጆ፣ ጋዜጠኛ አበበ ፈለቀ፣ ፀሃይ ካሳ፣ ደሳለኝ መልኩ፣ ዳምጠው(ተወዛዋዥ) ወደ አስር ገደማ ይሆናሉ፡፡ ከቦታው ጥበት አንፃር ብዙ ታዳሚዎች አልነበሩም፡፡ ኮንሰርቱን ትልቅ አዳራሽ ውስጥ ብናደርገው ኖሮ …ችግሩ ግን አሜሪካ ሰፊ አዳራሽ ለመከራይት ክፍያው ብዙ ነው፡፡ እንደውም ገቢውን በሙሉ እንዳይወስደው በመፍራት ነው በዚያ መልኩ እንዲሆን የመረጥነው፡፡ ከኮንሰርቱ 12 ሺ 500 ዶላር (212 ሺ 500 ብር ያህል) ተገኝቷል። የገንዘብ ማሰባሰቢያ ኮንሰርቱ አሁንም ይቀጥላል። አበበ ህክምናውን ለማጠናቀቅ የሚያስችል ገንዘብ እስኪያገኝ ድረስ ህይወቱን ለመታደግ ጥረታችንን እንቀጥላለን፡፡ አርቲስቶች በዚህ ተስማምተን ነው የተለያየነው፡፡
ከሳምንት በፊት ደግሞ ከዚሁ አርቲስት ገንዘብ ማሰባሰቢያ በተዘጋጀው ‹‹ውለታ ኮንሰርት›› ላይ ለመሳተፍ ወደ ኢትዮጵያ መጣህ–
አዎ ስመጣ ሙዚቀኞች ጥናት ላይ ነበሩ። ፖስተር ሁሉ ተዘጋጅቷል፡፡ እኔ እንደምኖር ስላልታወቀ ለህዝብ አልተገለፀም ነበር፡፡ ሆኖም በሰዓቱ ደርሼበታለሁ፤ እናም ሙዚቀኞች የ‹‹ዘገሊላ ዕለት›› የሚለውን ሙዚቃዬን አጠኑልኝና ደስ ብሎኝ ኮንሰርቱ ላይ ተጫወትኩ፡፡
ከአሁኑ ኮንሰርት ውጪ ኢትዮጵያ ውስጥ ኮንሰርት ሰርተህ አታውቅም--- ለምንድን ነው?
በአሁኑ ኮንሰርት እንደ ሰርፕራይዝ ነው የቀረብኩት፡፡ ህዝቡ ናፍቆኝ ስለነበረ በዚያች አጭር ጊዜ ውስጥ ከእስክስታውና ከዘፈኑ ጋር ተዳምሮ ደስታዬን እጥፍ ድርብ አድርጎልኛል፡፡ በእውነቱ በጣም ነው የተደነቅሁት---እንዴት ደስ አለኝ መሰለሽ---የኢትዮጵያ ህዝብ ሰው ማዳን የሚችል..ፍቅር የሆነ… አንቺ ምን ዓይነት ህዝብ ነው፡፡ በጣም ነው የተደሰትኩ---.ለሙዚቃ ያለው ፍቅር..እንባዬ ሁሉ ነው የመጣው..ቦታው ጢም ብሎ ሞልቶ ነበር፡፡ ታዳሚው ይጫወታል --- ይጨፍራል-- ይደሰታል…ይሄ እንግዲህ በአዲስ አበባ የመጀመሪያዬ ኮንሰርት ነው፡፡ መቼም ያየሁት ድባብ ልዩ ነበር፡፡ ህዝቡ ከእኔ ጋር በጣም ሲዘል፣ ሲጨፍር ነው ያመሸው፡፡ አይተሽው አይደል--
አዎ አይቼዋለሁ፡፡ እኔ የምለው-- አበበ መለሰ ለአንተ ዜማ ሰጥቶሃል እንዴ?
አልሰጠኝም፡፡ ግን አበበ ይሄ ሲያንሰው ነው። ከዚህ በላይ ሊደረግለትና፣ ብዙ መስዋዕትነት ሊከፈልለት የሚገባው አርቲስት ነው፡፡..
እንግዲህ ‹‹ውለታ ኮንሰርት›› አስፈንድቆኛል ብለሃል፡፡ ወደፊትስ እዚህ መጥተህ ኮንሰርት ለማቅረብ አላሰብክም?
ለአዲስ አመት አዲሱን ሙሉ አልበሜን ለማድረስ ዝግጅቴን አጠናቅቄአለሁ፡፡ በአገኘሁት አጋጣሚ ቀን ማታ ሳልል ግጥምና ዜማዎችን እያሰባሰብኩ ነው፡፡ በነገርሽ ላይ ባለፈው እሁድ ኢትዮጵያ ከደቡብ አፍሪካ ጋር ያደረገችውን ጨዋታ ተመልክቼ በጣም ነበር ደስ ያለኝ፡፡ ከድሉ በኋላ ስቱዲዮ ገብቼ ከአዲሱ ስራዬ ውስጥ ለአንድ ጉዳይ ያዘጋጀሁት ዘፈን ነበር --- ከእርሱ ላይ ቆረጥ ቆረጥ አድርጌ ለኢትዮጵያ ህዝብ ‹‹የእንኳን ደስ ያላችሁ›› ዜማ ሰርቼአለሁ፡፡
እስኪ ከዘፈኑ ግጥም ቀንጨብ አድርገህ ንገረን--
‹‹ዛሬ ነው ዛሬ ፋሲካ ነው ደስታ ነው ዛሬ
እንኳን ደስ አለሽ ኢትዮጵያ ሃገሬ››
የሚልና ተጫዋቾቹን የሚያወድስ ነው፡፡ ይሄን ዜማ ሌሊቱን ስንሰራ አድረን ነው የጨረስነው፡፡ የሙዚቃ ባለሞያዎች እንቅልፍ አጥተው ከእኔ ጋር አድረዋል፡፡ ግጥሙ የፀጋዬ ደቦጭ ሲሆን ዜማው የእኔ ነው፡፡ እነ አበበ ብርሃኔ፣ ሄኖክና ሌሎች ጓደኞቼ አብረውኝ ነበሩ፡፡ የኢትዮጵያ ህዝብ ለኳስ ያለው ፍቅር የሚደንቅ ነው፡፡ በባህላችን ደግሞ ድል ሲገኝ ‹‹እንኳን ደስ ያላችሁ ›› የመባባል ነገር ስላለ ነው ያንን ሙዚቃ የሰራሁት፡፡ እና ሌሊት ስንሰራ አድረን..ጠዋት ሲዲውን ለሚዲያ ልንሰጥ ስንል ግን ሌላ ነገር ተፈጠረ፡፡ አስደንጋጭ ዜና ሰማን። የእኛም ዘፈን ለጆሮ ለመብቃት ሳይታደል ቀረ፡፡ ዞሮ ዞሮ ውጤቱ ቡድናችን ለወደፊቱ ያለውን ተስፋ ጠቋሚ ነው፡፡ በተጨዋቾቻችንም እንኮራለን፡፡ ዘፈኑ ለሚቀጥለው ተመሳሳይ ድል እንደሚደመጥ ተስፋ አለኝ፡፡
አንድ ጊዜ ስትናገር--- ዘፈኖቼ ሳላስበው ከባህላዊ ወደ ዘመናዊነት እየወሰዱኝ ነው ብለህ ነበር፡፡ በአዲሱ ስራህስ?
በአዲሱ አልበም ባህላዊም ዘመናዊም ዘፈኖች ይካተታሉ፡፡ ‹‹የዘገሊላ እለት››፣ ‹‹አውማ››፣ ‹‹ዘንገና››--ሁሉም ነገሮች አሉበት፡፡ አቅሜ የፈቀደውን ያህል ጣፋጭ ዜማዎች ለህዝብ ለማድረስ እየሰራሁ ነው፡፡ ባህላዊ ነገሩ ቅድሚያ ተሰጥቶት ነው እየተሰራ ያለው.. አድማጮቼ በአዲሱ ስራዬ ትደሰታላችሁ ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ ስራዎቹ ባህላዊም ዘመናዊም ናቸው። ለአዲስ ዓመት የሚወጣ ሙሉ ካሴትና በቅርቡ የሚለቀቅ ነጠላ ዜማ አለኝ፡፡ መንደርደሪያ እና ቀብድ ሰጥቼ ከአስር ቀን በኋላ እሄዳለሁ፡፡
አባትህም ድምፃዊ ነበሩ ይባላል---እንደውም የአንድ ዘፈን ግጥም እንደሰጡህ ሰምቻለሁ---
አባቴ ከገጠር እየተመላለሰ ነበር የሚያየን፡፡ አባቴንም ሆነ ትልልቅ ሰዎች ወደ እኛ ቤት ሲመጡ መጠየቅ ደስ ይለኝ ነበር፡፡ አባቴንም እጠይቀው ነበር፡፡ ‹‹ለፍቅር…ለወደዳችኋት ልጅ፣ ለፋሲካም ሆነ ለገና በዓል ምን እያላችሁ ነው የምትዘፍኑት›› ብዬ ስጠይቀው፤
‹‹የዛሬን እኔ አለሁ አሳድርሻለሁ፣
ደግሞ ለነገው ይፈለጋል ሠው›› ነው የምንላት ብሎ ነገረኝ፡፡ ይሄንንም ‹‹እህና ናና ሆይና›› በሚለው ዘፈኔ ላይ ተጫውቼዋለሁ፡፡ በእኔ ሙዚቀኝነት ውስጥ የአባቴ ድርሻ ጉልህ ሥፍራ አለው። በአጠቃላይ የገጠሩ ህብረተሰብ አካል ነኝ። መሆን የምፈልገው፤ ይዤ የተነሳሁትም የአገሬን ባህል፣ቋንቋውን ማሳወቅ፣ ማስከበር ነው፡፡ ባህሌን ማሳወቅ የእኔ ግዴታ፣ ውዴታም ነው፡፡
እንደ ‹‹እህና ናና ሆይ እና››፣ ‹‹ሎጋው ሽቦ››፣ ‹‹የማይ ውሃ›› የመሳሰሉ የህዝብ ዜማዎች ትርጉማቸው ጠጠር ይላል የሚሉ ወገኖች አሉ----
በቃ እኮ ከህዝብ የሚፈልቅ ስሜት ነው፡፡ የፈጠራ፣ የጥበብ ሰው እኮ ነው ባላገር፡፡ የገጠሩ አካባቢ ሰው ሁሉም ዘፋኝ፣ አቀንቃኝ፣ ገጣሚ ነው፡፡ ቋንቋው የበሰለና ጥበብ የታከለበት ነው። በቃ ቅኔ ነው--- የህዝብ ህብረ ቀለም ያለው ቅኔ፣ የሚጣፍጥ--ከውስጥ ጥልቅ የሚል ቋንቋውና ፍሰቱ የሚያስደንቅሽ…ድንቅ ህዝብ፣ ድንቅ የባህልና የፈጠራ ባለቤት ነው ባላገር.. እኔ ይሄ ነኝ---የዚህ ህዝብ አካል፡፡
የአሜሪካ ኑሮህ እንዴት ነው?
አሜሪካ ስኖር ጎደለኝ የምለው ነገር የለም፤ እግዚአብሄር ይመስገን ሁሉ ሙሉ ነው፡፡ እኔ ደስ የሚለኝ በሃሳብ ወደ ኋላ ተመልሼ፣ የልጅነት ጊዜዬን፣ አገር ቤትን በትዝታ ስቃኝ ነው፡፡ በተለይ…ፍኖተ ሠላምን-- ያደኩበትን ሠፈር፣ጓደኞቼን አይቼ ስመለስ ስራዬን እንዴት እንደምሰራ አታውቂም! በተረፈ ግን..ብዙ ነገሮች ለእኔ ድግግሞሽ ናቸው። ልጆቼን ገጠር የአባቴ አገር ይዣቸው ሄጄ ደበሎ አልብሻቸዋለሁ፡፡ ሴትዋን ልጄን ባለገመዱን ቀሚስና መቀነት አልብሻታለሁ፡፡ ባህላቸውን አውቀው እንዲያድጉ ከከብቶች ጋር ፎቶ አንስቻቸዋለሁ፡፡ እንደውም ‹‹እምዬ ኢትዮጵያ አገረ ገነት›› የሚለው ዘፈኔ ቪድዮ ክሊፕ መፅሐፍ ቅዱስ እያነበብን ነው የሚጀምረው፡፡ ልጆቼ ይህን እንዲያገኙ፣ እንዲያውቁ፣ እንዲኮሩበት ስለምሻ ሁሌም አስተምራቸዋለሁ፡፡. ደበሎ ለብሰን አድገን በአሜሪካ የምንወልዳቸው ልጆች ባህላችንንና እኛን አያውቁንም፡፡ መሠረታችንን አመጣጣችንን አያውቁም… ብናግዛቸው መልካም ነው፡፡
ትምህርት እንደጨረስክ ነው ”ጊሽ ዓባይ” ኪነት ቡድንን የተቀላቀልከው?
ከዛ በፊት ለአንድ ወር በመሠረተ ትምህርት ዘመቻ ላይ ተሳትፌአለሁ፡፡ ባከል ገብርኤል ላይ ነበር የዘመትኩት፡፡ ገበሬው ደስ ይለው ነበር። ለአስተማሪ ትልቅ ክብር ስላለው ቤቱ አግብቶ ያበላል ያጠጣል… እንዴት ሰው ያከብራሉ መሰለሽ፡፡ በጣም ፍቅር ነው የገጠሩ ህብረተሰብ፡፡
ወደ “ጊሽ ዓባይ” እንግባ…
በ1979 ዓ.ም ነበር፡፡ ‹‹አንቱየዋ እነሱ እኮ ልጆች ናቸው ይጫወቱ በጊዜያቸው›› የሚለውን የሙዚቃ ፕሮግራም እኔ ነበርኩ ይዠው የሄድኩት፡፡ ፈጠራው የእኔ ነው፤ እኔ ነኝ የትርኢቱን ንድፍ (ስኬለተን የሰራሁት) ይሄ አለኝ ብዬ ስሰጣቸው የ “ጊሽ ዓባይ” ትርዒት ኃላፊ እሱባለው ጫኔ ..ሰማኸኝ በለው/አባት ፣ ሀብቱ/እረኛ፤ አለምወርቅ አስፋው/እናት፣ ብዙአየሁ ጎበዜ/ልጅ ሆኑና--ወዲያው ተቀነባበረ። እዛ ከደረሰ በኋላ እየተቀየረ መጣ..ሁሉም ሰው የራሱን ፈጠራ ይጨምራል..አንዱን ቀን የሰራነው ሌላ ቀን ሌላ ይጨመርበታል..እያደገ መጣ..ያን ከሰራን በኋላ ኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ጠሩን፡፡ እድገቴ ፈጣን ነበር፡፡ በ1981 ዓ.ም ካሴት አወጣሁ..‹‹የአገሬ ልጅ ባለጋሜ ትውልደ ጎጃሜ›› የሚለውን፡፡
ለመጀመሪያ ጊዜ አዲስ አበባ ስትመጣ ምን ዓይነት ስሜት ፈጠረብህ?
ከክፍለ ሃገር ለሚመጣ ሰው ደስ የምትል ከተማ ናት፡፡ መኪና ውስጥ ሆኜ--አዲስ አበባ ደረስን እስኪባል ድረስ አቀነቅን ነበር፡፡ የመጀመሪያው የህብረት ጉዞ ነበር፡፡ በየቦታው አብረን ነበር የምንቀሳቀሰው፡፡ ሁለተኛ ካሴት ለማሳተም ስመጣ ብቻዬን ስለመጣሁ--ትንሽ አደናግሮኝ ነበር፡፡ ከጎጃም የሚመጣ ሰው ማረፊያው ጎጃም በረንዳ ነው፡፡ ጎጃም በረንዳ ሆኜ በፊት ስመጣ ለተዋወቅኋቸው ጓደኞቼ ደወልኩላቸው፡፡ ማሲንቆ ተጫዋች አበበ ፈቃደ የሚባል አሁን ካናዳ ነው … ሁለት ቀን ከሆነኝ በኋላ ደወልኩለትና መጣ፡፡
‹‹ምን ሆነህ መጣህ›› አለኝ፡፡
‹‹ካሴት ላወጣ›› አልኩት፡፡
‹‹እና እዚህ ሆነህ ነው የምታወጣ›› አለኝ፡፡
የአዲስ አበባን የኑሮ ውድነት ስለሚያውቅ ነው እንደዚህ ያለኝ፡፡ ከዛ ይዞኝ ሄደ፡፡
የምሽት ክበብ ውስጥ አስቀጠረህ?
ጓደኛዬ ማታ ማታ ክለብ ውስጥ ይሰራ ነበር… እሱን ተከትዬ እሄድኩ ሲጫወት እሰማዋለሁ። ነገሮችን አጤናለሁ፡፡ ካሴት ካወጣሁ በኋላ ነው ካራማራ የተባለ ናይት ክለብ ውስጥ መስራት የጀመርኩት፡፡ ለአንድ ዓመት ከሰራሁ በኋላ አይቤክስ ሲከፈት፣ ሙዚቀኞችን አሰባስቤ ኮንትራት ወስጄ እየሰራሁ ሳለሁ ነው ወደ አሜሪካ የመሄድ እድል የገጠመኝ፡፡
አሜሪካ ከገባህ በኋላ በሙዚቃው ብቻ ሳይሆን በንግዱም ተሳክቶልሃል ይባላል…
አሜሪካ ሰፊ እድል አጋጥሞኛል፡፡ እንደሄድኩ ያላሰብኩት ጥሩ ፍቅር ገጠመኝ - ከአሁኗ ባለቤቴ ጋር። የባለቤቴ ራዕይና መልካም አቀራረብ ገዛኝና ጋብቻ መሰረትን፡፡ በትዳሬና በልጆቼ ደስተኛ ስለሆንኩ--በምሄድበት ቦታ ሁሉ ይቀናኛል። የመጀመሪያ ልጄ ፍቅር ይሁኔ ይባላል፡፡ ሴትዋ ሰላም ይሁኔ ትባላለች፡፡ ባለቤቴ ደግሞ የሺእመቤት ተስፋዬ፡፡ በአሜሪካ የሺእመቤት በላይ ነው የምትባለው፡፡ “ዘ በላይ ፋሚሊ” ተብለን ነው የምንጠራው፡፡ ባለቤቴ በቢዝነስ ነው የተመረቀችው---የእኔ ስራ እየዞሩ ኮንሰርት ማቅረብ ነው፡፡ በኋላ “ኢትዮጵያን የሎው ፔጅስ” የሚባል የመረጃ መጽሐፍ ማሳተም ጀመርን፡፡ እንደ ቢቢስ እና ሲኤንኤን ያሉ አለማቀፍ ሚዲያዎች ስለመጽሐፉ ብዙ ዘግበዋል፡፡ በዋሺንግተን ዲሲ የሎው ፔጅ በጣም የታወቀ ካምፓኒ ነው፡፡ ከኢትዮጵያ ኮሙኒቲ ጋር ጥብቅ ቁርኝት ፈጥሮልናል - ጥሩ መረጃ ነው የምንሰጣቸው፡፡ አሜሪካን አገር የሎው ፔጅ የሚባል ትልቅ የመረጃ መስጫ መፅሃፍ አለ - አሜሪካኖች በስፋት የሚጠቀሙበት፡፡ ባለቤቴ ያንን አይታ ነው ለምን ለኢትዮጵያ ተመሳሳይ ነገር አንጀምርም ብላ የጀመርነው፡፡ በየዓመቱ የሚወጣ ነው…በዚህ ስራ ላይ ለአስራ ዘጠኝ ዓመት ሰርተናል፡፡
በካምፓኒያችሁ አማካኝነት ከአሜሪካውያን ታዋቂ የመንግስት ባለስልጣናት፣ ሙዚቀኞችና ተዋንያኖች ጋር ግንኙነት መፍጠር እንደቻላችሁ ሰምቼአለሁ--
አዎ--- ሂላሪ ክሊንተን፣ ጆን ማኬን፣ ዴንዝል ዋሽንግተን፣ ኤሪክ ቤኔ፣ ዳጊ ፍሬሽ/ራፐር/…እንዲሁም ከበርካታ የመንግስት ባለስልጣናት፣ ሙዚቀኞችና ተዋንያኖች ጋር በሰፊው እንገናኛለን..በቅርቡ እንደውም አንዲት ኢትዮጵያዊት ከጥቁር አሜሪካዊ ጋር ተጋብታ እኔ ነበርኩ የሰርጉን ሙዚቃ የሰራሁላት፡፡
በፌስ ቡክ ፔጅህ ላይ የምርቃት ፎቶ አይቻለሁ። በምንድነው የተመረቅኸው?
ላለፉት ሁለት ዓመታት ትምህርት ቤት ነበርኩ፡፡ በኮምፒዩተር ቴክኖሎጂ ነው የተመረቅሁት፡፡ የኮምፒዩተር ጤንነትን በተመለከተ፣ ኮምፒዩተርን ቢዩልድ ማድረግ--ኔትዎርክ፣ ኢንተርኔት ሴኪዩሪቲ ተምሬአለሁ፡፡ ከአራት ወር በኋላ ደግሞ በ“አርት ኤንድ ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ” እመረቃለሁ፡፡ ወደፊትም መማሬን እቀጥላለሁ፡፡
በአገር ውስጥስ ኢንቨስት ለማድረግ አላሰብክም?
ብዙ ሃሳቦች አለኝ፡፡ ከሁለት ዓመት በፊት መጥቼ ፍኖተ ሠላምን ሳያት እየተለወጠች ነበር፡፡ አዳዲስ ግንባታዎች አሉ…በፍኖተ ሠላም ትልቅ ባዛር የተካሄደ ጊዜ “አንተም ልጃችን ነህ፤ የበኩልህን አስተዋፅዖ አድርግ” ተባልኩ፡፡ አፋጣኝ ምላሽ ነበር የሰጠሁት፡፡ ሁሉን ነገር ትቼ በሶስት ቀን ውስጥ ወደ አዲስ አበባ መጣሁ፡፡ ከዛም ወደ ፍኖተ ሠላም ሄድኩ፡፡ እንደ ጠዋት አዲስ አበባ ገብቼ ወዲያው በመኪና ተሳፍሬ ፍኖተ ሠላም ከምሽቱ አራት ሰዓት ነው የገባሁት፡፡
ህዝቡ፣ ከችኳንታ እስከ አውቶብስ፣ ባጃጁ ሳይቀር… ከፍኖተ ሠላም ተነስቶ ጅጋ የምትባል 12 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የምትገኝ ቦታ ድረስ መጥቶ እንደ ሙሽራ አጅቦ፣ እየፎከረ እየሸለለ አጅቦ አስገባኝ---ይህን ሳይ በጣም ነው ያለቀስኩት፡፡ ስደርስ የባዛሩ መዝጊያ ደርሶ ነበር፤ ሁለት ቀን ኮንሰርት ሰርቼ ተመለስኩ፡፡ ምን ያህል ገቢ እንደተገኘ ባላውቅም ገቢው ለከተማዋ የሚውል ነበር፡፡ ኢንቨስትመንቱን በተመለከተ ግን የጀመርኩት ነገር ጥሩ ደረጃ ሲደርስ እነግርሻለሁ፡፡
በባዛሩ ኮንሰርት ላይ አንተን ይተካል ተብሎ የሚጠበቀው የአካባቢህ ልጅ ሰለሞን ደምሴ “ነይማ ላሳይስ ነይማ ጎጃም ፍኖተ ሠላም” እያለ ሲያቀነቅን የእጅ ሰዓትህን አውልቀህ ሸልመኸዋል ይባላል--
የሚገርም ድምፃዊ ነው፡፡ በጣም የሚያድግ ልጅ ነው፡፡ እኛም ድሮ እንደዚህ የሚያበረታታን ስናገኝ ደስ ይለን ነበር፡፡ ለዚህ ነው ሲጫወት ሳየው ስላስደሰተኝ የእጄን ሰዓት ፈትቼ የሸለምኩት፡፡
ቀረ የምትለው ካለ…
እግዚአብሄር ያክብራችሁ፡፡ ጎተራውን ሙሉ…አገሩን ጥጋብ ያድርግላችሁ..አይለየን..አለማችሁን ያሳያችሁ…ፍቅር፣ ሰላም፣ ደስታ ከእናተ ጋር ይሁን!

Saturday, 22 June 2013 11:04

ጭፈራችንን መልሱልን

ኩርማን መግቢያ
እግዜር ከሞላው ኩሬ ውስጥ ፣ እስቲ እንዋኝ ብለን ገብተን
ሳንጨርሰው ውሃው ደርቆ፣ መካከል ላይ ዋጋ ከፈልን!
ለኩሬ ዋናው ተጥፈን
በውቂያኖሱ ተቀጣን!
***
አለሥራችን ገብተን፣ አንጨቅጭቀው እግዜአብሔርን፤
ይቅርታ እንጠይቅ እንጂ፣ ስለመፈጠራችን፤
ለመኖሪያችንማ፣ “የቀን ውሎ - አበል” አልን!
ተጠባባቂ ቤንች እንጂ፣ ቋሚ ተሰላፊ አደለን!
የካምቦሎጆን ነገር፣ የቀመሰ ያቀዋል
ለካስ ኳስ ሳይሞቁት በፊት፣ ጨዋታው ብርድ - ብርድ ይላል፡፡
***
ጭፈራችንን መልሱልን
ያገር ብርድ ሲቆነድደን
ኳስ ሜዳውን አልቤርጐ አርገን
ድንጋይ ጠርዙን ተንተርሰን
የታክሲ ውስጥ አልጋ አንጥፈን
ሌት በዋዜማ አልመን፣ ነገን በዕውነት ልናበራ፤
ባንዲራ እንደደመራ
ከምረን በየኳስ ጐራ፤
ተውለብልበን አውለብልበን
ላንቃችን እስኪበጣጠስ፣ ሆ ብለን በማታ በቀን፤
በጭለማ ድል ጐስመን
አገር ላዕላይ ነው ብለን፤
የሰው እግር እንደጅረት፣ ጨርቅ ማሊያው እንደጐርፍ
ባንዲራውን እንደ ጅራፍ
ስናጮኸው መኪና አፋፍ፤
በጥሩምባ መለከት አፍ
የሳግ ጩኸት ሞታችንን
ስናንባርቅ ድላችንን፣
ያን መሳይ ዝማሬ ቃና፣ ያን ጭፈራ ታስነጥቁን?!
እግዜር ለድል እያበቃን፣ እኛው “የእግዜር ስተት” ከሆን
ከመዋል ከማደር በቀር፣ ለህይወትም ያው “ቤንች” ነን!!
አዬ መጥኔ ካምቦሎጆ
አድሮ የንፍገት ኮሮጆ!
በሠርግ አጋፋሪ ጥፋት፣ ከፈረሰ ድንኳን ዳሱ
ገና ሜዳ ሳንገባ፣ ከተነፈሰማ ኳሱ፤
ለምን ላገር ይትረፍ ጦሱ?
ጭፈራችንን መልሱ!!
እናንተው ተከሳሰሱ
ብቻ ሳትውሉ ሳታድሩ፣ ጭፈራችንን መልሱ!!
ሰኔ 11/2005 (ለምስኪኑ ህዝባችን)

 

ከዕለታት አንድ ቀን የዱር አራዊት አያ አንበሶ ከበሽታቸው መዳናቸውን ምክንያት በማድረግ ድግስ እንዲደገስ ተስማሙ፡፡ አያ አንበሶም ፈቀዱ፡፡ በቅደም - ተከተል ባለሟሎቹ ስማቸው ተዘረዘረ ተፃፈና ጮክ ተብሎ ተነበበ፡፡

“አንደኛ - ነብሮ” ተባለ፡፡ ተጨበጨበ፡፡ “ሁለተኛ - አያ ዝሆን” ተባለ፡፡ ተጨበጨበ፡፡

“ሦስተኛ - አውራሪስ” ተባለ ተጨበጨበ፡፡

“አራተኛ - አጋዘን” ቀጠለ ተጨበጨበ፡፡

“አምስተኛ - ጅብ” ተጨበጨበ፡፡

“ስድስተኛ - ዝንጀሮ” እያለ ግንባር ግንባር ቦታ፤ ዋና ዋና ወንበር ላይ የሚቀመጡቱ በዝርዝር ታወቁ፡፡ አያ አንበሶ ቀጠሉና፤ “ታምሜ ያልጠየቁኝ ወደዚህ ድግስ እንዳይመጡ” ሲሉ አስጠነቀቁ፡፡

አክለውም “በተለይ ጦጣ!” አሉ፡፡ በዚሁ መሠረት ለሁሉም አራዊት የድግሱ ጥሪ እንዲደርሳቸው ተባለና ተላከባቸው፡፡ ድግሱ ድል ተደርጐ ተደግሷል፡፡ ያልተጠራ የዱር አራዊት የለም፡፡ አሰላለፋቸው የታወቀ ነው፡፡ አንበሳ ሁሉንም በደምብ በሚያይበት ዙፋን - አል ወንበሩ ላይ ኮራ ብሎ ተቀምጧል፡፡ እነ ነብር፣ እነዝሆን፣ እነ አጋዘን፣ እነድብ ወዘተ በየተከታታይ ተርታ ተሰድረዋል፡፡ ጦጢት የለችም፡፡ ምክንያቱም አያ አንበሶ ታመው፤ አንድ ሁለት ጊዜ አጭበርብራ ሳትጠይቃቸው በመቅረቷ ነው፡፡ ካዩዋት አይለቋትም፡፡ ሆኖም የተለየ ልብስ ለብሳ ዋና አጋፋሪ ሆና ድግሱን ስታሞቀው ውላለች፡፡

“እዚህ ድግስ ተጠርተሻል? እንዴ?” ሲል ከተጋባዦች አንዱ ጠየቃት፡፡ ውስጥ አዋቂ ብጤ ነው፡፡ “ኧረ አልተጠራሁም” አለች ጦጢት “ታዲያ ምን ታረጊ መጣሽ?” አላት ሌላው፡፡ “ዘመዶቼ ቅር እንዳይላቸው ብዬ ነው” “ኋላ አያ አንበሶ ቢያገኙሽና አንድ ቅጣት ቢቀጡሽስ? ፀፀቱ ለዘመዶችሽ አይሆንም ወይ? ደሞም ታላላቅ ዘመዶችሽ ውርደቱን አይችሉትም፡፡ መዘዝሽ ለሁሉ ይተርፋል፡፡ “እግዜር ጥሎ አይጥለኝም፡፡ ድፍረቱን ሰጥቶ ከድግሱ ከቀቀለኝ፣ ከእሳቱ መውጪያውንም እሱ ያበጅልኛል፡፡” ሁሉም ተሳሳቁ፡፡ ከመሀል አንደኛው፤ “አይ ጦጢት፤ ዱሮ በብልጠቷ ነበር የምትተማመነው፡፡ አሁን ለአምላክ እጇን ሰጠች፡፡ አይ ጊዜ! ጊዜ ሁሉን ያጋልጣል፡፡ ጦጢትንም ቢሆን” አለ፡፡

                                                        ***

ሁሌ ብልጠት አያዋጣም፡፡ “አፍና ቅብቅብ ሁልጊዜ አያበላም” ይላሉ አበው፡፡ በብልጠት ሸፋፍኖ ዛሬን ማለፍ ይቻል ይሆናል፡፡ ነገ ግን ብልጠቱ ያረጅና ዕውነቱ እንደአዲስ ቆዳ ብቅ ይላል፡፡ ስለዚህ “ሞት ላይቀር ማንቋረር” ነው የሚሆነው፡፡ የሀገራችን እስፖርት የብዙሃን መዝናኛና የብዙሃን መፎካከሪያ ነው፡፡ ውስጥ፣ እርስ በርሱ እንደየቲፎዞው አቅም ይሟገታል፡፡ ይወራረዳል፣ ይጋጫል፡፡ ከውጪ ቡድን ጋር ግጥሚያ ሲመጣ ግን ብዙሃኑ ህዝብ የእርስ በርስ ፉክክሩን፣ ፉክቻውንና፣ ሽኩቻውን ወደጐን ትቶ የአገር ጉዳይ ነው ብሎ፤ ሥጋውንም ነብሱንም ይሰጣል፡፡ ሲሸነፍ ደግሞ ፀጉሩን ይነጫል፤ አንጀቱ ያርራል፡፡ ሲያሸንፍ ዘራፍ ይላል፡፡ ያምባርቃል፡፡ መንገድ ይሞላል፡፡ የሞተር ብስክሌት አክሮባት፣ የመኪና ሰልፍ፣ የሰው ጐርፍ… ድብልቅልቁ ይወጣል፡፡

ደስታና ሁካታው ጣራ ይነካል! (The sky is the limit እንዲሉ ፈረንጆች) አንድ ክስተት የአገር ጉዳይ ሲሆን ህዝብ ከአፍ - እስከ ገደፉ እንደሚንቀሳቀስ መገለጫው እንዲህ ያለው የስፖርት ስሜት ነው፡፡ ነፍሱን - ልቡን ገብሮ የሚቆምለት ስሜት ነው!! ይህን ስሜት ማጭበርበር አይቻልም፡፡ ይህን ስሜት ማውገርገርና ማኮላሸት ክፉ ቁጣ፣ ሐዘንና ክፉ ፀፀት ይፈጥራል፡፡ ብርድ እየፈደፈደው፣ እንቅልፉን አጥቶ የጮኸለትን ድሉን በተራ ስህተት ሲነጠቅ ማየት እጅግ አሳዛኝ ነው፡፡ ስህተቱ የማንም ይሁን የማን አስተምሮ፣ አስምሮ፣ አመሳክሮ የመገኘትን ቁብ አጉልቶ አሳይቷል፡፡

“አንተ እኮ የእግዜር ስህተት ነህ” እንዳለው ነው ፀሐፌ - ተውኔቱ፤ በንዴት ስናጤነው፡፡ ዞሮ ዞሮ ዋና ዋና ቁቦቻችንን ብንነቁጥ:- አገር ድብብቆሽ መጫወቻ፣ አየሁሽ አላየሁሽ መባባያ አይደለችም! ስህተትን መወያየት እንጂ መደባበስ የትም አያደርሰንም፡፡ ይቅርታ መጠየቅ ክቡር ባህል ነው፡፡ ኃላፊነትን መቀበል የሰለጠነ መንገድ ነው፡፡ ውስጣችንን መፈተሽ፣ መረጃዎቻችንን በጥብቅ መያዝ፣ በየትንሹ ጉዳይ አለመበርገግ፣ አለመዝረክረክ ዋጋ ከመክፈል ያድናል፡፡ በመጨረሻም ህዝብ የጮኸልንን ያህል የጮኸብንና የተነሳብን ቀን ወዮልን ማለት አይቀሬ መሆኑን መገንዘብ የብስለት ምልክት ነው፡፡ አመንነውም አላመንነውም፤ መዘንነውም ሸቀብነውም፤ አስፈላጊውን ቅድመ - ሁኔታ ሳናሟላ ሜዳ ውስጥ መገኘት፤ “እንሥራዋን ጥላ ወንዝ ወረደች” እንደሚባለው ተረት መሆኑ የነገሩ ብልት ነው!

ዶ/ር ነጋሶ የመጀመሪያው ፈራሚ ሆነዋል

“የአገሩን በሬ በአገሩ ሰርዶ እንጂ በውጭ ተቋማት መተማመንይቅር” - ዶ/ር ያዕቆብ ኃ/ማሪያም

አንድነት ለፍትህና ለዴሞክራሲ ፓርቲ (አንድነት) ከትላንት በስቲያ በይፋ የጀመረው ህዝባዊ ንቅናቄ የፀረ-ሽብር አዋጁን ማሰረዝ ዋነኛ አላማው እንደሆነ ገለፀ፡፡ ለዚህ ዓላማውም የአንድ ሚሊዮን ሰዎችን የድጋፍ ፊርማ (ፒቲሽን) በዕለቱ ማስፈረም የጀመረ ሲሆን የመጀመሪያው ፈራሚ የፓርቲው ሊቀመንበር ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ ሆነዋል፡፡ ፓርቲው የፀረ-ሽብር ህጉን ለማሰረዝ ከሚንቀሳቀስባቸው ምክንያቶች አንዱ ህገ-መንግስቱን በእጅጉ የሚጥስና የኢትዮጵያን ዜጐች በማጥቃት የሚጀምር በመሆኑ ነው ብሏል - የህዝባዊ ንቅናቄው ኮሚቴ በሠጠው ጋዜጣዊ መግለጫ፡፡

ፓርቲው “የሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነት” በሚል መሪ ቃል የጀመረው የሶስት ወር ንቅናቄ የአንድ ሚሊዮን ህዝቦችን ድምፅ በማሰባሠብ የአገሪቱን ዜጐችና ተቋማትን በማጥቃት፣ በሀይማኖት ጣልቃ በመግባት፣ ከአባትና እናት የተወረሠን ንብረትና ሀብት በሽብርተኝነት ስም የሚገፈውን አዋጅ ለማሰረዝ ጥረት እናደርጋለን፤ ወደ ክስም እንሄዳለን” ብሏል፡፡ “ይህ ማለት ግን ኢትዮጵያ ካላት ተፈጥሯዊ ሀብትና መሠል ጉዳዮች ጋር በተያያዘ የፀረ-ሽብር ህግ አያስፈልጋትም ማለት እንዳልሆነ የገለፁት የንቅናቄው ኮሚቴ አባል አቶ ትዕግስቱ አወል፤ አሁን ስራ ላይ ያለው የፀረ ሽብር አዋጅ ግን ሰዎችን እና ተቋማትን የሚያጠቃ ነው ብለዋል፡፡

ከተጠቁት ተቋማት ውስጥ አንድነትና መድረክ ዋነኞቹ እንደሆኑ፣ ጋዜጠኞችና የፖለቲካ ሰዎችም የዚሁ አዋጅ ሠለባ መሆናቸውን፣ እንዲሁም ከህገ መንግስቱ ጋርም በከፍተኛ ሁኔታ ስለሚቃረን ትኩረት አድርገንበታል ሲሉም አክለዋል፡፡ “ምንም እንኳን በፍትህ ተቋማቱ ላይ ያለን እምነት የተሸረሸረ ቢሆንም አሁንም መብታችንን ከመጠየቅ የሚያግደን የለም” ያሉት የንቅናቄው ኮሚቴ አባል አቶ ዳንኤል ተፈራ፤ መንግስት የ1 ሚሊዮን ሠው ድምፅና ጥያቄ አልቀበልም ካለ የፓርቲውን ሳይሆን የህዝቡን ጥያቄ አልመልስም እንደማለት እንደሆነ አብራርተዋል፡፡

ፓርቲው በሶስት ወሩ ህዝባዊ ንቅናቄ ውስጥ ሰላማዊ ሰልፍ እንደሚካተት ገልፆ፤ በዋናነት ህገ-መንግስቱን የሚፃረረውን የፀረ ሽብር አዋጅ ማሰረዝ፣ በአገር አቀፍ ደረጃ እየተካሄደ ያለውን በገጠርና በከተማ የዜጐች መፈናቀልና የመሬት ቅርምት ማስቆም፣ የስራ አጥነትና የኑሮ ውድነት እንዲቀረፍ ማድረግ፣ የኢኮኖሚ ፖሊሲ ማሻሻያ እርምጃ እንዲወሠድና የንግዱ ማህበረሠብ ከወንጀለኝነት ስምና ስግብግብ ከመባል ወጥቶ ጤናማ ውድድር እንዲኖር፣ እንዲሁም ማጥላላትና ማዋከብ እንዲቆም ማድረግ የሚሉት በዋናነት ተቀምጠዋል፡፡ የንቅናቄው ኮሚቴ አባል የሆኑት አቶ ተክሌ በቀለ፤ ንቅናቄው አሁን የተጀመረበትን ምክንያት ሲያብራሩ፤ “እስከዛሬ ንቅናቄውን ያልጀመርነው ፓርቲው በአየር ላይ የተንጠለጠለ እንዳይሆን በእግሩ እንዲቆም በማድረግ ስራ ላይ እና በውስጥ አደረጃጀት ተጠምደን ስለነበር ነው” ብለዋል፡፡

“እስከዛሬ እግር ሲያወጡ እንቆርጣቸዋለን እየተባለን፣ እግር ስናወጣና ስንቆረጥ ቆይተናል” በማለት ያከሉት አቶ ተክሌ፤ አሁን ግን በኢህአዴግ የሚደርስብንን ብቻ ሳይሆን የውስጥ ህመማችንንም ስናክም ቆይተን ከጨረስን በኋላ በእውቀት ላይ የተመሠረተ የህዝብ ንቅናቄ ለመጀመር ጊዜው አሁን እንደሆነ ውሳኔ ላይ ደርሰናል ብለዋል፡፡ “በፍ/ቤቶች ላይ እምነታችን ቢሸረሸርም ፍትህ መጠየቃችንን አናቆምም” ያሉት አቶ ዳንኤል፤ የአንድ የሚሊዮኖችን ድምፅ የምናሠባስበውም ለዚሁ ነው ብለዋል፡፡

ዶ/ር ሀይሉ አርአያ በሠጡት አስተያየት አንድ አካል አጥፍቶ ያለመጠየቅን ነገር ፈረንጆቹ (Impunity) ይሉታል” ካሉ በኋላ “እዚህ አገርም አጥፍቶ የሚጠየቅ የለም፤ ስለዚህ በአገራችን ፍ/ቤት ካልተሳካ ወደ አለም አቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት የሚኬድበት አማራጭም መዘንጋት የለበትም” ብለዋል፡፡ ነጋዴዎችን በተመለከተ ለተነሳው ጥያቄ “የዚህን አገር ነጋዴዎች ለማወቅ የግድ የመጫኛ ነካሽ ልጅ መሆን አያስፈልግም” በማለት ምላሽ መስጠት የጀመሩት የንቅናቄው ኮሚቴ አባል አቶ አቶ ዳዊት ሰለሞን፤ በአሁኑ ሰዓት ነጋዴው ሌባ፣ ዘራፊ፣ ሙሰኛ እየተባለና እየተብጠለጠለ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ “ገዢውን ፓርቲ የተጠጉ አካላት በአንድ ጀምበር የሀብት ማማ ላይ ሲወጡ፣ በህጋዊ መንገድ የሚንቀሳቀሱ ነጋዴዎች በስቃይ ላይ ናቸው ያሉት አቶ ዳዊት፤ የጥሬ እቃ እጥረትና መሠል ችግር ሲፈጠር መንግስት ጣቱን በነጋዴ ላይ እንደሚቀስር ጠቁመው፣ ነጋዴው በአገሩ አንገቱን ደፍቶ እንዲኖር የሚደረግበት አካሄድ እንዲቆም እንጠይቃለን ብለዋል፡፡

“...ሁልጊዜ ጥሩ አስተያየት የሚሰጡኝን ሁለት ሰዎች በጣም እወዳቸዋለሁ፡፡ በሚያዩኝ ጊዜ ሁሉ ...ኦ...ዛሬ በጣም ጥሩ ነሽ፡፡ እርግዝናውም ቀለል ብሎሻል፡፡ ይሄ የሆድሽ ከፍታ እኮ ከትንሽ ጊዜ በሁዋላ ይቀላል፡፡ በተለይም ሊወለድ ሲል በጣም ይቀል ሻል፡፡ አይዞሽ የሚል አስተያየትን ከእነርሱ መስማት በጣም ያስደስተኛል ...ትላለች ፡፡በአሁኑ ወቅት እርግዝናዬ 34ኛ ሳምንቱን ይዞአል የምትለው ወይዘሮ፡ በተጨማሪም እንዲህ ትላለች፡፡ “… እኔ ለነገሩ በእርግዝናው ምክንያት በሚፈጠረው ሆርሞን ምክንያት ምንም ነገር ቢነገረኝ እንዳያናድደኝ ስለምጠነቀቅ ነው እንጂ እንኩዋንስ የማይሆን ነገር ተናግረ ውኝ ቀርቶ ደህናም ነገር ቢያወሩኝ በጥርጣሬ የምቀበል ሆኛለሁ፡፡ እስቲ በዚህ ጉዳይ የተለያዩ አባባሎችን ...ማለትም ከሰዎች የወሰድኩዋቸውን አንብቡ ብላለች አሊሰን ፋክለር...፡፡ ዶ/ር መብራቱ ጀምበር ባለፈው እትም ስለ ማህጸን ውጭ እርግዝና ያብራሩትን ካስነ በብናችሁ በሁዋላ አሊሰን ፋክለር በእርግዝና ጊዜ መነገር የሌለባቸው ያለቻቸውንና ከአገር ውስጥም ልምዳቸውን ያካፈሉንን አካተን ለንባብ እንላለን፡፡

“.....እንደሚታወቀው እርግዝና የሚፈጠረው በወንዱ ዘርና በሴቷ ዘር ግንኙነት መንስኤነት ነው፡፡ይህ በጤናማ መልኩ የተፈጠረ ከሆነ የሚገኘው በዘር ማስተላለፊያ ቱቦው ላይ ነው፡፡ በዚያም የተወሰነ ቀን ካሳለፈ በሁዋላ የተወሰነ የሰውነት ገንቢ ሕዋሳቶች ደረጃ ላይ ሲደርስ ወደ ዋናው የማህጸን ክፍል ውስጥ ይገባል፡፡ በማህጸን ውስጥም እርግዝናው እስኪጨርስ እና አድ ጎም ለመወለድ እስኪደርስ ድረስ ይቆያል፡፡ ነገር ግን አንዳንድ ጊዜ ይህ ሂደት ሊዛባ ይችላል፡፡ በዚህም ሳቢያ ጽንሱ ወደ ማህጸን ከመሄዱ ይልቅ የተለያየ ቦታ በመቅረት ባለበት ቦታ እድገቱን ይጀምራል፡፡ በተለይም በዘር ማስተላለፊያ ቱቦው ጫፍ ወይንም መሃል አለበለዚያም ወደ ማህጸን ተጠግቶ ሊያድግ ይችላል፡፡ ከዚህም ውጭ ጽንሱ እንደተፈጠረ ዝም ብሎ ሆድ እቃ ውስጥ በመውደቅ ሞራ ላይ ወይንም አንጀት ላይ እና በመሳሰሉት አካላት በመጠጋት በዚያው እድገቱን ሊጀምርም ይችላል፡፡.. ከላይ ያስነበብናችሁ የማህጸን ውጭ እርግዝና እንዴት እንደሚፈጠር የሚያስረዳውን ባለፈው እትም ዶ/ር መብራቱ ጀምበር ያብራሩትን ነበር፡፡ በተለይም በሆድ እቃ ውስጥ ሰለሚኖረው ከማህጸን ውጭ እርግዝና ሲገልጹ፡- “...ከማህጸን ውጭ እርግዝና ከሁለት እስከ ሶስት ወር ድረስ አደጋ የሚከሰትበት ወቅት ነው፡፡

ነገር ግን በሆድ እቃ ውስጥ የሚያርፈው ከማህጸን ውጭ እርግዝና አልፎ አልፎ እስከመጨረሻው የእርግዝና ወቅት ድረስ ደርሰው በሰላም ልጆቻቸውን የተገላገሉ አሉ፡፡በእርግጥ እርግዝናው በማህጸን ውስጥ እንደሚኖረው እርግዝና ሳይሆን አስቸጋሪና ከበድ ያለ ነው፡፡ በሆድ እቃ ውስጥ ያሉ ሌሎች አካላት ጨጉዋራ፣ ጉበት...ወዘተእንዳሉ ሆነው እርግዝናው ግን ባገኘው ክፍት ቦታ ላይ የሚቀመጥ ይሆናል፡፡ ዋናው ነገር የእንግዴ ልጁ የደም ስር ሊያገኝ እና ሊያድግ የሚችልበት ቦታ መሆን አለበት፡፡ እንግዴ ልጁ የሚመቸው ቦታ ላይ ካረፈ በሁዋላ ለልጁ ከእናቱ ደም ስቦ አጣርቶ በመመገብ እንዲያድግ ያደርገዋል፡፡ እርግዝናው በማህጸን ውስጥ ባለመሆኑ መጥፎ አጋጣሚ ነው ተብሎ ቢፈረጅም ልጁን በሰላም እስከመጨረሻው ጠብቆ መገላገል ግን እድለኝነት ይባላል፡፡ በእርግጥ ይህ ሁኔታ በቅርብ ጊዜ የተፈጸመ ሳይሆን በአሁኑ ጊዜ ያሉ ክኖሎ ጂዎች ባልነበሩበት ወቅት የነበረ አጋጣሚ ነው፡፡

በአሁኑ ጊዜ ግን አስቀድሞውኑ ጽንሱ የተፈጠረበት ስፍራ በምርመራ ስለሚታወቅ አደጋ ከማስከተሉ በፊት እርምጃ ይወሰ ዳል፡፡ አስቀድሞ በነበረው የህክምና ዘዴ ግን በሆድ እቃ ውስጥ የሚፈጠረው እርግዝና እስኪወለድ ድረስ ሊከሰት የሚችለውን አደጋ እንዳይደርስ ከመናፈቅ ባለፈ የሚደረግ ነገር አልነበረም፡፡ ጽንስ በማህጸን ውስጥም ሆነ በሆድ እቃ ውስጥ ሲረገዝ የራሱ የሆነ መሸፈኛ ይኖረዋል፡፡ ጽንስ በማህጸን ውስጥ ሲያድግ ላስቲክ መሰል በሆነ ስስ ሽፋን ውስጥ ሆኖ በሽፋኑ ውስጥ የሽርት ውሀ ከቦት ነው የሚያድገው፡፡ በእርግጥ ሽፋኑ እንደላስቲክ ስስ ሳይሆን ጠንከር ያለ እና ሞራ መሰል መልክ ያለው ነው፡፡ ይህ አፈጣጠር ጽንሱ በሆድ እቃ ውስጥም በሚፈጠ ርበት ወቅት በተመሳሳይ ሁኔታ ተሸፍኖ ስለሆነ ባለበት ቦታ ምንም ባእድ ነገር ሳያገኘው ሊያድግ ይችላል፡፡ ነገር ግን እርግዝናው ምን ያህል እንደሚቀጥል ማወቅ ስለማይቻል ዝም ብሎ እስከመጨረሻው መጠበቅ ያስቸግራል፡፡

ከማህጸን ውጭ በሆድ እቃ ውስጥ የተረገዘ ጽንስ የሚወለደው ካለምንም ችግር በኦፕራሲዮን ይሆናል፡፡ በማህጸን ውስጥ የተረገዘን ልጅ በኦፕራሲዮን ለማዋለድ በመጀ መሪያ የሆድ እቃ ከዚያ በሁዋላ ደግሞ ማህጸን ተከፍቶ ሲሆን እርግዝናው በሆድ እቃ ውስጥ ከሆነ ግን እንዲያውም በቀላሉ ሆድ እቃን ብቻ በመክፈት ማገላገል ይቻላል፡፡ የማዋለዱን ተግባር ልዩ የሚያደርገው ግን እንግዴ ልጁ በዚያው መቅረት ስለሚገባው ነው፡፡ የእንግዴ ልጅን ለማውጣት ትግል ከተፈጠረ ደም የመፍሰስ ነገር ስለሚከሰት አደጋ ላይ መውደቅን ያስከትላል፡፡ ስለዚህም እትብቱን ቆርጦ ልጁን ከማውጣትና አንባቢውን ከማጽዳት ያለፈ ምንም አይደረግም፡፡ እንግዴ ልጁ በዚያው እንዲጠፋ ይተዋል ፡፡ በማህጸን የተረገዘ ልጅ ሲወለድ የእንግዴ ልጁ በጥንቃቄ የሚወገድ እና ይቅር ቢባልም አደጋን የሚያስከትል ሲሆን በሆድ እቃ ውስጥ ግን ምንም ችግር ሳያስከትል በራሱ ጊዜ እንዲጠፋ ይደረጋል፡፡

ከማህጸን ውጭ የተረገዘ ልጅ እንቅስቃሴው ፊት ለፊት በቀላሉ የሚታይ ነው፡፡ ምክንያቱም በማህጸን ውስጥ እንዳለው ልጅ በሁለተኛ ደረጃ በማህጸን ግድግዳ ተሸፍኖ ስለማይገኝ ነው፡፡ በምጥ መውለድን በሚመለከትም በሆድ እቃ የሚኖር እርግዝና በትእግስት በሚጠበቅበት ዘመን በክሊኒክ በሚቆጠረው የጊዜ ቀመር በመመስረት በኦፕራሲዮን እንዲወለድ ይደረጋል እንጂ እንደ መደበኛው እርግዝና ምጥን መጠበቅ አይቻልም፡፡ ከማህጸን ውጭ እርግዝና በዘር ማስተላለፊያ ቱቦ ውስጥም ይሁን በሆድ እቃ ውስጥ ሲፈጠር አደጋ የሚያስከትልበት ሁኔታ መኖሩ እርግጥ ነው፡፡ በተለይም ከሁለት እስከሶስት ወር ድረስ ባለው ጊዜ ከሚከሰተው አደጋ ዋናው የደም መፍሰስ ነው፡፡ የዚህም ምክንያቱ ጽንሱ ያለበት ቦታ እስከመጨረሻው ስለማያሳድገውና መቀደድ ስለሚጀምር ነው፡፡

ይህንን ሁኔታ የሚያባብሰውም እርግዝና በሚፈጠርበት ጊዜ እርግዝናው ባለበት አካባቢ እርግዝናውን ለማሳደግ የደም ስሮች በብዛት ስለሚፈጠሩ ጽንሱ ያለበት ቦታ ሲፈነዳ ደም በኃይል እንዲፈስ ስለሚያደርግ ነው ፡፡ይህ የደም መፍሰስም ሴትየዋን እስከሞት ሊያደርስ የሚችል ነው፡፡ ከማህጸን ውጭ እርግዝናን አስቀድሞ መወቅ የሚቻልባቸው ምልክቶች አሉ፡፡ እርግዝናው መኖሩ ከተረጋገጠ በሁዋላ ከማህጸን ደም መፍሰስ ሊጀምር ይችላል፡፡ ከእምብርት በታች ባለው የሰ ውነት ክፍል ሕመም ሊኖር ይችላል፡፡ እግርን የመያዝ አይነት ስሜት ሊኖር ይችላል፡፡ እርግዝናው ውጥረቱ እየጨመረ ሲሄድ ከመፈንዳቱ በፊት የተገለጹት ስሜቶች ሊከሰቱ ይችላሉ፡፡በእርግጥ ሌሎች የጤና ሁኔታዎችም ተመሳሳይ የህመም ምልክቶችን ሊያሳዩ እንደሚችሉ መገመት ያስፈልጋል፡፡

ማንኛዋም ሴት የወር አበባዋ በሚቀርበት ጊዜ ገና ከጅምሩ ወደሐኪም ዘንድ ቀርባ ምርመራዋን ብትጀምር ሁኔታው አደጋ ከማስከተሉ በፊት እርምጃ ለመውሰድ ያስችላል እንደ ዶ/ር መብራቱ ጀምበር የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስት ማብራሪያ፡፡ ለእርጉዝ ሴቶች ሊነገሩ የማይገባቸው ነገሮች፡- እርግጠኛ ነሽ ...መንታ ላለማርገዝሽ? አንቺ ...ሆድሽ ሊፈነዳ ደርሶአል እኮ...ከዚህ በላይ መቆየት የምትችይ ይመስልሻል? የእኔ ሚስት አኮ አምስት ልጅ ወልዳለች፡፡ ግን እንዳንቺ ሰውነቷ አልተበላሸም፡፡ ለመሆኑ ሐኪምሽ ምን ይልሻል? በእርግጥ ሙሉ በሙሉ ጤነኛ ነሽ? አትናደጂ፡፡ ግን እርግዝና ነው ወይንስ ሌላ ነገር? መልክሽ እንዲህ የጠቆረው በጤና ነው? መልክሽ እንዲህ እስኪጠፋ ድረስ ያሳበጠሽ በእርግጥ እርግዝናው ብቻ ነው? አንቺ...ምን መሰልሽ? ምነው እርግዝናው ቢቀርስ? ...ወዘተ ከላይ የተጠቀሱትንና መሰል ነገሮችን ለእርጉዝ ሴቶች ማቅረብ ተገቢ አይደለም፡፡ በተለይም አርግዞ በመውለድ ዙሪያ ሊያጋጥሙ የሚችሉ አደጋዎችን ከመንገር ይልቅ ሴትየዋ በትክክል ወደሐኪም ሄዳ እርዳታ ማግኘት የምትችልበትን መንገድ መምከር ይገባል፡፡

  • ኳሷን ማሸነፍ ማለት ለእያንዳንዷ ኳስ ትኩረት መስጠት ነው
  • አጥቂዎች አንድ እድል ሲያገኙ አንድ ጎል ለማግባት ማሰብ አለባቸው
  • አጥቂዎች ወደ ጎል የሚሞክሯቸውን ኳሶች መሬት አስይዘው ይምቱ
  • ለዓለም ዋንጫ ማለፍ ማለት የአገር ገጽታን ሊቀይር የሚችል ነው


ኳስ ተጨዋች ነበር፡፡ ከ16 ዓመት በፊት በአርሰናል ተጠባባቂ ቡድን ውስጥ ለ6 ወራት የሙከራና የልምምድ ጊዜ አሳልፏል፡፡ የቅዱስ ጊዮርጊስም ተጨዋች ነበር፡፡ ዛሬ ግን ያሬድ ተስፋዬ የተዋጣለት ነጋዴ ሆኗል፡፡ በመዝናኛ ዘርፉ ላይ የሚሰራው ያሬድ፤ የታዋቂው ፕላቲኒዬም የምሽት ክለብ ባለቤት ነው፡፡ ፕላቲኒዬም የፈርኒቸር ማምረቻ የሚባል ድርጅትም አለው፡፡ ቢቲ ትሬዲንግ በተሰኘ የኤሌክትሮኒክስ እቃዎች አስመጭ ኩባንያ ውስጥም ከቤተሰቡ ጋር እንደሚሰራ ይናገራል፡፡ አሁን ያሬድ ወደ ስፖርቱ ለመመለስ አስቧል፡፡ ይህን ሃሳቡን በመደገፍም አብሮት የተማረው ጋዜጠኛ አማን ከበደ እያበረታታው እንደሆነም ይናገራል፡፡ “ካሳለፍኩት የተጫዋችነት ህይወት፣ ከነበረኝ ልምድና ተሞክሮ በመነሳት በኢትዮጵያ እግር ኳስ የለውጥ ምዕራፍ የበኩሌን አስተዋጽኦ ለማበርከት እፈልጋለሁ” ይላል፡፡ በክለብ ማኔጅመንት፣ በተጨዋች ወኪልነት፣ በስፖንሰርሺፕና ማርኬቲንግ እንቅስቃሴዎች የመስራት እቅዶች አሉት፡፡

ዛሬ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን የደረሰበት የብቃት ደረጃ ለስፖርቱ ዕድገት የሚያግዙ ተግባራትን ለማከናወን መልካም አጋጣሚ መፍጠሩን የሚገልፀው ያሬድ፤ በተጫዋችነት ዘመኑ ሊያሳካው ይሻው የነበረውን ህልም በመጪው ትውልድ እውን ሆኖ ማየት ይፈልጋል፡፡ የብሔራዊ ቡድኑ ውጤታማነት የኢትዮጵያ ሁለንተናዊ እድገት መገለጫ እንደሆነም ያምናል፡፡ እኔ ከያሬድ ተስፋዬ ጋር ሰሞኑን ጭውውት ሳደርግ ኢትዮጵያውያን የእግር ኳስ አፍቃሪዎች ሁሉ ወሬያቸው ነገ ብሄራዊ ቡድናችን ከደቡብ አፍሪካ ጋር የሚያደርገው ጨዋታ እንደሚሆን ቅንጣት ጥርጣሬ የለኝም፡፡ ያሬድ ተስፋዬም ያወጋኝ ስለዚሁ ጉዳይ ነው፡፡ ስለ ብሄራዊ ቡድኑ አባላትና ስለእግር ኳስና ስለነገው ግጥሚያ የተጨዋወትነውን እነሆ፡፡
ነገ ዋልያዎቹ ከባፋና ባፋና ጋር በሚያደርጉት ጨዋታ ምን ትጠብቃለህ?
ከደቡብ አፍሪካ ጋር የሚደረገው ጨዋታ በጣም ወሳኝ ነው፡፡ ዋልያዎቹ በዚህ ግጥሚያ ትልቅ አገራዊ ኃላፊነት አለባቸው፡፡ የሚገቡት ወደ ጦርነት ሜዳ ነው ማለት ይቻላል፡፡ የአገራቸውን ገፅታ የሚለውጡበት፣ የህዝባቸውን አንድነት የሚያጠናክሩበት፣ የኢትዮጵያውያን የዕድገት ተስፋ የሚያለመልሙበት ውጤት ነው የምጠብቀው፡፡
በነገው ጨዋታ የሚገኝ ውጤት እኮ ለዓለም ዋንጫ ማለፍ ያስችላል ማለት አይደለም፡፡ የነገውን ጨዋታ በአሸናፊነት ቢወጣ እንኳን ቡድኑን ገና ሌላ ምእራፍ ይጠብቀዋል ፡፡ ከአፍሪካ 10 ሃያል ቡድኖች አንዱ ሆኖ ብራዚል ለምታስተናግደው 20ኛው ዓለም ዋንጫ ለማለፍ በመጨረሻው የደርሶ መልስ ጨዋታ ላይ ውጤት ማምጣት የዋልያዎቹ ፈተና ይሆናል፡፡ ከደቡብ አፍሪካ ጋር የሚደረገው ፍልሚያ ወሳኝነት ታዲያ ምኑ ላይ ነው?
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በነገው ጨዋታ ደቡብ አፍሪካን አሸንፎ፣ ለመጨረሻው የጥሎ ማለፍ ውድድር ከሚበቁ የአፍሪካ 10 ብሔራዊ ቡድኖች አንዱ ለመሆን መብቃቱ ያጓጓል፡፡ ወደ ዓለም ዋንጫ የሚያሳልፈው የ10 ብሄራዊ ቡድኖች የደርሶ መልስ ትንቅንቅ የነገውን ወሳኝ ፍልሚያ በድል በማጠናቀቅ የሚደረስበት ምእራፍ ነው፡፡ ብሄራዊ ቡድኑ የነገውን ጨዋታ በድል ለመወጣት ቅድሚያ ትኩረት በመስጠት ስለነገው ነው ማሰብ ያለበት፡፡ ቀጣዩ ጨዋታ ከማን ጋር እንደሚሆን በማናውቀው ጉዳይ ላይ ማሰብ የለብንም፡፡ የነገውን ማሸነፍ ዓለም ዋንጫ እንደመግባት እንዲቆጥሩት ያስፈልጋል፡፡ ከዚህ በኋላ ሌላ ወሳኝ ምእራፍ አለ ብሎ መግባት ጥሩ አይሆንም፡፡ የነገውን ወሳኝ ጨዋታ አሸንፎ በማለፍ ነው ለመጨረሻው ምእራፍ የሚደረሰው፡፡

በመጀመርያ ደረጃ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በሜዳው በሚያደርገው ጨዋታ እንደሚያሸንፍ ተስፋ ተፈጥሮ መሸነፍ ማለት ለተጫዋቾቹም ሆነ ለስፖርት አፍቃሪው ሞራል የሚነካ ነው፡፡ ከደቡብ አፍሪካ ጋር 1ለ1 ከሜዳው ውጭ አቻ ወጥቶ የተመለሰ ቡድን፣ እዚህ አገሩ ላይ የሚሸነፍበት ምንም አይነት ምክንያት አይኖርም፡፡
ዋልያዎቹ ለዚሁ ወሳኝ ጨዋታ ምን ማድረግ አለባቸው? በእርግጥ በደጋፊያቸው ፊት እንደመጫወታቸው ማሸነፍ እንደሚችሉ ለመገመት አይከብድም፡፡ ይሁንና የጨዋታው ወሳኝነት የሚፈጥረው ጫና ቀላል የሚባል አይደለም፡፡ በዚህ ላይ ደቡብ አፍሪካ በዚሁ ጨዋታ ነጥብ ይዞ ለመውጣት በከፍተኛ ፍላጎት ዝግጅት ስታደርግ ቆይታለች፡፡ ከሳምንት በፊት ሴንትራል አፍሪካ ሪፐብሊክን 3ለ0 ማሸነፏም ስጋት መፍጠሩ አይቀርም ፡፡ አንተ እንደ ስፖርት አፍቃሪ፤ እንደ ቀድሞ ኳስ ተጨዋችነትህ እና ከነበረህ ልምድ አንፃር ምን ትላለህ?
ሁሉም የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ተጨዋቾች እና አባላት ከፍተኛ የሞራል መነቃቃት እና ትኩረት ያስፈልጋቸዋል፡፡ በጨዋታው እያንዳንዷን ኳስ ለ90 ደቂቃዎች አሸንፈው መጫወት አለባቸው፡፡ ኳስ ከተነጠቁ መንጠቅ፣ ከነጠቁ ደግሞ ወደ ተግባር መለወጥ አለባቸው፡፡ እያንዳንዷን ኳስ ለማሸነፍ መፋለም አለባቸው፡፡ ኳሷን ማሸነፍ ማለት ለእያንዳንዷ ኳስ ትኩረት መስጠት ነው፡፡

በእያንዳንዷ ቅፅበት ያለውን ሁኔታ ሁሉም ተጨዋቾች እኩል ትኩረት በመስጠት ሙሉ 90 ደቂቃዎችን መጫወት አለባቸው፡፡ ዋልያዎቹ ጨዋታቸውን እዚህ አገራቸው እንደማድረጋቸው፤ ፊሽካ ከተነፋባት የመጀመርያዋ ደቂቃ አንስቶ ጫና ፈጥረው መጫወት አለባቸው፡፡ በሜዳቸው እየተጫወቱ መከላከል የለባቸውም፡፡ አገር ላይ መጫወት ያለው ጥቅም ለማግባት መጫወት ነው፡፡ የደቡብ አፍሪካ ቡድን ከኢትዮጵያ የምድቡን መሪነት ለመንጠቅ ከጅምሩ የሚጫወተው በማጥቃት ስለሚሆን፤ ያን በመከላከል ለማቆም መሞከር ለተደጋጋሚ ጥቃቶች ራስን ማጋለጥ ነው፡፡ ለማሸነፍ ማግባት አለብን፡፡ ለማግባት ደግሞ ማጥቃት አለብን፡፡ ዋልያዎቹ ጨዋታውን ሙሉ ለሙሉ መቆጣጠር አለባቸው፡፡ የኢትዮጵያ ቡድን በምድቡ ከሴንትራል አፍሪካ ሪፐብሊክ ጋር ከሜዳው ውጭ ስለሚያደርገው ጨዋታ በፍፁም ማሰብ የለበትም፡፡ በነገው ጨዋታ ውጤቱን አሳምሮ ምድቡን በመሪነት ለመጨረስ መታሰብ አለበት፡፡ ማንም ተጨዋች ግጥሚያው የአገር ጉዳይ መሆኑን አምኖ መቶ በመቶ ብቃቱን ማሳየት አለበት፡፡ ይህን ለመወጣት የማይችል፤ በቂ እና የተሟላ ብቃት ለእለቱ ማበርከት እንደማይችል የሚያስብ ተጨዋች ካለ፣ ከእኔ ይልቅ እከሌ ቢገባ ይሻላል ብሎ በግልፅ ሃሳቡን ለአሰልጣኙ ማንፀባረቅ አለበት፡፡ ይህ ወሳኝ ምእራፍ የሙከራ ጊዜ አይደለም፡፡ ሜዳ የሚገቡ ተጨዋቾችም ያላቸውን ሙሉ ብቃት በመጠቀም፤ የላቀ የቡድን ስራ እና ቁርጠኝነት በማሳየት አስፈላጊውን ውጤት ለማስመዝገብ በልበሙሉነት መሰለፍ አለባቸው፡፡ ለብሔራዊ ቡድኑ ዋናው የስነልቦና ጥንካሬ የሚሆነው ለግጥሚያው በቂ ትኩረት ከማድረግ ባሻገር ለተጋጣሚው ቡድን ቀላል ግን ጠንቃቃ ግምት መስጠት ነው፡፡
ምንም አይነት ስህተት መሠራት የለበትም፡፡ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ደቡብ አፍሪካን በሜዳዋ ገጥሞ 1ለ1 አቻ መውጣቱ ይታወሳል፡፡ በርግጥ በዚያ ጨዋታ የተገኘው ውጤት በደቡብ አፍሪካ የሚኖሩ በርካታ ኢትዮጵያውያን ስታድዬም ገብተው ለዋልያዎቹ የሰጡት ድጋፍ አስተዋጽኦ ሊኖረው ይችላል፡፡ በነገው ጨዋታ ግን ዋልያዎቹ በሜዳቸው እንደመጫወታቸው የመላው ኢትዮጵያዊ ድጋፍ ይበልጥ የጨመረ ይሆናል፡፡ ሌላው ለዋልያዎቹ የስነልቦና ጥንካሬ የሚሆነው የሚያስመዘግቡት ውጤት ትልቅ የታሪክ ምእራፍ መሆኑን ማሰብ ነው፡፡ ሁሉም የብሔራዊ ቡድኑ አባላት ለነገው ጨዋታ ከሰሞኑ ዝግጅታቸውም በላይ ዛሬ ልዩ ትኩረት እና በምክክር የተደገፈ የመጨረሻ ዝግጅት ያድርጉ፡፡ በቂ ልምምድ ሰርተውና ጥሩ እረፍት አድርገው ለነገው ፍልሚያ በተነቃቃ ስሜት፤ በጥሩ የአካል ብቃት እና ቅልጥፍና ተሳስበው በአገር ፍቅር ስሜት መስራት አለባቸው፡፡
የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በአስተማማኝ ሁኔታ ለማሸነፍ ይችል ዘንድ እንደ ተመልካች ምን አይነት ሃሳቦችን ትሰጣለህ?
ለማሸነፍ ከተፈለገ ሶስት መሰረታዊ ነገሮችን መተግበር አለበት ብዬ ነው የማስበው፡፡ እነዚህ ተግባራዊ ሲደረጉ የማሸነፍ እድሉ 99 በመቶ ይሆናል፡፡ በመጀመርያ ደረጃ ማንኛውም ተጨዋች ያለበትን የስነልቦና ችግር ከአሰልጣኙ ጋር ከተወያየ እና በግልፅነት ከተመካከረ ለአገር የሚሆን ውጤት ያስገኛል፡፡ ሁለተኛ 90 ደቂቃዎቹን በሙሉ ትኩረት ሰጥቶ ከኳስ ጋር እና ከኳስ ውጭ በመንቀሳቀስ ከተጫወተ ግጥሚያውን ሙሉ ለሙሉ መቆጣጠር ይችላል፡፡ ሶስተኛ የቡድኑ የአጥቂ መስመር ተሰላፊዎች የሚሰጧቸውን ያለቁ ኳሶች አማራጭ እንደሌለ በማሰብ ሌላ እድል አገኛለሁ በማለት ሳይዘናጉ፣ ከመጀመርያው ያገኟትን ኳስ ወደ ግብ መሬት አሲይዘው ከሞከሩ ውጤታማ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ አጥቂዎች ወደ ጎል የሚሞክሯቸውን ኳሶች መሬት አስይዘው ይምቱ የምለው ያለምክንያት አይደለም፡፡
ከመረብ የመዋሃድ እድል ያላቸው ኳሶች መሬት ለመሬት የሚመቱ ናቸው፡፡ ወደ ላይ የሚነሳ ኳስ የመግባት እድሉ ጠባብ ነው፡፡ አጥቂዎች አንድ እድል ሲያገኙ አንድ ጎል ለማግባት ማሰብ አለባቸው፡፡ ይህ አይነቱን ሙከራ ለሙሉ 90 ደቂቃዎች መቀጠል ደግሞ ውጤታማ ያደርጋል፡፡ በእርግጥ በወቅቱ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ካየኋቸው ለውጦች የመጀመሪያው የአጥቂዎች የአጨራረስ ብቃት ማደግ ነው፡፡ ዛሬ በብሔራዊ ቡድን ያሉ አጥቂዎች ጐል የማግባት ብቃታቸውና በቅጽበታዊ ውሳኔ ውጤት የማግኘት ክህሎታቸው ተለውጧል፡፡ በተለይ ቡድኑ ከሜዳ ውጭ በሚያደርጋቸው ጨዋታዎች አጥቂዎች ጐል የማስቆጠር ድፍረት ማዳበራቸው ጉልህ ለውጥ ነው፡፡ በአጠቃላይ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ውጤት እያማረ እና እየተለወጠ የመጣው የአጥቂዎች አጨራረስ ዕድገት በማሳየቱ ነው፡፡ ለዚህ የአጥቂዎች ውጤታማነት ፈር ቀዳጅነት ሚና የተጫወተው ሳላሃዲን ሰኢድ ነው፡፡ የእሱ የአጨራረስ ድፍረት እና በየግጥሚያዎቹ የሚያስቆጥራቸው ወሳኝ ጐሎች ብሔራዊ ቡድን አሁን ለደረሰበት ደረጃ ከፍተኛ አስተዋጽኦ አድርጓል፡፡ ሌሎች በሱ መስመር የሚሰለፉ የቡድኑ ተጨዋቾችን በማነቃቃትም አርአያ ሆኗል፡፡
የነገው ጨዋታ በድል ተጠናቀቀ እንበል፤ ቀጣዩ ወሳኝ ምእራፍ ከዚያ በኋላ ይመጣል፡፡ አሁን ብዙዎቹ ዓለም አቀፍ ሚዲያዎች እንደሚገልፁት፣ የኢትዮጵያ ጊዜ ሆኖ ብሄራዊ ቡድኑ በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ ለዓለም ዋንጫ ቢያልፍ ስኬቱ ምን ትርጉም ይኖራዋል?
የማንም ተጨዋች፣ የየትኛውም እግር ኳስ ወዳድ ህዝብ አገር ህልምና ተስፋ የዓለም ዋንጫን መሳተፍ ነው፡፡ የብሔራዊ ቡድኑ ለዓለም ዋንጫ ማለፍ መቻል የእግር ኳሱን እድገት በአስደናቂ ሁኔታ የሚያፋጥነው ይሆናል፡፡የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ለዓለም ዋንጫ ሲያልፍ ለስፖርቱ ዕድገት በር ከፋች የሚሆኑ በርካታ እድሎች እና ሁኔታዎች ይፈጠራሉ፡፡ ለምሳሌ ያህል ቡድኑ ለዓለም ዋንጫ ካለፈ በኋላ በአገሪቱ በሚካሄደው የሊግ ውድድር ከፍተኛ የሆነ የፉክክር ደረጃ ይፈጠራል፡፡ ይህም ክለቦች በበቂ ሁኔታ ተደራጅተው እና በተጨዋቾች ስብስብ ተጠናክረው ወደ ውድድር የሚገቡበትን ሁኔታ ያነቃቃል፡፡ በየክለቡ ያሉ ተጨዋቾች በዓለም ዋንጫ በሚሳተፈው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ለመመረጥ ከፍተኛ ትጋትና ብቃት ማሳየታቸውም ሌላው ለውጥ ነው፡፡
ባለሀብቶች የአገሪቱ እግር ኳስ ለዓለም ዋንጫ በመብቃቱ በስፖርቱ ዘርፍ መዋዕለ ንዋያቸውን ለማፍሰስ፣ ክለቦችን በመግዛት እና በገንዘብ በመደገፍ ለመስራት በቀላሉ የሚነሳሱበትን ሁኔታም ይፈጥራል፡፡ ኩባንያዎች የተሰማሩባቸውን የኢንቨስትመንት መስኮች ለማስተዋወቅና ከስፖርቱ ለውጥ ጋር የንግድና የእድገት እንቅስቃሴያቸውን ለማስተሳሰር ፍላጎት ያድርባቸዋል፡፡ ስታድዬሞችም በስፖርት አፍቃሪዎች መጥለቅለቃቸው አይቀርም፡፡ ለምን ቢባል ህዝብ ወደ ስታድዬሞች የሚተመው በዓለም ዋንጫ የሚሳተፉ ተጨዋቾችን ለመመልከት ስለሚሆን ነው፡፡ የዓለም ዋንጫው ስኬት የመንግስትንም ትኩረት የሚስብ ነው፡፡ የተጀመሩ መሰረተ ልማቶች በአፋጣኝ እንዲያልቁም ያበረታታል፡፡ በመጀመርያ ደረጃ ውጤቱ መንግስትና ህዝብን በማገናኘት ለአገር ልማት እና እድገት በጋራ መተሳሰብ እና በበጎ ስሜት እንዲሰሩ ተፅእኖ ማሳደሩ አይቀርም፡፡ በአጠቃላይ ለዓለም ዋንጫ ማለፍ ማለት በውስጥም ሆነ በውጭ የአገርን ገጽታ ሊቀይር የሚችል ነው፡፡