Administrator

Administrator

     የኢትዮጵያ አየር መንገድ በቻይና በየአመቱ በሚካሄደው “ኢንደስትሪ ጎልደን ቼር አዋርድስ” በተሰኘ አለማቀፍ ሽልማት የዓመቱ ምርጥ አየር መንገድ ተብሎ ለሁለተኛ ጊዜ መሸለሙን አስታወቀ፡፡
አየር መንገዱ ባወጣው መግለጫ እንዳለው፤ ለስምንተኛ ጊዜ በተካሄደውና በአለማቀፍ ደረጃ የላቀ አፈጻጸም ያሳዩ አየር መንገዶች፣ ሆቴሎች፣ የጉዞ ወኪሎችና የቱሪዝም መዳረሻዎች በሚሸለሙበት በዚህ ዝግጅት ተሸላሚ መሆኑ እንደሚያኮራቸው ዋና ስራ አስፈጻሚው አቶ ተወልደ ገብረ ማርያም ተናግረዋል፡፡
ሽልማቱን ለሚያዘጋጀው ኤምአይሲኢ የተባለ መጽሄት፣ እንዲሁም ለአየር መንገዱ ድምጻቸውን በመስጠት ለተሸላሚነት ላበቁት የቻይና ደንበኞችም ዋና ሥራ አስፈፃሚው ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡
የኢትዮጵያ አየር መንገድ በዘመናዊዎቹና በምቹዎቹ 787 እና 777 አውሮፕላኖቹ ቻይና ውስጥ ወደሚገኙት የቤጂንግ፣ የሻንጋይ፣ ጉዋንግዡና ሆንግ ኮንግ መዳረሻዎች በየሳምንቱ በድምሩ 28 በረራዎችን በማድረግ ምርጥና ፈጣን አገልግሎት እየሰጠ እንደሚገኝም ገልጸዋል፡፡
በዘንድሮው የፈረንጆች አመት ኤር ትራንስፖርት ወርልድ በተባለው ታዋቂ የአቪየሽን ዘርፍ መጽሄት “ቤስት ሪጅናል ኤርላይን” የተሰኘ ሽልማት የተሰጠው አየር መንገዱ፣ ባለፈው አመትም ከአሜሪካ ታዋቂ የጉዞ መጽሄቶች አንዱ በሆነው ፕሪሚየር ትራቭለር “የአፍሪካ ምርጥ አየር መንገድ” ተብሎ መሸለሙንም መግለጫው አስታውሷል፡፡ በ “ፓሴንጀር ቾይዝ” እና በአፍሪካ አየር መንገዶች ማህበርም፣ “ቤስት ኤርላይን ኢን አፍሪካ” እና “አፍሪካን ኤርላይን ኦፍ ዘ ይር” ሽልማቶችን መሸለሙንም አክሎ ገልጿል፡፡

 ከዚህ በፊትም መታጠቢያ ክፍል ውስጥ ያገኘችውን የአልማዝ ቀለበት ለባለቤቱ መልሳለች
-በኳታር በመታጠቢያ ቤት ውስጥ ያገኘቻቸውን 129 ሺህ ዶላር የሚያወጡ ሁለት የአልማዝ የጣት ቀለበቶች ለባለቤቶቹ ያስረከበችው ኢትዮጵያዊት የጽዳት ሰራተኛ፣ ላሳየችው ታማኝነት በአሰሪዎቿ መሸለሟን ዶሃ ኒውስ ዘገበ፡፡
አንድነት ዘለቀው የተባለችው የ32 አመት ኢትዮጵያዊት የጽዳት ሰራተኛ፣ በምትሰራበት የኳታር ብሄራዊ የስብሰባ ማዕከል መታጠቢያ ክፍል ውስጥ ተረስተው ላለፉት አራት አመታት በማዕከሉ በጽዳት ሰራተኛነት ተቀጥራ ስትሰራ ለቆየችው አንድነት የገንዘብ ስጦታውን ያበረከቱት የማዕከሉ ዋና ስራ አስኪጅ ኬን ጄሚሰን፣ ግለሰቧ ያሳየችው የታማኝነት ተግባር እንደሚያስመሰግናትና ለማዕከሉም ኩራት እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
ቀለበቶቹን ባገኘችበት ቅጽበት፣ ይሄኔ የቀለበቶቹ ባለቤት እንደጠፋት ስታውቅ ምን ይሰማት ይሆን የሚል ስሜት እንደተሰማትና ባአፋጣኝ ለማዕከሉ ረዳት ስራ አስኪያጅ ደውላ ስለጉዳዩ በመንገር ቀለበቶቹን እንደመለሰች አንድነት ለዶሃ ኒውስ ተናግራለች፡፡ ታማኝነት ታላቁ የህይወት መርህ እንደሆነ አምናለሁ ስትልም ተናግራለች፡፡ አንድነት ከዚህ በፊትም አል ሙክታር በተባለ የኳታር የጽዳት ኩባንያ ውስጥ ተቀጥራ በምትሰራ ወቅት ውድ ዋጋ የሚያወጣ ከአልማዝ የተሰራ የጣት ቀለበት በመታጠቢያ ክፍል ውስጥ ወድቆ አግኝታ ለባለቤቶቹ ማስረከቧን ዘገባው አስታውሷል፡፡
የጣት ቀለበቶቹ ባለፈው የካቲት ወር በማዕከሉ በተካሄደው የዶሃ የጌጣጌጦችና የእጅ ሰዓቶች ኤግዚቢሽን ላይ የጠፉ እንደነበሩ ያስታወሰው ዘገባው፤ ማእከሉ ለኢትዮጵዊቷ የሸለመው ገንዘብ ምን ያህል እንደሆነ አለመገለፁን ጠቁሟል፡፡

    የ1997 ዓ.ም የኮንዶሚኒየም ቤት ፈላጊዎች ምዝገባ ሂደት የተወሳሰቡ ችግሮች የነበሩበት በመሆኑ ለተመዝጋቢዎች የመረጃ ሰነድ መጥፋትና አሁን ድረስ ለዘለቁ በርካታ ቅሬታዎች መነሻ ሆኗል ተባለ፡፡
በወቅቱ ምዝገባው በአዲስ አበባ አስሩም ክፍለከተሞችና በሌሎች ተቋማት የተከናወነ ሲሆን ሁሉም ወገን የምዝገባ ተራ ቁጥሮችን ከ001 የጀመሩ በመሆናቸው መረጃዎቹ ወደ አንድ ማዕከል ሲሰባሰቡ የመደበላለቅ ችግር ፈጥሯል ያሉት የአዲስ አበባ ቤቶች ልማት አስተዳደር ኤጀንሲ ዋና ሥራ አሥኪያጅ አቶ መስፍን መንግስቱ፤ አንድ ግለሰብ በተለያዩ መዝጋቢ ተቋማት ሶስትና አራት ጊዜ የተመዘገበበት አጋጣሚ እንዳለም ገልፀዋል፡፡
የምዝገባ ማረጋገጫ የነበረውን ቢጫ ካርድ ተመሳሳይ ቁጥር እስከ 15 የሚደርሱ ግለሰቦች ይዘው ወደ ማዕከሉ እንደሚቀርቡ ያስረዱት አቶ መስፍን፤ “ሁሉም መረጃዎች በአንድ ማዕከል ተሰባስበው ከተራ ቁጥር 001 እስከ 453ሺህ ድረስ በመቀመጡ፣ እነሱ ቁጥራችን የሚሉትና ሲስተሙ የሚያውቀው የምዝገባ ቁጥር የተለያዩ ናቸው” ብለዋል፡፡
ለወቅቱ ቤት ፈላጊዎች ምዝገባ እንደ ችግር የተጠቀሰው ሌላው ጉዳይ የ97 ምርጫን ተከትሎ የተፈጠረው ግርግር መረጃን በተገቢው መንገድ ለማደራጀት አለማስቻሉ ነው ይላሉ አቶ መስፍን። በወቅቱ ከተማዋን እንዲያስተዳድር አደራ የተሰጠው የባለአደራ አስተዳደር ስራውን ተላምዶ ወደ ተግባር እስኪገባ ድረስ መረጃዎቹ በተገቢው መንገድ ተይዘው ነበር ለማለት አያስደፍርም ብለዋል - ሃላፊው፡፡
በወቅቱ የተበላሸውን ለማስተካከል በርካታ ስራዎች መሠራታቸውን የጠቀሱት ሃላፊው፤ በ2005 ዓ.ም በተደረገው ምዝገባ፤ “መረጃን ጠፍቶብናል” ያሉ ቤት ፈላጊዎች በነባር የምዝገባ ስርአት ውስጥ ተካተው እንዲስተናገዱ መደረጋቸውን ተናግረዋል፡፡
የጋራ መኖሪያ ቤቶች መሠረተልማት ሳይሟላላቸው ለተጠቃሚዎች ይተላለፋሉ በማለት የቤት ባለቤቶች ቅሬታ የሚያቀርቡ ሲሆን የገላን ሶስት ኮንደሚኒየም ነዋሪዎች እስካሁን ድረስ የመብራት አገልግሎት እንደሌላቸው፣ በሌላው የገላን ሳይት ደግሞ የግቢው መንገድ በተገቢው መንገድ ባለመስተካከሉ ለአደጋ የተጋለጡ መሆናቸውን ይናገራሉ፡፡ ሃላፊው በበኩላቸው፤ የነዚህ ቅሬታዎች መነሻ ከመሠረተ ልማት ጋር ተያይዞ የነበሩ ክፍተቶች ናቸው ብለዋል፡፡ ከዚህ ቀደም የቤቶቹ ግንባታ 80 በመቶ ሲደርስ እድለኞች እንዲረከቡ ይደረግ እንደነበር የጠቆሙት ሃላፊው፤ በአሁን ወቅት ግን መቶ በመቶ ተጠናቀውና መሠረተ ልማት ተሟልቶላቸው እንደሚተላለፉ ገልፀዋል። በፊት ለነዋሪዎች መሠረተ ልማት ሳይሟላላቸው የተላለፉትም በአሁን ወቅት ትኩረት ተሰጥቷቸው እየተሟላላቸው እንደሆነ ሃላፊው ጨምረው ገልፀዋል፡፡ “አካባቢውን ለኑሮ የሚመች ማድረግ ግን የነዋሪው ሃላፊነት ነው” ብለዋል ሃላፊው፡፡
በስም አሊያም በሌላ የማጭበርበር ዘዴ በህገወጥ መንገድ የኮንዶሚኒየም ቤት ተጠቃሚ የሆኑ ግለሰቦች ካሉ ህብረተሰቡ በጥቆማ ማጋለጥ እንደሚገባው ያሳሰቡት አቶ መስፍን፤ እንዲህ ያሉ ችግሮች በተደጋጋሚ  እንደሚያጋጥሙ ሳይጠቅሱ አላለፉም፡፡  

     የየመን ሁቲዎች በባብኤል መንደብ በሚገኙ ደሴቶች ላይ ያከማቹት ከባድ የጦር መሳሪያ በአለምአቀፉ የመርከብ እንቅስቃሴ ላይ ስጋት እንደጋረጠ የጠቆመችው ጅቡቲ፤ በሳዑዲ አረቢያ የሚመራውና የመን ላይ ወታደራዊ እርምጃ በመውሰድ ላይ የሚገኘው ጥምር ሀይል እንዲያስወግደው ጠየቀች፡፡
በአለም አቀፍ ደረጃ ብዙ የባህር ላይ እንቅስቃሴዎችን በማስተናገድ የሚታወቀው የቀይባህር የፀጥታና ደህንነት ሁኔታ በየመኑ ሁቲ አማፂያን ምክንያት ስጋት እንደተጋረጠበት መረጃዎች ይጠቁማሉ። ኢትዮጵያ በብቸኝነት የምትጠቀምበት ወደብ ባለቤት የሆነችው ጅቡቲ፤ የሁቲዎቹ እንቅስቃሴ በአለም አቀፉ የመርከቦች ደህንነት ላይ ስጋት መደቀኑን አስታውቃለች፡
የጅቡቲ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር መሀሙድ አሊ ዩሱፍ ሰሞኑን በሰጡት መግለጫ፤ አገራቸው ጥምር ሀይሉን እንደምትደግፍ ጠቁመው በባብኤል መንደብ ሰርጥ  ባሉ ደሴቶች ላይ በሁቲዎች የተከማቸው ከባድ የጦር መሳሪያ ለአለም አቀፍ የመርከቦች ዝውውር ስጋት በመሆኑ በጥምር ሀይሉ እንዲወገድ ጠይቀዋል፡፡
 በቀይባህር በኩል የተፈጠረው የፀጥታና የደህንነት ስጋት በኢትዮጵያ መርከቦች ጉዞ ላይ የፈጠረውን ሁኔታ በተመለከተ ለማጣራት ያደረግነው ሙከራ ሳይሳካ ቀርቷል፡፡

    ታዋቂው የመኪና አምራች ኩባንያ ሃዩንዳይ ሞተር፤ የሾፌር እገዛ ሳያስፈልጋቸው ሙሉ ለሙሉ በራሳቸው መንቀሳቀስ የሚችሉበት ቴክኖሎጂ የተገጠመላቸውን ዘመናዊ መኪኖች አምርቶ በመጪዎቹ አምስት አመታት ውስጥ ለአለም ገበያ እንደሚያቀርብ አስታወቀ፡፡
ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተባባሰ በመጣው የዓለማችን የአውቶሞቲቭ ኢንዱስትሪ የቴክኖሎጂ ውድድር ተፎካካሪ ሆኖ በመዝለቅ ላይ ያለው የደቡብ ኮሪያው የመኪና አምራች ኩባንያ ሃዩንዳይ፣ እነዚህን መኪኖች እ.ኤ.አ እስከ 2020 በገበያ ላይ እንደሚያውል ባለፈው ማክሰኞ ማስታወቁን ሮይተርስ ዘግቧል፡፡
ሃዩንዳይ ሞተር፤ ከዚህ በፊትም በተለየ ሁኔታ ባመረታቸው ጄነሲስን የመሳሰሉና እግረኛ ድንገት ወደ መንገድ ሲገባ ያለ ሾፌሩ ትዕዛዝ ፍሬን የሚይዙ ውድ መኪናዎቹ ላይ፣ መሰል ቴክኖሎጂዎችን መግጠሙን ዘገባው አስታውሷል፡፡
የጀርመኑን መርሴድስና የአሜሪካውን ጄኔራል ሞተርስ የመሳሰሉ ታላላቅ የዓለማችን የመኪና አምራች ኩባንያዎች እንዲሁም፤ ጎግልንና አፕልን የመሳሰሉ የቴክኖሎጂው ዘርፍ ፊታውራሪዎች፣ ምንም አይነት የሰው ድጋፍ ሳያስፈልጋቸው ሙሉ ለሙሉ ራሳቸውን ችለው ረጅም ርቀት መሽከርከር የሚችሉ መኪናዎችን ከዚህ ቀደም ማምረታቸውን ዘገባው አስታውሷል፡፡
ይሄም ሆኖ ግን፣ አንዳንድ ተንታኞች ሾፌር አልባ መኪናዎች፣ ከአገራት ጥብቅ የትራንስፖርት ህጎችና አደጋን ለመከላከል ሲባል ከወጡ መመሪያዎች ጋር በተያያዘ በአፋጣኝ ተቀባይነት ያገኛሉ ብለው እንደማያስቡ መናገራቸውን የጠቀሰው ዘገባው፤ እ.ኤ.አ እስከ 2020 አጋማሽ ድረስ ለአለማቀፍ ገበያ ይቀርባሉ የሚል ግምት እንደሌላቸው መግለጻቸውንም አመልክቷል፡፡

- የማስደነስ ፈቃድ የሌላቸው ባሮችና የምሽት ክበቦች ይቀጣሉ
- ፖሊስ ዳንስ ለግርግርና ለብጥብጥ ይዳርጋል ብሏል
- 10 ሺህ ዜጎች የሚሳተፉበት የጎዳና ላይ የዳንስ ተቃውሞ ይደረጋል
   የአገሪቱ ዜጎች ህዝብ በተሰበሰበባቸውና በመዝናኛ ስፍራዎች የሚያደርጉትን እንቅስቃሴ በተመለከተ ገደብ የሚጥል አዋጅ አውጥቶ ሲተገብር የቆየው የስዊድን ፓርላማ፣ የአዋጁ አንድ አካል የሆነውና ህገ-ወጥ ዳንስን የሚከለክለውን አነጋጋሪ ህግ ተግባራዊ መደረጉን እንዲቀጥል መወሰኑን ዴይሊ ሜል ዘገበ፡፡
የአገሪቱ ፖሊስም ህገወጥ ዳንስ፤ለግርግርና ብጥብጥ የሚዳርግ በመሆኑ ህጉን እንደሚደግፈው ያስታወቀ ሲሆን አንዳንድ አስተያየት ሰጪዎች በበኩላቸው፤ አሳፋሪ የቢሮክራሲ መገለጫ በመሆኑ ሊሻር ይገባል ሲሉ ነቅፈውታል፡፡ ፓርላማው ድምጽ የሰጠበትና እንዲቀጥል የወሰነበት ይህ ህግ፣ ሙዚቃ ስለሰሙ ብቻ እግራቸውን ለዳንስ የሚያነሱ ግለሰቦችን በህገወጥነት የሚፈርጅ ሲሆን፣ የማስደነስ ፍቃድ የሌላቸው የባርና የምሽት ክለብ ባለቤቶች ሲያስደንሱ ከተገኙ እንደሚቀጡ ይደነግጋል፡፡
ደንበኞቻቸው በሰሙት ሙዚቃ ሁሉ ሳያቋርጡ ሲደንሱ ወይም ፈቃድ ሳያገኙ ሲውረገረጉ ከተገኙም የባርና የምሽት ክለብ ባለቤቶች እንደሚቀጡ ህጉ ይገልጻል፡፡ ህጉን የተቃወሙት አንድሪያስ ቫርቬስ የተባሉ ስዊድናዊ የምሽት ክለብ ባለቤት፣ ከዚህ በፊት እንደተደረገው ሁሉ በመጪው ነሐሴ ወር ላይ ህጉን የሚቃወም የጎዳና ላይ የዳንስ ተቃውሞ ለማድረግ  ማቀዳቸውን ተናግረዋል፡፡ በጎዳና ላይ ዳንሱ ከ10 ሺ በላይ ሰዎች ይሳተፋሉ ብለው እንደሚገምቱም ገልጸዋል፡፡

  የቻይና የአውቶሞቲቭ ኢንዱስትሪ መስክ መሃንዲሶች ለመጀመሪያ ጊዜ በባለሶስት አውታር ማተሚያ ማሽን (3D printer) አትመው ያወጧትን ቀላል መኪና ሃይናን በተባለችው የአገሪቱ ግዛት ውስጥ ለእይታ ማብቃታቸውን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
3.6 ሜትር ቁመትና 1.63 ሜትር ስፋት ያላትን ይህቺን መኪና፣ በቀላል ወጪ የሚገዙ ቁሳቁሶችን በግብዓትነት በመጠቀም በማተሚያ ማሽኑ አማካይነት ሰርቶ ለማጠናቀቅ፣ አምስት ቀናትን ብቻ እንደፈጀ የጠቆመው ዘገባው፣ ክብደቷም አነስተኛ እንደሆነ ገልጧል፡፡
የመኪናዋ ዋና ዲዛይነር የሆኑት ቼን ሚንጊያኦ እንዳሉት፤ ባለ ሁለት መቀመጫዋ መኪና ክብደቷ አነስተኛ ቢሆንም ጥንካሬን የተላበሰች ናት ብለዋል፡፡ ክብደቷ አነስተኛ መሆኑ ደግሞ ሃይል ለመቆጠብ ያስችላታል ሲሉም ተናግረዋል፡፡ ከኮምፒውተር ጋር በተያያዘ ባለሶስት አውታር ማተሚያ አማካይነት ቁሳቁሶችን ማተም የሚያስችለውን የዘመኑ ቴክኖሎጂ በመጠቀም በቻይና ታሪክ የመጀመሪያዋ የሆነችው ይህቺ መኪና፣ ቻርጅ ከሚደረግ ባትሪ በምታገኘው ሃይል የምትንቀሳቀስ ሲሆን በሰዓት እስከ 40 ኪሎ ሜትር ርቀት የመጓዝ አቅም አላት፡፡

Monday, 06 April 2015 09:06

የየአገሩ አባባል

ለጅል መድሃኒቱ ሞት ብቻ ነው፡፡
በፀሐይ እረስ፣ በዝናብ አንብብ፡፡
ያልተጠየከውን ምክር አትለግስ፡፡
አንዳንዴ መድኀኒቱ ከበሽታው ይከፋል፡፡
የጫማ ሰሪ ልጅ ሁልጊዜ በእግሩ ይሄዳል፡፡
ስጦታ የሚቀበል ነፃነቱን ይሸጣል፡፡
መንሾካሾክ ባለበት ሁሉ ውሸት አለ፡፡
ገንዘብ የሌለው ሰው ገበያ ውስጥ ጥድፍ ጥድፍ ይላል፡፡
አንዴ የሰረቀ ሁልጊዜ ሌባ ነው፡፡
ሆድ ሲሞላ ልብ ደስተኛ ይሆናል፡፡
ቁራ ካረባህ ዓይንህን ይጓጉጡታል፡፡
ማልዶ የተነሳ ያልደፈረሰ ውሃ ይጠጣል፡፡
ጥርጣሬ የዕውቀት ቁልፍ ነው፡፡
ፅጌረዳውን የፈለገ እሾሁን ማክበር አለበት፡፡
ዓይነስውር በራሰ በራ ይስቃል፡፡
እባብ ለመያዝ የጠላትህን እጅ ተጠቀም፡፡
ነፋስ ያመጣውን ነፋስ ይወስደዋል፡፡
ልብ ውስጥ ያለውን ምላስ ያወጣዋል፡፡
በወጣት ትከሻ ላይ አሮጌ ጭንቅላት መትከል አትችልም፡፡
ሰነፍ በግ ፀጉሩ የከበደው ይመስለዋል፡፡

   አሜሪካ ለግብጽ ስትሰጥ የቆየችውንና ለሁለት አመታት ያህል አቋርጣው የነበረውን ወታደራዊ ድጋፍ እንደገና ሙሉ ለሙሉ መስጠት ልትጀምር እንደሆነ ማስታወቋን ዋሽንግተን ፖስት ዘገበ፡፡ የኦባማ አስተዳደር ለግብጽ ሲሰጠው የቆየውንና ከ2013 ጥቅምት ወር ወዲህ አቋርጦት የነበረውን 1.3 ቢሊዮን ዶላር የሚገመት አመታዊ የወታደራዊ መሳሪያዎች ድጋፍ እንደገና ለመጀመር ውሳኔ ላይ መድረሱን ባለፈው ክሰኞ አስታውቋል፡፡የግብጹ ፕሬዚዳንት ሞሃመድ ሙርሲ ከስልጣን መውረዳቸውን ተከትሎ፣ አገሪቱ እስከምትረጋጋና ዲሞክራሲያዊ ማሻሻያዎችን ተግባራዊ ለማድረግ የሚያስችል ተጨባጭ ለውጥ እስኪታይ ድረስ፣ አሜሪካ ለግብጽ የምትሰጠውን ወታደራዊ ድጋፍ አቋርጣ መቆየቷን ዘገባው አስታውሷል፡፡ የአሜሪካ መንግስት ወታደራዊ ድጋፉን እንደገና ለመስጠት መወሰኑ፣ ግብጽን ከፍተኛ ዋጋ የሚያወጡ አሜሪካ ሰራሽ የወታደራዊ መሳሪያዎች ባለቤት ያደርጋታል ያለው ዘገባው፣ ላለፉት ሁለት አመታት በአሜሪካ እጅ የቆዩ 12 ኤፍ-16 ተዋጊ ጀቶችን፣ 20 ቦይንግ ሃርፖን ሚሳየሎችን፣125 አሜሪካ ሰራሽ አብራምስ ኤምዋንኤዋን ታንኮችንና ሌሎች መሳሪያዎችን ማግኘት እንደሚያስችላት የአሜሪካ ብሄራዊ የደህንነት ካውንስል ቃል አቀባይ በርናዴት ሜሃን መናገራቸውን ጠቁሟል፡፡  አሜሪካ ወታደራዊ ድጋፉን እንደገና ለመቀጠል የወሰነችው፣ የራሷን የብሄራዊ ደህንነት ፍላጎት መሰረት በማድረግ ነው ያሉት ቃል አቀባይዋ፣ ለግብጽ የምትሰጠውን ወታደራዊ ድጋፍ በተለይ ሽብርተኝነትን ለመዋጋት፤ የድንበርና የባህር ደህንነቶችን ለማስጠበቅና አይሲሲ የተባለው ታጣቂ ቡድን በሲናይ አካባቢ የሚያደርገውን እንቅስቃሴ ለመግታት በሚደረጉ እንቅስቃሴዎች ላይ እንዲውሉ በሚያስችል መልኩ ማሻሻሏንም አስታውቀዋል፡፡ ኦባማ ክግብጹ ፕሬዚዳንት አል ሲሲ ጋር ባደረጉት የስልክ ውይይት፣ 1.3 ቢሊዮን ዶላር የሚገመተውን ወታደራዊ ድጋፍ በዘላቂነት ለማስቀጠል ለአሜሪካ ምክር ቤት ጥያቄ እንደሚያቀርቡ ቃል ገብተዋል፡፡ ግብጽ ከ2018 ጀምሮ የጦር መሳሪያዎችን በብድር መግዛቷን ማቆም እንደሚገባት አሳስበዋቸዋል፡፡አልጀዚራ በበኩሉ፤ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ተቋማት አሜሪካ ለግብጽ ሙሉ ወታደራዊ ድጋፍ ለመስጠት መወሰኗ እንደሚያሳስባቸው መግለጻቸውን ጠቅሶ፣ ሂውማን ራይትስ ፈርስት የተባለው ተቋም ዳይሬክተር ኔል ሂክስ “አሜሪካ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት ለሚታዩባት ግብጽ ድጋፏን ለመቀጠል መወሰኗ ለሰብዓዊ መብቶች መከበር ቅድሚያ አትሰጥም የሚል አደገኛ መልዕክት ሊያስተላልፍ ይችላል” ማለታቸውን ዘግቧል፡፡አሜሪካ ባለፈው አመት ተመሳሳይ ወር ለግብጽ የምትሰጠውን ድጋፍ በከፊል እንደምትጀምር ማስታወቋን ያስታወሰው ዘገባው፣ ግብጽ ከአሜሪካ ከፍተኛ ወታደራዊ ድጋፍ በማግኘት ከእስራኤል ቀጥላ በሁለተኛ ደረጃ ላይ እንደምትገኝም ጠቁሟል፡፡

Monday, 06 April 2015 08:58

የፍቅር ጥግ

ፍቅር ልዩ ቃል ነው፡፡ የምጠቀምበት ከልቤ ሲሆን ብቻ ነው፡፡ ቃሉን ደጋግማችሁ ስትሉት ይረክሳል፡፡
ሬይ ቻርልስ
ድንገት በጭጋጋማው የለንደን ከተማ ውስጥ አየሁሽ፡፡ ፀሐይዋ ሁሉን ስፍራ አድምቃው ነበር፡፡
ጆርጅ ገርሽዊን
ፍቅር እንደ ቧንቧ መክፈቻ ነው፤ ይዘጋል ይከፈታል፡፡
ቢሊ ሆሊዴይ
ከፍቅረኛህ ጋር ስትለያይ ጠቅላላ ማንነትህ ይፈራርሳል፡፡ ልክ እንደሞት ማለት ነው፡፡
ዴኒስ ቋይድ
ለሥራ ጊዜ አለው፡፡ ለፍቅር ጊዜ አለው፡፡ ከሁለቱ የሚተርፍ ሌላ ጊዜ የለም፡፡
ኮኮ ቻኔል
በዓለም ላይ ምርጡ ጠረን የምትወጂው ወንድ ነው፡፡
ጄኔፈር አኒስተን
ጀግንነት ሰውን ያለቅድመ ሁኔታ፣ ምላሽ ሳይጠብቁ ማፍቀር ነው፡፡
ማዶና
ፍቅር እንደ ጦርነት ሁሉ ለመጀመር ቀላል፤ ለመጨረስ ግን ከባድ ነው፡፡
ያልታወቀ ሰው
ሦስት ነገሮችን መደበቅ አይቻልም፡- ጉንፋን፣ ድህነትና ፍቅር፡፡
የአይሁዳውያን አባባል
ፍቅር ማለቂያ የሌለው ይቅር ባይነት ነው፡፡
ፒተር ኡስቲኖቭ
ፍቅር ነበልባል የመሆኑን ያህል ብርሃንም መሆን አለበት፡፡
ሔነሪ ዴቪድ ቶሪዮ
ፍቅር የሌላው ሰው ደስታ ለራስህ ወሳኝ የሚሆንበት ሁኔታ ነው፡፡
ሮበርት ሔይንሌይን
ፍቅር ሰውን ከራሱ ባርኔጣ ውስጥ ስቦ የሚያወጣ ምትሃተኛ ነው፡፡
ቤን ሄሽት